“ግንቦት ልደታን ለግቢ ጉባኤያችን”

ማኅበረ ቅዱሳን የተመሠረተበትን ፴፩ኛ ዓመት ምክንያት በማድረግ “ግንቦት ልደታን ለግቢ ጉባኤያችን” በሚል መሪ ቃል ከሚያዚያ ፳፰ እስከ ግንቦት ፮ ቀን ፳፻፲፭ ዓ.ም በልዩ ልዩ መርሐ ግብሮች እንደሚከበር ዐቢይ ኮሚቴ አስታወቀ፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን ባለፉት ፴፩ ዓመታት ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎችን በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ዶግማ፣ ቀኖና እና ትውፊት መሠረት ሥርዓተ ትምህርት ቀርጾ በማስተማር በዕውቀት እና በሥነ ምግባር የታነጹ፤ ለሀገር እና ለቤተ ክርስቲያን ጠቃሚ ትውልድ በማፍራት የድርሻውን ሲወጣ መቆየቱንና ወደፊትም ያመጣቸውን ለውጦች መነሻ በማድረግ አጠናክሮ እንደሚቀጥል የዐቢይ ኮሚቴው ምክትል ኃላፊ  አቶ አበበ በዳዳ ገልጸዋል፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን ያለፈባቸውን ውጣ ውረዶችና መልካም አጋጣሚዎችን መነሻ በማድረግ የተሻለ አገልግሎት ለቤተ ክርስቲያንና ለሀገር ለማበርከት ባለው ጽኑ ዓላማ መሠረት ግቢ ጉባኤያትን በማጠናከር ያጋጠሙትን ችግሮች በመፍታት ዘመኑን የዋጀ አገልግሎት እንዲፈጽም ታስቦ “ግንቦት ልደታን ለግቢ ጉባኤያችን” በሚል መሪ ቃል ለማክበር መወሰኑን አቶ አበበ አብራርተዋል፡፡

አቶ አበበ በማብራሪያቸው “በእነዚህ የአገልግሎት ዘመናት የታዩ ውጤታማ ለውጦች የበለጠ ለማገልገል የሚያነሳሱ በመሆናቸው ማለትም፡- ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ተማሪዎችን ሥርዓተ ትምህርት ቀርጾ ማስተማሩ፣ የአብነት ትምህርት ተምረው በቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ሱታፌ እንዲኖራቸው ማድረጉ፣ ጊዜያቸውን በአግባቡ ተጠቅመው በመደበኛ ትምህርታቸው ውጤታማ በመሆን የዋንጫና የሜዳልያ ተሸላሚዎችን ማፍራቱ፣ በሥነ ምግባር የታነጸ ለቤተ ክርስቲያንና ለሀገር የሚጠቅም ትውልድ መፍጠሩ፣ ተተኪ መምህራንን ማፍራቱ… ወዘተ ዘመኑን የዋጀ አገልግሎት በተጠናከረ ሁኔታ ለመስጠት እንዲነሳሳ አድርጓል” ብለዋል፡፡

ከሚያዚያ ፳፰ እስከ ግንቦት ፮ ቀን ፳፻፲፭ ዓ.ም በሚኖረው መርሐ ግብርም በዋናነት በግቢ ጉባኤት ላይ የሚታዩ መልካም ለውጦችን ለማስቀጠል፣ ችግሮችን ለመፍታት እና አገልግሎቱን ለማጠናከር የገቢ ማሰባሰቢያ መርሐ ግብር እንደሚኖር አመልክተዋል፡፡

በዚህም የገቢ ማሰባሰቢያ መርሐ ግብር ከግቢ ጉባኤ ተማሪዎች፣ ከግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች ወላጆች፣ እንዲሁም ከግቢ ጉባኤ ተመርቀው በልዩ ልዩ ሥራ እና አገልግሎት ከተሠማሩ አካላት እና ምእመናን ገቢ ለማሰባበሰብ መታቀዱን አቶ አበበ አስታውቀዋል፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን በሀገር ውስጥ ፵፰፣ በውጪ ሀገር ፬ ማእከላት ሲኖሩት በአጠቃላይ ፬፻፶፪ ግቢ ጉባኤያት (፬፻፴፭ በሀገር ውስጥ፣ ፳፫ በውጭ ሀገራት) እንዳሉት መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡

0 replies

Leave a Reply

Want to join the discussion?
Feel free to contribute!

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *