“የእግዚአብሔር መልአክ በሚፈሩት ሰዎች ዙሪያ ይሰፍራል፤ ያድናቸውማል”

(መዝ. ፴፬፥፯)

ሊቀ መላእክት ቅዱስ ገብርኤል በሐምሌ ዐሥራ ዘጠኝ ቀን ሕፃኑ ቂርቆስንና እናቱ ቅድስት ኢየሉጣን ከሚነደው እቶን እሳት ያዳነበት ዕለት ነው፡፡ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችንም በየዓመቱ ዕለቱን በድምቀት ታከብረዋለች፡፡ የእነዚህም ቅዱሳን ታሪክ በስንክሳር እንዲህ ይተረካል፡፡

በዚህችም ቀን ሕፃኑ ቂርቆስና እናቱ ኢየሉጣ በሰማዕትነት መከራን ተቀበሉ፡፡ ይህም ሕፃን ዕደሜው ሦስት ዓመት ሲሆነው ከሮሜ ሀገር ወደ ሌላ ሀገር እናቱ ይዛው ሸሸች፤ በዚያም የሸሸችውን መኮንን አገኘችው፡፡

ሰዎችም ነገር ሠሩባት፤ ወደ አርሱ አስቀረባትና ስለ አምልኮ ጠየቃት፤ እርሷም “መኰንን ሆይ ዕድሜው ሦስት ዓመት የሆነው ሕፃን አለ፤ አማልእክቶችህ ማምለክ መልካም እንደሆነ ወይም እንዳልሆነ ያስረዳን ዘንድ እርሱን ጠይቅ” አለችው፡፡

ሕፃኑም አለበት ጭፍራውን ልኮ ወደርሱ አስመጣው፤ ሕፃኑንም ፊቱ ብሩህና ደስተኛ እንደሆነ አየውና “አንተ ደስተኛ ሕፃን ሆይ እንዴት ነህ?” አለው፡፡ ሕፃኑም መልሶ “አዎ ለእኔ ደስታ ተጠብቆልኛል፤ ለአንተ ግን ኃዘንና ልቅሶ ጥርስ ማፋጨትም ነው፡፡ መጽሐፍ ለዝንጉዎች ተድላ ደስታ የላቸውም፤ ብሏልና” አለው፡፡ እግዚአብሔር ኃይልና ንግግርን ሰጥቶታልና ብዙ ተናገረ፡፡ በዚያም ያሉትን እስከ አስደነገጣቸው ድረስ ንጉሡን፣ መኳንንቱንና ጣዖታቱን ረገማቸው፤ ከብርታቱም የተነሣ አደነቁ፡፡

መኰንኑም በአፈረ ጊዜ በየዓይነቱ በሆነ ስቃይ ታላላቆች የማይችሉትን ታላቅና አስጨናቂ የሆነ ስቃይን አሰቃየው፡፡ እናቱንም ከርሱ ጋር እንደ እርሱ አሰቃያት፤ እግዚአብሔርም ያለ ምንም ጉዳት ያስነሣቸው ነበር፡፡ ብዙዎች አሕዛብም ይህን ዐይተው አደነቁ፤ ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም አምነው በሰማዕትነት ሞቱ፤ የሰማዕትነትም አክሊል ተቀበሉ፡፡

በሕፃኑ ላይም የመንፈስ ቅዱስ ጸጋ አደረበት፡፡ ታላላቅ ድንቆችና ተአምራቶችንም አደረገ፤ ብዙዎች በሽተኛቹንም አዳናቸው፡፡ ከዚህም በኋላ መኰንኑ በታላቅ የናስ ጋን ውስጥ ውኃ ጨምረው በእሳት ያፈሉት ዘንድ አዘዘ፡፡ የፍላቱም ድምጽ እንደ ክረምት ነጐድጓድ ሆነ፤ ያን ጊዜም ፍርሃትና የሃይማኖት ጉድለት በእናቱ ላይ ደረሰባት፤ ሕፃኑም ስለ እናቱ ወደ እግዚአብሔር ጸለየ፡፡

ያን ጊዜ ጌታችን ልቧን ወደ ሰማይ አሳርጎ ለቅዱሳን ሰማዕታት የተዘጋጁ የብርሃን ማደሪያዎችን አየች፤ ከዚህም በኋላ ጸናች፤ እግዚአብሔርንም አመሰገነችው፡፡ ልጅዋንም “ልጄ ሆይ ከእንግዲህ አንተ አባቴ ነህ፤ እኔም ልጅህ ነኝ” አለችው፡፡ “ያቺ ከእኔ የተወለድክባትም ቀን የተባረከች ናት” አለች፡፡ ወደዚያ ወደ ጋኑ ውስጥ በገቡ ጊዜም የውኃው ፍልሐት እንደ ንጋት ጊዜ ውርጭ ቀዘቀዘ፡፡ ከእግዚአብሔር የታዘዘ የመላእክት አለቃ ቅዱስ ገብርኤል ከሰማይ ወርዶ የእሳቱን ኃይል አቀዝቅዞታልና፡፡

ከዚህም በኋላ መኰንኑ ሥጋቸው ተቆራርጦ እስከሚወድቅ ድረስ በመቃጥን ውስጥ አድርገው እንዲጎትቷቸው አዘዘ፡፡ ከእግዚአብሔርም የታዘዘ መልአክ አዳናቸው፡፡ መኮንኑም በታላቅ ስቃይ ያሰቃያቸው ዘንድ አስቦ እስኪመክር ድረስ በወኅኒ ቤት ዘጋባቸው፡፡

ያን ጊዜም ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ሕፃኑ ቂርቆስ ወርዶ አጽናናው፣ አረጋጋውም፡፡ ስሙን ለሚጠራና መታሰቢያውን ለሚያደርግ ቃል ኪዳን ሰጠው፡፡

ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱስ ቂርቆስና በኢየሉጣ ጸሎት ይማረን፤ በረከታቸውም ትድረሰን ለዘለዓለሙ አሜን፡፡  

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ምንጭ፡ ስንክሳር ዘወርኀ ሐምሌ ፲፱

0 replies

Leave a Reply

Want to join the discussion?
Feel free to contribute!

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *