የአሜሪካ ማእከል ያሠለጠናቸውን የግቢ ጉባኤ ተተኪ መምህራን አስመረቀ

በማኅበረ ቅዱሳን የአሜሪካ ማእከል የግቢ ጉባኤ ማስተባበሪያ በእንግሊዝኛ ቋንቋ የደረጃ ፩ የግቢ ጉባኤ ተተኪ መምህራንን አሠልጥኖ አስመረቀ፡፡

የማእከሉ የግቢ ጉባኤ ማስተባበሪያ ከአትላንታ ንዑስ ማእከል ጋር በመተባበር ከተለያዩ ግቢ ጉባኤያት ለተውጣጡና ተተኪውን ትውልድ የሚወክሉ ፲፭ የግቢ ጉባኤ ተማሪዎች የበጋ (Summer) የተተኪ መምህራን ሥልጠናን ለተከታታይ ፲፭ ቀናት በመስጠት አስመርቋል፡፡ ከሰኔ ፲፯ ቀን ፳፻፲፮ እስከ ሐምሌ ፩ ቀን 2016 ፳፻፲፮ ዓ. ም (June 24, 2024 – July 08, 2024) በአትላንታ ከተማ በእንግሊዝኛ ቋንቋ ለመጀመሪያ ጊዜ የተሰጠው ሥልጠናም በታቀደው መሠረት ውጤታማ እንደነበር ሥልጠናውን ያስተባበረው የአሜሪካ ማእከል የግቢ ጉባኤያት ማስተባበሪያ ገልጿል፡፡  

ሠልጣኞቹ የወሰዷቸው ፭ የትምህርት ዓይነቶች ሲሆኑ እነርሱም፡- ነገረ ሃይማኖት (Dogmatic Theology)፣ የቤተ ክርስቲያን ታሪክ (Church History)፣ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት (Bible Study)፣ ነገረ ቅዱሳን (Hagiology) እና ሐዋርያዊ ተልእኮና የስብከት ዘዴ (Apostolic service & Homiletics) ናቸው::

ሥልጠናው በነገረ መለኮት ትምህርት ከፍተኛ ልምድ ባላቸው መምህራን የተሰጠ ሲሆን ከእነዚህም መምህራን መካከል፡- ቀሲስ ዶ/ር አምሳሉ ተፈራ ፣ በኩረ ፍሥሐ ቀሲስ ዶ/ር ኃይለየሱስ አስናቀና ቀሲስ ዓለማየሁ ደስታ ይገኙበታል፡፡ ከሥልጠናው በተጨማሪም ማታ ማታ ሠልጣኞቹ ለሚያነሷቸው የተለያዩ ጥያቄዎች ከቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን መምህራን መካከል ዲን ብርሃኑ አድማስ፣ ዶ/ር አማኑኤል አስፋው፣ ዲ/ን ዮሴፍና ሌሎችም ተጋባዥ መምህራን ምላሽ በመስጠት፤ እንዲሁም የሕይወት ተሞክሮዎቻቸውን በማካፈል ልምድ እንዲቀስሙ ተደርጓል፡፡

ተማሪዎቹ የተሰጣቸው ሥልጠና የነበራቸውን መጠነኛ ዕውቀትና ክህሎት እንዲያዳብሩ እንደረዳቸው፣ በዚህም መደሰታቸውንና ለማገልገልም ዝግጁ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡ በመጨረሻም የተሰጧቸውን ተከታታይ ትምህርቶች (Course) ካጠናቀቁ በኋላ የምስክር ወረቀትና የመጽሐፍ ቅዱስ ስጦታ ተበርክቶላቸዋል፡፡

0 replies

Leave a Reply

Want to join the discussion?
Feel free to contribute!

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *