ወነአምን በአሐቲ ጥምቀት (ጸሎተ ሃይማኖት )

                                                                 በመ/ር ተመስገን ዘገዬ
ጥምቀት በጽርዕ ቋንቋ “ኤጲፋኒ “ በግእዙ “አስተርእዮ ” በአማርኛው “መገለጥ ” የሚል ትርጉም የያዘ ቃል ነው ፡፡ቤተ ክርስቲያናችን ከበዓለ ልደቱ ቀጥላ ከቅጽረ ቤተ ክርስቲያን ወጥታ በዱር በሜዳ በወንዝ በባሕር ዳርቻ ጥር ፲፩ ቀን በየዓመቱ በታላቅ ድምቀት የምታከብረው በዓለ ጥምቀቱን ነው፡፡
ከኢየሱስ ክርስቶስ ዘጠኙ ዐበይት በዓላት በሦስተኛ ደረጃ የሚገኘው በዓለ ጥምቀት ነው፡፡መጋቢት ፳፱ ቀን በየዓመቱ የምናከብረው በዓለ ጽንሰቱ አንድ ተብሎ ተቆጥሮ በሁለተኛ ደረጃ ታኀሣሥ ፳፱ ቀን የምናከብረው በዓለ ልደቱ ነው፡፡በሦስተኛው ደረጃ ጥር ፲፩ ቀን በየዓመቱ የምናከብረው በዓለ ጥምቀቱ ነው፡፡
ጥምቀት አጥመቀ፤ አጠመቀ (ነከረ)፣ውኃ ውስጥ ገብቶ መውጣት፣መጥለቅ ማለት ነው፡፡ ከሰባቱ ምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን የመጀመሪያውና የሌሎች ምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን መግቢያ በር ነው፡፡ በቁስጥንጥንያ የተሰበሰቡ ፻፶አባቶች ‹‹ወነአምን በአሐቲ ጥምቀት፣በአንዲት ጥምቀት እናምናለን፡፡)››በማለት እንደመሰከሩት፡፡መንግሥተ ሰማይ ለመግባት መጠመቅ ግድ ነው፡፡
ጥምቀት ምሥጢር የተባለበት ምክንያት፡- ላመኑ እንጂ ላላመኑ አይሰጥም፣
በዐይን የሚታየው በእጅ የሚዳሰሰው ውኃ በግብረ በመንፈስ ቅዱስ ማየ ገቦ ሲሆን አይታይምናምእመናንም ጥምቀት በሚታየው የማይታየውን ጸጋ ሲቀበሉ አይታይም ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በኅቱም ድንግልና ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም ተጸንሶ በኅቱም ድንግልና ተወለደ (ትምህርተ ሃይማኖት ርትዕት_ በማኀበረ ቅዱሳን )
ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በተወለደ በስምንት ቀን ቤተ ግዝረት በ፵ ቀኑ ወደ ቤተ እግዚአብሔር ዕጒለ ርግብ ዘውገ ማዕነቅ ይዞ በመግባት ሕግ መጽሐፋዊን ሕግ ጠባዕያዊን ሲፈጽም ለእናቱ እየታዘዘ አድጎ ፴ ዓመት ሲሆነው ወደ ዮርዳኖስ ወንዝ ሔደ በተወለደ በ፴ ዘመኑ በዘመነ ሉቃስ ጥር ፲፩ ቀን ማክሰኞ ከሌሊቱ ዐሥር ሰዓት በዮርዳኖስ ወንዝ ተጠመቀ (አምስቱ አዕማደ ምሥጢር ወምስለ ሥነ ፍጥረት )
ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በ፴ ዘመኑ በባሕረ ዮርዳኖስ በዮሐንስ እጅ ተጠምቆ አብነት ሰው ሁሉ ይድን ዘንድ መጠመቅ እንዳለበት ተናገረ‹‹ያመነ የተጠመቀ ይድናል ያልተጠመቀ ግን ይፈረድበታል›› (ማር.፲፮፥፲፮)
ጌታችን ለጥምቀት ከገሊላ ወደ ዮርዳኖስ ወንዝ በወረደ ጊዜ ቅዱስ ዮሐንስም ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ‹‹ጌታዬ እኔ በአንተ ልጠመቅ ይገባል እንጂ አንተ በእኔ ትጠመቃለህን? ገለባ ከእሳት ፊት ይቆማልን? እኔስ ከአንተ ፊት እንደምን እቆማለሁ? በማለት ተከራክሮ ነበር፡፡(ማቴ.፫፡፲፬) ጌታም ‹‹ወይደልወነ ከመ ንፈጽም ኵሎ ሕግ፤ሕግን ሁሉ ልንፈጽም ይገባናል›› አለው፡፡
ቅዱስ ዮሐንስ በዮርዳኖስ በኢየሩሳሌም በይሁዳ አውራጃዎች ከጌታ ቀድሞ ‹‹መንግሥተ ሰማያት በልጅነት በእምነት በጥምቀት ልትሰጥ ቀርባለችና ንስሐ ግቡ ከኃጢአት ከበደል ተመለሱ ›› እያለ ለኃጢአት ሥርየት የንስሓ ጥምቀት ያጠምቅ ነበር፡፡
እስራኤላውያንም በብዛት ወደ እርሱ እየመጡ የንስሓ ጥምቀትን ይጠመቁ ነበር ፡፡(ማቴ.፫፡፭-፮ ) ብዙ ሰዎችም ከኃጢአታቸው እየተናዘዙ በዮሐንስ ይጠመቁ ነበር ቢሆን ፍጹም ሥርየተ ኃጢአትን ልጅነትና ድኅነተ ነፍስን አያገኙም ነበር፡፡
ጌታችን ለመጠመቅ ወደ ባሕረ ዮርዳኖስ በወረደ ጊዜ ምድር ተጨነቀች የዮርዳኖስ ውኃም ግማሹ ወደ ቀኝ ግማሱ ወደ ግራ ሸሸ፡፡
ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊትም የጌታችንን ጥምቀት በትንቢት መነጽርነት አስቀድሞ በማየት ‹‹ ባሕርኒ ርእየት ወጎየት ወዮርዳኖስኒ ገብአ ድኅሬሁ አድባር አንፈርዐጹ ከመ ሐራጊት ወአውግርኒ ከመ መሓስአ አባግዕ ምንተ ኮንኪ ባሕር ዘጎየይኪ ወአንተኒ ዮርዳኖስ ዘገባእከ፤ድኅሬከ ፡ባሕር አየች ሸሸች ዮርዳኖስም ወደ ኋላው ተመለሰ ተራሮች እንደ ኮርማዎች ኮረብታዎችም እንደ ጠቦቶች ዘለሉ፡፡ አንቺ ባሕር የሸሸሽ አንተ፣ ዮርዳኖስ ወደ ኋላ የተመለስክ ምን ሆናችኋል? እናንተ ኮረብቶችስ እንደ ጠቦቶች ለምን ዘለላችሁ››ይላል (መዝ.፻፲፫(፻፲፬)፥፫-፮)
ቅዱስ ቄርሎስም ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በተጠመቀ ጊዜ ውኃዎች እንደ ሞቀ ውኃ ፈሉ ይላል፡፡ ይህ አስደናቂ ሥራ በአንድ በኩል የክርስቶስ መለኮታዊ ኃይል ሲያመለክት በሌላ በኩል ደግሞ ማንም ሰው በክርስቶስ አምኖ መንፈስ ቅዱስን እንደሚገኝ ያሳያል፡፡
ጌታችን ተጠምቆ ከውኃ ሲወጣ አብ በደመና ሁኖ ‹‹ዝንቱ ውእቱ ወልድየ ዘአፈቅር ሎቱ ስምዕዎ፤የምወደው ልጄ ይህ ነው እሱን ስሙት››ብሎ የባሕርይ ልጅነቱን መስክሮለታል፡፡ መንፈስ ቅዱስም በአምሳለ ርግብ ፀዓዳ ወርዶ በራሱ ላይ ዐርፎበታል፡፡ መንፈስ ቅዱስ መሆኑ በምን ይታወቃል ቢሉ ? ጌታችን የተጠመቀው በዐሥረኛው ሰዓት ሌሊት ነው በዚህ ሰዓት ደግሞ ተዋሐስያን ቦታቸውን ለቀው አይንቀሳቀሱም (አምስቱ አዕማደ ምሥጢር ወምስለ ሥነ ፍጥረት )
ጌታችን በማየ ዮርዳኖስ በፍጡሩ እጅ በዕደ ዮሐንስ መጠመቁ ኃጢአት ኖሮበት ሥርየት ለመቀበል አይደለም፡፡ለጌታችን መጠመቅ ብዙ ምክንያቶች አሉት፡፡
ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከገሊላ አውራጃ ከናዝሬት ከተማ ወደ ይሁዳ አውራጃ ወደ ዮርዳኖስ መውረድን በግልጥ ለማሳየት ሲባል ታቦታተ ሕጉ በካህናት ተይዘው ወደ ሜዳና ወንዝ ዳር በመሄድ ኢትዮጵያውያን በቅዳሴ በውዳሴ፣ በዝማሬ በዕልልታ፤በከበሮ ፤በጽናጽል በክብር በዓለ ጥምቀቱን በታላቅ ድምቀት ያከብሩታል ፡፡
ጌታችንም የተጠመቀበት የጥር ወር በዕብራውያን (እስራኤል) አገር የዝናብና የበረዶ ወራት ስለሆነ እንኳንስን ከወንዝ ዳር ከማንኛውም ቦታ ቢሆን ያለ መጠለያ መዋልና ማደር አይቻልም ነበር፡፡ ቅዱስ ቄርሎስ ዘኢየሩሳሌም (315-386 ዓ/ም) ‹‹ወደ ውኃ በወረድን ጊዜ ውኃነቱን ሳይሆን በውኃው አማካኝነት የምናገኘውን ድኅነት ተመልከት››ይላል፡፡
ጥምቀት በኦሪት ጊዜም ነበር ፡፡ ኢዮብና ንዕማን በዮርዳኖስ ወንዝ ተጠምቀው ከደዌ (ከሕመም) ድነዋል፡፡ ኢዮብና ንዕማን የአዳምና የልጆቹ ምሳሌ፤ደዌው (ሕመሙ) የመርገመ ሥጋ ወነፍስ ምሳሌ ዮርዳኖስ የጥምቀት ምሳሌ ነው (፩ኛ ነገስ ፭፡፰-፲)
ነብዩ ኤልሳዕ የደቀ መዝሙሩን መጥረቢያ ባሕረ ዮርዳኖስ ወንዝ ገብቶበት በነበረ ጊዜ የእንጨት ቅርፊትን አመሳቅሎ ውኃው ላይ ቢጥለው መዝቀጥ( መግባት) የማይችለው ቅርፊት ዘቅጦ( ገብቶ) መዝቀጥ የማይገባውን ብረት ይዞት ወጥቷል፡፡ ይህም ምሳሌ ነው የእንጨቱ ቅርፊት የጌታ ብረት የአዳም ዮርዳኖስ ወንዝ የጥምቀት (የሞት የመቃብር) ምሳሌ ሲሆን መዝቀጥ ( መግባት) የማይገባው ቅርፊት ዘቅጦ መዝቀጥ የሚይገባውን ብረት ይዞ መውጣቱ መሞት የማይገባው አምላክ ሞቶ ሞት የሚገባውን አዳምን ለማዳኑ ምሳሌ ነው፡(፪ኛ.ነገ.፮፡፩-፯)
ጌታችን ለምን በ፴ ዘመኑ ተጠመቀ?
ሰው ሁሉ በ፴ ዘመኑ ሕገ ነፍስን ይሠራልና ለአብነት አንደም ቅስና ምንኩስና በ፴ ዘመን ይገባል ሲል ነው፡፡ ቀጥሎም አዳምን የ፴ ዘመን ጎልማሳ አድርጎ ፈጥሮት የሰጠውን ልጅነት አስወስዶ ነበርና የአዳምን ልጅነት ለመመለስ በ፴ ዘመኑ ተጠመቀ
                                ጌታችን ለምን በባሕረ ዮርዳኖስ ተጠመቀ?
፩. ትንቢቱና ምሳሌውን ለመፈጸም ፦ጌታችን አምላካቸን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዕደ ዮሐንስ በፈለገ ዮርዳኖስ እንደሚጠመቅ ከልደተ ክርስቶስ በፊት በአንድ ሺህ ዓመተ ዓለም ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት የዘመራቸው የትንቢት መዝሙሮች የሚከተሉት ናቸው፡፡
ትንቢቱ፡ “ቃለ እግዚአብሔር ላዕለ ማያት አምላከ ስብሐት አንጎድጎደ እግዚአብሔር ላዕለ ማያት ብዙኀ ፤የእግዚአብሔር ቃል በውኃዎች ላይ ነው፡የተመሰገነ አምላክ ድምጹን አሰማ እግዚአብሔር በብዙ ውኃዎች ላይ ነው፡፡”(መዝ.፳፰፥፬)
“ርእዩከ ማያት እግዚኦ ርእዩከ ማያት ወፈርሁ ደንገጹ ቀላያተ ማያት ወድምጸ ማያቲሆሙ ፤አቤቱ ውኃዎች አዩህ ውኃዎች አዩህና ፈሩህ፤የውኃዎች ጥልቆች ደነገጡ ማዕበላቸውም ተሰማ”(መዝ.፯፥፮)“ በእንተዝ እዜከረከ እግዚኦ በምድረ ዮርዳኖስ በአርሞንኤም በደብር ንዑስ ቀላይ ለቀላ ትጼውኦ በቃለ አስራቢከ፤ሥለዚህ በዮርዳኖስ ምድር በአርሞንኤምም በታናሹ ኮረብታ አስብሃለሁ ………(መዝ.፵፩፥፮)
‹‹ ባሕርኒ ርእየት ወጎየት ወዮርዳኖስኒ ገብአ ድኀሬሁ አድባር አንፈርዐጹ ከመ ሐረጊት ፤ባሕርአየች ሸሸችም ዮርዳኖስም ወደ ኋላው ተመለሰ ተራሮች እንደ ኮርማዎች ኮረብታዎችም እንደ ጠቦቶች ዘለሉ፡፡ አንቺ ባሕር የሸሸሽ ዮርዳኖስም ወደ ኋላሽ የተመለሽ ምን ሆናችኋል? ›› በማለት ነብዩ አስፍቶና አጉልቶ ዘምሮአል፡፡ ይህ ትንቢት ስለነበር ጌታችን ከሌሎች አፍላጋት ሁሉ መርጦ በዮርዳኖስ ወንዝ ተጠመቀ (መዝ.፻፲፫፡፥፫-፭)
ምሳሌው፡- አባታችን አብርሃም ነገሥተ ኮሎዶ ጎሞርን ድል አድርጎ ከገንዘቡ ዐሥራት በኲራት በማውጣት ዮርዳኖስን ወንዝ ተሻግሮ ወደ ካህኑ መልከጼዴቅ ሲሄድ ኅብስተ አኮቴት ጽዋዐ በረከት ይዞ ተቀብሎታል፡፡አብርሃም የምእመናን የዮርዳኖስ ወንዝ የጥምቀት ካህኑ መልከጼዴቅ የቀሳውስት፤ኅብስተ አኮቴት ጽዋዐ በረከት የሥጋ ወደሙ ምሳሌ ነው(ዘፍ.፲፬፥፲፯፣ዕብ ፯፡፩-፰)
ዮርዳኖስ አንድ ወንዝ ሲሆን ዝቅ ብሎ በዮር እና በዳኖስ ተለይተዋል፡፡ዮር በእስራኤል በኩል ያለው ሲሆን ዳኖስ በአሕዛብ በኩል ያለው ነው፡፡ዝቅ ብሎ ደግሞ ሁለቱም ተገናኝተዋል፡፡ ሁለቱ በተገናኙበት ቦታ ጌታ ተጠምቋል፡፡ ይህ ምሳሌ ነው፡፡
ዮርዳኖስ ከላይ አንድ እንደሆነ ሁሉም የሰው ዘር የአንድ የአዳም ልጅ እንደሆነ ሲያስረዳ ዝቅ ብሎ መለየቱም እስራኤል በኦሪት አሕዛብ በጣዖት ተለያይተዋል፡፡ ዝቅ ብሎ መገናኘቱ ሁሉም በአንድ ወንጌል የማመናቸው ምሳሌ ነው፡፡
ጌታችንም ሁለቱ ከተገናኙበት ቦታ ተጠመቀ ሁላችሁንም አንድ ላደርጋችሁ መጥቻለሁ ሲል ነው፡፡ ሌላው ምሥጢር ግን አዳምና ሔዋን ሕግ ተላልፈው ከገነት ተባረው ጸጋቸው ተገፎ ራቁታቸውን ሆነው ከገነት ሲወጡ ዲያብሎስ የጨለማ ግርዶሽ ጋርዶ ፍዳ አጽንቶባቸው አዳም ገብሩ ለዲያብሎስ፤አዳም የዲያብሎስ ወንድ አገልጋይ ነው፤ሔዋን አመቱ ለዲያብሎስ ፤ ሔዋን ደግሞ የዲያብሎስ ሴት አገልጋይ ናት፡፡ ብላችሁ ስመ ግብርናትን ጽፋችሁ ስጡኝ አላቸው፡፡ እነርሱም ፍዳ የሚያቀልላቸው መስሏቸው እንዳላቸው አድርገው አዘጋጅተው ሰጡት ዲያብሎስም ያንን የዕዳ ደብዳቤ አንዱን በሲዖል አንዱን በዮርዳኖስ ወንዝ አኖረው፡፡
ዲያብሎስ በዮርዳኖስ ወንዝ ያስቀመጠውን የዕዳ ደብዳቤ ጌታ በጥምቀቱ ጊዜ እንደ ሰውነቱ ረግጦ እንደ አምላክነቱ አቅልጦ አጥፍቶታል፡፡ሊቁ ቅዱስ ኤፍሬም በሰኞ ውዳሴ ማርያም ድርሰቱ ‹‹ወሰጠጠ መጽሐፈ ዕዳሆሙ ለአዳም ወለሔዋን ፤የአዳምንና የሔዋንን የዕዳ ደብዳቤያቸውን ቀደደላቸው›› ይላል፡፡(ቆላ.፪፡፲፫)፡፡በአዳምና በሔዋን አንጻር የእኛንም የዕዳ ድበዳቤያችን ቀደደልን ፡፡
ጌታችን ወደ ዮሐንስ ሄዶ የተጠመቀበት ምክንያት
ትሕትናን ሲያስተምር ነው፡፡ምነው ጌታ ፈጣሪ፤ እግዚእ ሲሆን ወደ ትሑት ዮሐንስ ሄደ ቢሉ ሥጋ መልበሱ ለትሕትና ነውና፡፡ይህ ባይሆን ዛሬ ነገሥታት ቀሳውስትን ከቤታችን መጥታችሁ አጥምቁን አቁርቡን ይሉ ነበርና፡፡
ትንቢቱና ምሳሌውን ለመፈጸም (ት.ሕዝ ፴፮፡ መዝ.፻፲፫፡፥፫-፭)
ጌታችን መድኃኒታችን መጠመቅ ለምን አስፈለገው?
1.ጥምቀት ለሚያስፈልገን ለእኛ አርአያ ለመሆን ፡-እርሱ ተጠምቆ ተጠመቁ ባይለን ኑሮ ጥምቀት አያስፈልግም፡፡ አስፈላጊ ቢሆንማ ጌታ ራሱ ተጠምቆ አብነት በሆነን ነበር እንዳይሉ መናፍቃን ምክንያት አሳጣቸው፡፡
ሊቁ ቅዱስ ዮሐንስም” ወአርኃወ ለነ አንቀጸ ጥምቀት ከመ ንጠመቅ፤ እንጠመቅ ዘንድ የጥምቀትን በር ከፈተልን”ሲል የጥምቀትን ምስጢር ያስረዳናል፡፡
2. ትንቢቱ ይፈጸም ዘንድ፡- ‹‹አቤቱ ውኃዎች አዩህ ውኃዎች አይተውህ ፈሩ ጥልቆችም ተነዋወጡ ወኃዎችም ጮሁ ደመኖችም ድምጽን ሰጡ ፍላጾችም ውጡ ›› (መዝ.፸፯፡፲፮-፲፯) የሚል ትንቢት ነበርና ይህ እንዲፈጸም፡፡
3. በዮርዳኖስ ውስጥ የነበረውን የዕዳ ደብዳቤ ለመደምሰስ፦ ( ሰኞ ውዳሴ ማርያም)
አንድነትና ሦስትነቱን ለማስረዳት፡- ከዚህ በፊት የሥላሴ አንድነት ሦስትነት በግልጽ አይታወቅም ነበር፡፡ ጌታ በዮርዳኖስ በሚጠመቅበት ጊዜ ግን ምሥጢረ ሥላሴ ግልጽ ሁኖ አብ በደመና ሁኖ የምወደው ልጄ ይህ ነው በማለቱ የወልድ አባት መሆኑ ታወቀ፡፡ መንፈስ ቅዱስም የባሕርይ ሕይወቱ መሆኑ በርግብ አምሳል በራሱ ላይ ተቀምጦ ሲታይ ወልድ በተለየ አካሉ በዮርዳኖስ ሲጠመቅ ታየ ተገለጠ፡፡
ጌታን ተጠምቆ ከውኃ ሲወጣ የሚከተሉት ተአምራት ተፈጽመዋል
1.ሰማያት ተከፈቱ፡- ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በእደ ዮሐንስ በፈለገ ዮርዳኖስ ተጠምቆ ከውኃው ሲወጣ “ወናሁ ተርኀወ ሰማይ ወርእየ መንፈሰ እግዚአብሔር እንዘ ይወርድ ከመ ርግብ ወነበረ ላዕሌሁ፤ሰማይ ተከፍቶ መንፈስ ቅዱስ በአምሳለ ርግብ በራሱ ላይ ሲቀመጥበት አየ ” አሁን ሰማይ የሚዘጋና የሚከፈት ሁኖ ሳይሆን ታይቶ የማይታወቅ ታላቅ ምሥጢር ተገለጠ፡፡ማለትም የልዑል እግዚአብሔርአንድነት ሦስትነቱ ምሥጢር ጎልቶ ወጣ ለማለት ነው፡፡
2. መንፈስ ቅዱስ በርግብ አምሳል ወርዶ በራሱ ላይ ተቀመጠ
እግዚአብሔር አብ ከላይ ‹‹ መጽአ ቃል እምደመና ዘይብል ዝንቱ ዝንቱ ውእቱ ወልድየ ዘአፈቅር ወሎቱ ስምእዎ፤ ለተዋሕዶ የመረጥሁት በእርሱ ሕልውና በመሆን ልመለክበት የወደደሁት ልጄ ይህ ነው›› (ማቴ.፫፡፲፯) በማለት የባሕርይ አምላክነቱን መስክሯል፡፡ወንጌላውያኑ በዚህ ቃል ምሥጢረ ሥላሴን በግልጽ አስተምረውናል፡፡
ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለምን በውኃ ተጠመቀ?
ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በውኃ ተጠምቋል ጥምቀቱ በውኃ የሆነበት ምክንያት ‹‹ኢየሱስም ከተጠመቀ በኋላ ወዲያው ከውኃ ወጣ ›› ይላል (ማቴ፫፡፲፮) በቃሉም እንዲህ አስተማረ ‹‹ ሰው ከውኃና ከመንፈስ ቅዱስ ካልተወለደ በቀር ወደ መንግስተ ሰማያ ይገባ ዘንድ አይቻልም›› (ዮሐ.፫፡፭) በቅዱሳን ነቢያትም ሲነገር የነበረ ትንቢት ነበር‹‹ጥሩ ውኃንም እረጭባችኋለሁ እናንተም ትጠራላችሁ ከርኩስታችሁም ሁሉ አጠራችኋለሁ፡፡( ት.ሕዝ. ፴፮፥፳፭) የሚል አስቀድሞ ትንቢት ተነግሮ ነበር፡፡
ውኃ የሰውነትን ቆሻሻ እንደሚያጠራ ጥምቀትም የነፍስን ኃጢአት ያጠራልና፡፡አንድም ውኃ ጽንፍ እስከ ጽንፍ ይፈሳል ጥምቀትም ጽንፍ እስከ ጽንፍ ይከናወናልና፡፡ አንድም ውኃ በዙፋኑ ካለ ንጉሥ አንስቶ በዐደባባይ እስከ አለ ችግረኛ ሁሉ የተሰጠ በሁሉ ቤት የሚገኝ ነው፡፡
ጥምቀትም የተሠራው ለሰው ሁሉ ነው፡፡ ጎሳ፣ጎጥ፣ቀለም፣ደሀ፣ሀብታም አይለይበትም፡፡ አንድም በውኃ የታጠበ ልብስ ጥንካሬ እንደሚያገኝ ምእመናንም በውኃ ተጠምቀው ገድልና ትሩፋት እየሠሩ በጥምቀት ባገኙት ኃይል ባላጋራቸውን ዲያብሎስን ድል ይነሱታል፡፡ አንድም የርብቃ ለይስሐቅ መታጨት በውኃ ምክንያ ሁኗል (ዘፍ.፳፬፡፲-፳፯) መንፈሳዊ መታጨትም (ለእግዚአብሔር መንግሥት) በውኃ (በጥምቀት) ሁኗል፡፡
ጌታችን በማር በወተት ጥምቀቱን ማድረግ ሲቻለው በውኃ ያደረገበት ምክንያት ማርና ወተት በሁሉ አይገኝምና ሁሉም በሚያገኘው አደረገው፡፡ ቅዱሳን ሐዋርያትም ከአምላካቸው በቃልና በተግባር የተማሩትን በሥራ ሲተገብሩ ሕዝቡን በውኃ አጥምቀዋል፡፡
ለጥምቀት የውኃ አስፈላጊነት በፍትሕ መንፈሳዊ አንቀጽ-፫ ላይ ተደንግጓል፡፡ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን የጥምቀት በዓልን የምታከበረው የጌታችን የማዳኑን ምስጢር ለማዘከርና ለመመስከርም ነው፡፡አቡነ ጎርጎርዮስ ካልዕ “የጠበሉን መረጨት አይተው በቀድሞ ዘመን ወደ ሀገራችን መጥተው የነበሩ መናፍቃን የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን በየዓመቱ ይህን ምትፈጽመው ጌታችን ለእኛ ብሎ ያሳየውን ትሕትና ለመመሥከር ለምእመናን የጌታችን በረከተ ጥምቀት ለማሳተፍ እንጂ የተጠመቁትን ምእመናን እየመለሰች በየዓመቱ አታጠመቅም” ብለዋል፡
ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በዓለ ጥምቀትን የምታከብረው፣የበዓሉን ጥንታዊነት በጠበቀ መልኩ በመሆኑ ሀገራችንን በዓላም እንድትታወቅ የበርከታ ጎብኚዎች መስህብ እንድትሆን አድርጓታል ።” የአምላካችሁን የእግዚአብሔርን ቃል ኪዳን ታቦት ሌዋውያን ካህናት ተሸክመውት ባያችሁ ጊዜ፥ ከሰፈራችሁ ተነስታችሁ ተከተሉት” (ኢያ.፫፥፫)
በበዓለ ጥምቀት ዋዜማ የታቦታቱ ወደ ወንዝ መውረድና የባሕረ ጥምቀቱ መዘጋጀት ሃይማኖታዊ ታሪክና ምሳሌ አለው።የቃል ኪዳኑን ታቦት አክብሮ መጓዝና ወደ ወንዝ መውረድ የተጀመረው በአሮን ልጅ በአልዓዛር ጊዜ ነው።
ኢያሱ በሙሴ እግር ተተክቶ ሕዝበ እስራኤልን እየመራ ከዮርዳኖስ ወንዝ ሲደርስ ባሕሩ ከሁለት ይከፈልና ወራጁም ይቆም(ይከተር ) ነበር።እስራኤል ፈለገ ዮርዳኖስ ተሻግረው ወደ ኢያሪኮ መሔዳቸው ምእመናን በጥምቀት ከኃጢአት ቁራኝነት ተላቀው እግራቸውን ወደ ልምላሜ ገነት ወደ ዕረፍተ መንግሥተ ሰማያት አቅንተው ለመሔዳቸው ምሳሌ ነው።
ኢያሱ የጌታ ምሳሌ፣እስራኤል የምእመናን ፣ዮርዳኖስ የጥምቀት ፣ምድረ ርስት የገነት የመንግሥተ ሰማያት ምሳሌ ነው።
ታቦቱን አክብሮ የሚሔደው ካህን የቅዱስ ዮሐንስ ፣ታቦቱ የጌታችን፣ባሕረ ጥምቀቱ የዮርዳኖስ ወንዝ: ታቦታቱን አጅበው የሚሔዱትና በዓሉን የሚያከብሩት ምእመናን ወደ ቅዱስ ዮሐንስ እየመጡ የንስሓ ጥምቀት ሲጠመቁ የነበሩት ሰዎች ምሳሌዎች ነው፡፡

0 replies

Leave a Reply

Want to join the discussion?
Feel free to contribute!

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *