እግዚአብሐርን ማመስገን

በዳዊት አብርሃም

ክፍል አንድ

“እነሆም ሲሔዱ ነጹ፡፡ ከእነርሱም አንዱ እንደተፈወሰ ባየ ጊዜ በታላቅ ድምጽ እግዚአብሔርን እያከበረ ተመለሰ፤ እያመሰገነውም በእግሩ ፊት በግምባሩ ወደቀ፤ እርሱም ሳምራዊ ነበረ፡፡ ኢየሱስም መልሶ ዐሥሩ አልነጹምን? ዘጠኙስ ወዴት አሉ? ከዚህ ከልዩ ወገን እግዚአብሔርን ሊያከብሩ የተመለሱ አልተገኙም አለ፡፡” (ሉቃ. ፲፯፥፲፭-፲፰) በዚህ የወንጌል ክፍል የምናገኘው ታሪክ ስለ ምስጋና የሚያስተምር አንድ እውነት አለ፡፡ በጌታችን ገቢረ ተአምራት ከለምጽ ሕመም የዳኑት ዐሥር ሰዎች ናቸው፡፡ ታሞ የተነሣ ፈጣሪውን ረሳ እንደሚባለው የሀገራችን ብሂል በተደረገላቸው ታላቅ ነገር እግዚአብሔርን ማመስገን እንዳለባቸው ግን ዘጠኙ ትዝ አላላቸውም፡፡ ለምስጋ የመጣው አንዱ ብቻ ነው፡፡

እግዚአብሔርን ለማመስገን ብዙ ምክንያቶች አሉ፤ ፍጡር ነንና ፈጣሪን ማመስገን ግዴታ ነው፡፡ በሚገርም ሁኔታ ግን የሰው ልጅ ሌላው ሁሉ ቀርቶ ስለተደረገለት ታላቅ ውለታ እንኳ ማመስገን ሊዘነጋ ይችላል፡፡ ከላይ በመግቢያችን የጠቀስነው የወንጌል ቃል ይህን የሚገልጥ ነው፡፡ በክርስትና ውስጥ ግን ማመስገን ለተሰጠን ብቻ ሳይሆን ላልተሰጠንም ጭምር ነው፡፡ ለመልካሞቹ ነገሮች ብቻም ሳይሆን ለክፉዎቹም ነገሮች ለመከራዎቻችንም እንኳ ሳይቀር ለልናመሰግን እንዲገባን ቅዱሳት መጻሕፍት የሚያስተምሩን ነው፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ “ሁል ጊዜ ስለ ሁሉ በጌታችን በኢየሱስ ክርሰቶስ ስም አምላካችንንና አባታችንን ስለ ሁሉ አመስግኑ፡፡” (ኤፌ. ፭፥፳) ይለናል፡፡ በተጨማሪም “ሁል ጊዜ ደስ ይበላችሁ፤ ሳታቋርጡ ጸልዩ፤ በሁሉ አመስግኑ፤ ይህ የእግዚአብሔር ፈቃድ በክርስቶስ ኢየሱስ ወደ እናንተ ነውና፡፡” (፩ኛ ተሰ. ፭፥፲፮-፲፰)፡፡

ምስጋና በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ሁሌም ቢሆን የጸሎቶች ሁሉ መግቢያ ነው፡፡ በቅዳሴም ይሁን በማንኛውም የማኅበር ጸሎታችን ውስጥ ምስጋና ዋና ነገር ነው፡፡ በማዕድ ጸሎት እንዲሁም በጸሎተ ፍትሀት ውስጥ እንኳን ምስጋና ቀዳሜ ነው፡፡ በታላቁ ጸሎታችንም ውስጥ ከሁሉ አስቀድመን “አባታችን ሆይ በሰማያት የምትኖር ስምህ ይቀደስ” በሚል ምስጋና እንድንጀምር ጌታችን አስተምሮናል፡፡ ነቢየ እግዚአብሔር ዳዊት “ስለ ጽድቅህ ፍርድ በእኩለ ሌሊት አመሰግንህ ዘንድ እነሣለሁ” (መዝ. ፻፲፱፥፷፪) እንዳለው በቤተ ክርስቲያን በመዓልት ብቻ ሳይወሰን ምስጋናው በሌሊትም ይቀጥላል፡፡

እግዚአብሔርን ስለ ሁሉ ነገር ማመስገናችን እርሱ የሚያደርገው ማንኛውም ነገር ሁሉ መልካም ስለሆነ ነው፡፡ ጸሎታችን እርሱን ስናነሣ ቸር፣ ለጋስ፣ መሐሪ የምንለውም ለዚህ ነው፡፡ “እግዚአብሔርምን ለሚወዱት እንደ ሐሳቡም ለተጠሩት ሁሉ ነገር ከበጎ እንዲደረግ እናውቃለን፡፡” (ሮሜ. ፰፥፳፰) ሲል ሐዋርያው እንደገለጸው ክፉ ገጠመኝ ሲደርስብን እንኳ የአምላካችንን መልካምነት ተስፋ በማድረግ እንደ ኢዮብ ልናመሰግን እምነታችን ግድ ይለናል፡፡

እግዚአብሔር የሚሠራው ሁሉ ሙሉ በሙሉ መልካም መሆኑን ከዮሴፍ ሕይወት መማር እንችላለን፡፡ ወንድሞቹ በክፋትና በምቀኝነት ተነሳስተው ለባርነት አሳልፈው ሸጡት፡፡ እግዚአብሔር ግን ወደ መልካምነት ቀየረለት፡፡ ግብፅ ከወረደ በኋላ መልካም ነገር ገጠመው፡፡ ቀጥሎም ሌላ ክፉ ሰው ገጥሞት ወደ ወሕኒ ቢገባም አሁንም እግዚአብሔር ፈተናውን ለበጎ አድርጎለት በግብፅ ከንጉሡ ቀጥሎ ያለውን ሥልጣን ለመቀበል ቻለ፡፡ እርሱ ራሱ ዮሴፍ ለወንድሞቹ እንዲህ ነበር ያላቸው፡፡ “እናንተ ክፉ ነገርን አሰባችሁብኝ እግዚአብሔር ግን ዛሬ እንደሆነው ብዙ ሕዝብ እንዲድን ለማድረግ ለመልካም አሰበው፡፡”” (ዘፍ. ፶፥፳)፡፡

የምስጋና ደረጃዎች፡-

የምስጋና ትንሽ ደረጃ እግዚአብሔርን ስለ ተዓምራቶቹ፣ ስለ ስጦታዎቹ፣ ደስ ስላሰኘን፣ ስለ ምድራዊ በረከቶቻችን፣ ስላገኘነው ስኬት፣ ስለ ብልጽግናችን፣ ሕይወታችን ስለ መባረኩና ኑሮ ቀለል እንዲለን ስላስቻለን ብለን የምናቀርበው ምስጋና ነው፡፡ አንዳንድ ጊዜ ግን በዚህ ደረጃ እንኳ ማመስገን ሲሳነን ይታያል፡፡

የምስጋና ታላቁ ደረጃ ደግሞ አለ፡፡ ይኸውም በሕይወት ውስጥ ቀላል ከሚመስሉ በረከቶች ከራሱ ከሕይወት አንሥቶ፤ ታሞ መዳንን የመሰሉ አስደናቂ ስጦታዎችና በዓይን የማይታዩትን መንፈሳዊ በረከቶች ስለመቀበላችን የምናርበው የምስጋና ዓይነት ነው፡፡ መልካሙ ስለተደረገልን ብቻ ሳይሆን ክፉውም ስላልሆነብን የምናቀርበው ምስጋና ደረጃው ከዚሁ ጋር ነው፡፡ የምስጋና ከፍተኛው ደረጃ ደግሞ ስለገጠሙን መከራዎች የምናቀርበው ነው፤ በመከራ ውስጥ ሆነን እንኳ ልናመሰግነው ይገባናልና፡፡ ቅዱሳን ሐዋርት ይህ ዓይነት የምስጋና ሕይወት ነበራቸው፡፡ “እነርሱም ስለ ስሙ ይናቁ ዘንድ የተገባቸው ሆነው ስለተቆጠሩ ደስ እያላቸው ከሸንጎው ፊት ወጡ፡፡” (የሐዋ. ፭፥፵፩) መከራውን ተቋመቁን በአሸናፊነት እንድንወጣው ስላደረገን ልናመሰግን ይገባናል፡፡ ሌሎቹም የጌታ ደቀ መዛሙርት ሁላቸው መከራ በተቀበሉ ቁጥር የማይገባቸውን በረከት እንደተቀበሉ ቆጥረው ደስ እያላቸው ያመሰግኑ ነበር፡፡ “ይህ ስለ ክርስቶስ ተሰጥቷችኋልና ስለ እርሱ መከራ ደግሞ ልትቀበሉ እንጂ በእርሱ ልታምኑ ብቻ አይደለም፡፡” (ፊል. ፩፥፳፱) እንዲል፡፡ እንዲሁም “በመንፈቀ ሌሊት ግን ጳውሎስና ሲላስ እየጸለዩ እግዚአብሔርን በዜማ ያመሰግኑ ነበር፤ እስረኞቹም ያደምጧቸው ነበር፡፡” (ሐዋ. ፲፮፥፳፭) በማለት ምስጋና እንዲገባ ይነግረናል፡፡

ይቆየን

0 replies

Leave a Reply

Want to join the discussion?
Feel free to contribute!

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *