እሰይ እሰይ እሰይ

በትዕግሥት ባሳዝነው

በድቅድቁ ሌሊት፣

በዕንባ ጸሎት ተጠምጄ፣

በአታላዩ ምላሶቹ ፤

በጠላቴ ተከድቼ።

ነጋ ጠባ ማዳንህን ስጠባበቅ፣

የመምጣትህን ዜና መውረጃህን ስናፍቅ።

ተወለድክልኝ የኔ ጌታ ፣

ሞቴን አንተ ልትሞት፣

መጣህልኝ የኔ ተስፋ ፣

ልታድነኝ ከዳግም ሞት፣

ወረድክልኝ የኔ አለኝታ።

ልትፈታኝ ከባርነት፣

የአብርሃም ደግነት፣

ላያነጣኝ ከኃጢአቴ፣

የሙሴ የዋህነት፤

ላያስፈታኝ ከእሥራቴ፣

የዳዊት ንግሥና ፤

ላይጠብቀኝ ከጠላቴ፣

የሰለሞን ጥበብ፤

ላያጥናናኝ ከሐዘኔ፣

የመልከ ጼዲቅ ክህነት፤

ላያስፈታኝ ከእሥራቴ፣

የአስቴር ጸሎት፤

ላያስጥለኝ ከገዳዬ፣

የመርዶኪዎስ ታማኝነት፤

ላያሰርዝ የአዋጅ ደብዳቤዬን፣

የኤሊያስ ግሳፄ፤

ላይመልሰው ክፉ ልቤን፣

የዮናስ ስብከት፤

ላያሽረው ሕመም ቁስሌን።

በአክአብ ደም ተለውሰው እጆቼ፣

የአቤል ደሙ በፊትህ ሁነውብኝ ከሳሾቼ፣

ነበር እኮ ሰዶምነት አመል ግብሬ፣

ቂም በቀልም መልክ ግንባሬ።

አመንዝራ፣ ሴሰኝነት መለያዬ፣

መለያየት፣ አድመኝነት መድመቂያዬ።

አልነበረም መልክህ መልኬ፤

ግብርህ ግብሬ፤

ስምህ መጠራዬ።

እና መጣህልኝ የኔ ጌታ፤

ልትፈታኝ ከእሥራቴ፤

ወረድክልኝ የኔ አለኝታ፣

ልታድነኝ ከዳግም ሞት፣

ተወለድክልኝ የኔ ተስፋ።

በሞቴ አንተ ልትሞት፣

ክፋት በደል ቢያቆሽሸኝ፣

ሕግን መሻር ባሪያ አድርጎኝ።

ጽድቄም ቢሆን የመርገም ጨርቅ፣

መሥዋቴ እዚሁ ቢደርቅ፣

ጾም ጸሎቴ በደል ባይፍቅ።

ዕንባ ሐዘኔ ባያስጥለኝ ከባርነት፤

ግብሬ ሆኖ መለያዬ፣

መውጫ አጥቼ ከመከራ፣

ስሜ ጠፍቶ በስምህ ላልጠራ።

መምጣትህን እየናፈኩ፣

ማዳንህን እየጠበኩ።

መጣህልኝ የኔ ጌታ፣

በሞቴ አንተ ልትሞት፣

ወረድክልኝ የኔ ተስፋ።

ልታድነኝ ከዳግም ሞት፣

ተወለድክልኝ የኔ አለኝታ፣

ልታወጣኝ ከባርነት።

እሰይ እሰይ እሰይ፤

ተወለደ የኔ ጌታ፣

ተጠመቀ የኔ አለኝታ።

እሰይ እሰይ እሰይ!!!

 

እንኳን ለጌታችን ለመድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዓለ ልደት በሰላም አደረሳችሁ!

መልካም በዓል ይሁንላችሁ!!!

 

0 replies

Leave a Reply

Want to join the discussion?
Feel free to contribute!

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *