በኣታ ለማርያም

ታኅሣሥ ሦስት በዚህች ቀን አምላክን የወለደች እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ሦስት ዓመት ሲሆናት ወደ ቤተ መቅደስ የገባችበት ነው፡፡ እርሷ ለእግዚአብሔር የስእለት ልጅ ነበረችና፡፡

እናቷ ቅድስት ሐና ልጅ የሌላት ስለሆነች በቤተ እግዚአብሔር ውስጥ ከሴቶች ተለይታ ርቃ ትኖር ነበር፡፡ ሽማግሌ ከሆነ ከኢያቄም ከባሏ ጋርም እጅግ የምታዝን ሆነች፡፡ እግዚአብሔርም ሐዘናቸውን ሰማ፤ ቅድስት ሐናም እንዲህ ብላ ለእግዚአብሔር ተሳለች፡፡ “የሰጠኸኝን ፍሬ ለእግዚአብሔር አገልጋይ አደርገዋለሁ፡፡”

ቅድስት ድንግል እመቤታችን ማርያምንም በወለደቻት ጊዜ ሦስት ዓመት በቤቷ ውስጥ አሳደገቻት፡፡ ከዚህም በኋላ ከደናግል ትኖር ዘንድ ወደ ቤተ መቅደስ ወሰደቻት፡፡ ካህኑ ዘካርያስም ስለ ምግቧ በመጨነቁ ሕዝቡን ሰብስቦ ሳለ መልአኩ ፋኑኤል ኅብስት ሰማያዊ ጽዋዕ ይዞ ከሰማይ ወረደ፤ ዘካርያስ ለእርሱ የመጣ ሀብት መስሎት ታጥቆ እጅ ነሥቶ ቢቆም ወደ ላይ ራቀበት፡፡ ከስምዖን ጀምሮ በዚያ የተሰበሰቡት ሰዎችም በተራ ቢሞክሩ በተመሳሳይ ወደ ላይ ራቀባቸው፡፡ ምን አልባት ለእንግዶች የመጣ ሀብት እንደሆነ ብለው ሐና እና ኢያቄም እንዲቀርቡ አደረጓቸው፤ ለእነርሱም ራቀባቸው፤ ዘካርያስም ሐናን እግዚአብሔር የሚያደርገውን የሚያውቅ የለምና ልጅቷን ትተሸ ወደዚህ ነይ ባላት ጊዜ ቅድስት ድንግል ማርያም ድክ ድክ እያለች እናቷን ስትከተል መልአኩ ፋኑኤል ወደ እርሷ ቀርቦ አንድ ክንፉን አንጥፎ አንድ ክንፉን ጋርዶ መግቧት ዐረገ፤ ሊቀ ካህናቱም ሕዝቡም የምግቧ ነገር ከተያዘልን በቤት እግዚአብሔር ትኑር ብለው አስገቧት፤ ይህም ታኅሣሥ ፫ ቀን ነበር፡፡

በቤተ መቅደስም ምግቧን ከመላእክት እየተቀበለች አሥራ ሁለት ዓመት ኖረች፡፡ ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርሰቶስ ወደ ዓለም መጥቶ ከእርሷ ሥጋን እስከነሣ ድረስ፡፡

ከሴቶች ሁሉ የተመረጠች ይህቺ ናት፤ በቤተ መቅደስም በመኖር አሥራ ሁለት ዓመት ሲፈጸምላት እርሷ ለእግዚአብሔር የተሰጠች የስእለት ልጅ ናትና ለሚጠብቃት ይሰጧት ዘንድ ካህናት እርስ በእርሳቸው ተማከሩ፡፡ በሴቶች ላይ የሚደርስ በእርሷ ላይም ይደርስባታል ብለው ስለፈሩ በቤተ መቅደስ ውስጥ ይተዋት ዘንድ ለእነርሱ ትክክል መስሎ አልታያቸውም፡፡ ስለዚህም ሊጠብቃት ለሚገባው በእርሷ ላይ እጮ ለያኖሩ ወደዱ፡፡

ከዚህም አስቀድሞ ሊቀ ካህናት ዘካርያስ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን “ልጄ ማርያም ሆይ አንቺ እንዳደግሽና ለአካለ መጠን እንደደረስሽ ዕወቂ፤ ልትታጨ ትወጃለሽን? እግዚአብሔርን የሚፈራ መልካም የሆነ የተባረከ ጎልማሳ እንፈልግልሽን? ወይም በሕይወትሽ ዘመን ሁሉ በቤተ መቅደስ ተቀምጠሽ እግዚአብሔርን ልታገለግዪው የምትሺ ከሆነ በሴቶች ላይ የሚደርሰው በሚደርስብሽ ወራት ወደ ቤተ መቅደስ ደጅ ከመግባት ትጠበቂ ዘንድ በኦሪቱ የተፈጸመውን የርግማን ሥርዓት በአንቺ ላይ እንሠራለን” አላት፡፡

ቅድስት ድንግል እመቤታችን ማርያምም “እነሆ እኔ የእግዚአብሔር አገልጋዩ በፊታችሁ ነኝ፤ አባትና እናት የሉኝም፤ ስሙ ቡሩክ ምስጉን ከሆነ ከእግዚአብሔር በታች ከእናትና አባት ፈንታ እናንት ናችሁና የእግዚአብሔር ትእዛዝ እንደምታውቁ አድርጉ” ብላ መለሰች፡፡

ካህናቱና ማኅበሩም ሁሉ ዘካርያስን ወደ ቤተ መቅደስ ገብተህ ስለዚህች ብላቴና ማርያም ወደ እግዚአብሔር ጸልይ አሉት፡፡ ዘካርያስም ገብቶ ሲጸልይ በዚያን ጊዜ የእግዚአብሔር መልአክ ተገለጠለትና እንዲህ አለው፡- “ዘካርያስ ሆይ ወጥተህ ከዳዊት ወገን ሚስቶቻቸው የሞቱባቸውን ሁሉ ወንዶች ሰብስብ፤ የእያንዳንዱንም በትር ከስሙ ጋር ውሰድ፡፡ ወደ ቤተ መቅደስም በምሽት ገብተህ ወደ እግዚአብሔር ጸልይበት፡፡ በነጋ ጊዜም በትሮቻቸውን አውጣ፡፡ እግዚአብሔርም በበትሩ ላይ ምልክት ለገለጠልህ ለዚያ ሰው ማርያምን ተቀብሎ ሊጠብቃት ይገባዋል፡፡”

ካህኑ ዘካርያስም ወጥቶ አንድነት ለተሰበሰቡት ሕዝብ የእግዚአብሔር መልአክ የነገረውን ነገራቸው፡፡ በዚያንም ጊዜ “ከዳዊት ወገን ጎልማሳም ቢሆን ሽማግሌም ቢሆን ሚስቱ የሞተችበት ሁሉ በኢየሩሳሌም ወደ አለ ቤተ መቅደስ ይሂድ” እያሉ ዐዋጅን ዙረው የሚናገሩ በእስራኤል አገር ሁሉ ላከ፡፡

ከዳዊት ወገን የሆነ ጠራቢው ዮሴፍም በሰማ ጊዜ በትሩን ይዞ ከናዝሬት ወደ ኢየሩሳሌም ሄደ፡፡ ካህኑ ዘካርያስም የሁሉንም በትሮች ተቀብሎ ስማቸውን በላያቸው ጻፈ፡፡ ቁጥራቸውም አንድ ሺህ ዘጠኝ መቶ ሰማንያ አምስት በትሮችን ወደ ቤተ መቅደስ አስገብቶ ወደ እግዚአብሔር ጸለየ፡፡ እንዲሁም ሰዎች ሁሉ ከቤተ መቅደስ ውጪ ቆመው ይጸልዩ ነበር፡፡ ዘካርያስም ጸሎቱን በፈጸመ ጊዜ በማግስቱ  ለእያንዳንዱ በትራቸውን አውጥቶ ሰጠ፡፡ ጠራቢው ዮሴፍም በትሩን ሊቀበል በቀረበ ጊዜ የዮሴፍ በትር አብባና አፍርታ ተገኘች፡፡ ከበትሩም ጫፍ ላይ ኦ ዮሴፍ ወልደ ዳዊት ዕቀባ ለማርያም ፍኅርትከ፤ ዮሴፍ ሆይ እጮኛህ ማርያምን ጠብቃት” የሚል ጽሑፍ አገኙ፤ ርግብም እየበረረች መጥታ በአረጋዊው ዮሴፍ ራስ ላይ አርፋለች፤ ካህናቱና ሕዝቡም ሁሉ አይተው እጅግ አደነቁ፤ ምስጉን የሆነ እግዚአብሔርምን አመሰገኑት፡፡

ዘካርያስም ዮሴፍን “ዮሴፍ ሆይ ከእግዚአብሔር የታዘዘ መልአክ እንደተናገረ ድንግል ማርያምን ወደ ቤትህ ወስደህ ጠብቃት” አለው፡፡ የሴፍም ቅድስት ድንግል ማርያምን ከካህናት እጅ ተቀበላት፣ በእርሱም ዘንድ ኖረች፡፡ ከዚህም በኋላ የመላእክት አለቃ ቅዱስ ገብርኤል ስለ እግዚአብሔር ልጅ ከእርሷ ሰው ሁኖ ስለመወለዱ በዮሴፍ ቤት አበሠራት፡፡

ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ቃል ኪዳንና በረከት ያሳትፈን፡፡ አሜን፡፡

ምንጭ፡- ስንክሳር ታኅሣሥ ፫ ቀን

0 replies

Leave a Reply

Want to join the discussion?
Feel free to contribute!

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *