‹‹በመስቀሉ አርኀወ ገነተ፤ በመስቀሉ ገነትን ከፈተ›› ድጓ ዘቅዱስ ያሬድ

በመ/ር ለይኩን አዳሙ ባሕር ዳርማእከል
ክፍል -፪
  ፬.ቅድስት ዕሌኒ ማን ናት ?
ከመልካም ዛፍ የተገኘች መልካም ፍሬ የሆነችው ቅድስት ዕሌኒ መንፈሳዊ እና ሥጋዊ ጥበብን የሚያሳውቁ ቅዱሳት መጻሕፍትን እያነበበችና እየተማረች በጥበብና በሞገስ ካደገች በኋላ ተርቢኖስ ከተባለ ሰው ጋር በሕገ ቤተ ክርስቲያን ትዳር መሥርታ መኖር ጀመረች፡፡ የሚተዳደሩትም በንግድ ነበር፡፡ በድሮ ዘመን ነጋዴዎች ለንግድ ወደ ሌላው ሀገር ሲሄዱ ከአምስትና ከስድስት ዓመታት በላይ ቆይተው ለብዙ ዓመታት የሚሆናቸውን ገንዘብ አፍርተው ይመለሱ እንደነበር ታሪክ ያስረዳል፡፡ የዕሌኒ ባል ተርቢኖስም የሚተዳደረው ትዳሩንም የሚመራው በንግድ ስለነበረ ወደ ንግድ ሲሄድ ለቅድስት ዕሌኒ የምትረዳት የምታገለግላት ሠራተኛ ቀጥሮላት ከባልንጀሮቹ ጋር ወደ ንግድ ሄደ፡፡
ተርቢኖስ ጓደኞቹ ከአምስት ዓመታት በኋላ አቀበት ወጥተው ቁልቁለት ወርደው ባሕር አቋርጠው የሚሸጠውን ሽጠው የሚገዛውን ገዝተው ማዕበሉ ሞገዱ ሳያሰጥማቸው ወረታቸውን ይዘው ከተሻገሩ በኋላ በእግዚአብሔር ቸርነት ያሰብነው ተሳክቶልን ከማዕበል ከሞገድ ተርፈን ከዚህ መድረሳችን መልካም ነው፡፡ ነገር ግን ሚስቶቻችን ሌላ ወንድ ወደውና ለምደው እንዳይቆዩን እንጂ ተባባሉ፡፡ተርቢኖስም እንዲህ አለ «እኔስ ማዕበሉን ሞገዱን አምላኬ ጠብቆ ከዚህ አደረሰኝ እንጂ ሚስቴን እንዲህ ባለ ግብር አልጠራጠራትም» አለ ባልንጀሮቹም ‹‹የአንተ ሚስት ከሔዋን ልጆች የተለየች ናትን በማለት ተዘባበቱበት ፡፡ እርሱም መልሰ የእናንተ ሚስቶች ሃይማኖትና ምግባር ስለሚጎድላቸው ነው የኔ ሚስት ግን ሃይማኖትና ምግባር ፈሪሃ እግዚአብሔር በውስጧ ስላለ በዚህ አልጠራጠራትም በማለት መለሰላቸው፡፡
ከባልንጀሮቹ መካከል አንዱ እንዲህ አለ‹‹ሂጀ ወድጃት ለምጃት ብመጣ ምን ይቅጣህ አለው፡፡ እርሱም «በግብር ማወቅ ቀርቶ መልኳን አይተህ ብትመጣ እስከ አሁን ወጥቼ ወርጄ ያተረፍሁትን ወረቴን እሰጥሃለሁ አንተስ ወደሃት ለምደሃት ባትመጣ ምን ይቅጣህ» አለው ያም ነጋዴ የለፋሁበትን ወረቴን አስይዛለሁ»አለ ይህን ንግግራቸውን በመሐላ አጸኑት ተነሥቶም ወደ ተርቢኖስ ቤት ሂዶ ከደረሰ በኋላ የተርቢኖስን ጎረቤቶች ዕሌንኒን ጥሩልኝ አላቸው፡፡እነርሱም እርሷንስ ባሏ ከሄደ ጀምሮ እንኳንስ ሰው ፀሐይም አይቷት አያውቅ አሉት፡፡እርሱም ሠራተኛዋን ጥሩልኝ አለ የቤት ሠራተኛዋን አስጠርቶ እመቤትሽን ዕሌኒን እፈልጋታለሁ ጥሪልኝ አላት ሠራተኛዋም እርሷስ ይህ ሥራዋም አይደለም ለኔም አይቻለኝም አለችው፡፡
ብዙ ገንዘብ እሰጥሻለሁ ለእርሷም እሰጣታለሁ አላት ገንዘብ አያታልለው የለምና ሠራተኛዋም እሽ ብላ ወደ ዕሌኒ ሂዳ ሰው ይጠራሻል አለቻት ትሰፋ ነበር ቢሉ በወስፌዋ ትፈትል ነብር ቢሉ በእንዝርቷ እንዲህ ያለግብር ከወዴት ታውቂብኝ አለሽ ብላ መታቻት፡፡ ተመልሳ ተው ብልህ አስመታኽኝ አለችው፡፡ እርሱም ባልና ሚስቱ የሚተዋወቁበት አንድ ነገር ስጭኝ ብሎ ብዙ ገንዘብ ሰጣት እርሷም እንዲህ አለችው ‹‹በከተማው ነጋዴዎች መጡ ከባሕር ወጡ የብስ ረገጡ ብለህ አስነግር›› አለችው እርሱም ይህን ቃል በከተማው እንዲነገር አደረገ፡፡
ሠራተኛዋም ዕሌኒን ‹‹ነጋዴዎች መጡ ከባሕር ወጡ የብስ ረገጡ እየተባለ በከተማው ይነገራል ተነሽና ገላሽን ታጠቢ ልብስሽን ቀይሪ›› አለቻት፡፡ ቅድስት ዕሌኒም እውነት መስሏት ‹‹ይህን እኮ የምታደርጊው አንች ነበርሽ›› አለቻት፡፡ ‹‹በይ ተነሽ መታጠቢያ ቤት ግቢ ገላሽን ልጠብሽ›› አለቻት ዕሌኒም ወደ መታጠቢያ ቤት ገብታ ልብሷን አወለቀች ከደረቷ ላይ የበቀለ የአንበሳ ፀጉር የሚመስል ነበራት፡፡ ባልና ሚስቱ ሲጨዋወቱ የሚመለከቱት ከዕንቊ የተሠራ ቀለበት ከዚያ ላይ አስሮላት ነበር ስትታጠብ አውልቃ አስቀምጣው ስለነበረ ታጥባ ተመልሳ ስትቀመጥ ሠራተኛዋ አውጥታ ለዚያ ነጋዴ ሰጠቸው፡፡ እርሱም ደስ እያለው ወደጓደኞቹ ሄደ እንዴት ሁነህ መጣህ? አሉት ‹‹ወድጃት ለምጃት ወዳኝ ለምዳኝ መጣሁ›› አላቸው፡፡
ተርቢኖስም ‹‹አላምንም የኔ ሚስት ይህን አታደርገውም››አለው፡፡ ያነጋዴም ሁለቱ የሚተዋወቁበትን ያን የዕንቊ ቀለበት አሳየው እርሱም እውነት መስሎት ለብዙ ዓመታት የደከመበትን ወረቱን ለነጋዴው አስረከበና ወደ ቤቱ ሄደ፡፡ ጓደኞቹ ከቤታቸው ገብተው ከሚስቶቻቸው ጋር ተድላ ደስታ ሲያደርጉ እርሱ ግን አዝኖ ተክዞ ተቀመጠ፡፡ ዕሌኒም እንዲህ አለችው ‹‹ምነው በጓደኞችህ ቤት ተድላ ደስታ እየተደረገ አንተ አዘንህ ተከዝህ አንገትህን ደፋህ? አለችው ›› ተርቢኖስም እንዲህ አላት፡፡ ‹‹እነርሱ እኮ ወረታቸውን ማዕበል ሞገድ ሳያሰጥምባቸው በሰላም ይዘው ገብተው ነው እኔ ያላዘንሁትን ማን ይዘን? የወጣሁበትን የወረድሁበትን ንብረቴን ባሕር ሲያሰጥምብኝ›› አላት፡፡
እርሷም ‹‹ይህማ ምን ቁም ነገር አለው ያንተ ስልሳ ዘመድ የኔ ስልሳ ዘመድ አለን ተበድረህ ትሠራለህ አይዞህ›› አለችው፡፡ እርሱም በነገር እንዲህ ሲል ወጋት ‹‹አንችን እኮ ሁሉ ያምንሻል ይወድሻል እኔን ማን ይወደኛል? ማንስ ያምነኛል? እኔስ በተከበርኩበት ሀገሬ ተዋርጀ ባበደረሁበት ሀገሬ ተበድሬ አልኖርም ሀገሬን ጥየ እኼዳለሁ አላት›› እርሷም ‹‹አንተና እኔ አንድ አካል ነን ከምትሄድበት አብሬ እሄዳለሁ›› ብላ ተነሣች ‹‹እርሱም በይ ነይ›› ብሎ አስከተላት ወደ መርከብ ይዟት ገባ መርከብ ላይ ከተሳፈሩ በኋላ ‹‹እኅቴ ምነው ሳምንሽ ከዳሽኝ? ስወድሽ ጠላሽኝ?›› አላት፡፡ እርሷም ‹‹አንተን ጠልቼ ማነን ወድጄ? አንተን ከድቼ ማንን ለምጄ?›› አለችው፡፡
ተርቢኖስም የወደድሽው የለመድሽውማ ይኸው አለና ያን የሚተዋወቁበትን ዕንቊ አሳያት ‹‹እርሷም እንኳንስ ልወደው ልለምደው መልኩንም አላየሁት መልኬንም አላየኝ አለችው፡፡ ታግዘኝ ብለህ የሰጠኸኝ ሠራተኛ ነገሩን ነገረችኝ እንቢ ብየ መጥቼ መለስኋት ነጋዴዎች መጡ ይባላል ገላሽን ታጠቢ ልጠብሽ ብላ ከደረቴ ፈታችው ከዚያም ወስዳ ሰጥታው ይሆናል እንጂ እግዚአብሔር ምስክሬ ነው የማውቀው ነገር የለም አለችው”፡፡
ተርቢኖስም እንዲህ አላት ‹‹እግዚአብሔር ምስክርሽ ከሆነ ምንም ነገር ካለወቅሸማ ብሎ በሳጥን ቆልፎ ‹‹ግብርኪ ይትሉኪ፤ሥራሽ ይከተልሽ›› ብሎ ወደ ባሕሩ ወረወራት፡፡ እርሷም ዮናስን በባሕር ውስጥ የጠበቀ የምታመልከው አምላኳ በረድኤት ከልሏት ሳጥኑ ሳያፍናት ባሕሩም ሳያሰጥማት ብዙ መንገድ ከሔደች በኋላ ምንም ሳትሆን ሮም የምትባል ሀገር ላይ ስትደርስ ባሕሩ ሳጥኑን የብስ ላይ ተፋው፡፡
በዚያም የንጉሡ ባለሟሎች ነበሩና የነጋዴ ወርቅ መስሏቸው ደስ አላቸው ከፍተው ቢያዩት እንደ ፀሐይ የምታበራ ሴት አገኙ፡፡ ይቺስ ለእኔ ትገባለች ለእኔ ትገባለች በማለት እርስ በርሳቸው ተጣሉ መስማማት ሲያቅታቸው እንግዲያው ‹‹ለንጉሥ እንጂ ለእኛ አትገባም›› ብለው ወስደው ለንጉሡ ሰጡት፡፡

          ንጉሡ ቁንስጣም አይቶ በጣም ደስ አለው የአሕዛብ ነገሥታት ለግብረ ሥጋ ግንኙት አይቸኩሉምና የውስጥ ሰውነቷን የሚያጠራ ምግብና መጠጥ የውጭ ሰውነቷን የሚያጠራ ቅባትና ልብስ እየሰጣት ከቆየች በኋላ ለጋብቻ ጠየቃት፡፡ እርሷም አንተ አሕዛብ እኔ ክርስቲያን እንዴት ይሆናል? አለችው፡፡ በመልኳ ማማር ባነጋገሯ ለዛ ወዷታልና የአንቺን ሃይማኖት እከተላለሁ አምላክሽን አመልካለሁ አላት፡፡
እንግዲያወስ ዐርባ ቀን ስጠኝ ወደ አምላኬ ልጸልይ አለችው እሽ አላት፡፡ ሱባኤ ያዘች ወደ እግዚአብሔርም ጮኸች የዳዊት አባት የዳዊት ልጅ ሆይ ምነው ለአሕዛብ አሳልፈህ ሰጠኸኝ ብላ ከምግብ ተከልክላ በጾምና በጸሎት እግዚአብሔርን ጠየቀች፡፡ ከእግዚአብሔር የታዘዘ መልአክ መጥቶ ያንቺ ደም እርሱን ይቀድሰዋል በደምሽ አጥምቂው ከእርሱም ደግ ልጅ ትወልጃለሽ የአባቱንም መንግሥት ይወርሳል ንጉሥም ይሆናል አላት፡፡ እርሷም እንዲህ ስትል አምላኳን አመሰገነች ‹‹ከአቅሜ በላይ እንድፈተን ያልተውኸኝ አምላኬ አመሰግንሃለሁ በማለት አምላኳን አመሰገነችና እሽ በጄ አለችው፡፡ በዚያውን ቀን በግብር ተዋወቁ ፀነሰች ወንድ ልጅንም ወለደች ስሙንም ቆስጠንጢኖስ አለችው፡፡ ቆስጠንጢኖስ ማለት ሐመልማል ወይም ልምላሜ ማለት ነው፡፡
እናቱ ወደ ባሕር በተጣለች ጊዜ በእግዚአብሔር ጥበቃ ወጥታ ከወንዝ ዳር በሚገኝ ለምለም ቦታ ተገኝታ ነበርና፡፡ ቆስጠንጢኖስ ማለት ሐመልሚል ወይም ኅብረ ብዙ ማለት ሲሆን ኅብረ ነገዱን፣ኅብረ ትውልዱን፣ኅብረ ጥበቡን አስመልክቶ የወጣለት ምሥጢራዊ ስም ነው፡፡ በኅብረ ነገድ ከሁለት ወገን ከሕዝብና ከአሕዛብ ተወልዷልና በኅብረ ትውልድ በአባቱ አረማዊ ሲሆን በእናቱ አይሁዳዊ ነውና በኅብረ ጥበብም ጥበብ ሥጋዊ ጥበብ መንፈሳዊ ተሰጥቶታልና፡፡ ቅድስት ዕሌኒም ልጇን ክርስትናን ማለትም የክርቶስን ግርፋቱን ስቅላቱን ሞቱን ትንሣኤውን ዕርገቱን እየነገረች ስለክርስትና ሃይማኖትና በክርስቲያኖች ላይ የደረሰውን ግፍና መከራ ስደት የአብያተ ክርስቲያቱን መቃጠልና መዘጋት የመጻሕፍቶቹን መቆንጸል እየነገረች አሳደገቸው፡፡ የንጉሥ ልጅ ንጉሥ እንደሚሆን አስቀድማ ተረድተታ ነበርና፡፡

        ቁንስጣም ለመንግሥት የሚበቃ ልጅ ስላልነበረው ወንድ ልጅ ስለወለደችለት ከደስታው ብዛት የተነሣ የከበረ ስጦታ በመስጠት በዕንቊና በወርቅ አስጊጦ መኳንንቱና መሳፍንቱ ታላላቅ ሰዎች በተገኙበት በዓል አድርጎ አነገሣትና ንግሥት ዕሌኒ ተባለች (ድርሳነ መስቀል ዘጥር)
ቆስጠንጢኖስን የሀገሩን ባህልና ቋንቋ ጠንቅቆ ያውቅ ስለነበረ በበታቹ መስፍን አድርጎ ሾመው፡፡እርሱን በሾመው በሁለት ዓመቱ ቁንስጣ በተወለደ በዘጠና ዓመቱ ዐረፈ፡፡ ቆስጠንጢኖስም የአባቱን መንግሥት ተረክቦ የሮም ንጉሥ ኾነ ዕሌኒም የንጉሥ ሚስት የንጉሥ እናት ለመሆን በቃች፡፡
…………….. ይቆየን !

0 replies

Leave a Reply

Want to join the discussion?
Feel free to contribute!

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *