ኀበነ ንኅበር በዘዚአከ መንፈስ ቅዱስ- የአንተ በሆነ መንፈስ ቅዱስ አንድ መሆንን ስጠን!

በዐለም የክርስትና ታሪክ ውስጥ ምእመናን  ከተፈተኑበት ፈተናዎች አንዱ በአንድ በታወቀ መንበር ላይ ከአንድ በላይ ፓትርያርኮች ወይም ፖፖች መሾም ነው፡፡በቤተ ክርስቲያን ታሪክ ቀድሞ በነበረ ፓትርያርክ ወይም ፖፕ ለመጀመሪያ ጊዜ ተደርቦ እንደተሾመ የሚነገርለት ቅዱስ አቡሊዲስ ዘሮም ነው፡፡ ቅዱስ አቡሊዲስ (Hippolytus) ተቀናቃኝ ፖፕ የሆነበት መንገድ ከዘመኑ የተነሣ በታሪክ ብዙም ባይገለጽም ተቀናቃኝ ሆኖ የተሾመው ግን ካሊክሰቶስ ቀዳማዊ (Pope Callixtus I) የሮም ፖፕ በነበረበት ዘመን ነበር፡፡ ሆኖም ካሊክስቶስ ሲያልፍ በወንበሩ ከተተካው ከፖፕ ፖንትያን (Pope Pontian) ጋር ታርቆ ችግራቸውን ፈትተዋል፡፡ በመጨረሻም ያረፈው በሰማዕትነት ስለነበረ ተጋድሎው በቅድስና ይታሰባል፡፡ በሮም ካቶሊክ ዘንድ በዓሉ የሚከበርለት ከታረቀው ከፖፕ ፖንትያን ጋር በአንድነት በእነርሱ አቆጣጠር ኦገስት በሚባለው ወራቸው በ13ኛው ቀን ነው፡፡ በዚህም ምክንያት ዕርቅን አውርዶ ችግርንም ፈትቶ በአንድነት መከበርና መታሰብ የጀመረው ከመጀመሪያው ዐለምአቀፍ ጉባኤ ከጉባኤ ኒቅያ አንድ መቶ ዐመት በፊት ገና ሦስተኛው ክፍለ ዘመን  መጀመሪያ ላይ እንደነበረ ታሪካዊ አስረጅ አለው ማለት ነው፡፡

በርግጥ በፖፕ ላይ ፖፕ እየተሾመ መወዛገብ በሮማ ካቶሊክ ታሪክ ደጋግሞ ያጋጠመ ነገር ነበር፡፡አጥኝዎች እንደሚሉት በሮም ካቶሊክ ታሪክ ይህ ችግር ለ42 ጊዜ ያህል ተከስቷል፡፡ ሆኖም ከፍተኛ ውዝግብ ያስከተለው በ14ኛው ክፍለ ዘመን መግቢያ ላይ የተከሰተውና ለ40 ዐመታት የቆየው ታላቅ ውዝግብ ነው፡፡ከ1378 -1417 እንደቆየ የሚነገርለት ይህ ክፍፍል በሮማ ካቶሊክ ታሪክ ትልቁና በታሪክ ተመራማሪዎችም ዘንድ ትልቁ የምዕራቡ ክፍፍል እየተባለ የሚጠራና ከሦስት በላይ ፖፖች እኔ ነኝ ሕጋዊ ፖፕ በማለት የተወዘጋቡበት ነበር፡፡ መነሻውም በግልጽ ፖለቲካዊ ጣልቃገብነት የፈጠረው እንደነበር ይታወቃል፡፡ቢሆንም ከ1414 – 1418 ኮንስታንስ ላይ በተካሔደ ጉባኤ ችግሩን ፈትተው አንድነታቸውን ለመመለስ ችለዋል፡፡

በምሥራቁም ዐለም ድርጊቱ በተለያዩ ጊዜያት ሲከሰት ኖሯል፡፡ለምሳሌ በቁስጥንጥንያው ንጉሥ ታግዞ በእስክንድርያ መንበር  በቅዱስ አትናቴዎስ ላይ ተተክቶ የነበረው ጊዮርጊስ በእኛ ሊቃውንት ዘንድም በደንብ የሚታወቅ ታሪክ ነው፡፡ ቆይቶ ደግሞ በተለይ ከጉባኤ ኬልቄዶን በኋላ በአንጾኪያ እና በቁስጥንጥንያ መንበሮች ብዙ ውጣ ውረዶች መፈራረቆችና መተካካቶች መሳደዶች በተደጋጋሚ አጋጥመዋል፡፡

በቅርብ ጊዜ እንኳ በሩስያ፣በሕንድ እና በአርመን ኦርቶዶክሶች ተከስተው የነበሩት መከፋፈሎች ሊዘነጉ የሚችሉ አይደሉም፡፡ብዙዎቹ ወይም ሁሉም ልዩነቶች ተፈትተዋል፡፡ በግሪክ ኦርቶዶክስ ግን አሁንም ትልቅ ክፍፍል አለ፡፡ ሆኖም የእነርሱ ፖለቲካዊ ጫና የፈጠረው ሳይሆን የትውፊት መለወጥ ነው፡፡ ይኸውም የቀድሞውን ዮልዮሳዊ የዘመን አቆጣጠር ትተው በምዕራባዊ ጎርጎርዮሳዊ አቆጣጠር መጠቀም ሲጀምሩ ይህንን የተቃወሙት ለብቻቸው ተለይተው ወጥተዋል፤ ስማቸውም ኦልድ ካላንደሪስት ኦርቶዶከስ ቤተ ክርስቲያን (Old Calendarists orthodox Church) የሚል ነው፡፡

እነዚህ ሁሉ የሚያመለክቱት በፖለቲካ ጣልቃ ገብነት ምክንያት በቤተ ክርስቲያን አስተዳደር ላይ መለያየትና መከፋፈል በሌሎቹም ላይ ቀደም ብሎ ያጋጠመ እና ሲፈቱት የኖረ ችግር መሆኑን ነው፡፡ ሆኖም በሮም ለ40 ዐመታት የቆየው ውዝግብ ግን ብዙ ችግር ያስከተለ ከመሆኑም በላይ የተፈታበትም መንገድ ብዙ ትምህርት ሊወሰድበት የሚችል ነገር ነው፡፡ ምክንያቱም ወቅቱ ገና ከሉተር መነሣት በፊት ስለነበረ መላው ምዕራብ አውሮፓ በሮም ካቶሊክ ውስጥ ነበር፡፡ የመጀመሪያዎቹ ተወዛጋቢ ፖፖች ደግሞ ትውልዳቸው አንዱ ከፈረንሳይ ሌላኛው ከጣልያን ነበሩ፡፡ ይህም ማለት ተፎከካሪዎቹ ፖፖች በሁለት ሀገርና መንግሥታትም ጭምር ስለሚታገዙ ክፍፍሉ ጠንካራ ነበር፡፡ መንግሥቶቻቸው ደግሞ ሌሎቹን ሀገሮች እየቀሰቀሱ ከፊል የምዕራብ አውሮፓ መንግሥታት አንዱን ሌሎቹ ደግሞ ሌላውን ይደግፉ ስለነበር የጣልቃገብነቱንና ፍላጎት ያለው አካል ብዛትን ስናይ ብዙ ችግሮች እንደነበሩበት ለመረዳት አያዳግትም፡፡ ለአንዳንዶች ሌሎች ሦስተኛና አራተኛ ፖፖችን እስከመሾም ያደረሳቸውም ከዚህ ከመጀመሪያዎቹ የኃያላን መንግሥታት ፍላጎት የተላቀቀ አዲስ ሲሾም ይፈታል ብለው በማሰብ ነበር፡፡ ሆኖም አልተሳካም፡፡ በመጨረሻ ግን አራት ዐመት በወሰደው ጉባኤያቸው ሁሉንም መንግሥታት፤ ካርዲናሎች፤ ሕዝቡን፤ ደጋፊዎቻቸውንና የመከፋፈል ተጠቃሚዎች የነበሩትን ሁሉ አሳምነውና  አሸንፈው አንድ መሆን  በቁ፡፡ በእውነት ከሆነ እንኳን በቁጥር ከዐሥር በላይ የሆነ ሀገርና መንግሥታትንና ሕዝብ አሸንፈው ለዚህ ከመብቃት በላይ አስደናቂ ነገር የለም፡፡

በእኛ ሀገር የተከሰተውም ምክንያቱ ፖለቲካን ተገን ያደረገ እንደነበር ግልጽ ነው፡፡ ሆኖም ፖለቲካን ተገን አድርጎ ቤተ ክርስቲያንን መጉዳት ሲጀመር ይህ የመጀመሪያው አልነበረም፡፡ ከደርግ መምጣት ጋር ተያይዞ ባለ ትልቅ ራእይ በነበሩት በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ቴዎፍሎስ የተፈጸመው ግፍ ቢያንስ መንበሩ ወደ እኛ ከመጣ በኋላ ላለው ታሪካችን የመጀመሪያ ተደርጎ ሊወሰድ ይችላል፡፡ምንም እንኳ በየዋሕነት ለነበሩትና በእንዲህ ያለ ጊዜ ምን መደረግ እንዳለበት ግንዛቤ እንዳልነበራቸው ግምት በምንወስድላቸው አባቶች ላይ ሙሉ በሙሉ ለመፍረድ ቢያስቸግርም ፖለቲካዊ ሒደቱን ተቋቁሞ በሐዋርያዊ መንገድ ችግሩን ለመወጣት የተደረገ ጥረት ግን ጎልቶ አይሰማም፡፡ እንዲያውም የፖለቲከኞችን ተንኮል ካለመገንዘብም ይሁን ከሰብአዊ ድካም በመነጨ በማይታወቅበት መንገድ ባይብራራም ተወቃሽ ተደርገው ሲቀርቡም ይስተዋላል፡፡

የደርግ ዘመን አብቅቶ ኢሕአዴግ ሲገባም ግቡ ተመሳሳይ የሆነ ነገር ግን በመንበሩ ላይ በነበሩት አባት የወደፊት ሁኔታ ላይ ግን ለየት ያለ ድርጊት ተፈጸመ፡፡ በቀደመው ዘመን በአቡነ ቴዎፍሎስ የነበረውም ድርጊት ተወገዘ፡፡ ሆኖም የቀደመውን ድርጊት አውጋዦቹ ሌላ ተመሳሳይ ድርጊት ላለመፈጸማቸው ዋስትና ከመሆን ይልቅ የሚያወግዙትን ድርጊት አሻሽለው ከመፈጸም አልተመለሱም፡፡ በዚህ ወቅት የነበሩት አባቶችም አሁንም ከሐሜት መትረፍ አልቻሉም፡፡ ሐሜታውም በሀገር ውስጥም በውጭም ያሉትን የሚያጠቃልል ነው፡፡

ታሪኩን በዚህ መጠን ለማስታወስ ያህል የሞከርነውም የችግሩ ተጠያቂነት በሁሉም ላይ ያረፈ መሆኑን ለመጠቆም ያህል እንጂ በታሪኩ ላይ ለመነታረክ አይደለም፡፡ ይልቁንም በተጠያቂነት ከመጠየቅ አልፈን ታሪካችንን ለሚያድስና ያለፈውን ለትምህርት ብቻ እንድንተወው የሚያደርግ አዲስ ወርቃማ ዕድል በእጃችን መኖሩን አስተውለን ሁላችንም በኅብረተ መንፈስ ቅዱስ አንድ እንድንሆን የምንጸልለውን ጸሎት በተግባር እንድናውለው ለመጠየቅ ያህል ብቻ ነው፡፡

በዚህ መልእክታችንም በቅዳሴያችንና በዘወትር ጸሎታችን የምንጸልያቸውን መነሻ አድርገን ልናደርጋቸው የሚገቡንን በማስታወስ መልእክታችንን ለማቅረብ እንወዳለን፡፡

                 ሀበነ እግዚኦ አእይንተ አእምሮ

አባቶቻቸን አርእስተ መናብርቱ፣ በሁሉም በኩል ያሉ ሊቃነ ጳጳሳት፣ ጳጳሳትና ካህናት በሙሉ ቅዳሴ እግዚእን በሚቀድሱበት ጊዜ ሓዳፌ ነፍስ ወይም ነፍስን የሚያጸዳ የሚወለውል ተብሎ በሚጠራው የመጨረሻው ጸሎት ላይ “ኀበነ እግዚኦ አእይንተ አእምሮ ወትረ ኪያከ ይርአያ ወአእዛንነሂ ቃለ ዘባሕቲትከ ይስምዐ” ‘አቤቱ ጆሮዎቻችን የአንተን ቃል ብቻ ይሰሙ ዘንድ ዐይኖቻችንም አንተን ብቻ ያዩ ዘንድ የዕውቀትን የማስተዋልን ዐይኖች ስጠን’ እያሉ ስለራሳቸውም ስለ እኛም ይጸልያሉ፡፡እኛም ልጆቻችሁ ዛሬ ሌላ መልእክት የለንም፡፡ እንደምትጸልዩልን እንደምትለምኑልን ልክ እንደዚያው የሌሎችን ቃል ትታችሁ የጌታችንን ቃል ሰምታችሁ አስታውሳችሁ አንድ ሁኑልን ብቻ ነው የምንለው፡፡የእርሱን ቃል ደግሞ ልትዘነጉት አትችሉም፡፡የጌታችን ቃሉ ደግሞ ትናንት በተፈጠረው በታሪኩ ላይ እንድንነታረክና እንድንከራከር አይፈቅድልንም፡፡ ይልቁንም “ወንድምህን እስከ ሰባ ጊዜ ሰባት ይቅር በለው” እያለ የትላንቱን እንድንተወው ግዴታ ይጥልብናል እንጂ፡፡ እራሱም ጌታችን አስቀድሞ ሰይጣን ይህን ሊያደርገው ደጋግሞ የሚሞክረው መሆኑን “ስምዖን ስምዖን ሆይ፥ እነሆ፥ ሰይጣን እንደ ስንዴ ሊያበጥራችሁ ለመነ፤ እኔ ግን እምነትህ እንዳይጠፋ ስለ አንተ አማለድሁ፤ አንተም በተመለስህ ጊዜ ወንድሞችህን አጽና” (ሉቃ 22 ፥31-32)ሲል እንደገለጸልን ይህ የመለያየት ነገር የሰይጣን ነው፡፡ በመከራ ጊዜ ደግሞ እንደተጻፈው ብዙ ሰው ይፈተናል፡፡ በወቅቱ የድርጊቱ ተሳታፊዎች ባለመሆናችን የምንተቸው ሰዎች ሁሉ በቦታውና በጊዜው ብንኖር ኖሮ ከዚህ የከፋ ልናደርግ እንደምንችል ገምቶ ራስንም በእነርሱ አስገብቶ ይቅር ማለት ተገቢ ነው፡፡ ከዚህ አልፎ  እነ እገሌ ናቸው ተጠያቂ በሚል መንገድ መተቸት ነገሩን ከማባባስ ያለፈ የሚፈጥረው ፋይዳ የለም፡፡ በርግጥም እንዲህ ያለው ልዩነት ምእመናን በክርስትናቸው የሚበጠሩበት ነው፡፡ ጌታችን ግን በአንጻረ ቅዱስ ጴጥሮስ “እምነትህ እንዳይጠፋ አማለድሁ” ብሎ በሥጋዌው ቤዛ ሆኖ ያቀረበልንን የጸሎት መሥዋዕት ምልጃ ብሎ በመጥራት ነግሮናል፡፡ ይኸውም “ቅዱስ አባት ሆይ፥ እነዚህን የሰጠኸኝን እንደ እኛ አንድ እንዲሆኑ በስምህ ጠብቃቸው”(ዮሐ17፥11) የሚለው ነው። ስለዚህ በቅዳሴያችን  ላይ ጆሮቻችን የአንተን ቃል ብቻ ይሰሙ ዘንድ ካላችሁ አይቀር ቃሉ አንድ ይሁኑ የሚል ስለሆነ አንድ ትሆኑልን ዘንድ በታላቅ ትሕትና እንጠይቃለን፡፡

በርግጥም ልንሰማውና ልንከተለው የሚገባን የእርሱ ቃል ብቻ መሆን አለበት፡፡ በቤተ መቅደስ በቅዳሴ ጊዜ “ባርክ ላዕለ አባግዐ መርኤትከ፤ ወአብዝኀ ለዛቲ አጸደ ወይን እንተ ተከልካ በየማንከ ቅዱስ” እያላችሁ ምእመናንን ለማብዛትና ለመጠበቅ ፈቃዳችሁ ጸሎታችሁ መሆናችሁን ሁልጊዜ ትገልጻላችሁ፡፡”ባርኮ ለዘንቱ ኅብስት … ወሚጦ ለዝንቱ ጽዋዕ … ” እያላችሁ ቅዱስ ምስጢርን እንዲፈጸምላችሁ ትማጸኑታላችሁ፡፡ ያለ እርሱ ሊሆን ሊፈጸም የሚችል አይደለምና፡፡ ታዲያ ለምሥጢራት የምንጠራውን ጌታ ምሥጢራቱን ለሚፈጽሙት አበው አለመግባባት እንዴት ልንዘነጋው እንችላለን? በዚያ ጊዜ ብቻ ይህን አድርግ ብለን ለምነነው ይህን ጉዳይ ግን ብቻችንን ወይም ደግሞ ፖለቲከኞችንና ሌሎች የልዩነት ተጠቃሚዎችን ይዘን እንፈታዋለን ልንልምአንችልም፡፡እንግዲያው ጆሮዎቻችን እንደምንጸልየው የእርሱን ቃል ብቻ የሚሰሙበት፤ዐይኖቻችንም እንደ ምልጃ ጸሎታችን እርሱንም ብቻ ሊያዩበት እና ሌሎች ጊዜያዊ ነገሮችንና ፐሮፓጋንዳዎችን ቸል ሊሉበት የሚገባው እውነተኛው ጊዜ ዛሬ መሆን አለበት፡፡ ለወጡት ሚጠት (መመለስ)፣ለባዘኑት ዕረፍት፣ ለሚጨነቁት መረጋጋት፣ በግጭትና በዕልህም ውስጥ ላሉት ሰላምና አንድነት፣ ለቤተ ክርስቲያን አንድነት እና ለምእመናን ኅብረት ይሆን ዘንድ በእውነት ሌሎችንን ተጽእኖዎች ሁሉ ተቋቁመን መገኘት ይገባናል፡፡ ከዚህ ውጭ ከሆንን ግን”በገዛ ደሙ የዋጃትን የእግዚአብሔርን ቤተ ክርስቲያን ትጠብቁአት ዘንድ መንፈስ ቅዱስ እናንተን ጳጳሳት አድርጎ ለሾመባት ለመንጋው ሁሉና ለራሳችሁ ተጠንቀቁ”(ሐዋ፳ ፥፳፰) በሚለው ቃለ ሐዋርያ መወቀሳችን የማይቀር ይሆናል።

                 አድኅን እግዚኦ ዛተኒ ሀገረ

  የአባቶች አንድነት ለሀገር አንድነትና ሰላም ያለውም አስተዋጽኦ ከፍተኛ መሆኑ የማይጠረጠር ነው፡፡የጥላቻ፣ የወቀሳና የከሰሳ ፖለቲካ ወደ ኢትዮጵያውያን ልብ ዘልቆ ከገባበት ከላፉት ስድሳ ዓመታት ወዲህ ጥላቻና መለያየት፤መሰዳደብና መወጋገዝ፣ በቀልና ግድያ፣ ተንኮልና ሴራ ሲጨምር እንጂ ሲቀንስ አልታየም፡፡ ብሔራዊ መግባባት በተወሰነ ደረጃ በሚቀነቀንበት በአሁኑ ሰዓት እንኳ በሰላም አልባሳት የተደበቁ የበቀል ድምፆች ከአንዳንዶች የሚሰሙ መሆኑን ለማንም የተሰወረ አይደለም፡፡ ታዲያ እንደዚህ ባለጊዜ ዐለምን በሙሉ ወደ ሰላማዊ ኢየሱስ ክርስቶስ ለማቅረብ አደራውን ለተቀበሉ አባቶች ሓላፊነቱ ግልጽ ነው፡፡ ” … ሰላማዊ ኢየሱስ ክርስቶስ ሰላመከ ኀበነ ወአጽንዕ ለነ ሰላመከ” ብለን በየቅዳሴያችን እየለመንነው ሰላም አጣን ብንል ሁሉም ይታዘበናል፡፡ ምክንያቱም እኛ ካልገፋናት በስተቀር የእርሱን ሰላም ከእኛ ማንም ሊወስዳት አይችልምና፡፡

ይልቁንም እኛ ፍጹም ሰላም ሆነን ሀገራችንም ከየትኛውም ችግር እንድትወጣ በእውነት መጣር ይኖርብናል፡፡ በዐርብ የሊጦን ጸሎታችን “አድኅን እግዚኦ ዛተኒ ሀገረ ወካልኣተኒ አኅጉረ ወበሐውርተ እለ በሃይማኖተ ዚአከ የኀድሩ” ‘አቤቱ ይህች ሀገር እና አንተን በማመን የሚኖሩ ያሉባቸውን በዐለም ላይ ያሉ ሌሎችን ሀገሮችም ሁሉ አድን’ እያልን የምንማልድ ሰዎች በእኛ ልዩነት ምክንያት ሕዝበ ክርስቲያኑን ለያይተን፣በብዙ ውስብስብ ችግሮች ውስጥ አስገብተን ፣ በአንድ ቤት ሳይቀር ባልና ሚስት፤ ታላቅና ታናሽ ተለያይተው ጸሎቱ ምልጃው እንዴት ስሙር ሊሆን ይችላል፡፡ ሌላው ቀርቶ በልዩነቱ ምክንያት ሰብሳቢ አጥተው ባዝነው ከመንጋው እየተለዩ ወደሌሎቹ በረቶች ምንያህል ነፍሳት እንደሔዱ ከማንም የተሰወረ አይደለም፡፡ እንኳን    ከምእመናን መምህራንና አገልጋይ ከሚባሉት አንኳ ምን ያህሉ በነፍስ ተጨነቁ፤ ስንቶቹስ ባዘኑ፡፡ ስለዚህም ጸሎታችንን በተግባር እንግለጠው፡፡ያ ካልሆነ አቤቱ ሀገራችን አድን ስንለው ልዩነቱንና መለያየቱን እናንተ በተግባር አገዛችሁት እንጂ መች ተጸየፋችሁት የሚያስበለን ይመስላል፡፡ ስለዚህም ስለሀገራችንም፣ ስለሕዝበ ክርስቲያንም አንድነት ስንል አንድነቱን ያለ ቅድመ ሁኔታ በይቅርታ እና በዕርቅ ልንዘጋው ይገባናል፡፡ በዘመናችን የሀገራችን ፖለቲካዊ ችግሮች ለመፍታት ፖለቲከኞች ለሚሔዱበት የዕርቅና የሰላም ጉዞ አርአያ መሆን እንኳ ባይቻለን ፍኖተ ሣህሉን ለመከተል እንኳ ካልቻልን ጌታችን አይሁድን በዚህ ትውልድ ንግሥተ አዜብ ትፈርድበታለች እንዳለ በእኛም ላይ በመጨረሻው ዘመን የሚያስፈርድብን በእኛው ፖለቲከኞች መሆኑ የማይጠረጠር ነው፡፡ እነርሱ ከእኛ በብዙ መንገድ ተሽለው ተገኝተዋልና፡፡

          በኵሉ ልብ ናስተብቊዖ ለእግዚአብሔር አምላክነ

ይህ ይሆን ይፈጸም ዘንድ ጸሎት እንደሚደርግ የታመነ ነው፡፡ይልቁንም አሁን ደግሞ ነቢየ እግዚአብሔር ዳዊት”አመንኩ በዘነበብኩ”‘በተናገርሁት(በጸለይኩት) አመንኩ’ የአመንኩትንም ጸለይኩ፤ መሰከርኩ (መዝ115፥1)እንዳለው የምንጸልየውን የበለጠ አስተውሎ መፈጸም ሳይጠይቅ አይቀርም፡፡ይህን የምናስታውሰው አይደረግም ለማለት ሳይሆን አሁንም በምንቀድሰው ቅዳሴ ዲያቆኑ አስቀድሞ “ያማረ በመንፈስ ቅዱስ የሚፈጸም አንድነትን ይሰጠን ዘንድ እግዚአብሔር አምላካችን በፍጹም ልብ እንለምነው” ሲል የታወቀውን በአዋጅ እንደሚያነቃን እንደሚያስታውሰው ያለ የልጅነት ማስታወሻ ብቻ ነው፡፡ እናንተም “ኀበነ ንኅበር በዘዚአከ መንፈስ ቅዱስ” ‘የአንተ በሆነ መንፈስ ቅዱስ አንድ መሆንን ስጠን’ የምትሉትን በተግባር ማየት የማይመኝ የለም፡፡ይልቁንም በዐርብ ሊጦን ጸሎታችን “ሀበነ ከመ በአሐዱ ልብ ወበአሐዱ አፍ ንሰብሕ ለአብ ወወልድ መንፈስ ቅዱስ ይእዜኒ ወዘልፈኒ ወለዓለመ ዓለም” ስትሉ እንደምትማልዱት በአንድ ልብ እና በአንድ አፍ በአንድ መቅደስና በአንድ ቅዳሴ አንድ ላይ ሆናችሁ ለፈጣሪ ምስጋና ስታቀርቡ ለማየት አብዝተን የምንመኝና የምንጸልይ እርሱንም “በፍጹም ልብ”ይሁን የምንል መሆናችንን ለሁላችሁም በታላቅ ትሕትና እናቀርባለን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

 ምንጭ፤ሐመር    መጽሔት    26ኛ ዓመት ቊጥር 2፤ሰኔ2010 ዓ.ም

 

አቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስ

ሚያዝያ ፱ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

ጻድቁ አቡነ እስትንፋስ ክርስቶስ የስማቸው ትርጓሜ ‹‹የክርስቶስ፣ የአብ፣ የወልድ የመንፈስ ቅዱስ እስትንፋስ›› ማለት ነው፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በፊታቸው ላይ እፍ ብሎ ጸጋውን፣ በረከቱን ስላሳደረባቸው በዚህ ስም ይጠራሉ፡፡ የጻድቁ፣ አባታቸው መልአከ ምክሩ፤ እናታቸው ወለተ ማርያም ይባላሉ፡፡ የትውልድ ቦታቸው በሰሜን ወሎ ሀገረ ስብከት ዳውንት ዐወን ዓባይ የተባለ አካባቢ ነው፡፡ የተፀነሱት ሚያዝያ ፰፤ የተወለዱት ደግሞ ታኅሣሥ ፰ ቀን ነው፡፡

በተወለዱ ዕለት በእግራቸው ቆመው ሦስት ጊዜ ‹‹ስብሐት ለአብ ስብሐት ለወልድ ስብሐት ለመንፈስ ቅዱስ›› በማለት እግዚአብሔርን አመሰግነዋል፡፡ የሕፃናትን አንደበት ለሚያናግሩ፣ ለሥላሴ እና ለእመቤታችን እንደዚሁም ለክርስቶስ መስቀል ዘጠኝ ጊዜ ሰግደዋል፡፡ በልጅነታቸው፣ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ትለጽላቸው ነበር፡፡ ያደጉትም የእግዚአብሔር መልአክ ቅዱስ ሚካኤል እየጠበቃቸው ነው፡፡

ዕድሜያቸው ለትምህርት በደረሰ ጊዜም የመጻሕፍት ዂሉ ርእስ የሚኾን ፊደልንና የሐዋርያው ዮሐንስን መልእክት ደብረ ድባ በሚባል ቦታ ከመምህር ኪራኮስ ተምረዋል፡፡ የሐዋርያትን ሥራ፣ የቅዱስ ጳውሎስን መልእክት፣ የዳዊትን መዝሙር፣ እንደዚሁም ትርጓሜ መጻሕፍትን ተምረዋል፡፡ ከዚህ በኋላ በዘመኑ ከነበሩት ብፁዕ አቡነ ማርቆስ የዲቁና መዓርግ ተቀበሉ፡፡ ከዚያም በሐይቅ አቡነ ኢየሱስ ሞዐ ገዳም መነኰሱ፡፡ ከዚያም ወደ ሕንጻ ደብረ ድባ ሔደው የኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳሳት፣ የገዳማት አለቃ፣ የመነኮሳት አባት ከሚኾን ከአባ ሙሴ መዓርገ ቅስና፣ ቍምስና እና ኤጲስ ቆጶስነት በቅደም ተከተል ተቀብለዋል፡፡

አቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስ፣ ዐቢይ ጾምን ዐርባ ሌሊትና ዐርባ ቀን እኽልን ውኃ ሳይቀምሱ ይጾሙ ነበር፡፡ እግሮቻቸው እስኪያብጡ ድረስ ቆመው ይጸልዩ ነበር፡፡ ለሽፋሽፍቶቻቸውም ዕረፍትን አይሰጡአቸውም ነበር፡፡

በአንድ ወቅት ወደ አቡነ ኢየሱስ ሞዐ ገዳም ሲሔዱ ወደ ገዳሙ ለመግባት ሐይቁን የሚያሻግራቸው ቢያጡ ተንበርክከው ሲጸልዩ በቅዱስ ሚካኤል እጅ ደንገል (ታንኳ) ቀርቦላቸው ሐይቁን ተሻግረዋል፡፡ ዘጠኝ ዓመት ዓባይ ባሕር ውስጥ በራሳቸው ተዘቅዝቀው በመቆም ለኢትዮጵያ ሲጸልዩ ከቆዩ በኋላ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ እርሳቸው መጥቶ ‹‹ከመነኮሳት ዂሉ ብልጫ ያለህ ወዳጄ እስትንፋሰ ክርስቶስ ሆይ፥ ኢትዮጵያን ምሬልሃለሁና ከዚህ ባሕር ውጣ›› ብሏቸዋል፡፡ ከዚያም ማረፊያቸው ወደ ኾነች ዳውንት (ደብረ አስጋጅ) በመመለስ ዐሥራ ሰባት ገዳማትን መሥርተዋል፡፡

ወደ ደብረ ዳሞ በሔዱ ጊዜም በትእምርተ መስቀል አማትበው ያለ ገመድ ከደብረ ዳሞ ተራራ ላይ በመውጣት ከአቡነ አረጋዊ ጋር (ከተሰወሩበት ቦት መጥተው) ተገናኝተዋል፡፡

በየገዳማቱ ሲዘዋወሩ ከሞላ ውኃ በደረሱ ጊዜ በመስቀል ምልክት አማትበው በእግራቸው እንደ ደረቅ መሬት እየረገጡ ይሻገሩ ነበር፡፡ አምስት አንበሶችና አምስት ነብሮች ይከተሏቸው ነበር፤ እነዚያም አንበሶችና ነብሮች የሚመገቡትን ባጡ ጊዜ ድንጋዩን ባርከው ሥጋ ያደረጉላቸው ነበር እነሱም ያንን ይመገቡ ነበር፡፡

የትግራይን አድባራትና ገዳማትን ለመጐብኘት ወደ ቅዱስ ያሬድ ደብር ሲደርሱ እመቤታችን ከቅዱስ ያሬድ (ከብሔረ ሕያዋን መጥቶ) እና ከልጅዋ ጋር ወደ እርሳቸው መጥታ ብዙ ተአምራትን አድርጋላቸዋለች፤ ከቅዱስ ያሬድም ተምረዋል፤ ቡራኬ ተቀብለዋል፡፡

የጻድቁ የዕረፍታቸው ቀን በደረሰ ጊዜ እንደ ነጋሪት ቃልና እንደ ነጎድጓድ ያለ ድምፅ በሰማይ ተሰማ፤ እንደ ፀሐይ እና እንደ ጨረቃ እንደ ከዋክብት የሚያበሩ የተለያዩ መብራቶች ታዩ፡፡ መሬትም አራት ጊዜ ተንቀጠቀጠች፡፡ ተራሮችና ኮረብቶች እጅግ ተነዋወጡ፡፡ ነፍሳቸው ከሥጋቸው በምትለይበት ሰዓት እንደ መብረቅ የሚጮኽ ታላቅ ድምፅ ከሰማይ ተሰማ፡፡ ያን ጊዜ ሰው ዂሉ፣ እንስሳት፣ አራዊት፣ ዛፎችና ቅጠሎች፣ ተራሮች፣ ኮረብቶች፣ ወፎችም በየወገናቸው አለቀሱ፡፡ ፀሐይና ጨረቃ ጨለሙ፤ ከዋክብትም ረገፉ፡፡

አብ ወልድ መንፈስ ቅዱስ በታላቅ ግርማ፣ በአንድነትና በሦስትነት እየተመሰገኑ መጡ፡፡ ኪሩቤል፣ ሱራፌል ከነማዕጥንታቸው፣ ዘጠና ዘጠኙ ነገደ መላእክት፣ ዐሥራ ሁለቱ ሐዋርያት፣ ዐሥራ አምስቱ ነቢያት፣ ሰማዕታት ከቅዱስ እስጢፋኖስ እስከ ተፈጻሜተ ሰማዕት ሊቀ ጳጳስ ዼጥሮስ ድረስ ያሉት፣ ቅዱሳን መነኮሳት ከአባታቸው ከእንጦንስ ጋር መጡ፡፡ የሰማዕታት እናታቸው፣ የመነኮሳትና የደናግል አክሊላቸው፣ ክብራቸው፣ መመኪያቸው፣ የሐዋርያት ስብከታቸው፣ የነቢያት ትንቢታቸው፣ የመላእክት እኅታቸው፣ የኃጥኣን ተስፋቸው፣ የፍጥረት ሁሉ አማላጃቸው፣ የምሕረት እናት፣ ወላዲተ አምላክ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ደናግላንን አስከትላ መጣች፡፡

ጻድቁ አባታችን ከጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቃል ኪዳን ከተቀበሉ በኋላ ለዚህ ክብር ያበቃቸውን እግዚአብሔርን አመስግነው በሰላም ዐረፉ፡፡ ዕረፍታቸውም ሚያዚያ ዘጠኝ ቀን ሲኾን፣ ያረፉበት ቦታም ሰሜን ወሎ ሀገረ ስብከት ዳውንት ከተማ ደብረ አስጋጅ ገዳም ነው፡፡

አቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስ ከጌታችን ከመድኀኒታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ከተቀበሉት ቃል ኪዳን ጥቂቱ

  • ዝክራቸውን የዘከረ፣ መታሰቢያቸውን ያደረገ፣ ስማቸውን የጠራ፣ ገድላቸውን የጻፈ፣ ያጻፈ፣ ያነበበ፣ የተረጐመ፣ የሰማ፤ በፍጹም ልቡና ‹‹አምላከ እስትንፋሰ ክርስቶስ (የእስትንፋሰ ክርስቶስ አምላክ) ኀጢአቴን ይቅር በለኝ›› ብሎ የጸለየ ስሙ በሕይወት መጽሐፍ ይጻፍለታል፡፡
  • ለቤተ ክርስቲያናቸው መባዕ፣ ስንዴ፣ ዘይት፣ ዕጣን፣ ጧፍ የሰጠ ኀጢአቱ ይደመሰስለታል፤ በገነት፣ በመንግሥተ ሰማያት በደስታ ይኖራል፡፡
  • በስማቸው የተራቆተውን ያለበሰ፣ የተራበውን ያበላ፣ ያዘነውን ያረጋጋ፣ በመታሰበያቸው ዕለት ለአገልግሎት የሚፈለገውን መልካሙን ነገር ያደረገ ኀጢአቱ ይሰረይለታል፡፡
  • በየዓመቱ ሚያዚያ ፱ ቀን እና በየወሩ የዕረፍታቸውን መታሰቢያ በዓል ያከበረ፣ ዝክራቸውን የዘከረ ሰማያዊ ክብር ያገኛል፡፡ በስማቸው የጽዋ ማኅበር የሚጠጡ ሰዎች ቢኖሩ በመካከላቸው የጻድቁ አምላክ ይገኛል፡፡
  • ዝክራቸውን የዘከሩ፣ መታሰቢያቸውን ያደረጉ፣ በስማቸው የተማጸኑ፣ በገድላቸው የተሻሹ፣ በጠበላቸው የተጠመቁና የጠጡ መካኖች ልጅ ይወልዳሉ፡፡
  • ችግር ደርሶበት ስማቸውን የጠራ፣ ወንድ ወይም ሴት ልጁን በስማቸው የሰየመ፣ በበዓላቸው ቀን ቁራሽ እንጀራና ቀዝቃዛ ውኃ ለነዳያን የሰጠ ኀጢአቱ ይሰረይለታል፡፡

ጻድቁ በሕይወተ ሥጋ እያሉ ካደረጉአቸው ተአምራት መካከል ከፊሉ

  • ከደቀ መዝሙራቸው ከልብሰ ክርስቶስ ጋር በጎዳና ሲሔዱ የደረቀ የሰው አጥንት አግኝተው ፈጽሞ ወደ እግዚአብሔር ሲለምኑ ያን ጊዜ በጸሎታቸው ኃይል ያ የሞተውና የደረቀው አጥንት ነፍስ ዘርቶ ተነሥቷል፡፡
  • የቀትር ጋኔን ለክፏት ልቧን ሰውሮአት የአገኘችውን ሰው እና እንስሳ በጥርሷ ትነክስ የነበረች አንዲት ሴት ሕመሟ ጸንቶባት ሞታ ሰዎች ሊቀብሯት ሲሉ የእስትንፋሰ ክርስቶስን መስቀልና መታጠቂያውን በአስከሬኑ ላይ ሲያስቀምጡት በእግዚአብሔር ኃይል ተነሥታለች፡፡
  • አባታችን እስትንፋሰ ክርስቶስ በብርሃን ሠረገላ ወደ ሰማይ ሲያርጉ ዓይኑ የጠፋ፣ እግሮቹ ልምሾ የኾኑ ሰው ዐይቷቸው ‹‹አባቴ እስትንፋሰ ክርስቶስ ሆይ፥ በጸሎትዎ ፈውሱኝ›› ብሎ ተማጸናቸው፡፡ አባታችን እስትንፋሰ ክርስቶስም ያንን ሰው አዝነውለት በእጃቸው ያለውን መሐረብ ወረወሩለት፡፡ በዚያን ጊዜ ልምሾ የነበሩ እግሮቹ ዳኑ፤ ዓይኑም በራለት፡፡
  • ስንዴ ዘርተው፣ ወይን፣ ጽድንም፣ ወይራን፣ ግራርንም ተክለው በአንዲት ቀን ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ስንዴውን ለመሥዋዕት፣ ወይኑን ለቍርባን ዕለቱን በተአምራት አድርሰዋቸዋል፡፡

ካረፉ በኋላ (በዐጸደ ነፍስ) ካደረጉአቸው ተአምራት መካከል ጥቂቶቹ

  • በልጃቸው ዐይነ ሥውር መኾን ተጨንቀው የነበሩ አንዲት እናት እስትንፋሰ ክርስቶስ ልጃቸውን ቢፈውሱላቸው እንደሚመነኵሱ ስእለት ተስለው ጠበሉን ሲያስጠምቁት የልጃቸው ዐይኑ በራለት፡፡ ኾኖም ግን ተስለው የነበረውን ምንኵስና እንዳያደርጉ ዘመዶቻቸው ስለ ከለከሏቸው ልጃቸው ተመልሶ ዐይነ ሥውር ኾኗል፡፡
  • ወለተ ማርያም የተባሉ እናት ትዳር መሥርተው ለዐሥራ ሁለት ዓመታት ልጅ ሳይወልዱ ሲኖሩ የጻድቁን ገድል አዝለው በስማቸው ስም ቢማጸኑ ልጅ ለመውለድ በቅተዋል፡፡ ሊበተን የነበረውም ትዳራቸውም ተቃንቶላቸዋል፡፡ ከዚህም ባሻገር በጻድቁ አማላጅነት ከጡት ካንሰር በሽታ እንደ ተፈወሱ፣ ጤንነታቸው እንደ ተመለሰላቸው እኒህ እናት ምስክርነት ሰጥተዋል፡፡
  • የጻድቁ አቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስን በዓል ይዘክሩ የነበሩ ሰዎች ላም አካለ ጎደሎ ጥጃ ትወልዳለች፡፡ ከቤተሰቡ መካከል በእምነቷ ጠንካራ የነበረችው እኅታቸው ጥጃዋን በእስትንፋሰ ክርስቶስ ገድል ብታሻት በእግሯ ቆማ ሔዳለች፡፡ የእናቷንም ጡት ተንቀሳቅሳ ለመጥባት ችላለች፡፡
  • ለአምስት ዓመታት ሆዱ አብጦ የነበረ አንድ ዲያቆን የጻድቁ ገድል የተደገመበትን ጠበል ሲጠጣ ከሕመሙ ተፈውሷል፡፡

ምንጭ፡- ገድለ አቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስ

በአቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስ ስም እየተማጸኑ በገድላቸው በመጸለይና ሰውነታቸውን በማሻሸት፣ እንደዚሁም በገዳማቸው በሚገኘው በጠበላቸው በመጠመቅ፣ በእምነታቸው በመቀባት ብዙ ምእመናን አሁንም ከሕመማቸው እየተፈወሱ ናቸው፡፡ የጻድቁ ገዳም (ደብረ አስጋጅ) በሰሜን ወሎ ሀገረ ስብከት ዳውንት ከተማ አካባቢ ይገኛል፡፡

በረከት ለመቀበል ወደ ገዳሙ ለመሔድ ከወልድያ እስከ ዳውንት በመኪና የስምንት ሰዓታት መንገድ ይወስዳል፡፡ ከዳውንት ከተማ ወደ ገዳሙ አቅራቢያ የሚያደርሱ አነስተኛ ተሸከርካሪዎችም ይገኛሉ፡፡ ወደ ገዳሙ ለመግባት ለጠነከሩ የአንድ ሰዓት ያህል የእግር ጕዞ ይኖረዋል፡፡ የጻድቁ በዓለ ዕረፍት በሚከበርበት ዕለት (ሚያዝያ ዘጠኝ ቀን) ከወልድያ እስከ ገዳሙ የሚያደርሱ መጓጓዣዎች ስለሚገኙ ሕዝበ ክርስቲያኑ ወደ ገዳሙ በመሔድ ከበረከቱ ተሳታፊ እንዲኾኑ ገዳሙ ጥሪውን ያስተላልፋል፡፡

የጻድቁ ጸሎታቸው፣ በረከታቸውና አማላጅነታቸው ከዂላችን ጋር ይኹን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ከዕለተ ትንሣኤ እስከ ዳግም ትንሣኤ

በሊቀ ትጉሃን ኃይለ ጊዮርጊስ ዳኘ

ሚያዝያ   ቀን ፳፻፲ .

ከዕለተ ትንሣኤ እስከ ዳግም ትንሣኤ ባሉት ዕለታት በቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን የሚፈጸመው መንፈሳዊና ሐዋርያዊ አገልግሎት ልክ እንደ መጀመሪያው የትንሣኤ ሥርዓት ኾኖ ይከናወናል፡፡ ከትንሣኤ እሑድ ጀምሮ እስከ ሳምንቱ እሑድ ድረስ የሚገኙት ዕለታትም ‹ሰሙነ ፋሲካ› ወይም ‹ትንሣኤ› እየተባሉ ይጠራሉ፤ የየራሳቸው ምሥጢራዊ ስያሜም አላቸው፡፡ ስያሜአቸውንም በአጭሩ እንደሚከተለው እንመለከታለን፤

ሰኞ

የትንሣኤው ማግሥት ዕለተ ሰኞ ‹ፀአተ ሲኦል› ወይም ‹ማዕዶት› ትባላለች፡፡ ይህቺውም ጌታችን በትንሣኤው ነፍሳትን ከሲኦል አውጥቶ ወደ ገነት አሻግሮ ለማስገባቱ መታሰቢያ ናት (ዮሐ. ፲፱፥፲፰፤ ሮሜ. ፭፥፲-፲፯)፡፡

ማክሰኞ 

ይህቺ ዕለት፣ ለሐዋርያው ቶማስ መታሰቢያ ትኾን ዘንድ ‹ቶማስ› ተብላ ትጠራለች፡፡ የትንሣኤው ዕለት እሑድ ማታ ጌታችን በዝግ ቤት ገብቶ ለሐዋርያት ሲገለጽ ቶማስ ከእነርሱ ጋር አልነበረም፡፡ በመጣ ጊዜ ሌሎቹ ሐዋርያት ትንሣኤውን ቢነግሩት ‹‹ሳላይ አላምንም›› ብሎ ነበር፡፡ በሳምንቱ እርሱ በተገኘበት ጌታችን በድጋሜ ለሐዋርያት ተገለጸ፡፡ ስለዚህም ይህቺ ዕለት በሐዋርያው ቶማስ ስም ተሰይማለች (ዮሐ. ፳፥፳፬-፴)፡፡ 

ረቡዕ 

ጌታችን ከሞተና ከተቀበረ ከአራት ቀናት በኋላ ከመቃብር ጠርቶ ላስነሣው ለአልዓዛር መታሰቢያ ናት፡፡ በክርስቶስ ሥልጣን የአልዓዛርን ከሞት መነሣት አይተው ብዙ ሕዝብ በጌታችን ስለ አመኑ ዕለቲቱ (ረቡዕ) ‹አልዓዛር› ተብላ ትታሰባለች (ዮሐ. ፲፩፥፴፰-፵፮)፡፡ 

ኀሙስ 

ይህቺ ዕለት ‹‹ከአምስት ቀን ተኩል በኋላ (አምስት ሺሕ ከአምስት መቶ ዓመት ሲፈጸም) ከልጅ ልጅህ ተወልጄ አድንሃለሁ፤›› ተብሎ ቃል የተገባለት የአዳም ተስፋው ተፈጽሞ ከነልጅ ልጆቹ ወደ ቀደመ ክብሩ ለመግባቱ መታሰቢያ ኾና ‹የአዳም ኀሙስ› ወይም ‹አዳም› ተብላ ትከበራለች (ሉቃ. ፳፬፥፳፭-፵፱)፡፡ 

ዐርብ

የትንሣኤ እሑድ ስድስተኛዋ ዐርብ ደግሞ በክርስቶስ ደም ለተመሠረተችው ቅድስት ቤተ ክርስቲያን መታሰቢያ ትኾን ዘንድ ‹ቤተ ክርስቲያን› ተብላ ትጠራለች (ማቴ. ፳፮፥፳፮-፳፱፤ ሐዋ. ፳፥፳፰)፡፡

ቀዳሚት ሰንበት

በሰሙነ ፋሲካው ያለችው ቀዳሚት ሕዝቡ ከአንዳንዱ በቀር ገበያ እንኳን ስለማይገበያይባት ‹የቁራ ገበያ፣ የገበያ ጥፊያ› ተብላ ትጠራለች፡፡ በቤተ ክርስቲያን ደግሞ ጌታችን በዘመነ ሥጋዌው በገንዘባቸውና ጕልበታቸው ላገለገሉት፤ በስቅለቱ ጊዜ እስከ ቀራንዮ ድረስ ለተከተሉት፤ በትንሣኤው ዕለት በሌሊት ወደ መቃብሩ ሽቱና አበባ ይዘው ለገሰገሱት፤ በትንሣኤውም ጌታችንን ከዅሉ ቀድሞ ለማየት ለበቁት ሴቶች መታሰቢያ ትኾን ዘንድ ‹ቅዱሳት አንስት› ተብላ ትጠራለች (ማቴ. ፳፭፥፩-፲፩፤ ሉቃ. ፳፫፥፳፯-፴፫፤ ፳፬፥፩-፲)፡፡

እሑድ ሰንበት

በዋናው ትንሣኤ ሳምንት የምትመጣዋ ዕለተ እሑድ ‹ዳግም ትንሣኤ› ተብላ ትዘከራለች፡፡ ከላይ እንደ ተጠቀሰው ጌታችን በትንሣኤው ዕለት ማታ በዝግ በር ገብቶ፣ በቅዱሳን ሐዋርያት መካከል ተገኝቶ ‹‹ሰላም ለዅላችሁ ይኹን!›› በማለት ትንሣኤውን ሲገልጽላቸው ሐዋርያው ቶማስ አልተገኘም ነበር፡፡ በኋላ ከሔደበት ሲመጣ ጌታችን እንደ ተነሣ እና እንደ ተገለጸላቸው ሐዋርያት በደስታ ሲነግሩት ‹‹በኋላ እናንተ ‹አየን› ብላችሁ ልትመሰክሩ፤ ልታስተምሩ፤ እኔ ግን ‹ሰምቼአለሁ› ብዬ ልመሰክር፤ ላስተምር? አይኾንም፡፡ እኔም ካላየሁ አላምንም›› አለ፡፡

ስለዚህም የሰውን ዅሉ፤ ይልቁንም የመረጣቸው የወዳጆቹን የልብ ዐሳብ የሚያውቀው፣ ቸርነቱ ወሰን የሌለው የባሕርይ አምላክ መድኃኔ ዓለም ክርስቶስ ልክ እንደ መጀመሪያው ትንሣኤ ዕለት አበው ሐዋርያት በተዘጋ ቤት በአንድነት ተሰባስበው እንዳሉ በሩን ሳይከፍት ገብቶ ‹‹ሰላም ለዅላችሁ ይኹን!›› በማለት በመካከላቸው ቆመ፡፡ ቶማስንም ‹‹ያመንህ እንጂ ተጠራጣሪ አትኹን፤ እነሆ የተቸነከሩ እጆቼንና እግሮቼን፣ የተወጋ ጐኔንም ናና እይ፤›› ብሎ አሳየው፡፡

እርሱም ምልክቱን በማየቱ፣ በመዳሰሱ ትንሣኤውንና አምላክነቱን እንደ ፍላጎቱ በመረዳቱ ‹‹ጌታዬ፣ አምላኬ ብሎ መስክሮ›› የክርስቶስን ትንሣኤ አመነ፡፡ የሳምንቷ ዕለተ ሰንበት፣ የትንሣኤው ምሥጢር ለሁለተኛ ጊዜ ለሐዋርያት የተገለጠበት ዕለት በመኾኑ የትንሣኤው ሳምንት እሑድ ‹ዳግም ትንሣኤ› ተብሎ ይጠራል፤ ይከበራል (ዮሐ. ፳፥፳፬-፴)፡፡

ብርሃነ ትንሣኤውን የገለጸልን አምላካችን ለብርሃነ ዕርገቱም በሰላም ያድርሰን!

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

“ክርስቶስ ተንሥአ እሙታን”

በመ/ር ምሥጢረ ሥላሴ ማናየ

መጋቢት ፴ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

 “ክርስቶስ ተንሥአ እሙታን በዐቢይ ኃይል ወሥልጣን አሰሮ ለሰይጣን አግዐዞ ለአዳም ሰላም እምይዕዜሰ ኮነ ፍሥሐ ወሠላም፤ ክርስቶስ በታላቅ ኃይልና ሥልጣን ከሙታን ተለይቶ ተነሣ፡፡ ዲያብሎስን አሰረው፤ አዳምን ነጻ አወጣው፡፡ ሰላም! ከዛሬ ጀምሮ ሰላም ኾነ፡፡”

ይህ ኃይለ ቃል የትንሣኤው የምሥራች ለምእመናን የሚታወቅበት ኃይለ ቃል ነው፡፡ የሚቀድስ ካህን፣ ሰባኪ በዘመነ ትንሣኤ ከስብከቱ አስቀድሞ በዚህ ኃይለ ቃል የክርስቶስን መነሣት ያውጃል፡፡ የሚቀድሰው ካህንም በኪዳን ጊዜ ሕዝቡን ከመባረኩ አስቀድሞ ይህንኑ ቃል ይናገራል ሰላምታ የሚቀባበሉ ምእመናንም ሰላምታ ከመስጠት አስቀድሞ ይህን ቃል በመናገር የትንሣኤውን አዋጅ ማወጅና መመስከር ይገባቸዋል፡፡

እንኳን ለብርሃነ ትንሣኤው በሰላም አደረሰን! አደረሳችሁ!

የክርስቶስ ትንሣኤ እንደ እንግዳ ደራሽ፣ እንደ ውኃ ፈሳሽ አይደለም፡፡ ከጥንት በነቢያት የተነገረ፤ በኋላም እርሱ ክርስቶስ ከመሞቱ አስቀድሞ ለደቀ መዛሙርቱ ያስተማረው፤ ደግሞም በመነሣት የገለጠው፤ ሐዋርያትም በግልጥ ለዓለም የመሰከሩት ምሥጢር ነው፡፡

የክርስቶስ ትንሣኤ በትንቢተ ነቢያት

  • “እኔ ተኛሁ፤ አንቀላፋሁም፡፡ እግዚአብሔር አስነሥቶኛልና ተነሣሁ፤” (መዝ. ፫፥፭)፡፡
  • “እግዚአብሔር ይላል፤ ‹አሁን እነሣለሁ፤ መድኀኒት አደርጋለሁ፤ በእርሱም እገልጣለሁ፤›” (መዝ. ፲፩፥፭)፡፡
  • “እግዚአብሔር ይነሣል፤ ጠላቶቹም ይበተናሉ፡፡ … እግዚአብሔር ከእንቅልፍ እንደሚነቃ ተነሣ፤ የወይን ስካር እንደ ተወው እንደ ኃያልም ሰው፡፡ ጠላቶቹንም በኋላው መታ፤” (መዝ. ፸፯፥፷፭)፡፡

ቅዱስ ዳዊት በዚህ መልኩ የክርስቶስን ከሙታን መነሣት አስቀድሞ ተናግሯል፡፡ እርሱን መሰል ነቢያት ክርስቶስ እንደሚሞት በሦስተኛው ቀን ከሙታን ተለይቶ እንደሚነሣ ገልጸዋል፡፡ ምሳሌ ተመስሏል፤ ትንቢትም ተነግሯል፡፡ ዮናስ ሦስት መዓልትና ሦስት ሌሊት በዓሣ አንበሪ ሆድ እንደ አደረ ክርስቶስም ሦስት መዓልትና ሦስት ሌሊት በከርሠ መቃብር አድሮ ሙስና መቃብርን አጥፍቶ ብርሃነ መለኮቱን ገልጾ እንደሚነሣ ራሱ ባለቤቱ እግዚአብሔር ወልድ ተናግሯል (ዮና. ፪፥፩፤ ማቴ. ፲፪፥፵)፡፡

ነቢየ እግዚአብሔር ሆሴዕም “ከሁለት ቀን በኋላ ያድነናል፡፡ በሦስተኛው ቀን ያስነሣናል፡፡ በፊቱም በሕይወት እንኖራለን፤” በማለት የአምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ትንሣኤ ለእኛም ትንሣኤያችን፤ ሕይወታችን መኾኑን ገልጾ ተናግሯል (ሆሴ. ፮፥፪)፡፡ በተጨማሪም “ሞት ሆይ፥ መውጊያህ ወዴት አለ? ሲኦል (መቃብር) ሆይ፥ ድል መንሳትህ ወዴት አለ?” ብሎ ሞት እና መቃብር ሥልጣናቸው በክርስቶስ እንደ ተሻረ፤ በክርስቶስ ትንሣኤ የሰው ልጆች ትንሣኤ እንደ ተገለጸ ነግሮናል (ሆሴ. ፲፫፥፲፬)፡፡

በኦሪት ዘፍጥረት ፵፱፥፱ ላይ “ልጄ ሆይ፥ ከመሰማሪያህ (ከመቃብር) ወጣህ፡፡ እንደ አንበሳ ተኛህ፤ አንቀላፋህም፡፡ እንደ አንበሳ ደቦል የሚቀሰቅስህ የለም፤” የሚል ኃይለ ቃል እናገኛለን፡፡ በዚህ ኃይለ ቃል “የሚቀሰቅስህ የለም” የሚለው ክርስቶስ በገዛ ሥልጣኑ አስነሽ ሳይሻ ከሙታን ተለይቶ እንደ ተነሣ የሚያስረዳ ነው፡፡ ጌታችንም በራሱ ሥልጣን እንደሚነሣ እንዲህ በማለት አስተምሯል፤ “እንደ ገና አስነሣት ዘንድ እኔ ነፍሴን እሰጣለሁና ከእኔ ማንም አይወስዳትም፤ ነገር ግን እኔ በፍቃዴ እሰጣታለሁ፡፡ እኔ ላኖራት ሥልጣን አለኝ፤ መልሼ እወስዳት ዘንድ ሥልጣን አለኝና፤” (ዮሐ. ፲፥፲፯)፡፡ ይህ የሚያስረዳን ክርስቶስ ለዓለም ቤዛ ኾኖ በፈቃዱ እንደ ሞተና በሥልጣኑ እንደ ተነሣ ነው፡፡

የክርስቶስ ትንሣኤ በሐዲስ ኪዳን

አራቱም ወንጌላውያን እንደ አንድ ልብ መካሪ፣ እንደ አንድ ቃል ተናጋሪ ኾነው የክርስቶስን ትንሣኤ በወንጌል ጽፈውታል፡፡ ቅዱስ ማቴዎስ በወንጌሉ ምዕራፍ ፳፰፥፩-፲፮ “በሰንበትም ማታ ለእሑድ አጥቢያ ማርያም መግደላዊትና ሁለተኛዋ ማርያም መቃብሩን ሊያዩ መጡ፡፡ እነሆ ታላቅ የምድር መናወጥ ኾነ፤ የእግዚአብሔር መልአክ ከሰማይ ወርዷልና፡፡ ቀርቦም በመቃብሩ አፍ ላይ ድንጋይዋን አንከባሎ በላይዋ ተቀመጠ” ይላል፡፡ በዕለተ ትንሣኤ የክርስቶስን ትንሣኤ ለማየት መላእክት እንደዚሁም ቅዱሳት አንስት ተገኝተዋል፡፡ ሲወለድ የመወለዱን ዜና ለእረኞች የተናገሩ መላእክት በትንሣኤው ዕለትም ዜና ትንሣኤውን ለቅዱሳት አንስት ለማብሠር ከመቃብሩ ተገኝተው የትንሣኤው ምስክሮች ኾነዋል፡፡

ጌታችን ከሙታን ተለይቶ በተነሣ ጊዜም መቃብር ጠባቂዎቹ ከመለኮቱ ግርማ የተነሣ ታውከዋል፤ እንደ በድንም ኾነዋል፡፡ “ወእምግርማሁ ተሀውኩ ወኮኑ ከመ አብድንት እለ የዐቅቡ መቃብረ፤ እርሱን ከመፍራት የተነሣ መቃብሩን የሚጠብቁት ታወኩ፤ እንደ በድንም ኾኑ፤” እንዳለ ቅዱስ ማቴዎስ (ማቴ. ፳፰፥፬)፡፡ መልአኩ “እናንተስ አትፍሩ! የተሰቀለውን ኢየሱስን እንደምትሹ አውቃለሁና፡፡ በዚህ የለም፤ እርሱ እንደ ተናገረው ተነሥቶአል፡፡ ነገር ግን ኑና የተቀበረበትን ቦታ እዩ፤ ፈጥናችሁም ሒዱ፡፡ ከሙታን ተለይቶ ተነሣ፤” ብሎ የትንሣኤውን የምሥራች ለሴቶች መግለጡንም ማቴዎስ በወንጌሉ ጽፎአል፡፡

ቅዱስ ማርቆስም በምዕራፍ ፲፮፥፩-፲፮ ትንሣኤውን አስመልክቶ ከቅዱስ ማቴዎስ ጋር የሚመሳሰል መልእክት ተናግሯል፡፡ ቅዱስ ሉቃስም እንደዚሁ በምዕራፍ ፳፬፥፩-፳፬ የክርስቶስን ዜና ትንሣኤ ጽፎልናል፡፡ ቅዱስ ዮሐንስም በአጻጻፍ ስልቱ ከሦስቱ ወንገላውያን ረቀቅ ያለ ቢኾንም ትንሣኤውን በመመስከር ከሦስቱ ወንጌላውያን ጋር ተባብሯል፡፡ በወንጌሉ ምዕራፍ ፳ ከቍጥር ፩ ጀምሮ ማርያም መግደላዊትና ሌሎች ሴቶች ወደ መቃብሩ ገስግሰው በመሔድ ትንሣኤውን ለማየት እንደ በቁ፤ ለደቀ መዛሙርቱም የምሥራቹን እንደ ተናገሩ ዘግቦልናል፡፡

ከሦስቱ ወንጌላውያን በተለየ መልኩ ክርስቶስ ከተነሣ በኋላ በዝግ ደጅ ደቀ መዛሙርቱ ወደ አሉበት እንደ ገባ፤ ትንሣኤውን እንደ ገለጠላቸው፤ “ሰላም ለእናንተ ይኹን!” ብሎ የሰላም አምላክ ነውና ከሐዘናቸው እንዳጽናናቸው፤ ፍርሃታቸውንም እንዳራቀላቸው፤ “አይዞአችሁ! አትፍሩ! እኔ ነኝ፤ እጄን፣ እግሬን እዩ፤” በማለት ፍጹም ፍቅሩን እንደ አሳያቸው ቅዱስ ዮሐንስ በወንጌሉ ገልጾልናል፡፡

ትንሣኤው ምትሐት አለመኾኑን ይገልጥላቸውም ዘንድም “ደቂቅየ ቦኑ ብክሙ ዘንበልዕ፤ ልጆቼ፥ ጥቂት የሚበላ አላችሁን?” በማለት ጌታችን ደቀ መዛሙርቱን ጠይቋቸዋል፡፡ የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ትንሣኤ በሕቱም መቃብር የተፈጸመ፤ አምላካዊ ኀይሉ የገለጠበት ትንሣኤ ነው፡፡ የተነሣውም “መግነዝ ፍቱልኝ፤ መቃብር ክፈቱልኝ፤” ሳይል ነው፡፡

ጌታ ባረገ በስምንት ዓመት የተጠራው ቅዱስ ጳውሎስም ሐዋርያትን መስሎ እንዲህ ሲል ትንሣኤውን መስክሮአል፤ “ስለ ኃጢአታችን የተሰቀለውን፤ ሊያስነሣንና ሊያጸድቀን የተነሣውን ጌታችንን ኢየሱስን ከሙታን ለይቶ ባስነሣው ስለምናምን ስለ እኛም ነው እንጂ፤” (ሮሜ. ፬፥፳፬)፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ በዚህ መልእክቱ የጌታችን ትንሣኤ ለእኛም ትንሣኤያችን መኾኑን ይነግረናል፡፡

ትንሣኤው ለእኛ ሕይወት መኾኑን ሲነግረን ደግሞ “እርሱ ክርስቶስ በአባቱ ጌትነት ከሙታን ተለይቶ እንደ ተነሣ እኛም እንደ እርሱ በሐዲስ ሕይወት እንኖራለን፤” በማለት አስተምሮናል (ሮሜ. ፮፥፬)፡፡ ይህም ጌታችን በሞቱ ሞትን እንደ ሻረ፤ በትንሣኤው ትንሣኤያችንን እንዳበሠረ፤ እርሱ የትንሣኤያችን በኵር እንደ ኾነ፤ እኛም በሞቱ ብንመስለው የትንሣኤው ተካፋዮች እንደምንኾን ያሳየናል፡፡

ጌታችን በሚከተሉት አምስት ነገሮች በኵራችን መኾኑን ቅዱሳት መጻሕፍት ይነግሩናል፤

፩ኛ በጥንት፣ ገና ዓለም ሳይፈጠር፣ ዘመን ሳይቈጠር በመኖርና እኛን ፈጥሮ በማስገኘት በኵራችን ነው፡፡

፪ኛ በተቀድሶ (በመመስገን) በኵራችን ነው፡፡ ቅዱሳን የጸጋ ምስጋና የሚመሰገኑት እርሱን በኵር አድርገው ነውና፡፡

፫ኛ በትንሣኤው በኵራችን ነው፡፡ እርሱን በኵር አድርገን እንነሣለንና፡፡ “አሁንም ክርስቶስ ከሞቱ ሰዎች ዂሉ አስቀድሞ ተነሥቶአል፡፡ በመጀመሪያው ሰው ሞት መጥቶአል፤ በሁለተኛው ሰው ትንሣኤ ሙታን ኾነ፤” እንዳለ ቅዱስ ጳውሎስ (፩ኛ ቆሮ. ፲፭፥፳)፡፡

፬ኛ በዕርገቱ በኵራችን ነው፡፡ ቅዱሳን ዐረጉ መባሉ እርሱን በኵር አድርገው ነውና፡፡ “ዐርገ ከመ ያሌቡ ዕርገተ ጻድቃን ንጹሓን፤ የንጹሓን ጻድቃንን ዕርገት ያስረዳ ዘንድ አረገ” እንዲል (ቅዳሴ ዮሐንስ ወልደ ነጐድጓድ)፡፡

፭ኛ ነፍሳትን ከሲኦል አውጥቶ ምርኮን ማርኮ ገነት መንግሥተ ሰማያት በመግባት በኵራችን ነው፡፡

ስለዚህ በዓለ ትንሣኤውን ስናከብር የእኛም ትንሣኤያችን መኾኑን ዐውቀን ተረድተን ትንሣኤ ልቡና ተነሥተን መልካም ሥራ በመሥራት መኾን አለበት፡፡ እኛ ትንሣኤ ልቡና ሳንነሣ በየዓመቱ ትንሣኤውን ብናከብር ፈሪሳውያንን ወይም “ትንሣኤ ሙታን የለም፤ ፈርሰን፣ በስብሰን እንቀራለን” ብለው የሚያምኑ ሰዱቃውያንን መምሰል ይኾናል፡፡

ትንሣኤውን እንዴት ማክበር እንደሚገባን ቅዱስ ጳውሎስ እንዲህ ሲል ይመክረናል፤ “ከክርስቶስ ጋር ከተነሣችሁ ክርስቶስ በእግዚአብሔር ቀኝ ተቀምጦ ባለበት በላይ ያለውን ሹ፡፡ የላይኛውን ዐስቡ፤ በምድር ያለውንም አይደለም፡፡ እናንተ ፈጽማችሁ ሞታችኋልና፤ ሕይወታችሁም ከክርስቶስ ጋር በእግዚአብሔር ዘንድ የተሠወረች ናትና፡፡ ሕይወታችሁ ክርስቶስ በሚገለጥበት ጊዜ ያን ጊዜ ከእርሱ ጋር በፍጹም ክብር ትገለጣላችሁ፤” (ቈላ. ፫፥፩-፬)፡፡ የክርስቶስ ትንሣኤ ትንሣኤያችን ነው ብለን ለምናምን ዂሉ ከምድራዊ ዐሳብ ነጻ ኾነን ተስፋ የምናደርገው ትንሣኤ እንዳለን በማሰብ ከሞት በኋላ ሕይወት፣ ከትንሣኤም በኋላ የዘለዓለም ሞት መኖሩን ሳንዘነጋ በዓሉን ማክበር እንደሚገባን ሐዋርያው አስተምሮናል፡፡

ላይኛውን (ሰማያዊዉን መንግሥት) ለማያስቡ፤ መልካም ሥራ ለማይሠሩ ሰዎች ትንሣኤ ምን እንደሚመስል መድኅነ ዓለም ኢየሱስ ክርስቶስ ሲያስተምር እንዲህ ብሏል፤ “በመቃብር ያሉ ዂሉ ቃሉን የሚሰሙበት ጊዜ ይመጣል፡፡ ስለዚህ አታድንቁ፤ መልካም የሠሩ ለሕይወት ትንሣኤ፣ ክፉ የሠሩም ለፍርድ ትንሣኤ ይነሣሉ፤” (ዮሐ. ፭፥፳፰)፡፡

ምእመናን፣ የትንሣኤያቸውን በኵር ክርስቶስን አብነት አድርገው፣ ቃሉን ሰምተው፣ ሕጉን ጠብቀው፣ ትእዛዙን አክብረው፣ ትንሣኤ ልቡና ተነሥተው የትንሣኤን ዕለት ቢያከብሩ፤ ሥጋውን በልተው፣ ደሙን ጠጥተው፣ በንስሐ ተሸልመው፣ በፍቅረ እግዚአብሔርና ፍቅረ ቢጽ (ባልንጀራን በመውደድ) ጸንተው ቢኖሩ ላይኛውን ማሰብ ትንሣኤውን ማክበር ማለት ይህ ነው፡፡ እንደዚህ ካደረጉ የትንሣኤውን ትርጕም ዐውቀዋል፡፡

ከትንሣኤ ሥጋ ትንሣኤ ልቡና ተነሥተን ሥጋውን በልተን ደሙን ጠጥተን መንግሥቱን እንድንወርስ ስሙን እንድንቀድስ እግዚአብሔር አምላካችን ይፍቀድልን፡፡ መልካም የትንሣኤ በዓል ይኹንልን!

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

የትንሣኤው ብሥራት

በመ/ር ሳሙኤል ተስፋዬ

መጋቢት ፳፱ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

በጥንተ ጠላታችን ዲያቢሎስ አሳሳችነት አዳምና ሔዋን የእግዚአብሔርን ሕግ በመተላላፋቸው ሞተ ሥጋና ሞተ ነፍስ ተፈርዶባቸው ነበር፡፡ የዓለም መድኃኒት ኢየሱስ ክርስቶስ ለሰው ልጆች ካለው ፍጹም ፍቅር የተነሣ የተፈረደባቸውን ሞት በሞቱ ሊደመስስ ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ተወለደ (ዮሐ. ፩፥፩)፡፡ ሠላሳ ዓመት ሲሞላው በዮርዳኖስ ወንዝ ተጠመቀ፡፡ እንደ ተጠመቀም ልዋል ልደር ሳይል ወደ ገዳመ ቆሮንቶስ ሔደ፡፡ በዚያም ጾመ፤ ጸለየ፡፡ በዲያቢሎስም ተፈተነ፡፡

ሦስት ዓመት ከሦስት ወር ካስተማረ በኋላ የአዳምና የሔዋንን ዕዳ ደምስሶ ነጻ ሊያደርጋቸው በገባው ቃል ኪዳን መሠረት መከራ ተቀበለ፡፡ በአይሁድ ሸንጎ ፊት ቆመ፤ ምራቅ ተተፋበት፤ ተገረፈ፤ በገመድ ታሥሮ ተጎተተ፤ በመስቀል ላይ ተሰቅሎ ሞተ፡፡ በሞቱ ሞትን ድል አድርጎ የአዳምን፣ የሔዋንንና የልጆቻቸውን ዕዳ በደል ደመሰሰ (ማቴ. ፳፯፥፳፰)፡፡

ቅዱስ ጳውሎስ “ሞቱንም በሚመስል ሞት ከእርሱ ጋር ከተባበርን ትንሣኤውን በሚመስል ትንሣኤ ደግሞ ከእርሱ ጋር እንተባበራለን፤” በማለት እንደ ገለጸው (ሮሜ. ፮፥፭)፣ ሞቱ ሞታችን፤ ትንሣኤው ትንሣኤያችን ነውና የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃይማኖት ተከታዮች በየዓመቱ ጌታ የጾመውን ጾም በመጾም፣ በሰሙነ ሕማማት ደግሞ መከራውንና ስቃዩን በማሰብ የክርስቶስን ቤዛነት እንዘክራለን፤ የነጻነትና የድል በዓላችንንም እናከብራለን፡፡

“በጥንተ ጠላታችን ምክንያት አይሁድ ክብርህን ዝቅ ቢያደርጉ፣ ቢያዋርዱህ፣ ቢገርፉህ፣ ርቃንህን ቢሰቅሉህና ቢገድለህ እኛ ግን ‹ለከ ኃይል ክብር ወስብሐት ወእዘዝ ለዓለም ዓለም አማኑኤል አምላኪየ ለከ ኃይል ክብር ወስብሐት ወእዘዝ ለዓለም ዓለም ኦ እግዚእየ ኢየሱስ ክርስቶስ ለከ ኃይል ክብር ወስብሐት ወእዘዝ ለዓለም ዓለም – ኃይሌ፣ መከታዬና ረዳቴ ለኾንኸው ለአንተ ለአምላኬ ለአማኑኤል ለጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ክብርና ምስጋና ጽናትም ለዘለዓለሙ ይገባሃል›፤” እያልን አምላካችንን እናመሰግነዋለን፡፡

ቅዱስ ጳውሎስ በፊልጵስዩስ ፫፥፲ ላይ “እርሱንና የትነሣኤውን ኃይል እንዳውቅ በመከራወም እንድካፈል ወደ ሙታንም ትንሣኤ ልደርስ ቢኾንልኝ በሞቱ እንደመስለው እመኛለሁ፤” በማለት እንደ ተናገረው ምእመናን እንደ አቅማቸው እያዘኑ፣ እያለቀሱ፣ ከምግብ እየተከለከሉ፣ ጸጉራቸውን እየተላጩ የአምላካንን መከራ ያስባሉ፡፡

“ሞትን ድል አድርጎ ተነሥቷል!” የሚለውን የምሥራች ከቤተ ክርስቲያን ለመስማት በናፍቆት ይጠባበቃሉ፡፡ የትንሣኤውን ብሥራት ሰከሙ በኋላም “ጌታ በእውነት ተነሥቷል!” እያሉ ትንሣኤዉን ይመሰክራሉ፡፡ የጌታችን ትንሣኤ፣ የድኅነታችን ብሥራት በመኾኑ ለአምሳ ቀናት ያህል በቅዳሴው፣ በማኅሌቱ፣ በወንጌሉ፣ በሌሎችም ቅዱሳት መጻሕፍት በልዩ ሥርዓት ይዘከራል፡፡ በየአብያተ ክርስቲያኑ “ክርስቶስ ተንሥአ እሙታን በዓቢይ ኃይል ወሥልጣን አሠሮ ለሰይጣን አግዐዞ ለአዳም ሰላም እምይእዜሰ ኮነ ፍሥሐ ወሰላም” እየተባለ ሞት መደምሰሱ፣ ነጻነት መታወጁ ይበሠራል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ዐሥራ ሦስቱ ሕማማተ መስቀል

መጋቢት ፳፱ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

በሰሙነ ሕማማት ጠቅለል ባለ መልኩ የምናስባቸው የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ሕማማት ‹ዐሥራ ሦስቱ ሕማማተ መስቀል› ይባላሉ፡፡ ለክርስቲያኖች እነዚህን ሕማማተ መስቀል ማወቅና ዘወትር ማሰብ ተገቢ በመኾኑ እንደሚከተለው አቅርበናቸዋል፤

፩. ተኰርዖተ ርእስ (ራስና በዘንግ መመታት)

‹ተኰርዖት› የሚለው ቃል ‹ኰርዐ – መታ› ከሚለው የግእዝ ግሥ የተገኘ ነው፡፡ ‹ርእስ› ደግሞ ራስ ማለት ነው፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ራሱን በዘንግ መመታቱንና መቀጥቀጡን የሚገልጥ ነው፡፡ አገረ ገዥው ጲላጦስ ‹‹እኔ ከዚህ ጻድቅ ሰው ደም ንጹሕ ነኝ›› ብሎ እጁን ከታጠበ በኋላ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ገርፎ ለካህናት አለቆችና ለሽማግሎች አሳልፎ ሰጥቶት ነበር፡፡ በአይሁድ ሕግ የተገረፈ አይሰቀልም፤ የሚሰቀል ደግሞ አይገረፍም፡፡ እርሱ ጲላጦስ ግን ከገረፈው በኋላ፣ የበደል በደል፣ እንዲሰቅሉት አሳልፎ ሰጣቸው (ማቴ. ፳፯፥፳፬፤ ማር. ፲፭፥፲፭፤ ሉቃ. ፳፫፥፳፭፤ ዮሐ. ፲፰፥፴፱)፡፡

አይሁድ የእሾኽ አክሊል ጐንጕነው በጌታችን ራስ ላይ ደፍተውበታል፡፡ ራሱንም በዘንግ መትተውታል (ማር. ፲፭፥፲፱)፡፡ የሰው ዘር ከአዳም ጀምሮ በጠላቱ በዲያብሎስ በተጐነጐነ የኃጢአት እሾኽ ራሱ ተይዞ ነበርና ይህንኑ ለማስወገድ ከሰማይ የወረደ ሰማያዊ የኾነ ዳግማዊ አዳም ክርስቶስ አክሊለ ሦክ እንደ ዘውድ ደፋ፡፡ በሲኦል ወድቆ በዲያብሎስ ተረግጦ ራሱ የሚቀጠቀጠውን የሰውን ልጅ ለማዳን መድኃኔ ዓለም ክርስቶስ ራሱን በመቃ ተቀጠቀጠ፡፡ ከራሱ ላይ በሚወርደው ደም ፊቱ ተሸፈነ፡፡

፪. ተፀፍዖ መልታሕት (በጥፊ መመታት)

‹ተፀፍዖ› የሚለው ቃል ‹ፀፍዐ – በጥፊ መታ› ከሚለው የግእዝ ግሥ የወጣ ሲኾን፣ ‹መጥፊ መመታት› ማለት ነው፡፡ ‹መልታሕት› ደግሞ ‹ፊት፣ ጉንጭ› ማለት ነው፡፡ ይኸውም አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ እጃቸው በደም፣ ጣቶቻቸው በበደል በረከሰ በአይሁድ እጅ በጥፊ መመታቱን የሚገልጥ ነው፡፡ ለሊቀ ካህናት ቀያፋ እውነትን መናገር እንደ ስድብ ተቈጥሮበት አይሁድ ጌታችን መላልሰው ፊቱን በጥፊ መትተውታል፡፡ ፊቱንም በጨርቅ ሸፍነው ‹‹ክርስቶስ ሆይ! በጥፊ የመታህ ማነው? ትንቢት ተናገርልን!›› እያሉ ዘብተውበታል፡፡

በጠላት ዲያብሎስ እጅ ወድቆ በነፍሱ ይቀለድበትና ይንገላታ የነበረውን የሰውን ልጅ ለማዳን ብሎ መድኀኒታችን ክርስቶስ በጠላቶቹ በአይሁድ እጅ ወድቆ ተጐሰመ፤ ተንገላታ፤ በጥፊም ተመታ (ማቴ.  ፳፯፥፳፯)፡፡ ጲላጦስ አሳልፎ ከሰጠው በኋላም አክሊለ ሦክ በራሱ ላይ አኑረው ቀይ ልብስ አልብሰው ‹‹የአይሁድ ንጉሥ ሆይ! ሰላም ለአንተ ይኹን!›› እያሉ እየተሳለቁበት በጥፊ መትተውታል (ዮሐ. ፲፱፥፪)፡፡ አላወቁትም እንጂ እርሱ በመንግሥቱ ሽረት፣ በባሕርዩ ሞት የሌለበት የዘለዓለም አምላክ ነው፡፡

፫. ወሪቀ ምራቅ (ምራቅ መተፋት)

‹ወሪቅ› የሚለው ቃል ‹ወረቀ – እንትፍ አለ፤ ተፋ› ካለው ግእዛዊ ግሥ የተገኘ ሲኾን፣ ትርጕሙም ‹እንትፍ ማለት፣ መትፋት› ማለት ነው፡፡ ‹ምራቅ› በቁሙ ‹ምራቅ› ማለት ነው፡፡ ወሪቀ ምራቅ፣ አይሁድ በብርሃናዊው በክርስቶስ ፊት ላይ በሚያስጸይፍ ኹኔታ ምራቃቸውን እንደ ተፉበት የሚገልጥ ነው፡፡ በትንቢት ኢሳይያስ ፶፥፮ ላይ ‹‹ፊቴንም ከውርደትና ከትፋት አልመለስኩም›› ተብሎ እንደ ተነገረ፣ አይሁድ እየዘበቱ በአምላካችን ላይ ምራቃቸውን ተፍተውበታል (ማቴ. ፳፯፥፳፱-፴፤ ማር. ፲፭፥፲፱)፡፡

በኃጢአት የቆሸሸውን የሰውን ሕይወት ለማጥራት የመጣው ንጹሐ ባሕርይ አምላክ ምራቅ ተተፋበት፡፡ በሥራው ከገነት ተተፍቶ፤ ተንቆ፤ ተዋርዶ የነበረውን የሰውን ልጅ ለማዳን ኃጢአትን ይቅር የሚል እርሱ ጌታችን ያለ ኃጢአቱ ተተፋበት፤ ተናቀ፤ ተዋረደ፡፡ እንኳን በአምላክ ፊት በሰው ፊት እንኳን መትፋት እጅግ ያስነውራል፡፡ እርሱ ግን የኃጢአታችንን ነውር ከእኛ ሊያጠፋ ነውር የኾነውን ምራቅ በትዕግሥት ተቀበለ፡፡

፬. ሰትየ ሐሞት (አሞት መጠጣት)

‹ሰትየ› ማለት በግእስ ቋንቋ ‹ጠጣ› ማለት ሲኾን፣ ‹ሰትይ› ደግሞ ‹መጠጣት› የሚል ትርጕም አለው፡፡ ‹ሐሞት› የሚለው የግእዝ ቃልም ‹አሞት› ተብሎ በቁሙ ይተረጐማል፡፡ ቃላቱ በአንድ ላይ ‹ሰትየ ሐሞት› ተብለው ሲናበቡ ‹አሞት መጠጣት› የሚል ትርጕም ይሰጣሉ፡፡ ይኸውም ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመልዕልተ መስቀል ሳለ ‹‹ተጠማሁ›› ባለ ጊዜ መራራ አሞት መጠጣቱን የሚገልጥ ነው፡፡

‹‹ለመብሌ አሞት ሰጡኝ፤ ለጥማቴም ኾምጣጤ አጠጡኝ›› ብሎ ነቢዩ ዳዊትን በመዝሙረ ዳዊት መዝሙር ፷፰፥፳፩ ላይ ትንቢት ያናገረ የነቢያት አምላክ ኢየሱስ ክርስቶስ የመጽሐፉ ቃል ይፈጸም ዘንድ ‹‹ተጠማሁ›› ባለ ጊዜ ኾምጣጤ በሰፍነግ ሞልተው ወደ አፉ አቀረቡለት፡፡ ውኃ አጠጡኝ ቢላቸው በሐሞት የተደባለቀ የወይን ጠጅ ሊጠጣ አቀረቡለት፡፡ ቀምሶም ሊጠጣው አልወደደም (ማቴ. ፳፯፥፴፬)፡፡ ጌታችንም ኾምጣጤውን ከተቀበለ በኋላ ‹‹ተፈጸመ›› አለ፡፡ ራሱንም አዘንብሎ ነፍሱን በፈቃዱ አሳልፎ ሰጠ (ማቴ.፳፯፥፵፰፤ ማር. ፲፭፥፴፮፤ ሉቃ. ፳፫፥፴፮፤ ዮሐ. ፲፱፥፳፱)፡፡

ቢጠጡት ለዘለዓለም የማያስጠማ ውኃ የሚሰጥ አምላክ፤ የተጠማችውን ነፍስ የሚያረካ ጌታ፤ ለዘለዓለም የሚፈልቅ የሕይወት ውኃን የሚያድል ፈጣሪ በተጠማ ጊዜ የፈጠረውን ውኃ እንኳን የሚያጠጣው የሚያቀምሰውም አላገኘም (ኢሳ. ፶፭፥፩)፡፡ ዐርባ ዓመት ሙሉ በቃዴስ በረሃ ሲጓዙ ለነበሩ አባቶቻቸው ከሰማይ መና አውርዶ የመገባቸው፤ ከዐለት ላይ ውኃ አመንጭቶ ያጠጣቸው ክርስቶስ በተጠማ ጊዜ አይሁድ ቀዝቃዛ ውኃ ነፈጉት (ዘዳ. ፲፮፥፩-፳፤ ፩ኛ ቆሮ. ፲፥፫)፡፡ የዝናማት፤ የባሕርና የውቅያኖስ ጌታ በውኃ ጥም ተቃጠለ፡፡

መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሲኦል በረሃ ወድቀው በሕይወት ውሃ ጥም የተቃጠሉትን ነፍሳት ለማርካት ሲል እርሱ ተጠማ፡፡ በኃጢአት ወድቀው፣ በበደል ረክሰው፣ በነፍሳቸው ተጐሳቁለው፣ መራራ መከራን የሚቀበሉትንና ምረረ ገሃነም አፉን ከፍቶ ሆዱን አስፍቶ የሚጠብቃቸውን ዂሉ ለማዳን መራራ ሐሞትን ቀመሰ፤ ኾምጣጣውንም ጠጣ፡፡ የመረረውን የሰው ልጆችን ሕይወት ለማጣፈጥ የመረረውን መጠጥ ተቀበለ፡፡

፭. ተቀሥፎ ዘባን (ጀርባን መገረፍ)

‹ተቀሥፎ› የሚለው ቃል ‹ቀሠፈ – ገረፈ› ካለው የግእዝ ግሥ የተገኘ ሲኾን፣ ‹መገረፍ› ማለት ነው፡፡ ‹ዘባን› ደግሞ ‹ጫንቃ፣ ትከሻ፣ ጀርባ› የሚል ትርጕም አለው፡፡ መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጀርባው እስኪላጥ ድረስ ያለ ርኅራኄ የመገረፉን ነገር የሚገልጥ ነው፡፡ ከላይ እንደ ተጠቀሰው በዘመኑ የቅጣት ሕግ መሠረት የተገረፈ አይሰቀልም፤ የሚሰቀል ደግሞ አይገረፍም ነበር፡፡ ቅጣቱን ለማቅለል ዐስቦ ጲላጦስ ኢየሱስ ክርስቶስን ቢያስገርፈውም አይሁድ ግን በግፍ ሰቅለውታል፡፡ ጲላጦስ ‹‹ከደሙ ንጹሕ ነኝ›› ብሎ እጁን ከታጠበ በኋላ ጌታችንን ለአይሁድ አሳልፎ በመስጠት ‹‹ታጥቦ ጭቃ›› እንዲሉ የታጠበ እጁን መልሶ አቆሸሸው (ማቴ. ፳፯፥፳፰፤ ማር. ፲፭፥፲፭፤ ዮሐ. ፲፱፥፩)፡፡

በነቢዩ ኢሳይያስ ‹‹ጀርባዬን ለገራፊዎች፣ ጉንጬንም ለጠጉር ነጪዎች ሰጠሁ›› ተብሎ እንደ ተነገረ ጀርባውን ለገራፊዎች አሳልፎ ሰጠ፤ ጽሕሙንም ተነጨ፡፡ በመንፀፈ ደይን ወድቆ በእግረ አጋንንት ተጠቅጥቆ በእሳት አለንጋ የሚገረፈውን የሰው ልጅ ለማዳን ሲል ጌታችን ጀርባውን ለግርፋት ሰጠ፡፡ ሥጋው አልቆ አጥንቱ እስኪቈጠር ድረስም ተገረፈ፡፡ አይሁድ አገረ ገዥያቸው ጲላጦስ ላቀረበላቸው ምርጫ ይፈታላቸው ዘንድ ነፍሳትን ከሲኦል የሚያወጣውን ክርስቶስን ሳይኾን ራሱን እንኳን ከምድራዊ ወኅኒ ማውጣት ያልቻለውን ወንበዴውን በርባንን መረጡ፡፡ መገረፍ ይገባው የነበረ በርባን ተለቀቀ፡፡ ይህ ዂሉ የኾነውም የሰው ልጅ ከሚያድነው አምላክ ይልቅ የሚገርፈውንና የሚዘርፈውን ወንበዴ መርጦ ስለተገኘ ነው፡፡ በእርግጥ ክርስቶስ ካልሞተ ዓለም አይድንምና ሳያውቁም ቢኾን መድኃኒታቸውን መርጠዋል፡፡

፮. ተዐርቆተ ልብስ (ከልብስ መራቆት)

‹ተዐርቆተ› ማለት በግእዝ ቋንቋ ‹መታረዝ፣ መራቆት› ማለት ነው፡፡ ይኸውም አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ልብሱን መራቆቱን የሚገልጥ ነው፡፡ ፀሐይና ከዋክብትን ብርሃን አልብሶ የፈጠረ አምላክ ለእኛ ሲል ተራቆተ፡፡ ጸጋውን ለዕሩቃን የሚያለብስ አምላክ ለዓለም ድኅነት ሲል ራቁቱን ለፍርድ ቆመ፡፡ ጨለማን ለብሶ ጨለማን ተንተርሶ ይኖር የነበረውን ሰው መልሶ ብርሃን ያለብሰው ዘንድ የብርሃናት ጌታ፣ የዓለሙ ዂሉ አምላክ ኢየሱስ ክርስቶስ ተገፈፈ፤ ተራቆተ፡፡ የሲኦል ወታደሮች አጋንንት የሰውን ልጅ ጸጋ ገፍፈውት ነበርና ይህን ጸጋ ለማስመለስ ሲል ጌታችን በአይሁድ ወታደሮች ልብሱን ተገፈፈ፡፡

፯. ርግዘተ ገቦ (ጎንን በጦር መወጋት)

‹ርግዘት› የሚለው ቃል ‹ረገዘ – ወጋ› ከሚለው የግእዝ ግሥ የወጣ ሲኾን ‹በጦር መወጋት› የሚል ትርጕም አለው፡፡ ‹ገቦ› ማለት ‹ጎን›፤ ‹ርግዘተ ገቦ› ደግሞ ‹ጎንን በጦር መወጋት› ማለት ነው፡፡ መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነፍሱን ለሞት አሳልፎ ከሰጠ በኋላ ጎኑን በስለታም ጦር ተወግቷል፡፡ ጌታችን በመስቀል ላይ ሳለ ከጭፍሮች አንዱ ጎኑን በጦር ወጋው፡፡ በዚህ ጊዜ ድኅተ ሥጋ ድኅነተ ነፍስ የሚሰጥ ደምና ውኃ ከጎኑ ፈሰሰ (ዮሐ. ፲፱፥፴፫)፡፡ መላእክትም ደሙን ተቀብለው በዓለም ረጭተውታል፡፡

አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሞትን ድል ያደርገው ዘንድ ሞተ፤ የሰው ልጅ በዘለዓለማዊ ሞት ተይዞ ነበርና፡፡ ትልቁ ሞት በኃጢአት ምክንያት ከእግዚአብሔር መለየት ነው፡፡ በጌታችን ሞት ግን ሞት ራሱ ድል ተነሣ፡፡ የሞት መውጊያ በኾነ ኃጢአት የሞተውን ሰው ለማዳን ሲል አምላካችን ጎኑን በጦር ተወጋ፡፡ በሰው ልቡና ተተክሎ የነበረውን ኃጢአት ከነሥሩ ነቅሎ ስለ ጣለው ‹‹ሞት ሆይ፥ መውጊያህ የት አለ?›› ተብሎ ተዘመረ፡፡ የሞት መውጊያው ኃጢአት በክርስቶስ ሞት ድል ተደርጓልና (ኢሳ. ፳፭፥፰፤ ሆሴ. ፲፫፥፲፬፤ ፩ኛ ቆሮ. ፲፭፥፶፬-፶፭)፡፡

ከተወጋው ከጌታችን ጎን የፈሰሰው ደምና ውኃም የእግዚአብሔርን ልጅነትና የዘለዓለምን ሕይወት አጥቶ የነበረው ሰው ልጅነቱና ሕይወቱ እንደ ተመለሰለት የሚያረጋግጥ ነው፡፡ ምክንያቱም ከጎኑ በፈሰሰው ውኃ ተጠምቆ ልጅነትን፣ ደሙንም ጠጥቶ የዘለዓለም ሕይወትን ማግኘት ይቻላልና (ዮሐ. ፫፥፭፤ ፮፥፶፬)፡፡

፰. ተአሥሮተ ድኅሪት (ወደ ኋላ መታሠር)

‹ተአሥሮት› የሚለው ቃል ‹አሠረ (ሲነበብ ይላላል) – አሠረ› ወይም ‹ተአሥረ – ታሠረ› ከሚለው የግእዝ ግሥ የተገኘ ሲኾን ትርጕሙም ‹መታሠር› ማለት ነው፡፡ ‹ድኅሪት› የሚለው ቃል ደግሞ ‹ተድኅረ – ወደ ኋላ አለ› ከሚለው ግሥ የወጣ ነው፡፡ ሁለቱ ቃላት በአንድ ላይ (ተአሥሮተ ድኅሪት) ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሁለት እጆቹን ወደ ኋላ የፊጥኝ መታሠሩን የሚገልጥ ትርጕም ይሰጣሉ፡፡

መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ራሱን ለአይሁድ አሳልፎ በሰጠባት በዚያች ዕለት ሻለቃውና ጭፍሮቹ የአይሁድም ሎሌዎች እጁን የኋሊት አሥረው መሬት ለመሬት ጎትተውታል (ዮሐ. ፲፰፥፲፪)፡፡ በኃጢአት ሰንሰለት የኋሊት ታሥሮ ጠላት ዲያብሎስ የሚያፍገመግመውን የሰው ልጅ ለማዳን፣ ሰውንም ከኃጢአት እሥራት ለመፍታት ሲል መድኃኔ ዓለም ክርስቶስ በጠላቶቹ በአይሁድ እጅ የኋሊት ታሠረ፡፡

ከ ፱ – ፲፫ ያሉት የሕማማተ መስቀል ክፍሎች ደግሞ አምስቱ ቅንዋተ መስቀል ናቸው፡፡

በስምንቱ ሕማማት ላይ ሲደመሩ ዐሥራ ሦስት ይኾናል፡፡ ‹ቅንዋት› የሚለው ቃል ‹ቀነወ – ቸነከረ› ከሚለው የግእዝ ግሥ የተገኘ ነው፡፡ ‹መስቀል› ማለት ደግሞ የተመሳቀለ ዕንጨት ማለት ነው፡፡ ‹ቅንዋተ መስቀል› – መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመስቀል ላይ የተቸነከረባቸውን አምስቱን ጠንካራ የብረት ችንካሮች (ምስማሮች) የሚገልጥ ነው፡፡ አምስቱ ቅንዋተ መስቀል፡- ሳዶር፣ አላዶር፣ ዳናት፣ አዴራ፤ ሮዳስ በመባል ይታወቃሉ፡፡ እነዚህም የአምስቱ አዕማደ ምሥጢራት ምሳሌዎች መኾናቸውን አበው ያስተምራሉ፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ቀዳም ሥዑር

መጋቢት ፳፰ ቀን ፳፻፲ ዓ.

የሰሙነ ሕማማቷ ቅዳሜ ‹ቀዳም ሥዑር› ወይም ‹ቀዳሚት ሥዑር› ትባላለች፡፡ ትርጕሙም ‹የተሻረች ቅዳሜ› ማለት ነው፡፡ የማትጾመዋ ቅዳሜ ከቀድሞው በተለየ መልኩ የጌታችንን መከራ በማሰብ በጾም ታስባ ስለምትውል ‹የተሻረችው ቅዳሜ› ተብላ ተጠርታለች፡፡ ነገር ግን ቃሉ ጾምን እንጂ በዓል መሻርን አያመለክትም፡፡ በቀዳም ሥዑር  ሌሊት ሥርዓቱ የሚጀመረው በመኃልየ መኃልይ ዘሰሎሞን ምንባብ ነው፡፡ ማኅሌቱም እዝሉ እየተቃኘ፣ እየተመጠነ፣ እየተዘመመ፣ እየተመረገደ፣ እየተጸፋ ያድራል፡፡ ጠዋት አቡን፣ መዋሥዕት፣ ውዳሴ ማርያም ዜማ ተደርሶ ‹‹ወለመልአከ ሕይወትሰ ሰቀልዎ›› በሚለው ሰላም ሥርዓተ ማኅሌቱ ይጠናቀቃል፡፡

ካህናቱ ለምእመናን ለምለም ቀጤማ የሚያድሉበት ዕለት ስለ ኾነ ዕለተ ቅዳሜ ‹ለምለም ቅዳሜ› ተብላም ትጠራለች፡፡ በቀዳም ሥዑር ቀሳውስቱና ዲያቆናቱ ቃጭል (ቃለ ዓዋዲ) እየመቱ ‹‹ገብረ ሰላመ በመስቀሉ ትንሣኤሁ አግሃደ›› የሚለውን ያሬዳዊ ዜማ በመዘመር፤ ጌታ በመስቀሉ ሰላምን እንደ ሰጠን እና ትንሣኤውንም እንደ ገለጠልን በማብሠር፤ ቄጠማውን ለምእመናን ይሰጣሉ፡፡ ምእመናኑም በቤተ ክርስቲያን አገልግሎት የሚውል ገጸ በረከት ያቀርባሉ፡፡ ልብሰ ተክህኖ የለበሱ ካህናትና ዲያቆናት ቄጠማ ተሸክመው ቃጭል ሲያቃጨሉ መታየታቸው ዕለተ ትንሣኤውን ለሚናፍቅ ምእመን ትልቅ ብሥራት ነው፡፡

ቀጤማውንም ምእመናን እስከ ትንሣኤ ሌሊት ድረስ በራሳቸው ላይ አሥረውት ይቆያሉ፡፡ ይህም አይሁድ በጌታችን ራስ ላይ የእሾኽ አክሊል ማሠራቸውን የሚያስታውስ ነው፡፡ የቀጤማው አመጣጥና ምሥጢርም ከአባታችን ከኖኅ ታሪክ ጋር የተያያዘ ነው፡፡ ምድር በማየ አይኅ (በጥፋት ውኃ) በጠፋችበት ወቅት የኖኅ ታማኝ መልእክተኛ ርግብ የውኃውን መጉደል ያበሠረችው ቀጤማ ይዛ በመግባት ነው፡፡ ዛሬም ለሐዲስ ኪዳን ክርስቲያኖች ‹‹የኃጢአት ውኃ ጐደለ፣ የኃጢአት ውኃ ጠፋ፤ በክርስቶስ ሞትና ትንሣኤ ነጻነት ተሰበከ፤ ታወጀ፤›› በማለት ካህናት ቄጠማ ይዘው ምእመናንን ያበሥሩበታል፡፡

ዕለተ ቅዳሜ ‹ቅዱስ ቅዳሜ› እየተባለችም ትጠራለች፡፡ ቅዱስ መባሏም ቅዱስ እግዚአብሔር በጥንተ ተፈጥሮ ፍጥረታትን አከናውኖ ከፈጠረ በኋላ በዚህ ቀን ከሥራው ዅሉ ስላረፈባት ነው፡፡ በዘመነ ሐዲስ ደግሞ የማዳን ሥራውን ዅሉ ፈጽሞ በሥጋው በመቃብር ሲያርፍ፤ በነፍሱ ሲኦልን በርብሮ ባዶዋን አስቀርቷታል፡፡ በዚያ ለነበሩት ነፍሳትም የዘለዓለም ዕረፍትን ያወረሰበት ዕለት ስለ ኾነ ከሌሎቹ ዕለታት የተለየች ዕለት መኾኗን ለማመላከት ‹ቅዱስ› (ቅድስት) ተብላለች፡፡

ምእመናን ሆይ! በአጠቃላይ የጌታችንን የመከራ ሳምንት ‹ሰሙነ ሕማማት› ብለው ሰይመው፣ ሥርዓት አውጥተው አባቶቻችን ያቆዩልንን ትውፊት ልንጠብቀውም፣ ልንጠቀምበትም ይገባል፡፡ የዕለታቱን ክብርና ስያሜ ከማወቅና ከመረዳት ጋር በዕለታቱ የታዘዙትን ሃይማኖታዊ ግዴታዎችን መወጣት ይኖርብናል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ምንጭ፡ ስምዐ ተዋሕዶ፣ ማኅበረ ቅዱሳን፤ ከሚያዝያ ፲፭ ቀን ፳፻፬ .ም፣ አዲስ አበባ፡፡

ቀዳሚት ሥዑር

በመምህር ቸርነት አበበ

መጋቢት ፳፰ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

ዕለተ ቅዳሜ እግዚአብሔር አምላካችን የሚታዩትንና የማይታዩትን፣ በእግር የሚሔዱትን፣ በክንፍ የሚበሩትን እና በባሕር የሚዋኙትን እንስሳትን፣ በመጨረሻም ሰውን በአርአያውና በአምሳሉ ፈጥሮ ያረፈባት ዕለት ነች፡፡ የመጀመሪያዋ ቅዳሜ ለእግዚአብሔር የዕረፍት ዕለት ናት፡፡ እግዚአብሔርን ፍጥረታትን ፈጥሮ ከፈጸመ በኋላ ስላረፈባት ‹ሰንበት ዐባይ› (ታላቋ ሰንበት) ትባላለች፡፡ ይህቺን ዕለት እስራኤላውያን እንዲያከብሯት ታዟል፡፡ ዕለተ ቀዳሚት (ሰንበት ዐባይ) በዘመነ ሐዲስም የተለየ የደኅነት ሥራ ተከናውኖባታል፡፡ እግዚአብሔር ጥንት ሥነ ፈጥረትን በመፍጠር ዕረፍት እንዳደረገባት ዅሉ፣ የፍጥረት ርእስ የኾነውን አዳምን ለማዳን ሕማምና ሞት የተቀበለው አምላካችን ክርስቶስ በመቃብር አርፎባታል (ማቴ. ፳፯፥፷፩)፡፡

ቀዳሚት ሰንበት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በከርሠ መቃብር አርፎ የዋለባት ዕለት በመኾኗ ‹ቀዳሚት ሥዑር› ትሰኛለች፡፡ ‹ሥዑር› የተባለችበት ምክንያትም በዓመት አንድ ቀን ስለምትጾም (የጾም ቀን በመኾኗ) ነው፡፡ የጌታችን እናት ቅድስት ድንግል ማርያም፣ ወዳጆቹ ቅዱሳን ሐዋርያት ጌታችን ተላልፎ ከተሰጠበት ዕለት ጀምሮ ብርሃነ ትንሣኤውን እስኪያዩ ድረስ እኽል ውኃ በአፋቸው አልዞረም፡፡ ይመኩበትና ተስፋ ያደረጉት የነበረ አምላካቸው በመቃብር ስላረፈ ዕለቷን ሞቱን በማሰብና ትንሣኤውን በመናፈቅ በጾም አክብረዋታል፡፡

እመቤታችንና ቅዱሳን ሐዋርያት በማዘን፣ በመጾምና በመጸለይ ዕለቷን እንዳከበሯት ዅሉ የተዋሕዶ ልጆችም የተቻላቸው ከዓርብ ጀምረው በማክፈል (በመጾም) እኽል ውኃ ሳይቀምሱ ለሁለት ቀናት ያድራሉ፡፡ ያልተቻላቸው ደግሞ ዓርብ ማታ በልተው ቅዳሜን በመጾም ትንሣኤን ያከብራሉ፡፡ በዚህ ዕለት ከሰኞ ከሆሣዕና ማግሥት ጀምረው እስከ ስቅለተ ዓርብ ድረስ በስግደት እና በጾም ያሳለፉ ምእመናን በዕለተ ቅዳሜ በቅጽረ ቤተ ክርስቲያን ይሰበሰባሉ፡፡ የጠዋቱ ጸሎት ሲፈጸምም ካህናቱ ‹‹ገብረ ሰላመ በመስቀሉ፤ በመስቀሉ ሰላምን መሠረተ›› እያሉ በቤተ ክርስቲያን ለተሰበሰቡ ምእመናን የምሥራች ቄጠማ ያድላሉ፡፡

ቄጠማው የምሥራች ምልክት ነው፡፡ ቄጠማው የምሥራች ምልክት ተደርጐ የተወሰደው በኖኅ ዘመን ከተፈጸመው ታሪክ ጋር በማቆራኘት ነው፡፡ ቅዱስ መጽሐፍ እንደሚነግረን በጻድቁ ኖኅ ዘመን የነበሩ ሕዝቦች ከሕገ እግዚአብሔር ውጪ ኾነው እጅግ የሚያሳዝን ኃጢአት በሠሩ ጊዜ በንፍር ውኃ ተጥለቅልቀዋል፡፡ በወቅቱ ጻድቁ ኖኅ ወደ መርከብ ይዞአቸው ከገባው እንስሳት መካከል የውኃውን መጉደል ለመረዳት ርግብን በመርከብ መስኮት አሾልኮ ይለቃታል፤ እርሷም ቄጠማ በአፍዋ ይዛ ትመልሳለች፡፡ ኖኅም በዚህ ቄጠማ የውኃውን መድረቅ ተረድቶ ተደስቷል (ዘፍ. ፱፥፩-፳፱)፡፡

ቄጠማ ለጥፋት ውኃ መድረቅ የምሥራች መንገሪያ እንደ ኾነ ዅሉ፣ አሁንም ‹‹በክርስቶስ ሞት ሞተ ነፍስ ከሰው ልጆች ተወገደ፤›› ስትል ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ለልጆቿ ቄጠማ ታድላለች፡፡ ምእመናንም የምሥራች ተምሳሌት የኾነውን ቄጠማ በግንባራቸው ያስሩታል፡፡ የክርስቶስ ተከታዮች ዅሉ ከጨለማ ወደ ብርሃን፤ ከዋዕየ ሲኦል (የሲኦል ቃጠሎ) ወደ ጥንተ ማኅደራቸው ገነት መመለሳቸውን በዚህ አኳኋን እየገለጡ በዓለ ትንሣኤን በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ያከብራሉ፡፡

 ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

የእመቤታችን ኀዘን ስለ ጌታችን መከራ

መጋቢት ፳፰ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

… ለእኔስ በተሰቀለው ላይ ልቅሶ አለኝ፤ ‹‹በመስቀል ላይ ሞትህን?›› እላለሁ፡፡ የመስቀልህ ጥላ ሙታንን ሲያስነሣም ዐውቃለሁ፤ በመስቀል ላይ ዘንበል ማለትህን አደንቃለሁ፡፡ የሲኦልን መታወክ፣ በውስጧ ያሉ ሰባት መቶ የብረት በሮች እንደ ተሰበሩ አስታውሳለሁ፡፡ በዚያ ታስረው የነበሩትንም ከአባታቸው ከአዳም ጋር አወጣሃቸው፡፡ በዚያች ዕለትም ወደ ርስታቸው ወደ ገነት አስገባሃቸው፡፡ ነፍስህ ከሥጋህ በተለየች ጊዜም አለቅስሁ፡፡ በቀኝ ተሰቅሎ ለነበረው ወንበዴ አምስት ሺሕ አምስት መቶ ሠላሳ ሦስት ዘመን ተዘግታ የኖረች ገነትን በከፈትህ ጊዜም ተደሰትሁ፡፡

በዕንጨት መስቀል በሰቀሉህ ጊዜ ላልቅስ? ወይስ ፀሐይ በጨለመ ጊዜ ልደንግጥ? በመስቀል ላይ ራቁትህን ኾነህ በተመለከትሁህ ጊዜ ላልቅስን? ወይስ ቀኑ ሌሊት በኾነ ጊዜ ልደነቅ? ‹‹ክርስቶስ ሆይ! ማን መታህ? ንገረን!›› እያሉ በመቱህ ጊዜ ላልቅስን? ወይስ ‹‹ቅዱስ እግዚአብሔር ቅዱስ ኃያል ቅዱስ ሕያው የማይሞት፤ በመስቀል የተሰቀለ›› እያሉ ለማመስገን እልፍ አእላፍ ፍጥረታት ሲወድቁልህ ልደሰት? መጣጣዉን ከሐሞት ጋር ቀላቅለው ባጠጡህ ጊዜ ላልቅስን? ወይስ አምላካዊ የኾነች ደም፣ ከመስቀሉ ታችም ንጹሕ ውኃ በፈሰሰ ጊዜ?

የመለኮት ደም ዐለቱን ሰንጥቆ የአባታችን የአዳምን መቃብር አልፎ በአዳም አፍ ስለ መግባቱ ስለ ማዳኑም አደንቃለሁ፡፡ ስለዚህም ወንጌላዊው ‹‹ዐለቱ ተሰነጠቀ፤ የጻድቃን በድኖች ተነሡ፤›› አለ (ማቴ. ፳፯፥፶፩-፶፬)፡፡ በፊትህ ምራቅ በተፉብህ ጊዜ ላልቅስ? ወይስ ዕውር ኾኖ የተወለደዉን በማዳንህ ልደሰት? በአንገትህ ሐብል ባደረጉብህ ጊዜ ላልቅስን? ወይስ ሰይጣን ያሰራቸዉን ስትፈታቸው ላመስግንህ? ታስረህ በጲላጦስ ፊት ሲያቆሙህ ላልቅስን? ወይስ በባሕሩ እንደ የብስ ሔደህ ነፋሳትን እንደ ሎሌ በመገሠፅህ ላድንቅ? ወይስ ነቢያት አንተን ለማየት በመመኘታቸው ልደሰት?

ዛሬ በሁለት ወንበዴዎች መካከል ባየሁህ ጊዜ ላልቅስን? ከሌቦች፣ ከወንበዴዎች፣ ዓለሙን ዂሉ ካስለቀሱት ጋር በመስቀል በሰቀሉህ፣ በቸነከሩህ ጊዜ ላልቅስን? ወይስ በሙሴና በኤልያስ መካከል የመንግሥትህ ግርማ በታወቀ፤ የመለኮትህ ብርሃን ባንጸባረቀ ጊዜ ልደሰት? በቀራንዮ መስቀልን በተሸከምህ ጊዜ ላልቅስን? ወይስ መጻጕዕን ‹‹ኀጢአትህ ተሰረየልህ፤ ተነሥና አልጋህን ተሸከም፤ ሔደህም ወደ ቤት ግባ፤›› (ዮሐ. ፭፥፰) በማለትህ ልደሰት? ሐና እና ቀያፋ ‹‹ደሙ በእኛና በልጆቻችን ይኹን›› ባሉህ ጊዜ ላልቅስን? ወይስ ዐሥራ ሁለት ዓመት ደም ሲፈሳት የነበረችዉን ሴት በልብስህ ጫፍ በማዳንህ ልደሰት? በይሁዳ አማካይነት በሠላሳ ብር በመሸጥህ ላልቅስን? ወይስ ከዓሣ ሆድ ዲናር ያወጣ ዘንድ፣ በአንተ እንዳያጕረመርሙም ለቄሣር ግብር ይሰጥ ዘንድ ጴጥሮስን ባዘዝኸው ጊዜ ልደሰት?

በመስቀል ላይ ሳለህ ‹‹ተጠማሁ›› (ዮሐ. ፲፱፥፳፰) ስትል ላልቅስን? ወይስ በቃና ዘገሊላ ውኃዉን ወይን በማድረግህ ልደሰት? እናትህ እኔ በጉባኤው መካከል የፊቴን መሸፈኛ ገልጬ ስመለከት፣ ዮሐንስ ‹‹ልጅሽ ሞተ›› ባለኝ ጊዜ ላልቅስን? ወይስ ገብርኤል ‹‹ከአንቺ የሚወለደው የእግዚአብሔር ቃል በግብረ መንፈስ ቅዱስ ነው፤ ለመንግሥቱም ፍጻሜ የለውም፤›› (ሉቃ. ፩፥፴-፴፫) እያለ በነገረኝ ጊዜ ልደሰት? ዮሴፍና ኒቆዲሞስ ሥጋህን ለመገነዝ ሽቱ ሲገዙ ባየኋቸው ጊዜ ላልቅስን? ወይስ ምድራዊ ሳሙና እንደዚያ አድርጎ ማጽዳት የማይቻለው ፀዓዳ የኾነ የመንግሥት ልብስህን ባየሁ ጊዜ ልደሰት?

ሥጋህን ለመቅበር አዲስ መቃብር በፈለጉ ጊዜ ላልቅስን? ወይስ ከአራት ቀናት በኋላ አልዓዛርን ከመቃብር ባስነሣኸው ጊዜ (ዮሐ. ፲፩፥፵፫-፵፬) ልደሰት? በአፍህ መራራ ሐሞትን በጨመሩብህ ጊዜ ላልቅስን? ወይስ ከሴቶችና ከሕፃናቱ ሌላ በአምስት እንጀራ ለአምስት ሺሕ ሕዝብ በማጥግብህ፣ ተርፎም ዐሥራ ሁለት ቅርጫት በመነሣቱ (ማቴ. ፲፭፥፲፯-፳፩) ልደሰት? በመቃብርህ ላይ ድንጋይ በገጠሙበት ጊዜ ላልቅስን? ወይስ በአህያና ላም ባሟሟቁህ ጊዜ ላድንቅ? በሙታን መካከል በተኛህ ጊዜ ላልቅስን? ወይስ በጦር የወጋህን ሰው የታወረ ዓይኑን በመዳሰስ ባዳንኸው ጊዜ ልደሰት?

በመስቀል በምትጨነቅበት ጊዜ ላልቅስን? ወይስ ወንበዴዉን ‹‹ዛሬ እውነት እልሃለሁ፤ ከእኔ ጋር በገነት ትኖራለህ፡፡ ፈጽመህ እመን፤›› (ሉቃ. ፳፫፥፵፫) ባልኸው ጊዜ ልደሰት? የተረገሙ አይሁድን ምን እንላቸዋለን? በዮርዳኖስ ውኃ ዓለሙን የሸፈነዉን ራቀቱን ሰቅለውታልና፡፡ ዓለምን ከኀጢአት ሞት ያዳነ እርሱን ገድለውታልና፡፡

ምንጭ፡- ርቱዐ ሃይማኖት፣ መ/ር ተስፋ ሚካኤል ታከለ፤ ፳፻፬ ዓ.ም፣ አዲስ አበባ፤ ገጽ 211-214)፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

በጸሎተ ሐሙስ የሚፈጸም ሥርዓት

መጋቢት ፳፯ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

በዚህ ዕለት ስግደቱ፣ ጸሎቱ፣ ምንባቡ እንደ ተለመደው ይከናወናል፡፡ መንበሩ (ታቦቱ) ጥቁር ልብስ ይለብሳል፡፡ ጸሎተ ዕጣን ይጸለያል፤ ቤተ ክርስቲያኑም በማዕጠንት ይታጠናል፡፡ ኅፅበተ እግር ይደረጋል፡፡ ቅዳሴ ይቀደሳል፡፡ በየቤቱ ደግሞ ጉልባን ይዘጋጃል፡፡

ኅፅበተ እግር

ከቀኑ በዘጠኝ ሰዓት ዲያቆኑ ሁለት ኵስኵስቶችን ውኃ ሞልቶ ያቀርባል፤ አንዱ ለእግር፣ አንዱ ለእጅ መታጠቢያ፡፡ ‹ጸሎተ አኰቴት› በመባል የሚታወቀው የጸሎት ዓይነት ይጸለያል፡፡ ወንጌል ተነቦ ውኃው በካህኑ (በሊቀ ጳጳሱ) ይባረክና የኅፅበተ እግር ሥርዓት ይከናወናል፡፡ ይኸውም ጌታችን የደቀ መዛሙርቱን እግር በማጠብ ያሳየውን የተግባር ትምህርት ለማሳየት ነው (ዮሐ. ፲፫፥፲፬)፡፡ ከውኃው በተጨማሪ የወይራና የወይን ቅጠልንም ለሥርዓተ ኅፅበቱ ማስፈጸሚያነት እንጠቀምባቸዋለን፡፡ ምሥጢሩም የሚከተለው ነው፤

ወይራ ጸኑዕ ነው፡፡ ይህም ክርስቶስም ጽኑዕ መከራ መቀበሉን ከማስረዳቱ ባሻገር እኛም (እግራችንን የሚያጥቡን አባቶች እና የምንታጠበው ምእመናን) መከራ ለመቀበል ዝግጁ ነን ለማለት ሥርዓተ ኅፅበቱን በወይራ እንፈጽማለን፡፡ የወይኑ ቅጠልም መድኃኒታችን ክርስቶስ በወይን የተመሰለ ደሙን አፍስሶ ለምእመናን የሕይወት መጠጥ አድርጎ መስጠቱን ለማዘከር በወይን ሥርዓተ ኅፅበትን እናከናውናለን (ማቴ. ፳፮፥፳፮)፡፡ በቀኝና በግራ የቆሙ ሊቃውንትም ‹‹ሐዋርያቲሁ ከበበ እግረ አርዳኢሁ ኀፀበ›› እያሉ ይዘምራሉ፡፡ ይህ ሥርዓት ከተጠናቀቀ በኋላ ምእመናን ሥርዓተ ቅዳሴው ተከናውኖ ቅዱስ ሥጋውን ክቡር ደሙን ይቀበላሉ፡፡

 ቅዳሴ

የጸሎተ ሐሙስ ቅዳሴ የሚከናወነው በተመጠነ ድምፅ ሲኾን፣ እንደ ደወል (ቃጭል) የምንጠቀመውም ጸናጽልን ነው፡፡ ልዑካኑ የድምፅ ማጉያ ሳይጠቀሙ በለኆሣሥ (በቀስታ) ይቀድሳሉ፡፡ ምክንያቱም ይሁዳ በምሥጢር ጌታችንን ማስያዙን ለማመልከት ሲኾን፣ በሌላ በኩል ደግሞ የዘመነ ብሉይ ጸሎት ዋጋው ምድራዊ እንደ ነበር ለማስታወስ ነው፡፡ በመቀጠል ክብር ይእቲ፣ ዕጣነ ሞገር፣ ዝማሬ የተባሉ የድጓ ክፍሎች ተዘምረው አገልግሎቱ ይጠናቀቃል፡፡ ሕዝቡም ያለ ኑዛዜና ቡራኬ ይሰናበታሉ፡፡

ጉልባን

ጉልባን ከባቄላ ክክ፣ ከስንዴ ወይንም ከተፈተገ ገብስ ጋር አንድ ላይ ተቀቅሎ የሚዘጋጅና የጸሎተ ሐሙስ ዕለት የሚበላ ንፍሮ ነው፡፡ በጸሎተ ሐሙስ በቤት ውስጥ ከሚፈጸሙ ተግባራት አንዱ ጉልባን ማዘጋጀት ነው፡፡ ጉልባን እስራኤላውያን ከግብጽ ባርነት ሲወጡ በችኮላ መጓዛቸውን የምናስታውስበት ከእስራኤላውያን የመጣ ትውፊታዊ ሥርዓት ነው፡፡ በአገራችን ኢትዮጵያ አብዛኞቹ የትውፊት ክንዋኔዎች የብሉይ ኪዳን መነሻ ስላላቸው ይህ ሥርዓት ዛሬም በኢትዮጵያውያን ምእመናን ዘንድ ይከበራል፡፡

ጉልባን እስራኤላውያን ከባርነት በወጡ ጊዜ አቡክተው፣ ጋግረው መብላት አለመቻላቸውን ያስታውሰናል፡፡ በወቅቱ ያልቦካውን ሊጥ እየጋገሩ ቂጣ መመገብ፤ ንፍሮ ቀቅለው ስንቅ መያዝ የመንገድ ተግባራቸው ነበርና፡፡ ይህን ታሪክ ለማሰብም በሰሙነ ሕማማት በተለይም በጸሎተ ሐሙስ ቂጣና ጉልባን ይዘጋጃል፡፡ በጸሎተ ሐሙስ የሚዘጋጀው ጉልባንና ቂጣ ጨው በዛ ተደርጎ ይጨመርበታል፡፡ ይኸውም ጨው ውኃ እንደሚያስጠማ ዅሉ፣ ጌታችንም በመከራው ወቅት ውኃ መጠማቱን ለማስታወስ ነው፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡