የጌታችን መከራ በሊቃውንት አንደበት

መጋቢት ፳፯ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም 

‹‹ታመመ፤ ሞትን ከተቀበለበት ከሥጋ ተዋሕዶ በመስቀል ላይ በፈቃዱ ለሥጋውያን ሞተ፣ ባሕርየ መለኮት ሥጋን ተዋሕዶ በማኅፀን ካደረ ጀምሮ ሥጋ ገንዘቡ እንደመሆኑ በሥጋ ይኸንን ሥርዓት ፈጸመ፡፡ ለማይመረመር ለመለኮቱ ባሕርይ እንደሚገባ ደግሞ እርሱ ኅብስት አበርክቶ ዂሉን ያጠግባል፡፡ አይራብም፤ አይጠማም፤ አይደክምም፤ አያንቀላፋም፤ አይታመምም፤ አይሞትም፤ ሕይወትን ለዂሉ ይሰጣል፡፡ ዳግመኛ በዚያ በሲኦል ተገዝተው ያሉ ነፍሳትን ያድን ዘንድ በአካለ ነፍስ ወደ ሲኦል ወረደ፤ በመለኮቱም ሲኦልን በዘበዘ፤›› (የእስክንድርያው ሊቀ ጳጳሳት ቅዱስ ቄርሎስ)፡፡

‹‹እጆቹን፤ እግሮቹን በተቸነከረባቸው ችንካሮች መወጋቱንም እናምናለን፡፡ ነቢዩ ኢሳይያስእርሱ ደዌያችንን ወሰደሕማማችንንም ተሸከመ፤ እኛን ለማዳን ኃጢአታችንንም ለማስተስረይ መከራ ተቀበለእንዳለ፤ በባሕርዩ ሕማም የሌለበት ሲኾን በሥጋ የታመመ ነው፡፡ በእርሱ ከመከራ ሥጋ ከመከራ ነፍስ ድነናል፡፡ በተገረፈና በተቸነከረም ጊዜ በመከራው መለኮትን ሕማም ተሰማው የሚል ሰው ቢኖር የተለየ የተወገዘ ይሁን፤›› (ሊቀ ጳጳስ ቅዱስ ጎርጎርዮስ)፡፡

‹‹እርሱ መቼም መች ከመለኮቱ ሳይለይ የሰውነትን ሥራ ገንዘቡ አደረገ፡፡ ይኸውም መራብ፣ መጠማት፣ መንገድ በመሔድ መድከም፣ በመስቀል ላይ መሰቀል፣ በብረት ችንካር መቸንከር ነው፡፡ በሰውነቱ መቸም መች ሰው ነው፤ በአምላክነቱም ሰውን የፈጠረ ነው፡፡ ነገር ግን ከማይከፈል ተዋሕዶ በኋላ መከፈል የለበትም፡፡ ሰው እንደ መኾኑ ስለ እኛ የታመመው፣ የሞተው እርሱ ነው፡፡ በመለኮቱ ግን መቸም መች አይታመምም፤ አይሞትም፡፡ ሕማምንና ሞትንም አይቀበልም፡፡ በሞቱ ሞትን ያጠፋው እርሱ ነው፡፡ ሲኦልንም የበዘበዘው እርሱ ነው፤›› (የአንጾኪያው ሊቀ ጳጳስ ቅዱስ ዲዮናስዮስ)፡፡

‹‹ነፍሱን ከሥጋው በለየ ጊዜ ያን ጊዜ በሲኦል ፈጥኖ ብርሃን ታየ፡፡ ጌታችን በአካለ ሥጋ ያይደለ በአካለ ነፍስ ወደ ሲኦል ሔደ፡፡ ሲኦል ተነዋወጠች፤ መሠረቶቿም እፈርስ እፈርስ አሉ፡፡ ምድርን ያለ ጊዜዋ እንዳታልፍ ክብርት ደሙን በምድር ላይ አፈሰሰ፡፡ ከኅልፈት ጠበቃት በእርሷ ያለውንም ዂሉ ጠበቀ፡፡ ስለ ፍጥረት ሥጋውን በመስቀል እንደ ተሰቀለ ተወው፡፡ ነፍሱ ግን ወደ ሲኦል ወረደች ከዚያ ተግዘው የነበሩ ነፍሳትን አዳነች፤ ሲኦልንም በዘበዘች፡፡ ፍጥረትንም ዂሉ ገንዘብ አደረገች፡፡ ሥጋውም በመቃብር ያሉ ሙታንን አስነሣ፤ ነፍሱም በሲኦል ተግዘው የነበሩ ነፍሳትን ፈታች፤›› (የእስክንድርያው ሊቀ ጳጳስ ሐዋርያው ቅዱስ አትናቴዎስ)፡፡

‹‹ከብርሃን የተገኘ ብርሃን፣ ከባሕርይ አምላክ የተገኘ የባሕርይ አምላክ፣ የተወለደ እንጂ ያልተፈጠረ፣ በባሕርዩ ከአባቱ ጋር አንድ የሚኾን፡፡ ዂሉ የተፈጠረበት፤ ያለ እርሱ ግን ምንም ምን የተፈጠረ የሌለ፤ በሰማይ በምድር ያለውም ቢኾን፡፡ እኛን ስለ ማዳን ከሰማየ ሰማያት ወርዶ በግብረ መንፈስ ቅዱስ ከቅድስት ድንግል ማርያም ፍጹም ሰው ኾነ፡፡ የሠላሳ ዘመንልማሳ ኾኖ በጲላጦስ የሹመት ዘመን ስለ እኛ ተሰቀለ፤ ስለ እኛም ታመመ፤ ሞተ፤ ተቀበረ፤›› (ሠለስቱ ምእት)፡፡

‹‹ምትሐት ያይደለ በእውነት ተራበ፤ ተጠማ፡፡ ዳግመኛም ከኃጥአን፣ ከመጸብሐን ጋር በላ፤ ጠጣ፡፡ ያቀረቡለትንም በላ፡፡ ራሱን አሳልፎ ለመስቀል ሰጠ፡፡ እጁን፣ እግሩን ተቸነከረ፤ ጐኑን በጦር ተወጋ፡፡ ከእርሱም ቅዱስ ምሥጢር የተገለጠበት ደምና ውኃ ፈሰሰ (ወጣ)›› (ቅዱስ ባስልዮስ ዘቂሣርያ)፡፡

‹‹የሚሠዋ በግ እርሱ ነው፤ የሚሠዋ ካህን እርሱ ነው፡፡ ከባሕርይ አባቱ ከአብ ከባሕርይ ሕይወቱ ከመንፈስ ቅዱስ ጋርም መሥዋዕት የሚቀበል እርሱ ነው፡፡ በፈቃዱ መከራን በሥጋው የተቀበለ መከራንም የታገሠ እርሱ ነው፡፡ እንደ በግ ሊሠዋ መጣ፤ በግ በሚሸልተው ሰው ፊት እንደማይናገር አልተናገረም፡፡ በአንደበቱ ሐሰት አልተገኘበትም፤›› (ቅዱስ ጎርጎርዮስ ዘኑሲስ)፡፡

‹‹በሥጋ መወለድ፣ በመስቀል መከራ መቀበል፣ መሞት፣ መነሣት፣ ገንዘቡ የኾነ እርሱ እግዚአብሔር ቃል ነው፡፡ ስለዚህ በመስቀል ላይ ሳለ ከጥንት ጀምሮ በመቃብር ያሉ ሙታንን አስነሣ፤›› (ሰማዕቱ ሊቀ ጳጳስ ቅዱስ ፊልክስ)፡፡

‹‹ሙሴም ሞትን ያጠፋ ዘንድ አልቻለም፤ እርሱንም ይዞ ገዛው እንጂ፡፡ ከእርሱም በኋላ የተነሡ ነቢያትንም ሞት ገዛቸው እንጂ፡፡ ክርስቶስ ግን በቸርነቱ ለዂሉ ሕይወትን ሰጠ፤›› (የሮማ ኤጲስ ቆጶስ ቅዱስ አቡሊዲስ)፡፡

‹‹በመስቀል በሥጋ ተሰቅሎ ሳለ ለመለኮት ከሥጋ መለየት የለበትም፡፡ አንዲት ሰዓትም ቢሆን የዐይን ጥቅሻ ያህል ስንኳ ቢሆንም መለኮት ከትስብእት አልተለየም፣ በመቃብር ውስጥ በሰላም መለኮት ከትስብእት አልተለየም (የሮሜ ሊቀ ጳጳሳት ቅዱስ አዮክንድዮስ)፡፡

‹‹ከአብ ጋር አንድ እንደ መኾንህ ሞት የሌለብህ አንተ ነህ፡፡ ከእኛ ጋር አንድ እንደ መኾንህ በፈቃድህ የሞትህ አንተ ነህ፡፡ በመቃብር ያደርህ አንተ ነህ፡፡ በኪሩቤል ላይ ያለህ አንተ ነህ፡፡ ከሙታን ጋር በመቃብር የነበርህ አንተ ነህ፡፡ በአንተ ሕማምና ሞትም ድኅነት ተሰጠ፡፡ ከሙታን ጋር የተቈጠርህ አንተ ነህ፡፡ ለሙታንም ትንሣኤን የምትሰጥ አንተ ነህ፡፡ ሦስት መዓልት ሦስት ሌሊት በመቃብር ያደርህ አንተ ነህ፡፡ በዘመኑ ዂሉ ከአብ ከመንፈስ ቅዱስ ጋር የምትኖር አንተ ነህ፡፡ በመለኮት ሕማም ሳይኖርብህ በሥጋ የታመምህ አካላዊ የእግዚአብሔር ቃል አንተ ነህ፤›› (የኪስኪስ ኤጲስ ቆጶስ ቅዱስ ኤራቅሊስ)፡፡

‹‹ኃጢአታችንን ለማሥተስረይ በሥጋ እንዲህ ታመመ፤ እንደ ሞተ ከነፍሱም በተለየ ጊዜ ሥጋውን እንደ ገነዙ እናምናለን፤›› (የኢየሩሳሌም ኤጲስ ቆጶስ ቅዱስ ዮሐንስ እንዲህ አለ)፡፡

‹‹ነቢይ ዳዊትነፍሴን በሲኦል አትተዋትም፤ የባሕርይ ልጅህንም ሙስና መቃብርን ያይ ዘንድ አሳልፈህ አትሰጠውም› አለ፡፡ ይህም ጌታ በተዋሐደው አካል ያለውን የነፍስና የሥጋ ተዋሕዶ ያስረዳል፡፡ የቀና ልቡና ዕውቀት በእርሱ ጸንቶ ይኖር ዘንድ፡፡ ዳዊት እንደ ተናገረው እውነት ኾነ፤ ነፍስ መለኮትን ተዋሕዳ ወደ ሲኦል ወርዳለችና፡፡ ሥጋም ሦስት መዓልት ሦስት ሌሊት በመቃብር ሳለ መለኮት ከሥጋ አልተለየም፤ አምላክ ሰው የመኾኑን እውነት ያስረዳ ዘንድ፡፡ መለኮት ነፍስን ተዋሕዶ በአካለ ነፍስ የሲኦል ምሥጢርን ገልጦ ፈጽሟልና በሲኦልም በቁራኝነት አልተያዘምና፤›› (የቆጵሮስ ደሴት ኤጲስ ቆጶስ ቅዱስ ኤጲፋንዮስ)፡፡ 

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ምንጭ፡- ስምዐ ተዋሕዶ፣ ሚያዝያ ፩ -፲፭ ቀን ፳፻፯ .ም፡፡

ዕቅበተ እምነት በመጽሐፈ ምሥጢር – የመጨረሻ ክፍል

የካቲት ፴ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

፬. ነገረ ማርያም

፬.፩ አንጢዲቆማርያጦስ

እነዚህ መናፍቃን “አፅራረ ማርያም (የማርያም ጠላቶች)” ይባላሉ፡፡ መድኃኒታችንን ከወለደች በኋላ ከዮሴፍ ጋር በባልና ሚስት ልማድ ኖረች በማለት በእመቤታችን በቅድስት ድንግል ማርያም ላይ የጽርፈት ቃል የሚናገሩ መናፍቃን ናቸው፡፡ ለኑፋቄያቸው መነሻ ያደረጉት የበኵር ልጇን እስከምትወልድ ድረስ አላወቃትም የሚለው ንባብ ነው፡፡ አባ ጊዮርጊስም ይህ ንባብ እንዴት እንደሚፈታና እንዴት እንደሚተረጎም በማመሥጠር ለእነዚህ ዝንጉዓን መልስ ይሰጣቸዋል፡፡ ስለ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ንጽሕና፣ ቅድስናና ዘለዓለማዊ ድንግልና ቅዱሳት መጻሕፍትን በመጥቀስ ከተከራከራቸው በኋላ የመለኮትን አዳራሽ ሊቀርባት የሚችል የትኛው ሥጋዊ ነው? ምን ሰው ወደ መለኮት አዳራሽ ሊገባ ይችላል? በማለት ያሳፍራቸዋል፡፡ እኛ ግንድንግል ማርያምን የአምላክ እናት ናት፤ ከወለደችውም በኋላ ዘለዓለማዊት ድንግል ናት› እንላለን ይላል፡፡

፬.፪ “እመቤታችን በሩካቤ አልተወለደችም” ለሚሉ

አባ ጊዮርጊስ ለእነዚህ መናፍቃን መልስ ሲሰጥ “… መልአኩእነሆ ትፀንሻለሽ፤ ወልድንም ትወልጃለሽብሎ የምሥራች በነገራት ጊዜወንድ ስለማላውቅ ይህ እንዴት ይሆንልኛል?› ብላ ያደነቀች እርሷን እንደምንበሩካቤ አልተወለደችምይሏታል? እናቷ እርሷን ያለ ሩካቤ ፀንሳት ቢሆን ኖሮ ድንግልወንድ ስለማላውቅ ይህ እንደምን ሆንልኛል?› ባላለች ነበር! በማለት አባቷ ኢያቄም እናቷም ሐና መሆኗን በመጥቀስ ያሳፍራቸዋል፡፡

፬.፫ ድንግል ማርያምና መስቀልን ለሚያበላልጡ

ሊቁ እነዚህን ስለ ማርያምና ስለመስቀል እንደሚክዱ በጆሯችን የገባ ወሬ አለ፡፡ እኩሌቶቹ የወለደችው ማርያም ከመስቀሉ ትበልጣለች ይላሉ፤ እኩሌቶቹም በሕማማቱ ደም የተቀደሰ መስቀል ይበልጣል ይላሉ፡፡ እኛ ግን ማርያም አምላክን የወለደች እንደሆነች እናምናለን፡፡ መስቀሉም መለኮት በተዋሐደው የትስብእት ደም የተቀደሰ የብርሃን ማዕተብ መሆኑን እናምናለን በማለት ይመልስላቸዋል፡፡ አባ ጊዮርጊስ ከእነዚህም በተጨማሪ የቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮ ለማጣመም ለሚሞክሩ ሌሎች ስሑታንም መልስ ሰጥቷል፡፡ የተወሰኑትን ለመጥቀስ ያህል፡-

  • “ወደ ቤተ ክርስቲያን ኃይል አይወርድም፣ ኅብስቱም ወደ ክርስቶስ ሥጋነት፣ ወይኑም ደሙን ወደ መሆን አይለወጥም ለሚሉ ሊቁ ሲመልስ “‹ሰማየ ሰማያት የማይወስነው እግዚአብሔር አራት ጎኖቿ ባነሱ በሰው እጅ በተሠራች ቤተ ክርስቲያን ውስጥ እንዴት ያድራል?› የሚሉ አሉ፡፡ እኛ ግንበጽርሐ አርያም ያለ አኗኗሩ ሳይጎድል ይቀድሳት ዘንድ የመለኮት ኃይል በቤተ ክርስቲያን ያድራል› እንላለንይላል፡፡ በተጨማሪም “… ከከሐዲዎች መነሣሣት የተነሣ እንዳትነዋወጥ ኃይል ቤተ ክርስቲያንን ይጠብቃታል፡፡ የሚጠብቃት እርሱ ሲሆን ኃይልን ትሸከመዋለች፤ ኃይል ትጎናጸፋለች፤ ኃይልም ትታጠቃለች፤ ኃይላትም ይከቧታል፤ የሠራዊት ጌታ ሠረገላ አድርጓታልና በማለት ይመልስላቸዋል፡፡
  • ስለ ሥጋ ወደሙም “‹ኅብስቱ የክርስቶስን ሥጋ፣ ወይኑም ደሙን መሆን ይችላልን?የሚሉ አሉ፡፡ በመንፈስ ቅዱስ በተቀደሰ ጊዜ ኅብስት ከልማዳዊ ኅብስትነት ሥጋውን ወደ መሆን ይለወጣል፤ ወይንም ከልማዳዊ ወይንነት ደሙን ወደ መሆን ይለወጣል በማለት ምሥጢረ ቍርባንን ያብራራል፡፡ ለድንግል የእግዚአብሔር ልጅ በመንፈስ ቅዱስ መምጣት ልጅ ሆናት፤ እርሷም በልዑል ኃይል እናት ሆነችው፡፡ መንፈስ ቅዱስ ወደ እርሷ ባይመጣ፣ የልዑል ኃይልም ባይጋርዳት የልዑልን ልጅ ትሸከመው ዘንድ ባልተቻላት ነበር፡፡ ኅብስቱና ወይኑም እንዲሁ ካህኑ አቤቱ የጌታችን የመድኀኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስን ሥጋና ደም እንዲያደርገውበዚህ ኅብስትና ጽዋ ላይ ቅዱሱን ኃይል ትልክ ዘንድ እንለምንሃለን፤ እንማልድሃለንባለ ጊዜ በመንፈስ ቅዱስ መውረድ ሥጋና ደም ይሆናል በማለት ይመልሳል፡፡
  • ስለ ምሥጢረ ሥጋዌም የሚከተለውን ትምህርት ያስተምራል፤በማርያም ማኅፀን ፍጹም የሕይወት እንጀራ ተፀነሰ፡፡ ይኸውም ለተቀደሰች ምሥጢር የበረከት ፍሬ ሆኖ የተሰጠ ከአብርሃም ዘር የተገኘ ሥጋ ነው፡፡ ከባሕርይዋ ደምም በመንፈስ ቅዱስ መጐብኘት የወይን ፍሬ አፈራ፡፡ በአብም በመጋረዱ ኃይል የሚናገር የወይን ደም የመለኮትም ሥጋ ኅብስት ተፀነሰ፡፡ ስለዚህም መድኃኒታችንከሰማያት የወረደ የሕይወት እንጀራ እኔ ነኝ፤ ሥጋዬን የበላ የእኔን ሥጋ ስለበላ በሕይወት ይኖራል፤ ደሜንም የጠጣ ሞትን አይቀምስም› አለ፡፡ ዳግመኛምአብ ሕያው እንደሆነ እኔም የአብ ልጅ ስለሆንሁ ሕያው ነኝሥጋዬንም የበላ የእኔን ሥጋ ስለበላ በሕይወት ይኖራል› አለ፡፡ እንዲህ ያለውን ጸጋ አቃልለን እንደምን እንድናለን? እኛ ግን በመንበሩ ላይ ሆኖ በካህኑ እጆች የሚከብረው ኅብስትና ወይኑ ፍጹም የክርስቶስ ሥጋና ደም እንደሆነ እናምናለን፡፡

፬.፬ ሰዱቃውያን

ሰዱቃውያን ትንሣኤ ሙታን የለም የሚሉ መናፍቃን ናቸው፡፡ ሊቁ ጌታችን በሥጋዌው ወራት በትንሣኤስ እንደ እግዚአብሔር መላእክት በሰማይ ይሆናሉ እንጂ አያገቡም አይጋቡምም በማለት የመለሰላቸውን እየጠቀሰ መልስ ይሰጣቸዋል (ማቴ. ፳፪፡፴)፡፡

  • ነፍስ ከሥጋ ጋር ትሞታለች” ለሚለው፡- ይህ መናፍቅ ነፍስ ከሥጋ ጋር ትሞታለች፤ ሙታን በተነሡ ጊዜ ከሥጋ ጋር ትነሣለች የሚል ኑፋቄ ያስተማረ መናፍቅ ነው፡፡ ሊቁም ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በማቴዎስ ወንጌል ላይ ሥጋንም የሚገድሉትን ነፍስን ግን መግደል የማይቻላቸውን አትፍሩ፤ ይልቅስ ነፍስንም ሥጋንም በገሃነም ሊያጠፋ የሚቻለውን ፍሩ በማለት የተናገረውን በመጥቀስ ነፍስ የማትሞት መሆኗን ይመልስለታል (ማቴ. ፲፡፳፰)፡፡ ነፍስ ከሥጋ ተለይታ በሲኦል ወይም በገነት እንደምትቆይ የአልዓዛርን ታሪክ ድሀውም ሞተ፤ መላእክትም ወደ አብርሃም እቅፍ ወሰዱት የሚለውን በመጥቀስ ያሳፍረዋል (ሉቃ. ፲፮፡፳፪)፡፡
  • “… በዐርባ ቀን እግዚአብሔር በሕፃኑ ፊት ላይ የሕይወትን እስትንፋስ እፍ ይልበታል፤ በእግዚአብሔርም እጅ ይፈጠራልበማለት የተሳሳተ ትምህርት ለሚያስተምሩ ዝንጉዓን፡ ሊቁ እግዚአብሔር የሕይወት እስትንፋስን በአዳም ላይ እፍ እንዳለ በሔዋን ፊት ላይ ግን የሕይወትን እስትንፋስ እፍ እንዳላለ እይ፤ ሕፃን ከእግዚአብሔር አፍ የሕይወትን እስትንፋስ መቀበል የሚገባው ቢሆን ሔዋን ከፈጣሪዋ ከእግዚአብሔር አፍ ዳግመኛ የሕይወትን አስትንፋስ መቀበል በተገባት ነበር በማለት ትክክለኛው የቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ ሕፃን ልጅ ከአባቱና ከእናቱ ዘር የማትሞት ነፍስን ይቀበላል የሚለው እንደሆነ ገለጸልን፡፡
  • “ኦሪት፣ ነቢያትና ሰንበት ተሽረዋልለሚሉ፡- በወንጌል መምጣት ኦሪት እንደ ቀረች፣ በሐዋርያትም ስብከት የነቢያት ትንቢት እንደጠፋ፣ ሰንበትም ትንሣኤ በሆነባት እሑድ እንደተሻረች የሚናገሩ አሉ፡፡ እኛ ግንኦሪት በወንጌል ስብከት ከበረች፤ ነቢያትም በሐዋርያት ትምህርት ከፍ ክፍ አሉ፤ ዓለምን ከመፍጠር ያረፈባት ሰንበትም የዓለም አዳኝ በተነሣባት በሰንበተ ክርስቲያን ዘውድን ተቀዳጀች› እንላለንበማለት ይመልስላቸዋል፡፡
  • አዳምና ነቢያት በሲኦል አልነበሩም ለሚሉ፡- አባ ጊዮርጊስ እንዲህ የሚሉትን መናፍቃን ነቢያት የተናገሩትን በመጥቀስ እስከ ክርስቶስ መምጣት ድረስ በሲኦል ስለመኖራቸው፣ ገነትም ተዘግታ በምትገለባበጥ የእሳት ሰይፍ እየተጠበቀች መቆየቷን በመግለጽ ይገሥጻቸዋል፡፡
  • “ኤዶም ገነትና ሲኦል በሰማያት ናቸው” ለሚሉ፡- የተወሰኑት ኤዶም ገነት በሰማያት ናት፤ በምድር አይደለችም” ሲሉ፤ ሌሎቹ ደግሞ ሲኦል በሰማያት ናት” ይላሉ፡፡ አባ ጊዮርጊስ ገነትና ሲኦል ቁጥራቸው ከዓለመ ምድር እንጂ ከሰማያት እንዳልሆኑ ገነትን የሚያጠጡ ወንዞችን፣ አዳም ወደ ገነት እንዳይገባ በሱራፊ መጠበቋን ከቅዱሳት መጻሕፍት እየጠቀሰ መልስ ሰጥቷቸዋል፡፡

በአጠቃላይ አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ በመጽሐፈ ምሥጢር መጽሐፉ የመናፍቃንን ስሕተትና የስሕተታቸውን ምክንያት ነቅሶ በማውጣትና መጽሐፋዊ የሆነ መልስ በመስጠት መናፍቃንንና ስሑታንን ገሥጿል፡፡ የመጽሐፉ ዋና ትኩረት ምሥጢረ ሥላሴና ምሥጢረ ሥጋዌ ላይ ለተነሡ ኑፋቄዎች መልስ መስጠት ቢሆንም ሌሎችንም ጉዳዮች በማንሣት መልስ እንደ ሰጠ ከላይ ተመልክተናል፡፡ አዲስ መናፍቅ እንጂ አዲስ ኑፋቄ የለም እንደሚባለው በመጽሐፉ የተጠቀሱ መናፍቃን ትምህርቶች ዛሬም ድረስ በተለያዩ አካላት እንደ አዲስ ሲጠቀሱና ሲነገሩ እንሰማለን፡፡ በዘመናችን የተነሡ መናፍቃንና ግብረ አበሮቻቸው የሚያስተምሩትም ቤተ ክርስቲያን አውግዛ የለየችውና በየዘመናቱ የተነሡ ሊቃውንት መልስ የሰጡበት እንጂ አዲስ የተገለጠላቸው ትምህርት አለመሆኑን መረዳት ከክርስቲያኖች ይጠበቃል፡፡ ትምህርቷን ያልሰሙ አላዋቂዎች ዛሬም ቤተ ክርስቲያን ክርስቶስን እንደማትሰብክ አድርገው ይናገራሉ፡፡

ቤተ ክርስቲያን ክርስቶስን እንዴት እንደምትሰብከው በሚያስረዳው በሚከተለው የሊቁ ቃል ጽሑፋችንን እናጠቃልላን፤

ኢየሱስ ክርስቶስ የቅዱሳን ሁሉ ንጉሥ ነው፤ ኢየሱስ ክርስቶስ ለሚጠራው ስሙ የጣፈጠ፣ ኢየሱስ ክርስቶስ ለሚያዳምጠው ቃሉ የጣፈጠ፣ ኢየሱስ ክርስቶስ ለሚበላው ሥጋው የጣፈጠ፣ ኢየሱስ ክርስቶስ ለሚጠጣው ደሙ የጣፈጠ፣ ኢየሱስ ክርስቶስ ዜናውን ለሚነግር መታሰቢያው የጣፈጠ ነው፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ የእግዚአብሔር ልጅ የሰውም ልጅ ነው፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ በእግዚአብሔርና በሰዎች መካከል ያለ፣ ኢየሱስ ክርስቶስ እትራቶቹ ከእርሱ ጋር መስቀሉም በፊቱ ያለ፣ የአንድነታችን አለቃ፣ የትምህርታችን አስተማሪ፣ የእረኞቻችን አለቃ፣ የካህኖቻችን ሊቅ ነው፡፡ እርሱ ሰማያዊ ከሚሆን ከቸር አባቱና ሕይወትን ከሚሰጥ ከመንፈስ ቅዱስ ጋር እስከ ዘለዓለሙ ድረስ ከእኛ ጋር ይኑር፤ ለዘለዓለሙ አሜን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

የተወደዳችሁ የማኅበረ ቅዱሳም ድረ ገጽ ተከታታዮች! ይህ ትምህርት፣ ከጥር ፩ – ፲፭ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም በታተመው ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ፣ በንቁ ዓምድ ሥር ለንባብ መብቃቱን ለማስገንዘብ እንወዳለን፡፡

ዕቅበተ እምነት በመጽሐፈ ምሥጢር – ሦስተኛ ክፍል

የካቲት ፳፱ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

፪.፬ አርአያውን ወደ መስቀል አወጣ ለሚሉ መናፍቃን

ሥጋው የተቸነከረው በእውነት ካልሆነ ስለምን ከትንሣኤው በኋላ ቶማስንእጅህን አምጣና በመስቀል ችንካሮች የተጨነከሩትን እጆቼን ዳስስ፤ ጣቶችህንም አምጣወደ ጎኔም አስገባአለው በማለት ሊቁ ስንፍናቸውን ይገልጽባቸዋል፡፡ ከዚሁ ጋር አያይዞ አባ ጊዮርጊስ እግዚአብሔር አይወልድም አይወለድም ለሚሉ መናፍቃን እነዚህን በምን እንከራከራቸዋለን፤የኦሪት ሕግ አለንይሉናል፡፡ የኦሪታቸው ቃል ከእኛ ኦሪት ጋር፣ የነቢዮቻቸውም ቃል ከእኛ ነቢያት ጋር አይተባበርምና የአንደበታቸው ቃል ሁሉ ሐሰተኛ ነው፤ መንገዳቸውም ክፉ መንገድ ነው …” በማለት ክሕደታቸውን ይገልጽልናል፡፡

፪.፭ አርሲስ

“አርሲስ” በሃይማኖተ አበው እንደተጠቀሰው ስመ መናፍቃን ነው፡፡ አርሲስ በነፍስና በሥጋ ወደ ሲኦል ወረደ ብለው የሚናገሩ መናፍቃን ናቸው፡፡ ሊቁ እነዚህን መናፍቃን እስኪ እናንተ አስቀድማችሁ ንገሩን? የእግዚአብሔርን ልጅሞተ› ትሉታላችሁ? ወይስአልሞተምትላላችሁ?ብሎ ይጠይቃቸዋል፡፡ ሞተ” ካሉ “የነፍስ ከሥጋ መለየት በቀር ሞት ምንድን ነው?” አልሞተም” ካሉ ደግሞ ሞት ሳይኖር ትንሣኤ እንዴት ነው?” እያለ ይሞግታቸዋል፡፡ በትምህርታቸው ክርስቶስን የሚሞትና የማይሞት ሁለት ሥጋ ያለው እንዳስመሰሉት በመንገር ይነቅፋቸዋል፡፡ እኛ ግንመለኮታዊ ቃል ከብቻዋ ከነፍስ ጋር ወደ ሲኦል ወረደ፤ ሥጋን ግን ዮሴፍና ኒቆዲሞስ ከመስቀል ላይ አውርደዋት በከፈን ጠቅልለው ከመቃብር ውስጥ ጨመሯት፡፡ ሥጋም ያለ ነፍስ እስከ ትንሣኤው ዕለት ለብቻዋ ቆየች፡፡ መለኮት ግን ከነፍሱ እና ከሥጋው አልተለየም› እንላለን” በማለት መልስ ያሰጣቸዋል፡፡

፪.፮ ፎጢኖስ

በሰርቢያ ግዛት ትገኝ በነበረች የሰርሚየም ሊቀ ጳጳስ የነበረው ፎጢኖስ ለፌ እማርያም ክዋኔሁ (ህላዌሁ) ለወልድየወልድ ህልውና ከማርያም ከተወለደ በኋላ ነው የሚል ኑፋቄ ያስተማረ መናፍቅ ነው፡፡ ሊቁ አባ ጊዮርጊስም እኛ ግንህልውናው ከዘመናትና ከጊዜ፣ ከዕለታትና ከሰዓት አስቀድሞ ነው፣ በኋለኛው ዘመን ስለ እኛ ድኅነት ያለ ዘርዐ ብእሲ ከቅድስት ድንግል ማርያም ሰው ሆነ (በሥጋ ተገለጠ)› እንላለን በማለት ቅዱሳት መጻሕፍትን እያመሠጠረ መልስ ሰጥቶታል፡፡

፪.፯ የአብ ቃል ሰው ወደመሆን ተለወጠ ለሚሉ መናፍቃን

እነዚህ መናፍቃን አካላዊ ቃል ሥጋና ደም፣ አጥንትና ጠጉር፣ ሥሮችንም ወደ መሆን ተለወጠ፤ መለኮትም ሰውን ወደ መሆን ተለወጠ ብለው ይናገራሉ፡፡ ይህም ማለት ኢየሱስ ክርስቶስ ሰው የሆነው ተለውጦ ነው ወይም ሰው በመሆኑ አምላክነቱ ጠፍቷል” የሚሉ ናቸው፡፡ አባ ጊዮርጊስ ግን ሰው ሆነ ሲባል የጨው ሐውልት እንደሆነች እንደ ሎጥ ሚስት፣ የበርሃ አውሬ እንደሆነ እንደ ናቡከደነፆር ተለውጦ አይደለም ይላል፡፡ የመለኮት ኃይል ሰው ወደ መሆን ተለውጦ ቢሆን ኖሮ ሞትን ባልቀመሰ፣ ሞትንም ቢቀምስ ዓለምን የያዘው የመለኮት ኃይል ነውና፣ የሰማይ ጠፈር በፈረሰ፣ የምድርም መሠረታት በተበታተኑ ነበር፤ ሰውነት መለኮትን ወደ መሆን ተለውጦ ቢሆን መለኮት በእጅ አይነካም፣ ለዐይንም አይታይም፣ በሕሊናም አይመረመርምና ለሰቃዮች ባልተያዘ፣ በመስቀል ላይ እፍረትን ባልታገሠ ነበር በማለት ይዘልፋቸዋል፡፡ እኛ ግንያለጭማሪ ተዋሐደ እንጂ መለኮታዊ ቃል ከባሕርዩ አልተለወጠም፤ ያለመለወጥ የተዋሐደ ሆነእንላለን በማለት በተዐቅቦ እንደተገለጠ ይነግረናል፡፡

፪.፰ መንክዮስ

የክርስቶስ ሥጋ ምትሐት ነው፤ የሰው ልጅ ሥጋ አይደለም የሚል ኑፋቄ ያስተማረ መናፍቅ ነው፡፡ አባ ጊዮርጊስ የክርስቶስ ሥጋ ምትሐት አለመሆኑን፣ ፍጹም የሰው ሥጋ መሆኑን ከድንግል መወለዱን፣ ጡቶቿን እየጠባ ማደጉን፣ በዮርዳኖስ በዮሐንስ እጅ መዳሰሱን፣ በመስቀል ላይ መቸንከሩን በመጥቀስ መንክዮስ ሆይ! ስንፍናህን አደንቃለሁስለ ብዙዎች ቤዛ መገደሉን ካላመንክ አንተም በኢየሱስ ክርስቶስ ሞት አልዳንህም በማለት ይዘልፈዋል፡፡ እኛ ግን የክርስቶስ ሰውነት ፍጹም የሚዳሰስ ሥጋን የሚያጸና አጥንት የሚፈስ ደም ሰውነትንን የሚያስሩ ጅማቶች፣ የራስ ጠጉርና ቅንድብ፣ የማትታይ ነፍስ የምታስተውልና የምትናገር የሕይወት እስትንፋስ፣ የእጆችና የእግሮች ቡቃያ ጥፍሮች አሉት እንላለን ይለናል፡፡

፪.፱ አውጣኪ

አውጣኪ ወይም አፍቲኪስ የክርስቶስ ሥጋ እንደኛ ሥጋ አይደለም፤ መከራንም አልተቀበለም፤ የክርስቶስ ሥጋ ከሰማይ የወረደ ነው በማለት ያስተማረ መናፍቅ ነው፡፡ አውጣኪ ነገረ ተዋሕዶን ለማብራራት ሲሞክር ኢየሱስ ክርስቶስ በመለኮቱ ከአብ ጋር አንድ ነው” የሚለውን ትምህርት ቢቀበልም፣ በሥጋው ፍጹም ሰው መሆኑን ግን አልተቀበለም፡፡ ስለዚህ ክርስቶስ ተራበ፤ ተጠማ፤ ደከመ፤ መከራ ተቀበለ፤ ሞተ …” የሚሉትን ቃላት ለመጠቀም ይፈራል፡፡ አባ ጊዮርጊስ ወደ ደረቱ ተጠግቶ የተቀመጠ ወዳጁ ዮሐንስ የክርስቶስን ሥጋ መድከም ለመናገር ካላፈረ፣ በፊቱ መስታወትነት ያልታየህ፣ ጣቶቹ ያልዳሰሱህ፣ ጣቶችህም ያልዳሰሱት አንተ እንዴት ታፍርበታልህ? በማለት የሚወቅሰው ስለዚህ ነው፡፡ እኛ ግን ክርስቶስ በሥጋው ደከመ፣ ወዛ፣ ተራበ፣ ተጠማ፣ ታመመ፣ ሞተ፤ ከኃጢአት በቀር የሰውነትን ሥራ ሁሉ ሠራ እንላለን በማለት የቤተ ክርስቲያንን ቀጥተኛ አስተምህሮ በመግለጥ እኛን ስለማዳን ከተያዘበት ጊዜ ጀምሮ ቅድስት ነፍሱ ከቅዱስ ሥጋው እስከተለየችበት ድረስ የተቀበለውን ፀዋትወ መከራ ያብራራል፡፡

በተጨማሪም አፍቲኪስ የክርስቶስ ሥጋ ከሰማይ ወረደ በማለት ለሚናገረው ኑፋቄው ሊቁ ሲመልስ እናንተ ሰነፎችና ልባችሁ ከማመን የዘገየአዳም ከእኛ እንደ አንዱ ሆነ› ብሎ መናገርን እንዳስቀደመ ከአዳም ዘር ሰው ሆኖ እንደተወለደ ዕወቁ፡፡ መድኃኒታችን ከለበሰው ከአዳም ሥጋ በቀር የአዳም እንደ እግዚአብሔር መሆኑ ምንድን ነው? በዚያችም ሥጋ በምድር ላይ ጉስቁልናን ለበሰ፤ ያችንም ሥጋ በሰማያት ጌትነትን አለበሳት፡፡ በሰማያት ሥጋ ካለ ከእርሷ ሰው ሆኖ ይወለድ ዘንድ ስለምን በድንግል ማኅፀን አደረ፣ ከሥጋው ጋር በድንግል ማኅፀን አደረ ካላችሁ፣ የሥጋ በሥጋ ውስጥ ማደር ጥቅሙ ምንድን ነው? ቀድሞውንም ሥጋ ካለው የቀደመ ሥጋው በበቃው፤ ከድንግል ሥጋ መወለድን ባልፈለገ ነበር ይላል፡፡ እኛ ግንየክርስቶስ ሥጋና ነፍሱ ከአዳም ባሕርይ ብቻዋን ንጽሕት ድንግል (ከሆነች) ማርያም ከተባለች የገሊላ ሴት ያለ ወንድ ዘር የነሣው ነው› እንላለን በማለት ይመልስለታል፡፡

አባ ጊዮርጊስ የክርስቶስን አምላክነት በመሰከረበት በዚህ አንቀጹ የሚከተለውን ትምህርት አስተምሯል፤ ስለ ትሕትና ነገር መናገርን እናስቀድም፤ ኃይል በሴት ማኅፀን አደረ፤ እሳትም በሥጋና በደም መጐናጸፊያ ተጠቀለለ፡፡ ሕፃናትንም የሚሥል በሕፃናት መልክ ተሣለ፤ የሔዋን አባት ከሔዋን ሴት ልጅ ተወለደ፤ በኪሩቤል ላይ የሚቀመጥ በጉልበት ታቀፈ፤ እሳት በተሣለባቸው በአራቱ እንሰሳ ላይ የሚጫን በላምና በአህያ መካከል ተኛ፡፡ ሥጋዊን ሁሉ የሚመግበው የጡት ወተትን ተመገበ፡፡ በጊዜና በዘመናት የሸመገለ በየጥቂቱ አደገ፤ በታናሽነታቸው ጊዜ ሕፃናትን የሚጠብቃቸው በሜዳ ላይ ዳኸ፤ ለዓመታቱ ቁጥር ጥንት የሌለው በሰው መጠን ጐለመሰ፤ ተራሮችን በኃይል የሚያቆማቸው ደከመ፣ ወዛም፡፡ ኪሩቤል ሊነኩት ሱራፌልም ሊዳስሱት የማይቻላቸው እግሮቹ በአመንዝራይቱ ሴት፣ ልብሶቹም ደም በሚፈስሳት ሴት ተዳሰሰ፡፡

፪.፲ የእለእስክንድርያው ታውዶስዮስና የሕንድክያው ሳዊሮስ

እነዚህ የእግዚአብሔር ልጅ በግድ መከራን ተቀበለ፤ ያለፈቃዱ ሞተ ብለው የተናገሩ መናፍቃን ናቸው፡፡ ሊቁ ይህን ቤተ መቅደስ አፍርሱት” ማለቱን፣ አትሙትብን” ያለውን ቅዱስ ጴጥሮስን መገሠጹን፣ ነፍሴን ላኖራት ደግሞም ላነሣት ሥልጣን አለኝ” ማለቱን እየጠቀሰ ካሳፈራቸው በኋላ እኛ ግን በፈቃዱ መከራ ተቀብሎ ሞተ፣ በፈቃዱ በመለኮቱ ኃይል ተነሣ እንላለን ይላል፡፡ በፈቃዱ ስለሆነ መከራውና ሞቱም እርሱ ራሱ በፈቀደ አሰቃዩት፤ እርሱም በወደደ ገደሉት፤ እርሱ በፈቀደ በመስቀል ላይ በብረቶች ቸነከሩት፤ እርሱም በወደደ ሞትን በሥጋ ቀመሰ፤ እርሱ በፈቀደ ሆምጣጤ ከሐሞት ጋር ቀላቅለው አጠጡት፤ እርሱም በወደደ ነፍሱን ለአባቱ አደራ ሰጠ በማለት ይገልጽልናል፡፡

፪.፲፩ ፍላቭያኖስ

የቁስጥንጥንያ ሊቀ ጳጳስ የነበረና የመለኮትና የሰውነት ገጽ ሁለት ነው በማለት ያስተማረ መናፍቅ ነው፡፡ አባ ጊዮርጊስም መለኮትና ትስብእት ካልተዋሐዱ ኢሳይያስ አማኑኤል ያለው ማንን ነው? ‹ሥጋዬን ካልበላችሁ ደሜንም ካልጠጣችሁ የዘለዓለም ሕይወት የላችሁም› ያለን ማን ነው? በጲላጦስ ፊት የቆመው፣ የተቸነከረውና የተሰቀለው፣ ዓለምን ያዳነው ማን ነው? በማለት ጥያቄውን በጥያቄ ይመልስለታል፡፡

፫. ነገረ መንፈስ ቅዱስ

፫.፩ መቅዶንዮስ

መንፈስ ቅዱስሕጹጽ› (ፍጡር) ነው” ያለ መናፍቅ ሲሆን በሁለተኛው ዓለም አቀፍ የቤተ ክርስቲያን ጉባኤ የተወገዘ ነው፡፡ ሊቁ መንፈስ ቅዱስ ከአብና ከወልድ ያነሰ ቢሆን ኢየሱስ ክርስቶስ ለደቀ መዛሙርቱ ሲያዝዛቸውስታጠምቁ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም አጥምቁአለ፡፡ መንፈስ ቅዱስ ያነሰ ከሆነ ስለምን በማይስተካከለው መጠመቅን አዘዘ? በማለት በጥያቄ ይመልስለታል፡፡

፫.፪ “የመንፈስ ቅዱስ ህላዌ ከክርስቶስ ጥምቀት ወዲህ ነው” ለሚሉ መናፍቃን

እነዚህ መናፍቃን ጌታችን አምላካችን መድኀኒታች ኢየሱስ ክርስቶስ በተጠመቀበት ጊዜ የመንፈስ ቅዱስን በርግብ አምሳል መገለጥ የህላዌው መጀመሪያ አድርገው መናገራቸው እንዴት ስሕተትና ኑፋቄ እንደሆነ የእግዚአብሔር መንፈስ በውኆች ላይ ሰፍፎ ነበር የሚለውን ቃል በመጥቀስና በማብራራት መልስ ይሰጣቸዋል፡፡ ሊቁ እኛ ግንመንፈስ ቅዱስ ቅድመ ዓለም የነበረ ለዘለዓለም የሚኖር ነው› እንላለን በማለት አማናዊውን የቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ ይነግራቸዋል፡፡

ይቆየን

ዕቅበተ እምነት በመጽሐፈ ምሥጢር – ሁለተኛ ክፍል

የካቲት ፳፰ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

፩.፪ አቡሊናርዮስ

አቡሊናርዮስ የሎዶቅያ ሊቀ ጳጳስ ነበረ፡፡ አባ ጊዮርጊስ አቡርዮስ” በማለት ይጠራዋል፡፡ አብ ወልድ መንፈስ ቅዱስ ለየራስ ናቸው በማለት ያስተማረ መናፍቅ ነው፡፡ ሊቁ ለዚህ መናፍቅ ሲመልስ በአመክንዮ ይጀምራል አስቀድመህ በራስ ፍረድ፤ የሥላሴ ሥርዓት (ሥርዓተ ሥላሴ) ሦስት ከሆነ ማን ፈጠረህ? ማንስ አበጀህ? አብ ራሴን ፈጠረው፤ ወልድም እጄን አበጀው፤ መንፈስ ቅዱስም እግሬን አጸናው ትላለህን? በማለት ይወቅሰዋል፡፡ እንዲህ ካልህ የሥላሴን አንድነት እንደበተንህ የራስህንም አንድነት በተንህ፤የሥላሴን አንድነት እንደ አሕዛብ አማልክት ከፈልኸው፤ ጣዖት ከሚያመልኩ ጋር በሥርዓት ተባበርክ በማለት ይዘልፈዋል፡፡ እኛ ግንአብ ወልድ መንፈስ ቅዱስ አንድ አምላክ፣ አንድ ባሕርይ፣ አንድ መንግሥት፣ አንድ ፈቃድእንላለን በማለት የቤተ ክርስቲያንን ቀጥተኛ አስተምህሮ ይነግረዋል፡፡

የአቡሊናርዮስ ክሕደት የመለኮትንና የሥጋን ተዋሕዶ ሁለት ጊዜ እንደተፈጸመ ያደርገዋል፡፡ ይኸውም በፅንሰት ጊዜ በማኅፀን እና በሞት ተለያይተው የነበሩ ሥጋና መለኮት ከመቃብር በተነሣበት ጊዜ ማለት ነው፡፡ በተጨማሪም የአቡሊናርዮስ ክሕደት የነፍስ ድኅነትን ያልተፈጸመ የሚያስመስል ነው፡፡ ምክንያቱም ክርስቶስ ከድንግል ማርያም ነፍስን ካልነሣ ያልነሣውን አላደነምና ነፍስ አልዳነችም ያሰኛል፡፡ ክርስቶስ ከድንግል ማርያም ነፍስን አልነሣም፣ ስለ ልብና ነፍስ ፋንታ መለኮቱ ሆነው ብሎ ያስተማረም ራሱ ነው፡፡ አባ ጊዮርጊስም አንተ አቡሊናርዮስ ሆይ! ቀድሞ በጥርጥርህ አብና ወልድ መንፈስ ቅዱስም የተለያዩ ናቸው ብለህ ከአባቱ የተለየ ነው አልኸው፤ አሁን ደግሞ የክርስቶስ ሰውነት ነፍስና ልብ የለውም፣ መለኮቱም ስለ ነፍስና ልብ ሆነው አልህ፡፡ እንዴት እኮ እርሱ ራሱነፍሴን ፈጽሜ በፈቃዴ እሰጣለሁ› ያለ እንደዚህ ነፍስ የለውም ይባላል?ነፍስ ከሌለው መሞቱ እንደምን ይሆናል? ያለ ነፍስ ከሥጋ በመለየት ሞት የለምና በማለት አፉን ያስይዘዋል፡፡

፩.፫ ቢቱ

ከአባ ጊዮርጊስ ጋር በአንድ ዘመን የነበረ መናፍቅ ሲሆን ለኃጥአን ፍዳ፣ ለጻድቃን በጎ ዋጋ ለመክፈል ወልድ ከአባቱ ተለይቶ ይመጣልየሚል ኑፋቄ ያስተማረ ነው፡፡ አባ ጊዮርጊስ ቢቱን ሥጋን የለበሰ ሰይጣን፣ ሰው የሆነ ጋኔን ይለዋል፡፡ አባ ሕርያቆስ በቅዳሴው አብ ወልድ መንፈስ ቅዱስ ይቀመጣሉ፤ ይመረምራሉ፤ ይፈርዳሉ እንዳለ፣ አባ ጊዮርጊስም ከብሉይና ከሐዲስ ማስረጃዎችን እየጠቀሰ ቢቱን መልስ አሳጥቶታል፡፡ እኛ ግንአብ ወልድ መንፈስ ቅዱስ በሙታንና በሕያዋን ይፈርዱ ዘንድ በአንድ ዐደባባይ፣ በአንዲትም መወቃቀሻ ቦታ ይመጣሉ› እንላለን በማለት ይመልስለታል፡፡

፩.፬ አርዮስ

አርዮስ ወልድ ፍጡር በባሕርየ መለኮቱ፣ ሀሎ ዘመን አመ ኢሀሎ ወልድ፤ ወልድ በባሕርዩ ፍጡር ነው (ሎቱ ስብሐት) … ያልነበረበት ጊዜ ነበር ብሎ ያስተማረ መናፍቅ ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያንም አርዮስን ርእሰ መናፍቃን (የመናፍቃን አለቃ)” ትለዋለች፡፡ አባ ጊዮርጊስ አብ እና ወልድ በባሕርይ፣ በህልውና አንድ እንደሆኑ ከመጻሕፍት ከየወገኑ እየጠቀሰ አፉን ያስይዘዋል፡፡ የክሕደት ቡቃያ አርዮስ ሆይ!እኔና አብ አንድ ነን› ብሎ የተናገረውን የፍጥረታትን ፈጣሪ ፍጡር ትለዋለህን? ዳግመኛምእኔን ያየ አብን አይቷል፤ እኔን የሰማ የላከኝን ሰማው፤ እኔን የካደ የላከኝን ካደው፤ በእኔ ካልሆነ በቀር ወደ አብ መምጣት የሚቻለው የለም፤ የእኔ የሆነው ሁሉ የአንተ ነው፤ የአንተ የሆነው ሁሉ የእኔ ነው›፤ በማለት የተናገረው ፍጡር ነውን? በማለት ፍጹም ሰው ሆኖ የተገለጠው ፍጹም አምላክ እንደሆነ ይመልስለታል፡፡

ስለ ህልውናቸውም የዐይን ጥቅሻ፣ የሽፋሽፍትንም መገለጥ ያህል እንኳ ቢሆን አብ ከወልድ በህልውና መቅደም የለውም በማለት የመለሰለት ሲሆን እኛ ግን ያልተሠራ፣ ያልተፈጠረ፣ ያልጎደለ፣ ያልተለየ እንደሆነ እንናገራለን ይላል፡፡ ፈጽሞ ያልተፈጠረ፣ ያልተሠራ፣ ከአባቱ አኗኗር ያልጎደለና ያልተለየ እንደሆነ እንናገራለን በማለት የወልድን አምላክነት ይመሰክራል፡፡ የአባ ጊዮርጊስ መልስ ዛሬም ኢየሱስ ክርስቶስን ፍጡር ነው” ለማለት “አማላጅ” በሚል ቅጽል ለሚጠሩት ሁሉ መልስ መሆኑን አንብቦ መረዳት የሊቃውንቱንም መልስ የመስጠት መንፈሳዊ ፈሊጥ መገንዘብ ተገቢ ነው፡፡

፩.፭ አርጌንስ

አርጌንስ (ኦሪገን) መዓርገ ርቀትን (‹ቀ› ይጠብቃል) ያስተማረ መናፍቅ ነው፡፡ አብ ከወልድ እና ከመንፈስ ቅዱስ፣ ወልድም እንደዚሁ ከመንፈስ ቅዱስ እንደሚበልጥ አድርጎ ይናገራል፡፡ ዛሬም በዚህ ኑፋቄ የወደቁና አብ ይበልጠኛል፣ ወደ አምላኬና ወደ አምላካችሁ አርጋለሁ ብሏል በማለት ኢየሱስ ክርስቶስን ከአብ እንደሚያንስ አድርገው የሚናገሩ አሉ፡፡ አባ ጊዮርጊስ እነዚህን ኀይለ ቃላት እንዲህ ይተረጉማቸዋል፡፡ ከዕርገቱ በፊትወደ አባቴና ወደ አባታችሁ፣ ወደ አምላኬና ወደ አምላካችሁያለው ለሰውነት የሚገባ ትሕትናን እያሳየ ነው፤ ለእነርሱ በጸጋ አባታቸው ነው፣ ለእርሱ ግን በእውነት የባሕርይ አባቱ ነው፡፡ ለእነርሱ በእውነት አምላካቸው ነው፤ ለእርሱ ግን ሰው ስለመሆኑ ነው፡፡ ለአርጌንስም እኛ ግን ‹በሥላሴ መዓርግ የመብለጥም ሆነ የማነስ ነገር የለም፤ በመለኮት አንድ ናቸው እንጂ› ብለን እናምናለን በማለት ይመልስለታል፡፡ አርጌንስ ከዚህም በተጨማሪ እግዚአብሔር እንዳይበሉ ከከለከላቸው ዛፍ በበሉ ቀን አዳምንና ሔዋንን ያለበሳቸው ለምድ በእኛ ላይ ያለው የቆዳ ልብስ ነው፤ የቁርበት ለምድ ልብስ አይደለም ማለቱን በመንቀፍ እኛ ግን ሥጋስ ቀድሞም በተፈጠሩ ጊዜ አላቸው፤ በኋላ እግዚአብሔር ያለበሳቸው ግን የቁርበት ልብስ ነው፤ ትእዛዙን ስላቃለሉ የነቀፋ ልብስ ነው እንላለን ብሎ ይመልስለታል፡፡

፪. ምሥጢረ ሥጋዌ (ነገረ ክርስቶስ)

፪.፩ ንስጥሮስ

ንስጥሮስ የቁስጥንጥንያ ሊቀ ጳጳስ የነበረ ሲሆን የክርስቶስን አካልና ባሕርይ ለሁለት በመክፈል ሁለት አካል ሁለት ባሕርይ በማለት ኅድረትን ያስተማረ መናፍቅ ነው፡፡ አባ ጊዮርጊስ ወልድንከነቢያት አንዱ ነው፤ የዮሴፍ ልጅ ነው› ለማለት እንዴት ደፈርህ?” የሚለው ስለዚህ ነው፡፡ ንስጥሮስ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን የሰው እናት (Anthropothokos) እንጂ የአምላክ እናት (Theotokos) መባል የለባትም ያለ መናፍቅ ነው፡፡ በእርግጥ ያሻሻለ መስሎ የክርስቶስ እናት (Christotokos) እላታለሁ” ብሏል፡፡ ይህን ቢልም ግን ለንስጥሮስ ክርስቶስ እግዚአብሔር ያደረበት ደግ ሰው እንጂ አምላክ አይደለም (ሎቱ ስብሐት)፡፡ ለዚህ ነው አባ ጊዮርጊስ ንስጥሮስን እመቤታችን ማርያምን መለኮት ያደረበትን ሰው የወለደች እንጂ የአምላክ እናት እንደማይሏት ስለ ልጆችህ ዜና ሰማን በማለት የሚዘልፈው፡፡

ሊቁ ለዚህ ኑፋቄው መልስ ሲሰጥ በእውነት ኢየሱስ ክርስቶስ ዐመጽ የሌለበት አምላክ፤ ኃጢአት የሌለበት ሰው፤ እድፍ የሌለበት ንጹሕ በግ፤ ነውር የሌለበት ፍሪዳ፤ ርኵሰት የሌለበት የበሰለ ኅብስት፤ አተላ የሌለው የጠራ የወይን ጭማቂ፤ የተወደደ ዕጣን፤ የሚያንጸባርቅ ሽቱ፤ የሕዝብን ኃጢአት ይቅር የሚል ኃጢአት የሌለበት ካህን፤ ፊት አይቶ ለሀብታም፣ ለደሀ የማያዳላ ንጉሥ ነው በማለት አምላክ ወሰብእ መሆኑን ይመሰክራል፡፡ ስለ እመቤታችንም ቀድሞ እግዚአብሔር ወልድ ከእግዚአብሔር አብ እንደተወለደ፣ በኋለኛው ዘመን የእግዚአብሔር አንድያ ልጅ ከብቻዋ ከድንግል ማርያም ተወለደ፡፡ በመጀመሪያ የማይታይ እርሱ ከማይታየው ተወለደ፤ በኋላም የማይያዝ የሕይወት እሳት፣ ከምትዳሰስ ሥጋ ተወለደ፡፡ በመጀመሪያ የሀልዎቱ መጀመሪያ ሳይታወቅ ተወለደ፤ በኋላም የዘመናት ፈጣሪ ዓመታትንም የሚወስን እርሱ ዕድሜዋ ዐሥራ አምስት ዓመት ከሆነ ከታናሽ ብላቴና ተወለደ፡፡ የመጀመሪያ ልደቱን ምሥጢር የኋለኛ ልደቱንም ድንቅ አደረገ በማለት እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ወላዲተ አምላክ መሆኗን በማስረዳት ከብሉያትና ከሐዲሳት እየጠቀሰ ያሳፍረዋል፡፡ ከሥጋዌ በኋላ ምንታዌ እንደሌለም የአርዮስን ክሕደት በዘለፈበት ድርሳኑ ሰው ከሆነ በኋላ በመለኮቱ የእግዚአብሔር ልጅ፣ በሰውነቱ የማርያም ልጅ አንለውምበማለት ይነግረናል፡፡

፪.፪ የሮሜ ሊቀ ጳጳስ ልዮን

ርጕም ልዮን በሦስተኛው ዓለም አቀፍ የቤተ ክርስቲያን ጉባኤ (ጉባኤ ኤፌሶን) ሁለት መቶ ሊቃነ ጳጳሳት ተሰብስበው ያወገዙትን የንስጥሮስን ክሕደት በማሻሻል አንድ አካል ሁለት ባሕርይ” የሚል ክሕደት የጀመረ መናፍቅ ነው፡፡ ለቤተ ክርስቲያን መከፈልም ተጠያቂ ነው፡፡ ልዮን ሥጋ ከመለኮት ያንሳል ይላል፡፡ ኢትዮጵያዊው ቄርሎስ” የተባለ አባ ጊዮርጊስ እኔ እና አብ አንድ ነን፤ ከሰማይ የወረደ ኅብስት እኔ ነኝ፤ ባለመድኃኒት ከሰማይ መጣ …” የሚሉትን ንባባት በመተርጎም እኛ ግን ‹ከተዋሕዶ በኋላ የክርስቶስ ትስብእት ከመለኮቱ አያንስም (አይጎድልም)› እንላለን፡፡ ባለመድኃኒት በድውዮች ሴት ልጅ ዘንድ አደረ፤ ከእርሷም ምድራዊት ሥጋን ተዋሐደ፡፡ ለድውዮችም ፈውስ በሚሆን ገንዘብ ከመለኮቱ ጋር አንድ አደረገው፡፡ ባለመድኃኒት ከሰማየ ሰማያት መጥቷልና የፈውስ እንጨት በዳዊት ቤት ተገኘ፡፡ ያለመለኮት ከሥጋ ጋር መዋሐድ ፈውስ እንደማይገኝ ባለመድኃኒቱ ዐወቀ፤ ስለዚህም ራሱን ሰው ለመሆን ሰጠ፡፡ ታማሚስ ለራሱ ፈውስን ያደርግ ዘንድ አይቻለውም፤ ነገር ግን በሚድንበት ገንዘብ መድኃኒት እንዲያደርግለት ባለመድኃኒቱን ይማልደዋል በማለት አፉን ያስይዘዋል፡፡

፪.፫ የኬልቄዶን ማኅበርተኞች

በቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት ዘንድ ጉባኤ ከለባት በመባል በሚጠራው በኬልቄዶን ጉባኤ የተሳተፉት ስድስት መቶ ሠላሳ ስድስት ኤጲስቆጶሳት ናቸው፡፡ እነዚህ ጉባኤተኞች መለኮትና ሥጋን በመለያየት ሁለት አካል ሁለት ባሕርይ ናቸው” የሚል እንግዳ ትምህርት ያመጡ ናቸው፡፡ አባ ጊዮርጊስም መለኮት በሰውነት ሥጋ እንደሆነ፤ ሰውነትም በመለኮት አምላክ ሆነ፡፡ በመለኮቱ መቀየርን ስለ ሰውነቱም መለወጥን አናስብ፤ ስለ አንድነቱ መቀላቀልን፣ ስለ ባሕርይውም መለያየትን አናስብ፡፡ እርሱ በመለያየት ያልተከፈለ፣ በወንድማማችነትም ሁለት ያልሆነ ነው፡፡ በመለኮቱም በሰውነቱም አንድ እግዚአብሔር ነው በማለት መልስ ሰጥቷቸዋል፡፡ እኛ ግንከድንግል ማርያም ሰው የሆነ አንድ አካል አንድ ባሕርይ (ፈቃድ) ነውእንላለንበማለትም የቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮ አስረድቷቸዋል፡፡

ይቆየን

ዕቅበተ እምነት በመጽሐፈ ምሥጢር – የመጀመሪያ ክፍል

የካቲት ፳፯ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

ዕቅበተ እምነት የቤተ ክርስቲያን የዕለት ከዕለት አገልግሎት ነው፡፡ በቤተ ክርስቲያን ታሪክ ውስጥ በጎላና በተረዳ ለመናገር የዐቃብያነ እምነት ዘመን የሚባል ወቅት ቢኖርም ቤተ ክርስቲያን የዕቅበተ እምነት ተግባር ያልፈጸመችበት ጊዜ የለም፡፡ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን ታሪክ በቃልም በመጽሐፍም የቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮ ያስጠበቁ ብዙ ሊቃውንትን እናገኛለን፡፡ አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ ከእነዚህ ስመ ጥር ዐቃብያነ እምነት ውስጥ አንዱ ነው፡፡ አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ በድርሰቱ ዳግማዊ ያሬድ”፣ በመንፈሳዊ ዕውቀቱ ዐምደ ሃይማኖት”፣ መናፍቃንን ተከራክሮ በመርታቱ ኢትዮጵያዊው ቄርሎስ” ተብሎ ይጠራል፡፡

ዜና ገድሉን የጻፈው ሊቁ ወልደ አብ እንደ ሙሴ የኦሪት መምህር፣ እንደ ሄኖክ የተሰወረውን የሚያይ፣ እንደ ኤልያስ ለአምላኩ ሕግ የሚቀና፣ እንደ ኢሳይያስ ልዑለ ቃል (ቃሉ ከፍ ያለ)፣ ጎልያድን የገደለው ዐዲሱ ዳዊት፣ የመንግሥተ ሰማያት መክፈቻዎችን የተቀበለ ጴጥሮስ፣ ከኢየሩሳሌም እስከ እልዋሪቆን ያስተማረ ልሳነ ዕፍረት ጳውሎስ፣ …” (ገድለ አባ ጊዮርስ ምዕራፍ ፩፡፲፮-፲፰) በማለት ክብሩን ልዕልናውን ይገልጸዋል፡፡ የሊቁን ዜና ዕረፍት በሰሙ ጊዜ ንጉሡና ሕዝበ ክርስቲያኑ ያለቀሱት ለቅሶ የአባ ጊዮርጊስን ጸጋና ተወዳጅነት የሚያስረዳ ነበር፡፡ አባ ቸር ጠባቂ፣ አባ የምስጋና ክቡር ዕቃ፣ አባ ዐዲሱ ዮሐንስ አፈወርቅ፣ አባ ቀዩና አረንጓዴው ወርቅ፣ አባ ሰማያዊ ሰውና ምድራዊ መልአክ፣ አባ የማይዛባ የሃይማኖት ምሰሶ፣ አባ የኢትዮጵያ ብሩህ ፀሐይና በምልዐቱ የሚታይ ጨረቃ፣ አባ ሰማያዊ ኮከብ፣ በእውነት መለኮታዊ እሳት የተዋሐደውን ቅዱስ ቍርባን የዳሰሱ እጆችህ ደረቁን? እግሮችህስ በሞት መግነዝ ተገነዙን? አባ በእውነት ዐይኖችህ ተከደኑን? አፍንጮችህስ ተዘጉን? አፍና ከንፈሮችህስ ተከደኑን? …” በማለት ነበር ኀዘናቸውን የገለጹት፡፡

አባ ጊዮርጊስ በመጻሕፍት አዋቂነቱ እና በቅድስናው የተመሰከረለት አባት ነው፡፡ በተለያዩ ጊዜያት የተነሡ የመናፍቃንን ጥያቄዎች በቃልም በመጽሐፍም በመመለስ ይታወቃል፡፡ በገድሉ ላይ ተጠቅሰው ከምናገኛቸው የቃል ክርክሮች አንዱ የአይሁዳዊው ታሪክ ነው፡፡ በአንድ ወቅት አንድ አይሁዳዊ ጌታችሁ የእግዚአብሔር ልጅ ከሆነአልዓዛርን የት ቀብራችሁት?› ብሎ ለምን ጠየቀ?” ብሎ በጠየቀ ጊዜ አባ ጊዮርጊስ እግዚአብሔር አብ በኦሪት ለምንአዳም ሆይ ወዴት ነህ?› ብሎ ጠየቀው? አብርሃምንስሚስትህ ሣራ ወዴት ናት?› ብሎ ለምን ጠየቀው?” በማለት እንዳሳፈረው በገድሉ ተጽፏል፡፡

አባ ጊዮርጊስ ብዙ ድርሳናትን ደርሷል፤ የሚበዙት የምስጋና ድርሰቶች ናቸው፡፡ ከጻፋቸው ብዙ መጻሕፍት መካከል አንዱ መጽሐፈ ምሥጢር ነው፡፡ መጽሐፈ ምሥጢር በቤተ ክርስቲያናችን ከሚጠቀሱ የዕቅበተ እምነት መጻሕፍት ውስጥ አንዱ ሲሆን የአባ ጊዮርጊስ የነገረ ሃይማኖት ሊቅነቱ የተመሰከረበት መጽሐፍ ነው፡፡ መጽሐፉ አባ ጊዮርጊስ በነገረ እግዚአብሔር ላይ ጽርፈት የተናገሩ መናፍቃንን ለመገሠጽና ለእነርሱ መልስ ለመስጠት የጻፈው መጽሐፍ ነው፡፡ በምን ዓይነት ቅንዐተ መንፈስ ቅዱስ ተነሣሥቶ መልስ እንደሰጠ ሲነግረን “… የቅዱሳንን ዜናቸውን ለመናገር ፍቅር ግድ ይለኛል፤ ቅንዐትም ከሐዲዎችን እነቅፋቸው ዘንድ ያስገድደኛል፤ ፍቅር ክርስቶስን እንዳመሰግነው ግድ ይለኛል፤ ቅንዐትም ሰይጣንን አወግዘው ዘንድ ያስገድደኛል፤ ፍቅር የክርስቶስን ሐዋርያት እንድከተላቸው ያስገድደኛል፤ ቅንዐትም ዝንጉዎችን እንድዘልፋቸው ግድ ይለያኛል፤ ፍቅር ሰማዕታትን አወድሳቸው ዘንድ ግድ ይለኛል፤ ቅንዐትም ጠንቋዮችን እንድዘልፋቸው ያስገድደኛልበማለት ይገልጽልናል፡፡

አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ በዚህ መንፈሳዊ ቅናቱ ምክንያት እግዚአብሔር የገለጠለትን ምሥጢር አምስት ጸሐፊዎችን ሰብስቦ እርሱ በቃል እየነገራቸው በሁለት ዕለታት ጽፈውታል፡፡ መጽሐፉ ሲያልቅ ጸሓፊዎቹ እጅግ አደነቁ፡፡ ምሥጢረ እግዚአብሔርን እየሰማ ያጻፈው አባ ጊዮርጊስም ጽሑፉን ተመልክቶ አደነቀ፤ እኔ የዚህን መጽሐፍ ቃል አልተናገርኩም፤ መንፈስ ቅዱስ በእኔ አንደበት ተናገረ እንጂ በማለት ተናግሯል፡፡ ይህንም መጽሐፍ የመለኮትን ነገር ይናገራልና መጽሐፈ ምሥጢር”  ሲል ሰየመው፡፡ መጽሐፉ በመጀመሪያ የተጻፈው በግእዝ ቋንቋ ሲሆን አሁን ግን ወደ አማርኛ ተተርጕሞ በብዙዎች እጅ ደርሷል፡፡

የመጽሐፈ ምሥጢር አጻጻፍ ወይም መልስ አሰጣጥ ስልትን ስንመለከት አባ ጊዮርጊስ በየምዕራፉ በምስጋና ይጀምራል፡፡ ከምስጋና ቀጥሎ መልስ የሚሰጣቸውን መናፍቃን ኑፋቄና ጥንተ ታሪክ ይገልጻል፡፡ ደርሰውበት የነበረውን የክህነት መዐርግ ጠቅሶ ከተናገሩት የክሕደት አዘቅት ጋር በማወዳደር ይወቅሳቸዋል፡፡ ከዚያም ለኑፋቄያቸው የተራቀቀ የነገረ ሃይማኖት ዕውቀቱን ተጠቅሞ ከብሉይና ከሐዲስ እየጠቀሰ መልስ ይሰጣል፡፡ በመልሱ ውስጥ በብሉይም ሆነ በሐዲስ የተነገሩ ትንቢትና ምሳሌዎችንም መንፈስ ቅዱስ በገለጠለት መሠረት ትርጉም ለአንባብያን ግልጥ እንዲሆኑ አድርጓል፡፡ አባ ጊዮርጊስ ለመናፍቃኑ መልስ በአብዛኛው የጠቀሰው ከብሉይና ከሐዲስ ነው፡፡ ከቅዱሳት መጻሕፍት እየጠቀሰ ለመናፍቃኑ መልስ የሰጠበትን ክፍል ዘለፋ፣ ወቀሳ” ይለዋል፡፡

ሊቁ በእግዚአብሔር ላይ የነቀፋ ቃል የተናገሩትን ይዘልፋቸዋል፣ ይገዝታቸዋል፣ ይረግማቸዋል፡፡ በሥላሴ ላይ የነቀፋ ቃል ባይናገሩም እንኳን የተሳሳተ ትምህርት ያስተማሩትን ደግሞ በጽድቅ ጎዳና ስላልቆሙ እንዘልፋቸዋለን፤ ርግማን ግን በሥላሴ ላይ ሐሰት ስላልተናገሩ አንረግማቸውም በማለት በተግሣጽ ያልፋቸዋል፡፡ በየአርእስቱ መጨረሻም በሃይማኖት አባቶቹን እንደሚመስል በምግባር ግን ደካማ እደሆነ በመጥቀስ አንባብያን በጸሎት እንዲያግዙት በመማጸን ያጠቃልላል፡፡ ይህም ቅዱስ ጴጥሮስ በእናንተ ስላለ ተስፋ ምክንያትን ለሚጠይቋችሁ ሁሉ መልስ ለመስጠት ዘወትር የተዘጋጃችሁ ሁኑ፤ ነገር ግን በየዋሕነትና በፍርሃት ይሁን (፩ኛ ጴጥ. ፫፡፲፭) ያለውን ፍርሃትና የዋህነት የሚያስገነዝብ ነው፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በጸሎትና በልመናም ሁሉ ዘወትር በመንፈስ ጸልዩ በዚህም አሳብ ስለ ቅዱሳን ሁሉ እየለመናችሁ በመጽናት ሁሉ ትጉ፤ ዳግም የወንጌልን ምሥጢር በግልጥ እንዳስታውቅ አፌን በመክፈት ቃል ይሰጠኝ ዘንድ፣ ስለ እኔ ለምኑ፤ ስለ ወንጌልም በሰንሰለት መልእክተኛ የሆነው መናገር እንደሚገባኝ ስለ እርሱ በግልጥ እናገር ዘንድ ለምኑ በማለት እንዳስተማረው፡፡

አባ ጊዮርጊስ በመጽሐፉ ለአሕዛብ፣ በቤተ ክርስቲያን ታሪክ ለሚታወቁ መናፍቃንና በዘመኑ ለተነሡ እንደ ቢቱ ላሉ መናፍቃን መልስ ሰጥቷል፡፡ አጠቃላይ መልስ የሰጠባቸውን ርእሰ ጉዳዮች ስናይ ምሥጢረ ሥላሴ፣ ምሥጢረ ሥጋዌ፣ ነገረ ክስቶስ፣ ነገረ መንፈስ ቅዱስ፣ ነገረ ማርያም ላይ ያተኮሩ ሲሆኑ በአንድ ማሕቀፍ ሥር የማይጠቃለሉ ለሌሎች ልዩ ልዩ ጉዳዮችም መልስ ሰጥቷል፡፡ የዚህ ጽሑፍ ዋና ዓላማ ሊቁ አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ በተለያዩ ዘመናት የተነሡ መናፍቃንና ከሐዲያን  ላነሧቸው የኑፋቄ ትምህርቶች የሰጠዉን መልስ በማሳየት ምእመናን ከመሰል ክሕደቶች እንዲጠበቁ ማድረግ ነው፡፡ የእኛ ታሪክ አለማወቅ እንጂ አዲስ ኑፋቄም፤ አዲስ ትምህርትም አለመኖሩን የቤተ ክርስቲያን ታሪክ ለሚያጠና በሦስቱ ዓለም አቀፍ ጉባኤያት መልስ የተሰጠባቸውን ኑፋቄዎች አባ ጊዮርጊስ የጻፈውን መጽሐፈ ምሥጢር በቅርቡም መልአከ ብርሃን አድማሱ ጀንበሬ እና አለቃ አያሌው ተአምሩ የሰጧቸውን መልሶች ማየት ተገቢ ነው፡፡

ከሐዋርያት ጀምሮ እስከ ዘመነ ሊቃውንት ለተነሡት መናፍቃን የቤተ ክርስቲያን አባቶች መልስ ሰጥተዋል፡፡ ጉባኤ ዘርግተው፣ ተከራክረው መንፍቃንን አሳፍረው መልሰዋል፡፡ ሊቁ አባ ጊዮርጊስ የቀደሙ አባቶችን አክሎና መስሎ ቅዱሳት መጻሕፍትን በመተርጎምና የሊቃውቱን ቃል በማራቀቅ መልስ በመስጠቱ የአባቶቹ የግብር ልጅ መሆኑን አስመሰከረ፤ የእግዚአብሔርን ቃል የተናገሯችሁን ዋኖቻችሁን አስቡ፣ የኑሯቸውንም ፍሬ እየተመለከታችሁ በእምነት ምሰሏቸው የሚለውንም አሳየን፡፡ ስለ ምሥጢረ ሥላሴ ከሰጠው ትምህርት መካከልም የሚከተለው ኃይለ ቃል ተጠቃሽ ነው፤ አብ ብርሃን አንደሆነ ወልድም ለሰው ሁሉ የሚያበራ ብርሃን ነው፡፡ ወልድ ብርሃን እንደሆነ መንፈስ ቅዱስም ፍጹም በሆነ አንድ ጸዳል ያለ ብርሃን ነው፡፡ አብ የማይዳሰስ እሳት እንደሆነ ወልድም የማይያዝ እሳት ነው፡፡ ወልድ የማይያዝ  እሳት እንደሆነ መንፈስ ቅዱስም በሃይማኖት ሙቀት ቤተ ክርስቲያንን የሚያሞቃት እሳት ነው፡፡ አብ የማይታይ ኃይል እንደሆነ ወልድም ሰው በመሆኑ ካልሆነ በቀር የማይገለጥ ኃይል እንደሆነ መንፈስ ቅዱስም ከጥፋት ሰዎች መነሣሣት የተነሣ እንዳትናወጽ ቤተ ክርስቲያንን የሚጠብቃት ኃይል ነው፡፡ አብ ፍጹም አምላክ እንደሆነ ወልድም ፍጹም አምላክ ነው፡፡ ወልድ ፍጹም አምላክ እንደሆነ መንፈስ ቅዱስም በአንድ ኅብር መልክእ ያለ ፍጹም አምላክ ነው፡፡

ከዚህ በመቀጠል መናፍቃን አንሥተዋቸው ሊቁ በመጽሐፈ ምሥጢር ኦርቶዶክሳዊ መልስ የሰጠባቸውን ዋና ዋና ጉዳዮች እናቀርባለን፡፡

፩. ምሥጢረ ሥላሴ

፩.፩ ሰባልዮስ

ሰባልዮስ በአባ ጊዮርጊስ አጠራር ሰብልያኖስ” ተብሎ ተጠቅሷል፡፡ በሦስተኛው መቶ ክፍለ ዘመን የተነሣ መናፍቅ ነው፡፡ እግዚአብሔር አንድ ገጽ ነው፤ አንዱ እግዚአብሔር በብሉይ ኪዳን አብ፣ በሐዲስ ኪዳን ወልድ፣ በበዓለ ኀምሳ ደግሞ መንፈስ ቅዱስ ሆኖ ተገለጠይላል፡፡ በአጭሩአብ ወልድ መንፈስ ቅዱስ አንድ ገጽ ነው የሚል የኑፋቄ ትምህርት ያስተማረ መናፍቅ ነው፡፡ በሊቃውንቱ ቋንቋ የሰባልዮስ ኑፋቄ አንድ ገጽ (ሞናርኪያኒዝም) ሲባል ተከታዮች ደግሞ ሰባልዮሳውያን” ይባላሉ፡፡ የሥላሴን አካላት አንድ አድርገው በመናገራቸውም ሰቃልያነ አብ ይባላሉ፡፡ አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ ለሰባልዮስ ከብሉይ ከሐዲስ እየጠቀሰ መልስ ሰጥቷል፡፡ ሊቁ እኛ ግን ሦስት ገጽ አንድ ባሕርይ፣ ሦስት አካል አንድ አምላክ፣ ሦስት ስሞች አንድ እግዚአብሔር እንላለን በማለት የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት ይመሰክራል፡፡ ሰባልዮስንም ተጠራጣሪ ሆይ እንግዲህ ባንተ ያለውን ክሕደት ትተህ በሥላሴ እመን፤ ለሥላሴ ገጻትም ምስጋናን አቅርብ በማለት ይመክረዋል፡፡

ይቆየን

መጽሐፍ ቅዱስ በቤተ ክርስቲያን ዐይን

የካቲት ፳፮ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በሐዋርያትና በነቢያት መሠረት ላይ የታነፀች፣ ከሁሉ በላይ የሆነች አንዲትና ቅድስት አካለ ክርስቶስ ናት (ኤፌ. ፩፥፳፪፤ ኤፌ. ፪፥፳)፡፡ ‹‹ከሁሉ በላይ የሆነች›› የሚለው ሐረግ ሰማያዊ ሥልጣኗን እና ልዕልናዋን የሚገልጽ ነው፡፡ ይህም ማለት የትኛውም ቅዱስ መጽሐፍ ወይም ንዋይ በእርሷ ውስጥ ይሆናል እንጂ ከበላይዋ ሊሆን አይችልም ማለት ነው፡፡ መጽሐፍ ቅዱስም እግዚአብሔር ለቤተ ክርስቲያን የገለጸውን እውነት የያዘ እንጂ ከቤተ ክርስቲያን በላይ አይደለም፡፡ ምክንያቱም ቤተ ክርስቲያን የክርስቶስ አካል ስለሆነች ከክርስቶስ አካልነት በላይ የሆነ ስለሌለ ነው፡፡ ከቤተ ክርስቲያን በላይ ያለ የቤተ ክርስቲያን ራስ ክርስቶስ ብቻ ነው (ቆላ. ፩፥፲፰)፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ የመጻሕፍት ሁሉ ራስ ሲሆን ቤተ ክርስቲያን ደግሞ የመጽሐፍ ቅዱስ ባለቤት ናት፡፡

መጽሐፍ ቅዱስ በሰዎች ቋንቋ የተጻፈ የእግዚአብሔር ቃል ነው፡፡ የተጻፈውም በመንፈስ ቅዱስ ምሪት ነው፡፡ ጸሓፊዎቹ ደግሞ የቤተ ክርስቲያን አባቶች ናቸው፡፡ በቅድስናቸው ለእግዚአብሔር ቅሩባን ስለሆኑ የእግዚአብሔር ቃል ለሚላክላቸው አብያተ ክርስቲያናት በሚገባቸው ቋንቋ ጽፈዋል፡፡ መጻፋቸውም የእነርሱን ክብር ለመግለጽና ቤተ ክርስቲያን የምትመራበትን ሕግ ለመደንገግ ሳይሆን ቤተ ክረስቲያን የምታምነውን እምነት ለመመስከርና በመንፈሳዊ ሕይወት ውጣ ውረድ ውስጥ ያሉ ምእመናን እንዲመከሩበት፣ እንዲገሠጹበት፣ ልባቸውን እንዲያቀኑበት ነው፡፡ ስለዚህ መጽሐፍ ቅዱስ እግዚአብሔር ለቤተ ክርስቲያን የገለጠውን እውነትና ቤተ ክርስቲያን ስለ እግዚአብሔር የምታምነውን እምነት የያዘ እንጂ የቤተ ክርስቲያን ሥርዓት ተሰፍሮና ተቈጠይሮ ሁሉ ነገር የተካተተበት ማለት አለመሆኑን መረዳት ይገባል፡፡

ቤተ ክርስቲያን በማየት፣ በማድረግ፣ በቃል የሚተላለፍ ብዙ ሀብት አላት፡፡ እንዲያውም የተጻፈው በጣም ጥቂቱ ነው፡፡ ሆኖም በአንዳንድ የእምነት ድርጅቶች ዘንድ ነገረ ቤተ ክርስቲያንን በሙሉ ጠቅልሎ በመጽሐፍ ሥር የማድረግ የተሳሳተ አካሔድ አለ፡፡ ይህም በሉተራውያን ዘንድ “Sola Scriptura” ወይም “Only Bible” (መጽሐፍ ቅዱስ ብቻ) ተብሎ የሚታወቀው ሲሆን ያልተጻፈው ቅዱስ ትውፊትም ሆነ መጽሐፍ ቅዱስ የማይደግፈው ግለሰባዊ አሳብ እንጂ የቤተ ክርስቲያን ትምህርት አይደለም፡፡ የዚህ ጽሑፍ ዓላማ ቤተ ክርስቲያን ቅዱሳት መጻሕፍትን የምትቀበልበትን ሃይማኖታዊ እይታ በግልጽ ማሳየት ነው፡፡

የቅዱሳት መጻሕፍት ጥንተ ታሪክ

ፈጣሬ ኵሉ ዓለም እግዚአብሔር ከፈጠራቸው ፍጥረታት ሁሉ እጅግ አክብሮ የፈጠረው የሰው ልጅን ነው፡፡ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ይህን ክብሩን ሲገልጹ ሰውን “የፍጥረታት አክሊል – The Crown of Creation” ብለው ይጠሩታል፡፡ የፍጥረታት አክሊልነቱም በእግዚአብሔር አርአያና ምሳሌ መፈጠሩ፣ ፍጥረታትን ሁሉ ከእግዚአብሔር በታች እንዲገዛ በፍጥረታት ላይ መሠልጠኑ ነው፡፡ እግዚአብሔር “ሥሉጥ በላዕለ ኵሉ ፍጥረት፤ በፍጥረት ሁሉ ላይ የሠለጠነ (ሥልጣን ያለው)” እንደሆነ ሁሉ ሰውንም በጸጋ “ሥሉጥ በላዕለ ኵሉ ምድር፤ በምድር ሁሉ ላይ የሠለጠነ (ሥልጣን ያለው)” አድርጎታል፡፡ በጥንተ ተፈጥሮው የሰው ልጅ መጻሕፍትም ሆኑ መምህራን የማያስፈልጉት ዐዋቂ ፍጥረት ነበር፡፡ እንደ አባ ማቴዎስ በአእምሮ ጠባይዕ፣ እንደ አብርሃምና እንደ ሙሴ ጸሊም በሥነ ፍጥረት ተመራምሮ የሚያውቅ ማለት ነው (ትርጓሜ ወንጌለ ዮሐንስ)፡፡ በለባዊ አእምሮው ሥነ ፍጥረትን አንብቦና መርምሮ ረቂቁን እውነት የሚረዳ ከሃሊ ዘበጸጋ ነበር፡፡ የሰው የመጀመሪያ መጽሐፍም ሥነ ፍጥረት ነው፡፡ ለሰው የመጀመሪያ እውነተኛ መምህሩ መምህረ ኵሉ ዓለም እግዚአብሔር ነው፡፡

እግዚአብሔር ለአዳም ትእዛዛቱን አስተማረው፡፡ ከመጀመሪያ ትምህርቶቹም ዋናው “ከገነት ዛፍ ሁሉ ትበላለህ፤ ነገር ግን መልካምንና ክፉን ከሚያስታውቀው ዛፍ አትብላ ከእርሱ በበላህ ቀን ሞትን ትሞታለህና” (ዘፍ. ፪፥፲፮-፲፯) የሚለው ነበር፡፡ አዳም ግን እውነተኛ መምህሩን ትቶ የክፉ ፍጡር ትምህርትን ተማረ፤ “ሞትን አትሞቱም፤ ከእርስዋ በበላችሁ ቀን ዓይኖቻችሁ እንዲከፈቱ እንደ እግዚአብሔርም መልካምንና ክፉን የምታውቁ እንድትሆኑ እግዚአብሔር ስለሚያውቅ ነው እንጂ” (ዘፍ. ፫፥፬-፭) ብሎ ሰይጣን የነገረውን ሰማ፡፡ ተማሪው ከሁለቱ ትምህርቶች ሁለተኛውን መረጠና በፈተና ወደቀ፡፡ የመጀመሪያ መምህሩን ትምህርት ይረዳም ዘንድ ከዚያ በኋላ ብቁ ልቡና አልነበረውም፡፡ ወደ ታላቁ መምህር ለመመለስ ሌሎች መምህራን እንዲደግፉት ግድ ሆነ፡፡

ክፉው መምህር ካሳታቸው በኋላ አዳምና ሔዋን ያልተጻፈውን ፊደል አዩ፣ ያልተከተበውን አነበቡ፡፡ “ሴቲቱም ዛፉ ለመብላት ያማረ እንደ ሆነ፥ ለዓይንም እንደሚያስጎመጅ፥ ለጥበብም መልካም እንደ ሆነ አየች (ዘፍ. ፫፥፮) እንዲል፡፡ ከዚህም በኋላ ፍጥረታትን የሚያነቡ ሳይሆኑ ፍጥረታት የሚያስደነግጡአቸው ድንጉጦች ሆኑ፡፡ እግዚአብሔር ካደላቸው ከንጽሐ ጠባይ ደረጃ ስለወደቁና ወደ ቀደመ ክሂሎታቸው መመለስ ስላልቻሉ በሰውኛ ፊደል የተጻፉ መጻሕፍትን በማንበብ መመርኮዝ ግድ ሆነባቸው፡፡ የሰው ልጅ ፍጡር ባልሆነ ብርሃን ረቂቁንና የማይታየውን ዓለም ከማየት እና በማየት ከሚገኘው ዕውቀት ከመስማት ወደሚገኘውና ውስን ወደሆነው ዕውቀት በመውረዱ ምክንያት መጽሐፍ አስፈለገው፡፡ ስለዚህ መጻሕፍት የሰው የባሕርዩ መምህራን አይደሉም፡፡ ከውድቀቱ በኋላ የተሰጡት ደጋፊዎች እንጂ፡፡ ይህንም የቤተ ክርስቲያን መምህራን በሚከተለው ምሳሌ ይገልጹታል፤

ሰው የሚራመደው በሁለት እግሩ ነው፡፡ እግሩን ሲታመም ወይም ሲያረጅ በሁለት እግሩ መራመድ ስለሚያቅተው ምርኩዝ ይይዛል፡፡ ልክ እንደዚሁ ሰው በቅድመ ተፈጥሮው በራሱ መቆምና መራመድ የሚችል ነበር፡፡ ነገር ግን በኃጢአት ካረጀና ከታመመ በኋላ መቆምም መራመድም ይችል ዘንድ መጻሕፍትና መምህራን ምርኩዝ እንዲሆኑት ተሰጡት፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ በማቴዎስ ወንጌል ትርጓሜው ይህን ይበልጥ ሲያብራራልን “በቀለም ከተቀረፁ የመጻሕፍት ቃላት ይልቅ በልቡናችን ያደረ የመንፈስ ቅዱስ ጸጋ ይመራን ዘንድ እጅግ ንጹሕ ሕይወት ሊኖረን እንጂ የተጻፈ ነገር ሊያስፈልገን አይገባም ነበር” ብሏል፡፡ ይህን ካለ በኋላ ግን መጻሕፍትን በጥንቃቄ መያዝ እንደሚገባን ሲያስተምረን “ይህን ጸጋ ከእኛ እንዲርቅ አድርገናል፡፡ እንግዲህ ሁለተኛውን ታላቅ ስጦታ (መጻሕፍትን) አጥብቀን እንያዝ” ብሏል፡፡ ይህ ሁሉ ቅዱሳት መጻሕፍት ከጊዜ በኋላ አስፈላጊ በመሆናቸው የተሰጡ እንጂ ሁሉ ነገር ከእነርሱ የጀመረ አለመሆኑን የሚያስረዳ  ነው፡፡

ወንጌል ከተጻፈውም በላይና የቀደመች እንደሆነች

ብዙ ጊዜ ወንጌል ስንል አራቱ የወንጌላውያን መጻሕፍት ብቻ ቀድመው ይታሰቡን ይሆናል፡፡ አንዳንድ “መጽሐፍ ቅዱስ ብቻ” የሚሉ የእምነት ድርጅቶች እንደሚሉትም የተጻፈው ብቻ ወንጌል የሚመስለንም እንኖር ይሆናል፡፡ የተጻፈውም ሆነ ያልተጻፈው ቅዱስ ትውፊት ግን ወንጌል በጽሑፍ ብቻ የተገደበ እንዳልሆነ ያስተምረናል፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ወንድሞች ሆይ፥ የሰበክሁላችሁን ደግሞም የተቀበላችሁትን በእርሱም ደግሞ የቆማችሁበትን በእርሱም ደግሞ የምትድኑበትን ወንጌል አሳስባችኋለሁ፤” ሲል አራቱ ወንጌላት ተጠቃለው አልተጻፉም ነበር (፩ኛ ቆሮ. ፲፭፥፩)፡፡ ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “እውነት እላችኋለሁ፥ ይህ ወንጌል በዓለም ሁሉ በማናቸውም ስፍራ በሚሰበክበት እርስዋ ያደረገችው ደግሞ ለእርስዋ መታሰቢያ እንዲሆን ይነገራል” ብሎ ስለ ማርያም እንተ ዕፍረት በመሰከረ ጊዜ ማቴዎስም፣ ማርቆስም፣ ሉቃስም፣ ዮሐንስም ገና ወንጌልን አልጻፉም ነበር (ማቴ. ፳፮፥፲፫)፡፡ ይህ ቃል በተነገረ ጊዜ እንኳን ወንጌልን ሊጽፉ እምነታቸውም የተሟላ አልነበረም፡፡ ይህም በመከራው ጊዜ ከዮሐንስ በስተቀር ሁሉም በመሸሻቸው ተገልጧል፡፡ ስለዚህ ጌታ “ይህ ወንጌል” ሲል የተጻፈውን ብቻ የምናስብ ከሆነ ስሕተት መሆኑን ልብ ይሏል፡፡

ወንጌል በቃልም፣ በመጽሐፍም፣ በሕይወትም የምትሰበክና የተሰበከች እንጂ በመጻሕፍት ተጠቃላና ተካትታ የተቀመጠች ብቻ አድርጎ ማሰብ ስሕተት ነው፡፡ ሐዋርያት በቃልም በመጽሐፍም ሰብከዋል፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ደግሞ በሕይወቱ ባገኘው መገለጥ ተሰብኳል (ሐዋ. ፱)፡፡ እንዲያውም የቅዱሳት መጻሕፍት ጸሐፍያን በጽሑፍ የተሰበከው ጥቂት መሆኑንና በቃል ብዙዎች እንደተሰበኩ ገልጸዋል፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ ወንጌሉን ጽፎ ሲያጠቃልል “ኢየሱስም ያደረገው ብዙ ሌላ ነገር ደግሞ አለ፤ ሁሉ በእያንዳንዱ ቢጻፍ ለተጻፉት መጻሕፍት ዓለም ራሱ ባልበቃቸውም ይመስለኛል” (ዮሐ. ፳፩፥፳፭) የሚለው ሁሉ ነገር አለመጻፉን ያስረዳል፡፡ ስለዚህ ከተጻፉት በላይ ቤተ ክርስቲያን በትውፊት ያቆየችልን ብዙ ነገር መኖሩን መረዳት ተገቢ ነው፡፡

ቅዱስ ሉቃስም ገና ወንጌሉን መጻፍ ሲጀምር ለሚጽፍለት ቴዎፍሎስ ለተባለው ሰው “የከበርህ ቴዎፍሎስ ሆይ፥ ከመጀመሪያው በዓይን ያዩትና የቃሉ አገልጋዮች የሆኑት እንዳስተላለፉልን፥ በኛ ዘንድ ስለ ተፈጸመው ነገር ብዙዎች ታሪክን በየተራው ለማዘጋጀት ስለ ሞከሩ፥ እኔ ደግሞ ስለ ተማርከው ቃል እርግጡን እንድታውቅ በጥንቃቄ ሁሉን ከመጀመሪያው ተከትዬ በየተራው ልጽፍልህ መልካም ሆኖ ታየኝ” (ሉቃ. ፩፥፩-፬) ብሏል፡፡ ይህ በዓይን ያዩ፣ ወንጌልን ሳይጽፉ በቃል ወይም በሌሎች መጻሕፍት ያስተማሩና ለነቅዱስ ሉቃስም ያስተላለፉ መኖራቸውን በቅድሚያ ሲያስረዳ ወንጌሉ የተጻፈለት ቴዎፍሎስ እንኳን አስቀድሞ በቃል መማሩንም የሚያሳይ ነው፡፡ ቅዱስ ሉቃስም እርግጡን ያውቅ ዘንድ ወይም ያረጋግጥ ዘንድ ጻፈለት እንጂ ከዚያ በፊት ያልተማረ ስላልነበር ለማስተማርና ለማሳወቅ የጻፈለት አይደለም፡፡

ከመጽሐፍ ቅዱስና ከቅድስት ቤተ ክርስቲያን የቱ ይቀድማል?

ቤተ ክርስቲያን ከመጽሐፍ ቅዱስ በፊት የነበረችና መጽሐፍ ቅዱስን የጻፈች፣ ከእግዚአብሔር የተቀበለችውን በመጽሐፍ የተቀመጠውን እውነት ጠብቃ ያስተላለፈች የእግዚአብሔር መንግሥት ናት፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ የተጻፈው በቤተ ክርስቲያን ለቤተ ክርስቲያን ነው፡፡ ከተጻፉት መጻሕፍትም ውስጥ አምላካውያት የሆኑትን በቀኖና ለይታና ቀድሳ ለምእመናን የሕይወት ምግብነት የሰጠች መሆኗን መገንዘብ ተገቢ ነው፡፡ ስለዚህ ቤተ ክርስቲያን ከመጽሐፍ ቅዱስ ትቀድማለች፤ መጽሐፍ ቅዱስ የእግዚአብሔር ቃል ለመሆኑም ምስክሯ ቤተ ክርስቲያን ናት፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ ቤተ ክርስቲያን በመንፈስ ቅዱስ ምሪት የጻፈችውና የምትተረጉመው እንጂ ቤተ ክርስቲያንን ያስገኘ አይደለም፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ ለአዋልድ መጻሕፍት ወላጃቸው ነው፡፡ ይህንም በብዙ ማስረጃና አመክንዮ እንደሚከተለው እናያለን፤

፩. መጽሐፍ ቅዱስ ራሱ የቤተ ክርስቲያንን ቀዳሚነት ይመሰክራል

የሚከተሉት ጥቅሶች ቅዱሳት መጻሕፍቱ ከመጻፋቸው በፊት ቤተ ክርስቲያን እንደነበረች በደንብ ያስረዳሉ፤

  • በቆሮንቶስ ላለች ለእግዚአብሔር ቤተ ክርስቲያን፥ በክርስቶስ ኢየሱስ ለተቀደሱት፥ የእነርሱና የእኛ ጌታ የሆነውን የጌታችንን የኢየሱስ ክርስቶስን ስም በየስፍራው ከሚጠሩት ሁሉ ጋር ቅዱሳን ለመሆን ለተጠሩት (፩ኛ ቆሮ. ፩፥፪)፡፡

አንድ መልእክት (ደብዳቤ) ሲጻፍ ሦስት አካላት መኖራቸውን መረዳት ተገቢ ነው – ላኪው፣ መልእክቱና ተቀባዩ፡፡ ላኪውና ተቀባዩ በሌሉበት መልእክቱ ሊጻፍ አይችልም፡፡ የመልእክቱ ላኪ ቅዱስ ጳውሎስ ነው፡፡ ተቀባይዋ ደግሞ በቆሮንቶስ አገር ያለች የእግዚአብሔር ቤተ ክርስቲያን ናት፡፡ ከመልእክቱ ላኪውና ተቀባዩ የሚቀድሙ ከሆነ መልእክቱን ለመቀበል ቅዱስ ጳውሎስንና ቤተ ክርስቲያንን በቅድምና መቀበል ያስፈልጋል ማለት ነው፡፡ ይህን ሲያስረዳ ቅዱስ ጳውሎስ ገና መልእክቱን ለመጻፍ ሲጀምርና ለማን እንደሚጽፍ ሲገልጽ “በቆሮንቶስ ላለች ለእግዚአብሔር ቤተ ክርስቲያን” ማለቱ እርሱ መልእክቱን ከመጻፉ በፊት የቆሮንቶስ ቤተ ክርስቲያን እንደነበረች የሚያሳይ ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያኗ ቀድማ መኖሯ ብቻ ሳይሆን ሰዎችን ስትቀድስም ነበር፡፡ በሌላ አገላለጽ ሰዎችን ለመቀደስ የግድ መጽሐፍ ቅዱስ ወይም ቅዱስ ጳውሎስ ለቆሮንቶስ ሰዎች የጻፈው መልእክት አላስፈለጋትም ነበር፡፡ ይህም ይታወቅ ዘንድ የመልእክቱ ባለቤት “በክርስቶስ ኢየሱስ ለተቀደሱት” በማለት ገለጸ፡፡ ይህን የመሰሉና ተመሳሳይ እውነትን የሚመሰክሩ ብዙ ጥቅሶችን ማንሣት ይቻላል፡፡

  • በእግዚአብሔር ፈቃድ የኢየሱስ ክርስቶስ ሐዋርያ የሆነ ጳውሎስ ወንድሙም ጢሞቴዎስ፥ በአካይያ አገር ሁሉ ከሚኖሩ ቅዱሳን ሁሉ ጋር በቆሮንቶስ ላለች ለእግዚአብሔር ቤተ ክርስቲያን፤” (፪ኛ ቆሮ. ፩፥፩)፡፡
  • “በኢየሱስ ክርስቶስ ከሙታንም ባነሣው በእግዚአብሔር አብ ሐዋርያ የሆነ እንጂ ከሰዎች ወይም በሰው ያልሆነ ጳውሎስ ከእኔም ጋር ያሉት ወንድሞች ሁሉ፥ ወደ ገላትያ አብያተ ክርስቲያናት፤(ገላ. ፩፥፩)፡፡
  • ጳውሎስና ስልዋኖስ ጢሞቴዎስም፥ በእግዚአብሔር አብ በጌታ በኢየሱስ ክርስቶስም ወደምትሆን ወደ ተሰሎንቄ ሰዎች ቤተ ክርስቲያን፤ (፩ኛ ተሰ. ፩፥፩)፡፡
  • እንዲሁም የምታየውን በመጽሐፍ ጽፈሕ ወደ ኤፌሶንና ወደ ሰምርኔስ ወደ ጴርጋሞንም ወደ ትያጥሮንም ወደ ሰርዴስም ወደ ፊልድልፍያም ወደ ሎዶቅያም በእስያ ወዳሉት ወደ ሰባቱ አብያተ ክርስቲያናት ላክ አለኝ” (ራእ. ፩፥፲፩)፡፡ ባለራእዩ ቅዱስ ዮሐንስም በተመሳሳይ ራእዩን ካየ በኋላ ለሰባቱ አብያተ ክርስቲያናት እንዲጽፍ ተገለጸለት፡፡ ይህም ከመጽሐፉ በፊት አብያተ ክርስቲያናቱ እንደነበሩ የሚያስረዳ ነው፡፡ ዮሐንስም ራእዩን በማየት ይከብር ዘንድ መጽሐፍ አላስፈለገውም ነበር፡፡

፪. አመክንዮአዊ ማረጋገጫ

ከመጻሕፍት ሁሉ ቀድሞ የተጻፈው መጽሐፈ ሄኖክ ነው፡፡ መጽሐፈ ሄኖክ ከመጻፉ በፊት ሰው ከአንድ ሺሕ ዓመት በላይ ያለ መጽሐፍ ኖሯል፡፡ መጽሐፈ ኢዮብና አምስቱ የኦሪት መጻሕፍት ከዚያ በመቀጠል ተጻፉ፡፡ የነቢያት መጻሕፍት ሺሕ ዓመታት ዘግይተው ክርስቶስ ሊወለድ በመቶዎች የሚቈጠሩ ዓመታት ሲቀሩት ተጻፉ፡፡ በሐዲስ ኪዳንም ለመጀመሪያዎቹ ዐርባ ዓመታት መጻሕፍት አልተጻፉም፡፡ ከዚያ በኋላም የማቴዎስ ወንጌልንና የያዕቆብ መልእክትን የመሰሉት ቀድመው ተጻፉ እንጂ አብዛኞቹ የተጻፉት እስከ ፸ ዓ.ም. ድረስ ቆይተው ነው፡፡ የሐዲሳት መጻሕፍት የተጻፉት ደግሞ በመጀመሪያው ምዕተ ዓመት መገባደጃ ነበር፡፡ ይህም የሚያስገነዝበው፡-

ሀ. ለጽድቅና ለድኅነት የሚያስፈልገው መጽሐፍ ቅዱስ ብቻ ቢሆን ኖሮ መጽሐፉ በአንዴ አልቆና ተጠቃሎ ከአዳም ጀምሮ ላሉት ሁሉ ካለመድሎ መሰጠት አልነበረበትምን? መጽሐፍ ያልተሰጣቸውስ “እኛ በኃጢአት የወደቅነው መጽሐፍ ቅዱስ ስላልነበረን ነው” ብለው ምክንያት እንዲያቀርቡ ዕድል አይፈጥርላቸውም ነበርን? አምልኮን በመጽሐፍ ቅዱስ ብቻ የምንገድበው ከሆነ ለሁሉም ሁሉንም መጻሕፍትን ባለ መስጠቱ የእግዚአብሔር ፈታሒነት ላይ ጥያቄ አያስነሣም ነበርን?

ለ. በጥንቱ ዘመን መጻሕፍት ለየተጻፉላቸው ሰዎች በጥቅል (Scroll) መልክ ይገኙ ነበር እንጂ አሁን እንዳለው ሁሉም በአንድነት ተጠርዘው በአንድ ሰው እጅ ማግኘት አይቻልም ነበር፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ አሁን ባለው መልኩ ተሰብስቦ በአንድነት መገኘት የቻለው የማተሚያ ማሽን ከተሠራና በወረቀት ማተም ከተጀመረ በኋላ ነው፡፡ ምዕራፍና ቊጥር ወጥቶለት ለንባብ አመቺ የሆነው ደግሞ ከዐሥራ ስድስተኛው ክፍለ ዘመን በኋላ ነው፡፡ በጥንቱ ዘመን እያንዳንዱ መጽሐፍ በየቦታው በጥቂት መጠን ብቻ ይገኝ ነበር፡፡ የሮሜ መልእክት የሚገኘው ሮማውያን ዘንድ፣ የቆሮንቶስ መልእክት ከቆሮንቶስ ሰዎች ዘንድ … ወዘተ እንጂ እንደዚህኛው ዘመን በአንድ ጊዜ ተባዝተው ሁሉም ዘንድ የሚገኙ አልነበረም፡፡ ለዐራት ሺሕ ዓመታት ያክል የተጻፉትን እነዚህን ቅዱሳት መጻሕፍት ከሐሰተኞቹ ለይታና በቀኖና ወስና “እነዚህን ተጠቀሙ” ያለችው ቤተ ክርስቲያን አይደለችምን?

ቤተ ክርስቲያን ይህን ባታደርግ እኛም ከመጽሐፍ ቅዱስ ፈጽሞ የማንገናኝ በሆንን ነበር፡፡ ወንጌላትን በጊዜው ብዙዎችን ያስቱ ከነበሩት “የይሁዳ ወንጌል”፣ “የበርናባስ ወንጌል” ከተባሉትና እነዚህን ከመሰሉት እንዲሁም “የማቴዎስ፣ የማርቆስ ወንጌል” ተብለው ብዙ ሐሰት ከተጨመሩባቸው ለይታ “መጻሕፍተ ወንጌላት ዐራቱ ብቻ ናቸው” ባትለን ኖሮ በብዙ ጥፋት ውስጥ የምንሆን አልነበርንምን? እርሷ በቀኖና ሰፍራ ቈጥራ የሰጠችውን መጽሐፍ ተቀብሎ ሰጪዋን ቤተ ክርስቲያንን አልቀበልም ማለትስ ስሕተት አይደለምን? በተመሳሳይ መልኩ ቀኖናን ሠርታ አዋልድ መጻሕፍትን ስትሰጥ አለመቀበልስ አለማወቅ አይደለምን?

ሐ. የቤተ ክርስቲያንን ከሁሉ በላይ መሆንና ፍጹም የሆነ ሥልጣኗን የምናውቅ አሥራው መጻፍት ተብለው የሚታወቁት መጻሕፍትን ሰብስቦ ሰማንያ አንድ ብቻ ናቸው ብሎ ማን ነገራችሁ? ብንባል “ቤተ ክርስቲያን” እንላለን፡፡ “መጽሐፍ ቅዱስ ብቻ” የሚሉት ወገኖች ግን “መጽሐፍ ቅዱስን ‘ስልሳ ስድስት’ ያላችሁ ማነው” ቢባሉ ማን ይሉ ይሆን? እንቀበላቸዋለን የሚሏቸው “ስልሳ ስድስትቱ መጻሕፍት” ራሳቸው “ስልሳ ስድስት ብቻ” ወይም “መጽሐፍ ቅዱስ ብቻ” አይሉምና፡፡

፫. መጽሐፍ ቅዱስ ሁሉንም ነገር ጠቅልሎ አለመያዙን ያስረዳል

ወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስ ኢየሱስም በዚህ መጽሐፍ ያልተጻፈ ሌላ ብዙ ምልክት በደቀ መዛሙርቱ ፊት አደረገ፤ (ዮሐ. ፳፥፴) በማለት ክርስቶስ ያደረጋቸው ሁሉ የተጻፉ እንዳልሆነ አስረድቷል፡፡ እንዲያውም እርሱ ያደረገውን ሁሉንም እንጻፍ ማለት እንደማይቻል ሲገልጽ ኢየሱስም ያደረገው ብዙ ሌላ ነገር ደግሞ አለ፤ ሁሉ በእያንዳንዱ ቢጻፍ ለተጻፉት መጻሕፍት ዓለም ራሱ ባልበቃቸውም ይመስለኛል” ብሏል፡፡ ይህ መጽሐፍ ቅዱስ ሁሉንም ታሪክ፣ ሁሉንም ሥርዐት … ወዘተ ጠቅልሎ እንዳላካተተ የሚያሳይ ነው፡፡ ይህን ስንል ግን በጽሑፍ ደረጃ አልዘረዘረም ማለታችን እንጂ ከምሥጢር ምልዐት አንጻር የጎደለው ነገር አለው ማታችን አይደለም፡፡ የእግዚአብሔር ቃል ሁሌም ምሉዕ ነውና የእግዚአብሔር ቃል የሚገኝበት መጽሐፍም ሕፀፅና ጉድለት የማይገኝበት ምሉዕ ነው፡፡ ይህ ብቻ ሳይሆን መጽሐፍ ቅዱስ ባነሣው ጉዳይ ላይ ተጨማሪ መንፈሳዊ ዕውቀት የምንፈልግ ከሆነ የቀረው ነገር የት እንደሚገኝ አዋልድ መጻሕፍትን ጠቁሞናል እንጂ “ሁሉንም ጠቅልዬ ይዣለሁና እኔን ብቻ አንብቡ” አላለም፡፡ የሚከተሉት አሳቦችም ይህንኑ የሚያስረዱ ናቸው፡፡

  • የቀረውም ፊተኛውና ኋለኛው የሰሎሞን ነገር በነቢዩ በናታን ታሪክ፥ በሴሎናዊውም በአሒያ ትንቢት፥ ስለ ናባጥም ልጅ ስለ ኢዮርብዓም ባየው በባለ ራእዩ በአዶ ራእይ የተጻፈ አይደለምን?” (፪ኛ ዜና. ፱፥፳፱)፡፡
  • የቀረውም የሮብዓም ነገር፥ ያደረገውም ሁሉ፥ በይሁዳ ነገሥታት ታሪክ መጽሐፍ የተጻፈ አይደለምን?” (፩ኛ ነገ. ፲፬፥፳፱)፡፡
  • “የቀረውም የሰሎሞን ነገር፥ ያደረገውም ሁሉ፥ ጥበቡም፥ እነሆ፥ በሰሎሞን ታሪክ መጽሐፍ ተጽፎአል (፩ኛ ነገ. ፲፩፥፵፩)፡፡

ማጠቃለያ

መጽሐፍ ቅዱስ የቅዱሳት መጻሕፍት ሁሉ ምንጭና ራስ ነው፡፡ ማንኛውም ትምህርት፣ የቤተ ክርስቲያን ታሪክ ወይም ሥርዐት በመጽሐፍ ቅዱስ ከተጠቀሰው ጋር የሚጋጭ ከሆነ በቤተ የቤተ ክርስቲያናችን ተቀባይነት የለውም፡፡ የቤተ ክርስቲያናችን የትምህርተ ሃይማኖት ዋና ምንጭ መጽሐፍ ቅዱስ ነው፡፡ የሥርዐትና የታሪክ ዋና ምንጭም መጽሐፍ ቅዱስ ነው፡፡ ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያናችን መጽሐፍ ቅዱስ የሚያዘውን የምትፈጽም፣ የምታስተምርና የምትኖር መጽሐፍ ቅዱሳዊት ቤተ ክርስቲያን ናት፡፡ መጽሐፍ ቅዱስንም እንድናነበውና እንድንማርበት አዘጋጅታ የሰጠችን እርሷው ናት፡፡ ይሁንና አንዳንድ መናፍቃን መጽሐፍ ቅዱስን የሚከተሉ መስለው ቤተ ክርስቲያን መጽሐፍ ቅዱስን ያልሰበከች አስመስለው ስለሚያቀርቡ ተንኮላቸውን ተረድተን ልንጠነቀቅ ይገባል፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ የማይለውን እንደሚል አድርገው በማቅረብና አጣመው በመተርጎም የሚስቱ ብዙዎች ናቸው፡፡ ለዚህም ነው ከሁሉ የምትቀድመውን ቤተ ክርስቲያን እየተቃወሙ እርሷ ለዓለም ሁሉ የሰጠችውን ቅዱስ መጽሐፍ የተቀበሉ የሚያስመስሉት፡፡

ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን ከሚዋጉአት ክፍሎች ተሐድሶ ፕሮቴስታንቶች ዋናዎቹ ናቸው፡፡ የቤተ ክርስቲያን ልጆችን ከሚያታልሉበት ፕሮቴስታንታዊ መንገድ አንዱ ደግሞ “መጽሐፍ ቅዱስ ብቻ” የሚለው አስተምህሮ ነው፡፡ መጽሐፍ ቅዱስም አመክንዮም የማይደግፉትን ይህን የስሕተት መንገድ በመያዝ ቤተ ክርስቲያንን ይከሳሉ፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ ብቻ ቢሉም መጽሐፍ ቅዱስ የሚመሰክርላትን ልዕልናዋን አይቀበሉም፡፡ የመረጡትን ይወስዳሉ፤ ያልተስማማቸውን ይተዋሉ፡፡ አስቀድመን እንዳየነው አንድ አማኝ ቤተ ክርስቲያን ሁሉን የምትይዝና ከሁሉ ይልቅ የበለጠች መሆኗን መረዳት ይገባዋል፡፡ አንድ ጥያቄ ቢፈጠርበት እንኳን በቤተ ክርስቲያ ውስጥ ካለ አይቸገርም፡፡ ምክንያቱም ዛሬ ያላወቀውን ነገ ያውቃል፤ ዛሬ ያልተረዳውን በሕይወትም፣ ከአባቶች ጠይቆም ይረዳል፡፡ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥቅስ ካላሳያችሁኝ የሚል አይሆንም፡፡ ይልቁንስ በመጽሐፍ ተጽፎ ያላገኘውን ከሁሉ ይልቅ ከፍ ካለችው ከቤተ ክርስቲያን ለማግኘት ይጥራል እንጂ፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

የተወደዳችሁ የማኅበረ ቅዱሳን ድረ ገጽ ተከታታዮች! ይህ ትምህርት፣ ከታኅሣሥ ፲፮ – ፴ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም በታተመው ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ፣ በንቁ ዓምድ ሥር ለንባብ መብቃቱን ለማስገንዘብ እንወዳለን፡፡

አንቀጸ መድኃኒት ቤተ ክርስቲያን – ካለፈው የቀጠለ

የካቲት ፳፪ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

… ኵላዊት (ካቶሊክ፣ Universal) የሚለው አገላለጽ በምዕራባውያን (በካቶሊካውያን) አስተሳሰብ የተለየ ትርጕም አለው፡፡ በምዕራባውያን ዘንድ ለቤተ ክርስቲያን ኵላዊት መሆን ዋናው መሠረቱ ለሮሙ ፖፕ መታዘዝ ነው፡፡ በእነርሱ አስተሳሰብ መሠረት የማይሳሳትና የክርስቶስ ወኪል አድርገው ለሚቈጥሩት ለፖፑ የማትገዛ ቤተ ክርስቲያን ኵላዊት አይደለችም፡፡ በምሥራቃውያንና በኦሬንታል ኦርቶዶክስ አብያተ ክርስቲያናት ደግሞ ቤተ ክርስቲያንን ኵላዊት የሚያሰኛት ሥላሴ በአንድነት በሦስትነት የሚመለኩባት፣ ከሐዋርያት ጀምሮ ባልተቋረጠ ክትትል ጳጳስ ያላትና የክርስቶስ ሥጋና ደም የሚፈተትባት መሆኗ ነው፡፡ ኵላዊትነት በምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን አንድነት (በተለይም በቅዱስ ቊርባን) እንጂ በፖፕ አንድ መሆን አይደለምና፡፡

ቅዱስ አግናጥዮስ ምጥው ለአንበሳ ወደ ስሚርናስ በላከው መልእክቱ እንደተናገረው፥ ቤተ ክርስቲያን ኵላዊት (ፍጽምት፣ ርትዕት፥ ሁሉንም የምትይዝ) የምትባለው ቅዱስ ሥጋውና ክቡር ደሙ የሚፈተትባት በመሆኗ ነው፡፡ በዚህ ቅዱስ ምሥጢር አማካይነት በየትኛውም ሥፍራ የምንኖር ክርስቲያኖች (በግብፅም፣ በኢትዮጵያም፣ በሰማይም፣ በምድርም) አንድ ወደ መሆን፣ ወደ ፍጽምና፣ ወደ እውነት እንመጣለን፡፡ በመሆኑም ያለዚህ ምሥጢር ቤተ ክርስቲያን ኵላዊት አትባልም፡፡ በዚህም የሐዋርያውያነ አበው ትምህርት መሠረት ቅዱስ ሥጋውንና ክቡር ደሙን አማናዊ አይደለም፤ አምሳል ነው የሚሉ ሰዎች ስብስባቸው ቤተ ክርስቲያን እንዳልሆነ እንረዳለን፡፡

. አንዲት

እግዚአብሔር አንድ ነው፤ የክርስቶስም ማዳን አንዲት ናት፤ ተስፋ የምናደርጋት መንግሥተ ሰማያት አንዲት ናት፤ የምንቀበለው የክርስቶስ ቅዱስ ሥጋና ክቡር ደምም አንድ ነው፡፡ በአጭር አገላለጽ የተገለጠው እውነት ከነማብራሪያው አንድ ነው፡፡ ይህን የምታስተምር ቤተ ክርስቲያንም አንዲት ናት፡፡ የክርስቶስ አካል ስለሆነች አንዲት ናት፡፡ የክርስቶስ አካል አይከፈልምና ቤተ ክርስቲያን አንዲት እንጂ ብዙ አይደለችም፡፡ ይህቺ አንዲት ቤተ ክርስቲያን ተአምኖዋ በአንድ እግዚአብሔር ስለሆነ መለያየት አይስማማትም፡፡ ምእመናኗም አንድ ትምህርት ይማራሉ፤ አንድ እምነት ያምናሉ፤ አንድ ጥምቀት ይጠመቃሉ፡፡ ሰዎች ወይም መላእክት ከእርሷ ውጪ ወጥተው በክሕደት በኃጢአት ሊሔዱ ይችላሉ፡፡ ነገር ግን ሌላ ቤተ ክርስቲያን ሊመሠርቱ አይችሉም፡፡ እንመሥርት ቢሉም የመሠረቱት ስብስብ ቤተ ክርስቲያን ተብለው ሊጠሩበት አይችሉም ምክንያቱም ከክርስቶስ የተለየች ቤተ ክርስቲያን የለችምና፡፡

ሰዎች በተለያየ መንገድ ከአንዲቷ ማኅበር ቢወጡም ቤተ ክርስቲያን ተከፋፈለች አይባልም፡፡ ቤተ ክርስቲያን አትከፈልም፤ አንዱ እንግዚአብሔር አይከፈልምና፡፡ አንዳንድ ወገኖች ለራሳቸው በየሰፈሩ “ቸርች” ብለው ይመሠርታሉ፡፡ ነገር ግን ይህ ስብስባቸው ፈጽሞ ቤተ ክርስቲያን ሊባል እንደማይችል ማወቅ ተገቢ ነው፡፡ ምክንያቱም ቤተ ክርስቲያን አንዲት ናትና፡፡ ቤተ ክርስቲያን በክርስቶስ የተመሠረተች እንጂ ሰዎች ተሰብስበው የሚመሠርቷት አይደለችም፡፡ በሰዎች መሰባሰብ የተመሠረተች፣ እግዚአብሔር በአንድነት በሦስትነት የማይመለክባት፣ ምሥጢራት የማይፈጸሙባት በመሆኗ ድርጅት ወይም ተቋም እንጂ ቤተ ክርስቲያን አትባልም፡፡ በክርስቶስ ደም ወደተመሠረተችው ቤተ ክርስቲያን አንድነት መግባት የሚቻለው በምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን እንጂ በአንድነት ተሰብስቦ ስያሜ በመስጠት እንዳልሆነ ማወቅ ይገባናል፡፡

በኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ መሠረት የቤተ ክርስቲያን አንድነት፥ ክርስቲያኖች በእውነት አምነው በፍቅር ተመላልሰው ከእግዚአብሔር ጋር በሚፈጥሩት አንድነት የሚመዘን ነው፡፡ ይህን አንድነት ሰዎች በጠረጴዛ ዙሪያ ተሰብስበው ወይም የፍርድ ቤት ፈቃድ ይዘው ሊመሠርቱት አይችሉም፡፡ ቤተ ክርስቲያንን የመሠረታት እግዚአብሔር ነውና፡፡ ማንኛውም ሰው የቤተ ክርስቲያን አካል ሆኖ የሚኖረው ወይም ክርስቲያን ነው የሚባለውም በቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ እስካለ ድረስ ብቻ ነው፡፡ የአንድነታችን መሠረቱም በሥጋ ወደሙ የታተመው የክርስቶስ አካልነታችን ነው፤ ጌታ እንዲህ እንዳለ፡- “ሥጋዬን የሚበላ ደሜንም የሚጠጣ በእኔ ይኖራል፤ እኔም በርሱ እኖራለሁ” (ዮሐ. ፮፡፶፮)፡፡ “አባት ሆይ፥ አንተ በእኔ እንዳለህ እኔም በአንተ፥ እነርሱ ደግሞ በእኛ አንድ ይሆኑ ዘንድ እለምናለሁ” (ዮሐ. ፲፯፡፳፩)፡፡ ስለዚህ ቤተ ክርስቲያን ማኅበረሰብ (Society) ሳትሆን የምእመናን አንድነት ናት፡፡ ጌታችንም የዚህች አንድነት ራስ ነው፡፡

በመሆኑም ቤተ ክርስቲያን የክርስቶስን አሠረ ፍኖት ተከትላ የምትሔድና ክርስቶስን የምታምን እርሱ ራስ ሆኖላት አካሉና በእርሱ ውስጥ ያለች ናት፡፡ ክርስቲያኖች የዚች አንድነት አካል የሚሆኑት፣ በአንድነቱ ውስጥ ጸንተው የሚኖሩትና እግዚአብሔርን ወደ መምሰል የሚያድጉት በምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን ነው፡፡ ሲታመሙም (በኃጢአት ሲወድቁም) በእነዚህ ምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን እየታከሙ አንድነታቸውን ያጸናሉ፡፡ ከእርስዋ ውጭ ድኅነት የሌለውም ለዚህ ነው፡፡ “ዋናው በክርስቶስ ማመናችን ነው” ብለው የሚወጡት ሰዎችም ድኅነት እንዳገኙ አድርገው መናገራቸው ከዚህ ኦርቶዶክሳዊ አስተምህሮ ያፈነገጠ ከመሆኑም በላይ ስሕተት ነው፡፡

ክርስቲያኖች በዚህች አንዲት ቤተ ክርስቲያን ስንኖር ከእግዚአብሔር ጋር ያለን አንድነት እያደገ እየጠበቀ ይሔዳል፡፡ ይህ አንድነትም በጊዜ ሒደት፣ ወይም በተለያየ ቦታ በመሆን የሚቋረጥ አይደለም፡፡ ቤተ ክርስቲያን በውስጧ ቅዱሳን መላእክትን እንዲሁም በብሔረ ሕያዋን፣ በብሔረ ብፁዓን፣ በገነት፣ በዐጸደ ሥጋና በዐጸደ ነፍስ ያሉትን ምእመናን ሁሉ የምትይዝ አንዲት ኅብረት ናት ማለታችንም ስለዚሁ ነው (ዕብ. ፲፪፡፳፪-፳፬)፡፡ በዐጸደ ነፍስ ያሉት ምእመናን በንስሓ የተመላለሱ፣ ሩጫቸውን የጨረሱና ድል ያደረጉ ሲሆኑ፥ በዐጸደ ሥጋ ያለን ደግሞ ሩጫችንን ገና ያልጨረስንና በተጋድሎ ውስጥ የምንገኝ ነን፡፡ ሐዋርያው እንዲህ እንዳለ፡- “እንዲሁ ብዙዎች ስንሆን በክርስቶስ አንድ አካል ነን” (ሮሜ. ፲፪፡፭)፡፡ ይህ ትምህርት የነገረ ሃይማኖት መሠረት ነው፡፡ እንዲህ የተባለበትም ምክንያት በቤተ ክርስቲያን ምንነትና ማንነት ላይ ያለን ልዩነት ለጠቅላላ ነገረ ሃይማኖት መለያየት ምክንያት ስለሚሆን ነው፡፡  ይህን የሚያስረዱ ሁለት ማሳያዎችን በማንሣት እንመልከት፡፡

፩. በካቶሊካውያን ዘንድ አንድ ሰው የፖፑን የክርስቶስ እንደራሴነት ካልተቀበለ የካቶሊክ ቤተ እምነት አባል አይሆንም፡፡ በኦርቶዶክሳዊ ትምህርት ግን ቅዱሳን መላእክት እንዲሁም በብሔረ ሕያዋን፣ በብሔረ ብፁዓን፣ በገነት፣ በዐጸደ ሥጋ ያለንና በዐጸደ ነፍስ የሚኖሩ ምእመናን አንድ የምንሆነው በክርስቶስ ኢየሱስ አካልነት ነው፡፡ ይህም በቅዱስ ሥጋውና በክቡር ደሙ የምናገኘው ጸጋ ነው፡፡

፪. በፕሮቴስታንቱ ዓለም ያለውን ስንመለከት ደግሞ በዐጸደ ሥጋ ያሉትና በዐጸደ ነፍስ ያሉት አማኞች የተለያዩ ናቸው፤ እርስ በርሳቸው አይተዋወቁም፡፡ በሌላ አገላለጥ እንደ እነሱ አባባል “ቤተ ክርስቲያን የሚታዩ አባላት ብቻ ያሏት ተቋም ናት”፡፡ የቅዱሳንን ምልጃ የማይቀበሉትም ስለዚሁ ነው፡፡ ይህም ሐዋርያው ጳውሎስ ከላይ ከነገረን (ዕብ. ፲፪፡፳፪-፳፬) የእውነት መሠረት የተለየ ትምህርት ነው፡፡ ዳግመኛም ይህ የፕሮቴስታንቶቹ አስተምህሮ (አይቻልም እንጂ)፥ ስሙ ይክበር ይመስገንና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አንድ ያደረገንን የሚለያይ ነው፡፡ ከዚህም በተጨማሪ እያንዳንዱ ሰው ቤተ ክርስቲያን መባሉን አጉልቶ በመስበክ የምእመናንን አንድነት የሚበታትን ነው፡፡ በኦርቶዶክሳዊው ትምህርት ይህ ፍጹም ስሕተት ነው፡፡ ሐዋርያዊት ከሆነችው ቤተ ክርስቲያን ትውፊት ያፈነገጠ በመሆኑም ተቀባይነት የለውም፡፡ እንዲያውም በቅድስት ቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ ከሚታየው የቤተ ክርስቲያን አካል የማይታየው ይበልጣል፡፡

የቤተ ክርስቲያን የአንድነቷ መሠረት ከላይ እንደገለጽነው ክርስቶስ እንጂ በአንድ ፖፕ ሥር መተዳደር ወይም በዓለም አብያተ ክርስቲያናት ኅብረት ውስጥ አባል መሆን ስላልሆነ ቤተ ክርስቲያን ተቋም ወይም ድርጅት አይደለችም፡፡ ለአገልግሎት መፋጠን የፈጠረቻቸውን ተቋማት በማሰብ ድርጅት ወይም ተቋም የምትመስለን ካለን ተሳስተናል፡፡ ቤተ ክርስቲያን ራሷ ክርስቶስ የሆነላት በሰማይ ያሉ የድል ነሺዎች፣ በምድር ያሉ የክርስቲያኖች ኅብረት ወይም አንድነት ናት፡፡ ይህች አንድነት የሚታይና የማይታይ አካል አላት፡፡ የሚታይ አካል የተባለውም መዋቅሩ ሳይሆን እኛ ራሳችን ክርስቲያኖች እያንዳንዳችንና አንድነታችን ነው፡፡ የማይታየው አካሏ ደግሞ በሰማይ የሚኖሩ ቅዱሳንና እኛ የማናያቸው እግዚአብሔር ብቻ የሚያውቃቸው የቤተ ክርስቲያን አካል የሆኑ ስውራን ናቸው፡፡ አንድ ኦርቶዶክሳዊ ክርስቲያን ከምንም በፊት ይህን ኦርቶዶክሳዊ የነገረ ቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ ማወቅና መረዳት አለበት፡፡

. ቅድስት

መሥራቿ እግዚአብሔር ቅዱስ ስለሆነ ቤተ ክርስቲያንም ቅድስት ናት፡፡ የቤተ ክርስቲያን የቅድስና ምንጭ እግዚአብሔር ነው፡፡ ቅዱስ ማለት የተለየ ማለት እንደሆነ፥ ቤተ ክርስቲያንም ከዓለም ተለይታ የእግዚአብሔርን ማዳን የምትመሰክር ናትና ቅድስት ናት፡፡ በሌላ አገላለጽ ደግሞ “እስመ ኢይትረከብ ነኪር በማዕከሌሃ – ባዕድ በመካከሏ አይገኝምና” እንዲል በሃይማኖት በምግባር የጸኑ ቅዱሳን መሰብሰቢያ ናትና ቅድስት ናት፡፡

እግዚአብሔር እጅግ ቸር ከመሆኑ የተነሣ፥ ሩጫችንን ያልጨረስን ክርስቲያኖች ኃጢአት ብንሠራ እንኳ በንስሓ እየተመላለስን ከምሥጢራቱ እንድንካፈል በማድረግ የድኅነት መንገዱን እንዳንለቅ ቀስ በቀስም ከአርአያ እግዚአብሔር ወደ አምሳለ እግዚአብሔር እንድናድግ አድርጎናል፡፡ ከበደላችን ተመልሰን ከምሥጢራቱ ስንካፈልም ከእግዚአብሔር ጋር እንዋሐዳለን፡፡ ለዚህም ነው ቅዱስ ጴጥሮስ “የእርሱን በጎነት እንድትነግሩ የተመረጠ ትውልድ የንጉሡ ካህናት ቅዱስ ሕዝብ ለርስቱ የተለየ ወገን ናችሁ” ያለን (፩ኛ ጴጥ. ፪፡፱)፡፡ ዳግመኛም ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ “ቅዱሳን ልትሆኑ ለተጠራችሁ” (ሮሜ. ፩፡፯፣ ፩ኛ ቆሮ. ፩፡፪)ያለንም ስለዚሁ ነው፡፡ ስለዚህ ከዚህ ቅድስና የሚያርቀን ክሕደትና ኃጢአት ብቻ ነው ማለት ነው፡፡

አንድ ሰው ቅዱስ ሆኖ ለመኖር በዚህ አንድነት ውስጥ መኖር ይገባዋል፡፡ ከቤተ ክርስቲያን ማለትም ከክርስቶስ ውጪ ቅድስና የለምና ከዚህ አንድነት ከተለየ ምንም ያህል በጎ ምግባር ቢኖረውም ቅዱስ አይባልም፡፡ የቤተ ክርስቲያን ቅድስና ከመሥራቿ ከክርስቶስ ስለሆነ በሰዎች ኃጢአት ቅድስናዋን አታጣም፡፡ አንድ ሰው ወደ ቤተ ክርስቲያን ቢመላለስም በኃጢአት ውስጥ የሚኖር ከሆነ የቤተ ክርስቲያን አካል ነው ማለት አይቻለም፡፡ ምክንያቱም ቤተ ክርስቲያን ቅድስት ስለሆነች እርሱም የቅድስና ሥራ መሥራት ይገባዋልና፡፡ ለዚህ ነው በቅዳሴ ጊዜ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ለተሰበሰቡት ሰዎች ዲያቆኑ “በንስሓ ውስጥ ያላችሁ ራሳችሁን ዝቅ ዝቅ አድርጉ” ሲል ካህኑ በሚያደርጉት ጸሎት ውስጥ “የቀደመ ሥራቸውን ይቅር ብለህ በሰላም ነፍሳቸውን አድን፤ ከቅድስት ቤተ ክርስቲያንህ አንድ አድርጋቸው፡፡ ተቀዳሚ ተከታይ በሌለው በአንድ ልጅህ በጌታችን በአምላካችን በኢየሱስ ክርስቶስ በይቅርታውና በምሕረቱ ከቅድስት ቤተ ክርስቲያን ጨምራቸው” በማለት የሚጸልዩት፡፡ ስለዚህ ማንኛውም ክርስቲያን ቅድስት ከሆነችው አንድነት እንዳይለይ ራሱን ሁልጊዜ በምሥጢራት መቀደስ አለበት ማለት ነው፡፡

. ሐዋርያዊት

ሐዋርያዊት የሚለው ቃል በውስጡ ሦስት መሠረታዊ መልእክታትን የያዘ ነው፡፡ አንደኛው ትርጕም ቤተ ክርስቲያን ሲባል የሐዋርያትን እምነት የሚያስረዳና በዚህም ከመናፍቃንና ከአረማውያን እምነት የተለየች መሆኗን የሚገልጽ ነው፡፡ ሁለተኛው ሐዋርያዊ ውርርስ (ቅብብሎሽ) እንዳላት የሚያስረዳ ነው፡፡ ይህም ማለት አሁን ያለው እውነት ወደኋላ በሔድን ቊጥር ሳይዛነፍ፣ ሳይሸራረፍ፣ በመሀልም የሚቋረጥ መስመር ሳይኖረው ከሐዋርያት ዘንድ እንደሚያደርሰን ያሳያል፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ይህን እምነት በጃንደረባው (ሐዋ. ፰፡፳፮-፵)፥ ሐዋርያዊ ሥልጣኑን ደግሞ በአኀት አብያተ ክርስቲያናት በኵል ተቀብላዋለች፡፡ ሦስተኛውና የመጨረሻው ደግሞ ተልእኮዋን መናገር ነው፡፡ ይህም ማለት ቤተ ክርስቲያን “ሒዱና አሕዛብን ሁሉ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም እያጠመቃችኋቸው ያዘዝኋችሁንም ሁሉ እያስተማራችኋቸው ደቀ መዛሙርት አድርጓቸው” (ማቴ. ፳፰፡፲፱) የሚለውን ትርጕም የያዘ ነው፡፡

በመሆኑም ቤተ ክርስቲያን ሰውን ሁሉ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ለመማረክ ዋና ተልእኮዋ ነው፡፡ አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደዚህ ዓለም የመጣበት ዋናው ዓላማ ሰዎችን ወደ ቀደመ ክብራቸው ለመመለስና ወደ ራሱ መንግሥት ለማምጣት ነው፡፡ ይህን ግብር ስለፈጸመም የሃይማኖታችን ሐዋርያ ተብሏል (ዕብ. ፫፡፩)፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከባሕርይ አባቱ ከአብ ተልኮ ወደዚህ ዓለም እንደመጣ ሁሉ፥ እርሱም ሐዋርያትን ወደ ዓለም ልኳቸዋል፡፡ “አብ እንደላከኝ እኔ ደግሞ እልካችኋለሁ አላቸው፡፡ ይህንም ብሎ እፍ አለባቸውና መንፈስ ቅዱስን ተቀበሉ” (ዮሐ. ፳፡፳፩-፳፪)፡፡ ሐዋርያት ወደ ዓለም ሁሉ በመሔድም የቤተ ክርስቲያንን መሠረት አስቀምጠዋል፡፡ ዳግመኛም በዚህ ምድራዊ አጥቢያ ያለችው ቤተ ክርስቲያን በሰማያት ላለው የእግዚአብሔር መንግሥት በቃልና በገቢር ምስክር ትሆን ዘንድ ስለተላከች ሐዋርያዊት ትባላለች፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

የተወደዳችሁ የማኅበረ ቅዱሳን ድረ ገጽ ተከታታዮች! ይህ ትምህርት፣ ከታኅሣሥ ፩ – ፲፭ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም በታተመው ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ፣ በንቁ ዓምድ ሥር ለንባብ መብቃቱን ለማስገንዘብ እንወዳለን፡፡

አንቀጸ መድኃኒት ቤተ ክርስቲያን  – የመጀመሪያ ክፍል

የካቲት ፳፪ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

ነገረ ቤተ ክርስቲያን ስለ ቤተ ክርስቲያን ያለው ኦርቶዶክሳዊ አስተምህሮ ምን እንደ ሆነ የምንማርበት የትምህርት ዘርፍ ነው፡፡ ምንም እንኳን ትምህርቱ እጅግ ጥልቅና ራሱን የቻለ መጽሐፍ የሚወጣውና ሰፊ አሳቦችን የያዘ ቢሆንም በዚህ ጽሑፍ ግን በተለያዩ አካላት ስለ ቤተ ክርስቲያን የሚነሡ ጥያቄዎችን ለመመለስ ያህል ብቻ በጥቂቱ ለማንሣት እንሞክራለን፡፡ የዚህ ጽሑፍ ዋና ዓላማም ቤተ ክርስቲያን ድርጅት (ተቋም) ዲኖሚኔሽን ናት፤ ከቤተ ክርስቲያን ውጪ ድኅነት ይገኛል፤ ለቤተ ክርስቲያን ስግደት አይገባም፤ ቤተ ክርስቲያን መሔድ አያስፈልግም፤ ቤተ ክርስቲያን ትሳሳታለች፣ ስለዚህ ትታደሳለች፤ ወዘተ” የሚሉ የተሳሳቱ አሳቦችን ለሚያነሡ አካላት መልስ መስጠት ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያን የሚለው ቃል ሦስት ዓይነት ሰዋስዋዊና ዘይቤአዊ ትርጕም አለው (አባ ጎርጎርዮስ ፲፱፻፸፰፣ ገጽ ፲፪-፲፯)፡፡

  • የመጀመሪያው ሕንፃ ቤተ ክርስቲያንን ያመለክታል፡፡ ይኸውም ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ፡- ወደ ማኅበር ስትሰበሰቡ በመካከላችሁ መለያየት እንዳለ እሰማለሁ (፩ኛ ቆሮ. ፲፩፡፲፰) እንዳለው የክርስቲያኖች ቤት፣ የክርስቲያኖች መኖሪያ ማለት ነው፡፡ መንፈስ ቅዱስ ባወቀ የክርስቶስ ደም በነጠበበት የምትተከል፣ በብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት በቅዱስ ሜሮን የከበረች፣ ሥላሴ በአንድነት በሦስትነት የሚመሰገኑባት፣ የክርስቶስ ሥጋዌ የሚነገርባት፣ ሥጋውና ደሙ የሚፈተትባት ቅድስት መካን ቤተ ክርስቲያን ተብላ እንደተጠራች ቅዱሳት መጻሕፍት በስፋት ይገልጻሉ፡፡

ቤተ ክርስቲያን እንሒድ ባሉኝ ጊዜ ደስ አለኝ (መዝ. ፻፳፩፡፩)፤ በቤተ ክርስቲያንም አንድ ዓመት ሙሉ ተሰበሰቡ” (ሐዋ. ፲፩፡፳፮) የሚሉት ንባቦች የቤተ ክርስቲያን አንደኛው ዘይቤአዊ ትርጕም ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን መሆኑን ያስረዳሉ፡፡ ዳግመኛም የእግዚአብሔር ቤት (ዘፍ. ፳፰፡፲፯)፣ በምሕረትህ ብዛት ወደ ቤትህ እገባለሁ (መዝ. ፭፡፯)፣ የአባቴ ቤት (ሉቃ. ፪፡፵፱)፣ የእግዚአብሔር ቤት (ዕብ. ፲፡፳፩) የሚሉት ይህን የሚያስረዱ ማሳያዎች ናቸው፡፡ በተለይም ቅዱስ ጳውሎስ በመንፈስ ለወለደው ልጁ ለጢሞቴዎስ፡- ብዘገይ ግን፣ በእግዚአብሔር ማደሪያ ቤት መኖር እንዴት እንደሚገባ ታውቅ ዘንድ እጽፍልሃለሁ፤ ቤቱም የእውነት ዓምድና መሠረት፣ የሕያው እግዚአብሔር ቤተ ክርስቲያን ነው (፩ኛ ጢሞ. ፫፡፲፭) በማለት የገለጠው የእግዚአብሔር ቤት (ሕንፃ) ቤተ ክርስቲያን እንደሚባል ሁነኛ ማሳያ ነው፡፡

  • ሁለተኛው ደግሞ እያንዳንዱ ምእመን (ክርስቲያን) ቤተ ክርስቲያን የሚባል መሆኑን የሚያስገነዝብ ትርጕም አለው፡፡ ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስ የእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ እንደሆናችሁ የእግዚአብሔርም መንፈስ እንዲኖርባችሁ አታውቁምን? ማንም የእግዚአብሔርን ቤተ መቅደስ ቢያፈርስ እግዚአብሔር እርሱን ያፈርሰዋል፤ የእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ ቅዱስ ነውና፥ ያውም እናንተ ናችሁ (፩ኛ ቆሮ. ፫፡፲፮)፣ “… ወይስ ሥጋችሁ ከእግዚአብሔር የተቀበላችሁት በእናንተ የሚኖረው የመንፈስ ቅዱስ ቤተ መቅደስ እንደ ሆነ አታውቁምን? በዋጋ ተገዝታችኋልና ለራሳችሁ አይደላችሁም፤ ስለዚህ በሥጋችሁ እግዚአብሔርን አክብሩ (፩ኛ ቆሮ. ፮፡፲፱) በማለት የገለጸው ይህን ነው፡፡ ይኸውም በመንፈሳዊና በምሥጢራዊ ልደት ከክርስቶስ የተወለዱ፥ እርሱ አድሮባቸው የሚኖሩ፥ በቅዱስ ሜሮን የታተሙ (፩ኛ ዮሐ. ፪፡፳) እና ሥጋውንና ደሙን የተቀበሉ ምእመናንን ለማመልከት ነው፡፡
  • ሦስተኛው ትርጕም ደግሞ በባቢሎን ያለች ቤተ ክርስቲያን ልጄም ማርቆስ ሰላምታ ያቀርቡላችኋል (፩ኛ ጴጥ. ፭፡፲፫) እንዲል የክርስቲያኖችን ኅብረት ወይም አንድነት (ማኅበረ ምእመናንን) የሚያመለክት ነው፡፡ በሰማይ ያሉ የድል ነሺዎች፣ በምድር ያሉ ከፍትወታት፣ ከኃጣውእና ከርኵሳን መናፍስት ጋር የሚጋደሉ የክርስቲያኖች አንድነትና ኅብረት ማለት ነው፡፡ ይህች ኅብረትና አንድነት ራሷ ክርስቶስ የሆነላት፣ የክርስቶስ አካል ናት፡፡ ኅብረታችንም በደስታ ከተሰበሰቡት አእላፋት መላእክት፣ በሰማያትም ከተጻፉ ከበኵራት ማኅበር፥ የሁሉም ዳኛ ከሚሆን ከእግዚአብሔር፥ ፍጹማንም ከሆኑት ከጻድቃን መንፈሶች (ዕብ. ፲፪፡፳፪-፳፬) ጋር እንደሆነ ቅዱስ ጳውሎስ ነግሮናል፡፡ እኛም በዚህ ክፍል ትኵረት የምናደርገው በዚሁ በሦስተኛው ትርጓሜ ላይ ነው፡፡

እኛ ኦርቶዶክሳውያን በግእዝ ቋንቋ ቤተ ክርስቲያን” የምንለውን ጽርዓውያን (ግሪካውያን) ኤክሌሲያ ይሉታል፡፡ ትርጓሜውም ለአንድነትና ለአንድ ልዩ ዓላማ የተጠሩ ማለት ነው፡፡ ይኸውም ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ፡- ወደ ጌታችን ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ ኅብረት የጠራችሁ እግዚአብሔር የታመነ ነው (፩ኛ ቆሮ. ፩፡፱) ብሎ ከገለጸው ጋር የተስማማ ነው፤ የቤተ ክርስቲያን ዓላማ ሰዎችን ወደ እግዚአብሔር አንድነትና ሰማያዊ ዓላማ በሃይማኖት መጥራት ነውና፡፡ ግሪኮች ኤክሌሲያ” የሚለውን ቃል መጀመሪያ አንድን ፖለቲካዊ፣ ማኅበራዊ ወይም አስተዳደራዊ ችግር ለመፍታት ለተሰበሰቡ ሽማግሌዎች መጠሪያ ይጠቀሙበት ነበር፡፡ በ፪፻፹፬ ከክርስቶስ ልደት በፊት ብሉይ ኪዳንን ከዕብራይስጥ ወደ ጽርዕ የተረጐሙት ሰብዓ ሊቃናት ግን ቀሃል የሚለውን የዕብራይስጥ ቃል ኤክሌሲያ” ብለው ተርጕመውታል፡፡ ትርጕሙም የእስራኤልን ጉባኤ የሚገልጽ ነው፡፡ እንደ ምሳሌም የሚከተሉትን ኃይለ ቃላት እንመልከት፤

ማኅበሩንም ሁሉ ወደ መገናኛው ድንኳን ደጃፍ ሰብስባቸው (ዘሌ. ፰፡፫)፡፡ እዚህ ላይ ማኅበሩ ተብሎ የተገለጠው በምሥጢር ስለዚህች ጉባኤ ነው፡፡ በዚህች ጉባኤም አሮን ሊቀ ካህን ሆኖ ተሾሟል (ዕብ. ፭፡፬)፡፡ ቅዱስ ቄርሎስ ዘኢየሩሳሌም እንዳስተማረው፥ ይህ የአይሁድ ጉባኤ የቤተ ክርስቲያን አምሳል፣ መርገፍ ወይም ጥላ ነበር (The Catechetical Lectures of St. Cyril, Archbishop of Jerusalem, P. 335)፡፡ እንደ ሊቁ አስተምህሮ አብዛኞቹ አይሁዳውያን በጌታችንና በመድኃኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ የባሕርይ አምላክነት ባለማመናቸው ምክንያት ከዚሁ ጉባኤ ቢወጡም ጉባኤው ግን አልተበታተነም፤ ሊበታተንም አይችልም፡፡ ይልቁንም ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ፡- በዚህም ዓለት ላይ ቤተ ክርስቲያኔን (ጉባኤዬን) እሠራለሁ፤ የገሃነም ደጆችም አይችሏትም (ማቴ. ፲፮፡፲፰) በማለት በኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ጉባኤ አጸናት እንጂ፡፡

ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ምንም በሰዎች አመለካከት የተለያየ ዓይነት ስያሜ (እንደ አይሁዳውያኑና አሁን እንደምንሰማው ብዙ ስም) ቢሰጠውም ይህ የሰዎች የተሳሳተ ግንዛቤ የባሕርይ አምላክነቱን ሊለውጠው አይችልም፡፡ ቤተ ክርስቲያን የገሃነም ደጆች አይችሏትም የሚለው ኃይለ ቃልም ይህን ጥልቅ ነገረ ሃይማኖታዊ ጽንሰ ሐሳብ በውስጡ የያዘ ነው፡፡ በኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ መሠረት ይህቺ ጉባኤ (ቤተ ክርስቲያን) በቅድስት ሥላሴ ባለው እምነቷ ህልውናዋን የጀመረችው በዓለመ መላእክት ማለትም ሰው ከመፈጠሩ በፊት ነው፡፡ ከዚያም ከአቤል ጀምሮ እስከ ሐዲስ ኪዳን መግቢያ ድረስ በነበረው የደጋግ ሰዎች አንድነት ቀጠለች፡፡

በቅዳሴያችን እግዚአብሔር ይስማዕከ ኵሎ ዘሰአልከ ወይትወከፍ መሥዋዕተከ ወቊርባነከ ከመ መሥዋዕተ መልከ ጼዴቅ ወአሮን ወዘካርያስ ካህናተ ቤተ ክርስቲያኑ ለበኵር፤ እግዚአብሔር የለመንኸውን ሁሉ ይስማህ፤ የቀደመችዋ ቤተ ክርስቲያን ካህናት የሚሆኑ የመልከ ጼዴቅንና የአሮንን የዘካርያስንም መሥዋዕት እንደተቀበለ መሥዋዕትህን ቊርባንህንም ይቀበልልህ የሚለው ንባብ የቤተ ክርስቲያን ህልውና ግእዛን ያላቸው ፍጥረታት ከተፈጠሩበት ጊዜ ጀምሮ እንደሆነ የሚያስገነዝብ ነው፡፡ በመጨረሻ ከላይ እንደገለጥነው በክርስቶስ ደም ጸናች፡፡ አሁንም ይህ ጉባኤ ከሥላሴ ጋር ያለው ግንኙነት ዘወትር አይቋረጥም፡፡

ቤተ ክርስቲያን ጉባኤ ናት ሲባል ግን አንዳንዶች እንደሚሉት እንዲሁ የሰዎች ስብስብ ሳትሆን የምርጦች ስብስብ ናት፤ የተጠሩ ብዙ የተመረጡ ግን ጥቂቶች ናቸውና (ማቴ. ፳፡፲፮)፡፡ እነዚህ ጥቂትና የተመረጡትም የልጅነት ሥልጣን የተሰጣቸው (ዮሐ. ፩፡፲፫)፣ እግዚአብሔርን በአንድነቱና በሦስትነቱ የሚያመልኩ፣ ክርስቶስ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ (ማቴ.፲፮፡፲፮) በሚል ጽኑዕ መሠረት የታነፁ ናቸው እንጂ እንዲሁ በአንድ ቤት ውስጥ የተሰበሰቡ ሰዎች አይደሉም፡፡ ቤተ ክርስቲያን አካለ ክርስቶስና ሕያዊት ናት (ኤፌ. ፩፡፳፪-፳፫)፡፡ የክርስቶስ ሙሽራ (መኃ. ፭፡፩፣ ዮሐ. ፫፡፳፱፣ ራእ. ፳፩፡፱)፣  የእግዚአብሔር ሕያው ቤተ መቅደስ (ኤፌ. ፪፡፳፩)፣ የእውነት ዓምድና መሠረት (፩ኛ ጢሞ. ፫፡፲፭) ትባላለች፡፡

እነዚህ ስያሜዎች ቅድስት ቤተ ክርስቲያን መለወጥ የማይስማማው የአምላካችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ አካል መሆኗን በግልጽ ያስረዳሉ፡፡ የክርስቶስ አካል ስለሆነች አትሳሳትም፣ አትለወጥም፡፡ ትምህርቷም ከአምላኳ ከእግዚአብሔር የተቀበለችውና በመንፈስ ቅዱስ የሚጠበቅ ስለሆነ ስሕተትና ነቅ አይገኝበትም፡፡ ቤተ ክርስቲያን ትክክል ለመሆኗ ማስረጃችን መጽሐፍ ቅዱስ ሲሆን መጽሐፍ ቅዱስ የእግዚአብሔር ቃል ለመሆኑ ደግሞ ምስክሯ ቤተ ክርስቲያን ናት፡፡ ብዙ ልዩ ልዩ የእግዚአብሔር ጥበብ አሁን በቤተ ክርስቲያን በኩል በሰማያዊ ስፍራ ውስጥ ላሉት አለቆችና ሥልጣናት ትታወቅ ዘንድ (ኤፌ. ፫፡፲) የሚለው የቅዱስ ጳውሎስ ቃል ለዚህ ሁነኛ ማስረጃ ነው፡፡

ኢየሱስ ክርስቶስ ራሷ የሆነላት ቤተ ክርስቲያን አርጅታለች ትታደስ፣ ተሳስታለች ትመለስ አትባልም፡፡ እንዲህ ማለት ክርስቶስን ማረም፣ ክርስቶስን ማስተካከል ይሆናልና፡፡ አምላካችን ደግሞ መለወጥ የማይስማማው ፍጹም አምላክ መሆኑን በነቢዩ በሚልክያስ አድሮ እኔ እግዚአብሔር አልለወጥም (ሚል. ፫፡፮) በማለት የነገረን ሲሆን፤ ቅዱስ ጳውሎስም ኢየሱስ ክርስቶስ ትናንትና ዛሬ እስከ ዘለዓለምም ያው ነው። ልዩ ልዩ ዓይነት በሆነ በእንግዳ ትምህርት አትወሰዱ(ዕብ. ፲፫፡፰-፱) ብሎ በየጊዜው የሚሻሻል አዲስ ትምህርት እንደሌላት አስረግጦ ነግሮናል፡፡

ቅዱስ ያሬድ በድጓው አንቀጸ መድኃኒት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን እምነ ይእቲ ንበላ በሐ ወይእቲ ትኩነነ መርሐቅድስት ቤተ ክርስቲያን የድኅነት በር ናት፤ እናታችን ናት፤ ለድኅነታችን መንገድ መሪ እንድትሆነን ሰላም እንበላት በማለት የድኅነት በር እንደሆነችና ለእርሷ ሰላምታ ማቅረብ እንደሚገባን ይነግረናል (ጾመ ድጓ ዘቅድስት)፡፡ በጾመ ድጓ ዘዘወረደም ላይ እንዲሁ አመ ኖኅ ይእቲ መድኃኒት እንተ ኮነት አንቀጸ ሕይወት ቤተ ክርስቲያን ቅድስትክብርት የምትሆን ቤተ ክርስቲያን ከኖኅ ዘመን ጀምሮ የሕይወት መንገድ (በር) ናት በማለት ብቸኛዋ የድኅነት በር እንደሆነች ያስረዳናል፡፡

በሉቃስ ወንጌል ምዕራፍ ፲ ላይ የተጠቀሰው በወንበዴዎች የተደበደበው ሰው የተወሰደባት የእንግዶች ማረፊያ የቤተ ክርስቲያን ምሳሌ ናት፡፡ በደጉ ሳምራዊ የተመሰለው ክርስቶስ አዳምን ለማዳን የፈጸመውን ማዳን በምሥጢራት በማደል ሰዎችን ከቁስለ ኃጢአት እንድትፈውስ ሥልጣን የተሰጣት ቤተ ክርስቲያን ናት፡፡ መድኃኒትነቷም የክርስቶስን ሥጋና ደም በመፈተትና በማቀበል ነው፡፡ ምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን ከቤተ ክርስቲያን ውጪ አይፈጸሙም፡፡ ሰው ደግሞ ሳይጠመቅና ሥጋ ወደሙን ሳይቀበል የክርስቶስ አካል፣ የመንግሥተ ሰማያት አባል መሆን አይችልምና ቤተ ክርስቲያን መሔድ የግድ የሚያስፈልገው ለዚህ ነው፡፡

ወደ ቤተ ክርስቲያን የምንሔደው እግዚአብሔር ሌላ ቦታ ሆነን ብንጸልይ ስለማይሰማን ሳይሆን ያለ ምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን የክርስቶስ ድኅነት ተሳታፊ ስለማንሆንና እነዚህን ምሥጢራት ደግሞ ከቤተ ክርስቲያን ውጪ ማግኘት ስለማንችል ነው፡፡ ስለዚህ ቤተ ክርስቲያን የምታምነውን ሳያምኑ፣ በምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን የክርስቶስ አካል ሳይሆኑ ድኅነት የለም፡፡ በአጠቃላይ ከክርስቶስ ውጪ የሆነች ቤተ ክርስቲያንን፣ ከቤተ ክርስቲያን ውጪ የሚገኝ ድኅነት የለም፡፡

የቤተ ክርስቲያን ባሕርያት

ቤተ ክርስቲያን አራት ባሕርያት አሏት፡፡ እነዚህ ባሕርያቷ እንዲሁ የተጠራችባቸው ሳይሆኑ እጅግ ጥልቅ የሆነ የነገረ ሃይማኖትን ትምህርት የሚያስረዱ ናቸው፡፡ እነዚህም በጸሎተ ሃይማኖታችን ሁልጊዜ የምንመሰክራቸው ናቸው “… ከሁሉ በላይ (ኵላዊት) በምትሆን (፩) ሐዋርያት በሰበሰቧት (፪) በአንዲት (፫) ቅድስት (፬) ቤተ ክርስቲያን እናምናለን፡፡”

. ኵላዊት

ቤተ ክርስቲያን ኵላዊት ናት ሲባል በብዙዎቻችን ልቡና የሚመጣው በሁሉም ቦታ፣ በሁሉም ስፍራ፣ ለሁሉም ሰው ያለች የሚል ትርጓሜው ነው፡፡ ርግጥ ነው ቤተ ክርስቲያን በሁሉም ቦታ፣ በሁሉም ስፍራ፣ ለሁሉም ሰው አለች፡፡ ነገር ግን በኦርቶዶክሳዊ አስተምህሮ ቤተ ክርስቲያን ኵላዊት ናት ሲባል ከዚህ ያለፈ (የላቀ) ትርጓሜ አለው፡፡ ኵላዊት የሚለው ቃል ከብዛት ይልቅ ርቀትንና ምልዐትን፣ ርቱዕነትን፣ እውነተኛነትን፥ ፍጹምነትን የሚያመለክት ቃል ነው፡፡ ስለዚህ ቤተ ክርስቲያን ኵላዊት ናት ስንል ፍጽምት ናት፤ ሁሉንም የምትይዝ ናት፤ ምንም የሚጐድላት ነገር የለም ማለታችን ነው፡፡

ቤተ ክርስቲያን እንደ አሁኑ በዓለም ሁሉ ከመስፋፋቷ በፊት እንኳን ኵላዊት ትባል ነበር፡፡ የኢየሩሳሌም የአንጾኪያ፣ የኤፌሶን፣ የቆሮንቶስ፣ የሮም አብያተ ክርስቲያናት ኵላዊት ይባሉ ነበር፡፡ ቤተ ክርስቲያን ኵላዊት መባሏ ከቦታ ወይም ከቊጥር አንጻር ሳይሆን የክርስቶስ አካል በመሆኗ ያገኘችው ነው፡፡ ዳግመኛም ቤተ ክርስቲያን ኵላዊት የምትባለው ከእግዚአብሔር የተገኘች የሐዋርያት ትምህርታቸው፣ የክህነት ውርሳቸው (ቅብብሎሽ) ስላላት ነው፡፡ ኵላዊት ናት ስንል ምልዕትና ፍጽምት ናት ማለት ነው፡፡ የማትታደሰውም፣ የማትለወጠውም ከዚህ የተነሣ ነው፡፡ ክርስቶስ ራስ የሆነላት ሕያዊትና ፍጽምት አካሉ ናትና፤ እግዚአብሔር እንደማያረጅ እርስዋም አታረጅምና የሚገቡባትን ታድሳለች እንጂ አትታደስም፡፡

ይቆየን

ይህ ጽሑፍ፣ ከታኅሣሥ ፩ – ፲፭ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም በታተመው ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ፣ በንቁ ዓምድ ሥር ለንባብ መብቃቱን ለማስገንዘብ እንወዳለን፡፡

ታቦተ እግዚአብሔርን ከጣዖት ጋር አንድ የሚያደርግ ማን ነው? (፪ኛ ቆሮ. ፮፥፲፮)

በማኅበረ ቅዱሳን ትምህርተ ወንጌልና ሐዋርያዊ አገልግሎት ማስተባበሪያ

በስብከተ ወንጌል ማስፋፊያ ዋና ክፍል የተዘጋጀ

የካቲት ፳ ቀን ፳፻፲ .

‹ታቦት› ማለት ‹የእግዚአብሔር ክብር መገለጫ፣ የእግዚአብሔር የክብሩ ዙፋን› ማለት ነው፡፡ እግዚአብሔር አምላክ ሙሴን በታቦት ላይ ኾኖ ያነጋግረው ነበር (ዘፀ. ፳፭፥፳፪፤ ዘኍ. ፯፥፹፱)፡፡ ሕገ እግዚአብሔር በወረቀት ላይ መጻፍ ሲጀምር ብዙ ምሥጢራት በእግዚአብሔር አንደበት ለሊቀ ነቢያት ሙሴ ተነግረዋል፡፡ ነቢዩ ሙሴ ከእግዚአብሔር ጋር ቃል በቃል ከተነጋገረባቸው አንዱ ምሥጢር ደግሞ ‹‹እንደ ቀደመው የድንጋይ ጽላት ቅረፅ›› የሚለው ትእዛዝ ነው፡፡ ኃይለ ቃሉም ‹‹እግዚአብሔር ሙሴን አለው፤ ሁለት የድንጋይ ጽላት እንደ ፊተኛው አድርገህ ቅረፅ፤ ወደ እኔም ወደ ተራራው ውጣ፡፡ በሰበርሃቸው በፊተኞቹ ጽላቶች የነበሩትን ቃላት እጽፍባቸዋለሁ፤›› የሚል ነው (ዘፀ. ፴፬፥፩-፪)፡፡ ከመጽሐፍ ቅዱሱ ንባብ ውስጥ በማያሻማ መልኩ እንደ ተመለከትነው ሙሴ በቀደሙት ጽላቶች ፈንታ ሌላ ጽላት እንዲቀርፅ ትእዛዝ ተሰጥቶታል፡፡ ዝቅ ብሎም ‹‹ሙሴም ሁለት ጽላት እንደ ቀደመው አድርጎ ቀረፀ›› በማለት ይደመድማል (ዘፀ.፴፬፥፬)፡፡

እንግዲህ ይህን ቃል እንዲሁ በዓይነ ሥጋም ኾነ በዓይነ ልቡና (ነፍስ) ለተመለከተው እግዚአብሔር በአንደበቱ ‹‹ታቦት ቅረፅ›› ብሎ ለሙሴ ሲናገር፣ ሙሴም ‹‹አሜን›› ብሎ ትእዛዙን ሲፈጽም ያሳያል፡፡ ይህም ብዙ ምሥጢር እንዳለው ግልፅ ነው፡፡ ለምን ቢሉ? አንደኛ ታቦት እንዲቀርፅ ሙሴ መታዘዙ ታቦት ለጊዜው ለእስራኤል ዘሥጋ የሥርዓተ አምልኮ መፈጸሚያና መማጸኛ እንዲኾን ነው፡፡ ሁለተኛ የፊተኛው ታቦት ከተሰበረ በኋላ ሁለተኛ ታቦት እንዲቀርፅ ሙሴ መታዘዙ ታቦት በቅዱሳን ስም እየተቀረፀ ለትውልደ ትውልድ እንደሚተላለፍ ለመግለጽ ነው፡፡ በሌላ አነጋገር የቀደሙት ጽላቶች በጣዖት ምክንያት ከተሰበሩ በኋላ ዳግመኛ እንዲቀረፁ ማዘዙ ታቦት አንድ ጊዜ ብቻ ለአምልኮት የሚፈለግ ከዚያ በኋላ የሚጣል እንዳልኾነ ለማስተማር ነው፡፡ የዚህ ዂሉ የምሥጢር መሠረት ግን ታቦቱ በብሉይም ኾነ በሐዲስ ኪዳን እስከ ወዲያኛው ሊኖር ከእግዚአብሔር መሰጠቱን እንድናውቅ ይረዳናል፡፡ ይህም ‹‹እንደ ቀደሙት ዂሉ ዐሠርቱ ቃላትን በዚህ ላይ እጽፋለሁ›› ማለቱ ነው፡፡

ስለዚህ በብሉይም ኾነ በሐዲስ ኪዳን ታቦቱ ላይ ዐሥሩ ቃላት መኖራቸው ነው፡፡ ከዐሥሩ ቃላት አንዱ ደግሞ ‹‹ከእኔ በቀር ሌሎች አማልክት አይኑሩህ›› የሚለው ትእዛዝ አንደኛው ነው (ዘፀ. ፳፥፫)፡፡ ከታቦቱ ላይ የእግዚአብሔር እንጂ የጣዖት ስም አልተጻፈበትምና፡፡ ለታቦት መስገዳችንም ይህን ሥርዓተ ምሥጢር በማወቅ እንጂ ባለማወቅ ለቅርፃ ቅርፅ ወይም ለጣዖት እየሰገድን አምልኮ ባዕድ እየፈጸምን አይደለም፡፡ እንግዲህ ስሙ ስመ አምላክ ከኾነ፣ ትእዛዙም ጣዖታዊ ሳይኾን አምላካዊ ከኾነ፣ በእግዚአብሔር ቃል አንደበት ታቦት እንዲቀርፅ ለሙሴ መለኮታዊ ትእዛዝ ከታዘዘ፣ ታቦት የስሙ ማረፊያ ኾኖ ሊኖር እንጂ በዘመን ሊሻር የሚችል አይደለም፡፡ ለምን ቢሉ በሊቀ ነቢያት ሙሴ ጊዜም ኾነ ዛሬ ከታቦቱ ላይ የታተመው ስመ አምላክ (የአምላክ ስም) ነውና፡፡

ሊቀ ነቢያት ሙሴ በተሰጠው ታቦት አምልኮተ እግዚአብሔርን ሲፈጽምበት ኑሮ ዐረፈ፡፡ ከእርሱ ቀጥሎ ኢያሱም እንደ ሙሴ ካህናቱን ታቦት አሸክሞ ወደ ምድረ ርስት ገባ፡፡ በኋላም ዳዊት ከአቢዳራ ቤት ወደ ኢያቡስ አስመጥቶ በቃል ኪዳኑ ታቦት ፊት ዘመረ፡፡ (ኢያ. ፫፥፩-፲፯፤ ፪ኛ ሳሙ. ፮፥፲-፲፪)፡፡ ቤተ አቢዳራ (የአቢዳራ ቤት) በታቦቱ እንደ ከበረ ዳዊትም በታቦቱ ሊከብር መፈለጉ የታቦቱን ክብር በመንፈሰ ትንቢት በማወቁ ነው፡፡ ስለዚህ ከሙሴ እስከ ዳዊት፣ ከዳዊት እስከ ልደተ ክርስቶስ ታቦት የእግዚአብሔር የክብሩ መገለጫ ኾኖ ሲሰገድለት ኑሯል፡፡ ወደፊትም በዚህ ሥርዓት ይቀጥላል፡፡

በሐዲስ ኪዳን ጌታችን አምላካችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሰውን ሥጋ ተዋሕዶ፣ በመስቀል ተሰቅሎ፣ በከርሠ መቃብር ሦስት መዓልትና ሦስት ሌሊት አድሮ፣ ከሙታን ተነሥቶ ወደ ዙፋኑ ሲያርግ ዐረገ፡፡ ከዚህ በኋላ አበው ሐዋርያት ወንጌልን አስተማሩ፡፡ በአንድ ቀን ትምህርት በእልፍ የሚቈጠሩ ምእመናን አመኑ፡፡ ከእነዚህ ውስጥ የቆሮንቶስ ምእመናን በቀዳሚነት ይጠቀሳሉ፡፡ እነዚህ የቆሮንቶስ ምእመናንም አምነው ከተጠመቁ፣ ከጨለማ ከወጡ በኋላ የለመዱት ልማድ እንዲህ ቶሎ ሊለወጥ አይችልምና በቅዱስ ጳውሎስ መዋዕለ ስብከት እየሾለኩ ወደ ቤተ ጣዖት መሔዳቸው አልቀረም፡፡

ይህን የተረዳው ቅዱስ ጳውሎስ የታቦትን ቅዱስነት የጣዖትን ርኩስነት ሲገልጽ ታቦቱን ‹‹ታቦተ እግዚአብሔር›› ብሎ ጣዖቱን ‹‹ርኩስ›› በማለት ገለጸው፡፡ ይኸውም ‹‹የእግዚአብሔርን ታቦት በጣዖት ቤት ውስጥ የሚጨምር ማን ነው?›› (፪ኛ ቆሮ. ፮፥፲፮) ብሎ ካነጻጸረ በኋላ ወደ ጣዖት የሚገሰግሱ ባዕዳንን ሲመክር ደግሞ ‹‹ወደ ረከሱት አትቅረቡ›› ሲል መክሯቸዋል፤ አስተምሯቸዋል፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ‹‹ርኩስ›› ብሎ  የነቀፈው ጣዖቱን ሲኾን፣ ‹‹ታቦተ እግዚአብሔር›› ብሎ የገለጸው ደግሞ ታቦቱን ነው፡፡ እንግዲህ ታቦትና ጣዖት በቅዱስ ጳውሎስ አንደበት እንዲህ የሰማይና የምድርን ያህል ርቀት አላቸው፡፡

በሐዲስ ኪዳን ታቦት አያስፈልግም ለሚሉ ዂሉ ይህ ‹‹ታቦተ እግዚአብሔር›› ተብሎ በቅዱስ ጳውሎስ አንደበት የተመሰከረለት ታቦት ለመኖሩ በቂ ምስክር ነው፡፡ በሌላ አገላለጽ በቅዱስ ጳውሎስ ዘመን ጣዖት እንደ ነበረ ታቦትም ነበረ፡፡ ነገር ግን አለፈ ብሎ በማስተማር ፈንታ ታቦቱን ከጣዖት ክርስቶስን ከቤልሆር ለይቶ አያስተምርም ነበር፡፡ እርሱ ግን ‹‹ክርስቶስና ቤልሆር በማንኛውም ነገር ኅብረት እንደሌላቸው ታቦትና ጣዖትም እንዲሁ ናቸው›› ብሎ ታቦቱን ‹‹ታቦተ እግዚአብሔር››፣ ጣዖቱን ‹‹ርኩስ›› ብሎ ለይቶ አስተማረ፡፡ እንግዲህ ይህ ቃል አማናዊ እንጂ የምሳሌ ትምህርት ስላልኾነ በብሉይም ኾነ በሐዲስ ኪዳን  ታቦት መኖሩን በሚገባ ያስረዳል፡፡ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ታቦቱ መኖሩ በዚህ ቃል መሠረት ነው እንጂ አላዋቂዎች እንደሚሉት በስሕተት አይደለም፡፡

ታቦቱ ላይ ስመ አምላክ ታትሞበታል፡፡ ስመ አምላክ የታተመበት እንዴት ‹‹ቅርፅ ቅርፅ›› ተብሎ ሊጠራ ይችላል? እርግጥ ነው ራሱ እግዚአብሔር ታቦት እንዲቀርፅ ‹‹እንደ ቀደመው አድርገህ ቅረፅ›› በማለት ሙሴን አዝዞታል (ዘፀ. ፴፬፥፩-፪)፡፡ ታቦቱ ስመ አምላክ ከተጻፈበት በኋላ ታቦት እንጂ ‹‹ቅርጻ ቅርፅ›› ተብሎ በመጽሐፍ ቅዱስ አልተመዘገበም፡፡ ቅርፃ ቅርፅ የሚባለው ስመ አምላክ ያልተጻፈበት ተራ ነገር ነው፡፡ ቅዱስ ጳውሎስም አክብሮ ‹‹ታቦተ እግዚአብሔር›› ብሎ ጠራው እንጂ ‹‹ቅርፃ ቅርፅ›› ብሎ አላሳነሰውም፡፡ ለምን ቢሉ ስሙ ታትሞበታልና ነው፡፡ እግዚአብሔር ደግሞ ስሙን በወደደው ላይ ጽፎ ማስተማር ይችላልና፡፡ እግዚአብሔር ለሙሴ ሲነግረው ‹‹በመንገድህ ይጠብቅህ ዘንድ ወዳዘጋጀሁትም ሥፍራ ያገባህ ዘንድ እነሆ እኔ መልአኬን በፊትህ እሰዳለሁ፤ በፊቱም ተጠንቀቁ፡፡ ቃሉንም አድምጡ፡፡ ስሜም በእርሱ ስለ ኾነ ኀጢአት ብትሠሩ ይቅር አይልምና አታስመርሩት›› ብሎታል (ዘፀ. ፳፫፥፳-፳፪)፡፡

በዚህ ኹኔታ ስንመለከተው ደግሞ ታቦቱ ላይ ስሙ ታትሞበታል፡፡ ስሙ የታተመው ደግሞ የምናመልከው እግዚአብሔር ለመኾኑና የምንሰግደውም ለስመ እግዚአብሔር እንጂ ለሌላ እንዳልኾነ ምስክር ሊኾነን ነው፡፡ እናም አምላካችን እግዚአብሔር የቃል ኪዳኑን ታቦት ለሙሴ ሲሰጠው ታቦቱ ላይ ስሙ ተጽፎ ነበር፡፡ ይህም የክብሩ መገለጫ ሊኾን  እስራኤል ዘሥጋ ስሙን እየጠሩ እንዲያመልኩት ነው፡፡ ዛሬም በሐዲስ ኪዳን ለታቦት እንሰግዳለን፤ ስሙ ተጽፎበታልና፡፡ አምልኮ ባዕድ አልፈጸምንም፡፡ ‹‹ወንሰግድ ውስተ መካን ኀበ ቆመ እግረ እግዚእነ፤ የጌታችን እግር በቆመበት ዂሉ እንሰግዳለን›› ብሎ ቅዱስ ዳዊት እንዳስተማረን (መዝ. ፻፴፩፥፯)፡፡ ምክንያቱም ታቦት እግዚአብሔር በጸጋ፣ በረድኤት የሚያድረበትና የሚገለጽበት ነውና (ዘፀ. ፳፭፥፳፪፤ ዘኍ. ፯፥፹፱)፡፡

በዘመነ ኦሪት የእግዚአብሔር ታቦት የሥርዓተ አምልኮ መፈጸሚያ ኾኖ አግልግሎት ሰጥቷል፡፡ ይኸውም ስመ እግዚአብሔር ስለ ተጻፈበት ነው፡፡ በሐዲስ ኪዳንም ታቦተ እግዚአብሔር የሥርዓተ አምልኮ መፈጸሚያ ነው፡፡ ለምን ቢሉ ስመ እግዚአብሔር ተጽፎበታልና ነው፡፡ ዛሬም በሕገ ወንጌል ክብሩ ሊገለጽ የሚችለው ስመ እግዚአብሔር ስለ ተጻፈበት ነው፡፡ ስመ እግዚአብሔር ደግሞ ትናንት በብሉይ ኪዳን ዛሬም በሐዲስ ኪዳን አንድ ነው፡፡ አንድ ነው ማለትም ያው ስሙ ሌላ እርሱ ሌላ አይደለም ማለት ነው፡፡ እናም ዛሬም ኾነ ነገ ስመ እግዚአብሔር መጥራት ለስሙ መስገድ ሃይማኖታዊ ምሥጢራችን ነው፡፡ ‹‹በሰማይም ኾነ በምድር ለስሙ ጕልበት ዂሉ ይንበረከካል፤ ይሰግዳል›› ተብሎ እንደ ተጻፈ (ፊል. ፪፥፲)፡፡ እስራኤልም በታቦቱ ፊት ስግደት ያቀርቡ ነበር (ኢያ. ፯፥፮)፡፡

ሕዝበ እስራኤል ታቦቱን ለማክበር ሲሉ ካህናቱ ታቦቱን ተሸክመው ሲሔዱ ሕዝቡ ከታቦቱ ሁለት ሺ ክንድ ያህል ይርቁ ነበር (ኢያ. ፫፥፬) ዛሬ በቤተ ክርስቲያናችን ምእመናን ለእግዚአብሔር ክብር ሲሉ ከታቦቱ ራቅ ይበሉ የሚባለው ከዚህ የተነሣ ነው፡፡ ሰሎሞን ታላቁን ቤተመቅደስ ከሰራ በኋላ ታቦቱን በታላቁ ቤተመቅደስ ውስጥ በክብር አስቀምጦታል (፩ኛ ነገ. ፰፥፮)፡፡ ከዚያም አገልግሎቱ ቀጥሏል፡፡ የዚህ ታቦት ክብር በሐዲስ ኪዳን በሰማይ ታይቷል (ራእ. ፲፩፥፲፱)፡፡ በእግዚአብሔር ዘንድ በተለይ በሐዲስ ኪዳን የታቦት ክብር በምድር ብቻ ሳይኾን ሰማያዊ ኾኗል፤ ‹‹የእግዚአብሔር ታቦት በሰማይ ታየ›› ተብሎ እንደ ተጻፈ (ራእ. ፲፩፥፲፱)፡፡ ይኸውም ከብሉይ ኪዳን ዘመን ይልቅ በሐዲስ ኪዳን ዘመን የታቦት ክብር እጅግ የበለጠ መኾኑንና በሐዲስ ኪዳን ልንገለገልበት እግዚአብሔር የፈቀደ መኾኑን ያመለክታል፡፡ እግዚአብሔር ባይፈቅድ ኖሮ ክብሩን በሰማይ አይገልጽም ነበርና፡፡

በሐዲስ ኪዳን ደግሞ ታቦት ማለት ለዓለም ራሱን መሥዋዕት አድርጎ የሰጠ ለአምላካችንና ለመድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቅዱስ ሥጋ እና ክቡር ደም የክብር ዙፋን (መሠዊያ) ነው፡፡ በታቦቱ ላይ የሚጻፈውም ቃልም ‹‹አልፋ ዖሜጋ›› (ፊተኛውና ኋለኛው፤ መጀመሪያውና መጨረሻው የዘላለም አምላክ) የሚለው ቅዱስ ስሙ ነው (ራእ. ፳፪፥፲፫)፡፡ በታቦቱ ፊትም የሚሰገደው ለዚህ ቅዱስ ስም ነው፡፡ ‹‹በላይ በሰማይ፣ በታች በምድር የማናቸውንም ምሳሌ እና ቅርፅ በፊትህ አታድርግ፤ አትስገድላቸውም፤›› (ዘፀ. ፳፥፬-፭) የመሳሰሉትን ኃይለ ቃላት በመጥቀስ ታቦት፣ ሥዕል፣ መስቀል አያስፈልግም የሚሉ ሰዎች አሉ፡፡ ኾኖም ይህ ኃይለ ቃል በእግዚአብሔር ፈንታ ለሚመለክ ጣዖት እንጂ የክብሩ መገለጫ ለኾነው ታቦትና እርሱ ፈቅዶ ለሰጠን የቅዱሳን ሥዕልና መስቀል የሚጠቀስ አይደለም፡፡

በተመሳሳይ መልኩ በትንቢተ ኤርምያስ ፫፥፲፮ ላይ ‹‹ከእንግዲህ የእግዚአብሔርን ታቦት ብላችሁ የማትጠሩበት ጊዜ ይመጣል›› ተብሎ ስለ ተጻፈ በሐዲስ ኪዳን የእግዚአብሔር ታቦት ብለን መጥራት የለብንም የሚሉ ሰዎችም አሉ፡፡ ነቢዩ ኤርምያስ ይህን ቃል የተናገረው ለእስራኤል ነው፡፡ እስራኤል ከእግዚአብሔር ጋር የሚገናኙበትን፣ ጠላትን ድል የሚያደርጉበትን፣ ከእግዚአብሔር በረከት የሚያገኙበትን የቃል ኪዳን ታቦቱን እየተዉ ወደ አምልኮ ጣዖት ተመለሱ፡፡ በዚህ ጊዜ ግልጥ አድርጎ ከባቢሎን ናቡከደነፆር ይመጣል፤ ኢየሩሳሌምን ይወራል፡፡ ቤተ መቅደሱን ያፈርሳል፡፡ እናንተንም ማርኮ ወስዶ ሰባ አመት ይቀጠቅጣችኋል ብሎ ትንቢት ተናገረባቸው፡፡ የተናገረው አልቀረም፤ ናቡከደነፆር መጣ፤ ኢየሩሳሌምም ተወረረች፤ ቤተ መቅደሱም ፈረሰ፤ ንዋያተ ቅድሳቱም ተዘረፉ፤ እስራኤልም ተማረኩ፡፡ አሁን በሰው አገር ጠላትን ድል የሚያደርጉበት፣ ከእግዚአብሔር የሚገናኙበት የእግዚአብሔር ታቦት አልተገኘም፡፡ ያን ጊዜ የነቢዩ ቃል ተፈጸመ፡፡ የእግዚአብሔር ታቦት አልተገኘምና የታቦቱን ስም መጥራት አልቻሉም፡፡ ይህን ትንቢት ለምን ተናገረ ብለው ኤርምያስን የገዛ ወገኖቹ ከመጸዳጃ ቤት ከተውታል፡፡ የተናገረው ግን አንዱም አልቀረም፤ ተፈጸመ፡፡

እኛ የሐዲስ ኪዳን ክርስቲያኖች ግን ታቦታችን አልጠፋብንም፤ ምናልባት የጠፋባቸው ለማያምኑ ነው እንጂ፤ ታቦተ ጽዮን በኢትዮጵያ አሁንም ትገኛለች፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

የክህነት አገልግሎት

በማኅበረ ቅዱሳን ትምህርተ ወንጌልና ሐዋርያዊ አገልግሎት ማስተባበሪያ

በስብከተ ወንጌል ማስፋፊያ ዋና ክፍል የተዘጋጀ

የካቲት ፲፫ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

‹ክህነት›፣ ‹‹ተክህነ – አገለገለ›› ከሚል የግእዝ ቃል የወጣ ሲኾን ትርጕሙም ‹‹አገልግሎት፣ መላላክ፣ ለሌሎች መኖር፣ መጥዎተ ርእስ (ራስን መስጠት) መላ ሕይወትን ለእግዚአብሔር ማስረከብ›› ማለት ነው፡፡ ክህነት ካለ ካህናት ይኖራሉ፤ ክህነት አገልግሎቱ፣ ሹመቱ፤ ካህናት ደግሞ አገልጋዮቹ፣ ተሿሚዎቹ ናቸው፡፡ የመጀመሪያዎቹ ካህናት መላእክት ናቸው፡፡ የመጀመሪያ የእግዚአብሔር እና የሰው ልጆች አገልጋዮች፡፡ ‹‹በዙፋኑ ዙሪያ ሃያ አራት ወንበሮች ነበሩ፡፡ በእነዚያ ወንበሮችም ሃያ አራት አለቆች (ካህናተ ሰማይ) ተቀምጠዋል፡፡ ነጭ ልብስም ለብሰዋል፡፡ በራሶቻቸው ላይ የወርቅ አክሊሎች ደፍተው ነበር … በዂለንተናቸው ዓይኖችን የተመሉ ናቸው፡፡ ‹ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ የነበረውና ያለው፣ የሚመጣውም፤ ዂሉንም የሚገዛ ጌታ አምላክ› እያሉ›› ቀንና ሌሊት አያርፉም፡፡  እነዚህ በዙፋን ላይ ለተቀመጠው ከዘለዓለም እስከዘለዓለም በሕይወት ለሚኖረው ለእርሱ አክሊላቸውን በዙፋኑ ፊት አውርደው ይሰግዳሉ፡፡ እንዲህም ይላሉ፤ ‹ጌታችን እና አምላካችን ሆይ፣ አንተ ዂሉን ፈጥረሃልና በፈቃድህም ኾነዋልና ተፈጥረውማልና ክብርና ውዳሴ ኀይልም ለአንተ ይገባል፤››› ተብሎ እንደ ተጻፈ (ራእ. ፬፥፬)፡፡

ይህ ከላይ የተመለከትነው ኃይለ ቃል ለክህነት እና ለካህናት አገልግሎት መሠረቱ ነው፡፡ ‹‹በመዓልትም በሌሊትም አያርፉም›› ያለው የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ካህናትን የዘወትር አገልግሎት በግልጽ ያሳያል፡፡ ቤተ ክርስቲያናችን፣ ‹‹ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ ምስጋናው በሰማይና በምድር የሞላ ነው›› በማለት የምታሰመግነው በክህነት እና በካህናት አማካይነት ነው፡፡ ካህናት፣ ምድራውያን መላእክት ናቸው፡፡ መላእክት እንደሚያመሰግኑ ያመሰግናሉ፤ በእግዚአብሔር ፊት እንዲቆሙ ይቆማሉ፡፡ የክህነት አግልግሎት ከመላእክት ቀጥሎ የተሰጠው ለሰው ልጅ ነው፡፡ ለሰው የተሰጠው ክህነት ፈጣሪውን እንዲያመሰግንበት ብቻ አይደለም፡፡ መሥዋዕት ሊሠዋበት፣ ዕጣን ሊያሳርግበት፣ ሰውን ሊረዳበት የተሰጠ ነው፡፡ ለሰው ክህነት ተሰጠው ስንል ሰው ዂሉ ካህን ነው ማለት አይደለም፡፡ ከሰው ልጆች ወገን ለክህነት የተመረጡ አሉ፡፡ ዂሉም ሰው ተነስቶ ካህን ነኝ ሊል አይችልም፡፡ ይህ ማለት የአካል ክፍል እንደማጥፋት ማለት ነው፡፡ በአካል ውስጥ ዓይን፣ እጅ፣ እግር፣ አፍ፣ አፍንጫ … አሉ፡፡ ዂሉም የአካል ክፍሎች ዓይን መኾን አይችሉም፡፡ እጅ መዳሰስ፣ እግር መሔድ፣ ዓይን ማየት፣ አፍንጫ ማሽተት፣ አፍ መጉረስ ነው የሥራ ድርሻቸው፡፡ እጅ፣ እግር፣ አፍ፣ አፍንጫ፣ ጆሮ ካላየን ቢሉ፣ ዓይን እንኹን ብለው ቢያስቡ ወይም ነን ቢሉ ዓይን መኾን (ማየት) አይችሉም፡፡ ማየት የዓይን ተግባር እንደ ኾነ ዂሉ ሰዎችም ካህን ሳይኾኑ ነን በማለት መዓርገ ክህት አይገኝም፡፡ እግዚአብሔር የመረጣቸው ካህናት ይኾናሉ እንጂ፡፡

ክህነት በብሉይ ኪዳን

እግዚአብሔር ሙሴን ለምስፍና (ለመስፍንነት)፣ አሮንን ለክህነት መርጧቸዋል፡፡ የመረጠበት ግብርም ረቂቅ ነው፡፡ ዂሉም እስራኤል ግን መሳፍንት፣ ገዢዎች፣ መሪዎች አልነበሩም፡፡ የሌዊ ወገን ለክህነት፣ የይሁዳ ወገን ለመንግሥት የተመረጠ ነበር (ዘኍ. ፫፥፮)፡፡ የሌዊ ነገድ ተለይተው የክህነቱን አገልግሎት፣ መሥዋዕት መሠዋት የመሳሰሉትን ይሠሩ ነበር (ዘዳ. ፲፥፰፤ ፳፰፥፩-፵፫)፡፡ ሌሎች ነገደ ፳ኤል ድንኳን በመሸከም ልዩ ልዩ አገልግሎት ይሠጡ ነበር፡፡ ይህን የተላለፈ ፳ኤላዊ መቀሠፍቱ ከባድ ነበር፡፡ ከላይ እንደ ተመለከትነው ለክህነት መመረጥ፣ መለየት፣ መቀባት፣ መሾም፣ መቀደስ የግድ ያስፈልጋል፡፡ ማንም ዝም ብሎ ካህን ነኝ፤ ነቢይ ነኝ ማለት አይችልም፡፡ መሥዋዕቱን ምእመናነ እስራኤል ያመጣሉ፤ አሮንና ልጆቹ ደግሞ መሥዋዕቱን ያቀርባሉ፡፡ ሕዝቡ በጉን፣ ርግቡን፣ ዋኖሱን፣ በሬውን ያመጣሉ፤ ካህናቱ እጃቸውን ጭነው ይጸልያሉ፤ ኀጢአትን ያስተሰርያሉ፡፡ ሕዝቡን ያስተምራሉ፤ ይመክራሉ፡፡ ሕዝቡም ይመከራል፤ ይገሠፃል፡፡

በእግዚአብሔር ሳይመረጡና ሳይሾሙ ካህን ነን ቢሉ የሚመጣው ቅጣት ከባድ ነው፡፡ ከሌዊ ወገን የተወለዱ ዳታንና አቤሮን የደረሰባቸው ቅጣት በመጽሐፍ ቅዱስ ተመዝግቧል (ዘኍ. ፲፮፥፩-፶፩)፡፡ ያልተሰጣቸውን ሽተው፣ ከህነት ሳይኖራቸው ለማጠን ገብተው የእሳት ራት ሆነዋል፡፡ መሬት ተከፍቶ ውጧቸዋል፡፡ በሕይወት ሳሉ ተቀብረዋል፡፡ ለክህነት የተመረጠው አሮንና ልጆቹ ግን አልጠፉም፡፡ ከዚህ እንዳየነው ለክህነት መመረጥ፣ መቀደስ፣ መለየት፣ መሰጠት ያስፈልጋል፡፡ ይህ ሳይኾን ማንም ተነሥቶ ካህን ነኝ፣ ነቢይ ነኝ ቢል ይህ ዕጣ ፋንታ ይገጥመዋል፡፡ እግዚአብሔር አልመረጠውምና፡፡ የእነዚህ ሰዎች ዕጣን ማሳረግ (ማጠን) ለመቅሠፍት፤ የሳኦል መሥዋዕትም መንግሥትን ለማጣት ዳርጓቸዋል፡፡ ሳኦል፣ ሳሙኤል እስኪመጣ መታገሥ አቅቶት መሥዋዕት በመሠዋቱ ነው መንግሥቱን የተነጠቀው (፩ኛ ሳሙ. ፲፭፥፳፪፤ ፳፰፥፲፯)፡፡

ክህነት በሐዲስ ኪዳን

ክህነት በዓለመ መላእክት፣ በብሉይ ኪዳን ምን እንደሚመስል ተመልክተናል፡፡ በዓለመ መላእክት መሥዋዕቱ ምስጋና፣ ውዳሴ፣ ተልእኮ ነው፡፡ ካህናቱ መላእክት ናቸው፡፡ ቤተ መቅደሱ ዓለመ መላእክት ነው፡፡ በብሉይ ካህናቱ ከሌዋውያን የአሮን ልጆች፣ ቤተ መቅደሱ የመገናኛው ድንኳን፣ መሥዋዕቱ ላም፣ በግ፣ ፍየል፣ ርግብ፣ ዋኖስ የእኽል አይነቶች ናቸው፡፡ የሐዲስ ኪዳን ክህነቱም፣ መሥዋዕቱም፣ ካህናቱም ከተመለከትነው የተለየ ነው፡፡ ክህነቱና ካህናቱ ልዩ የሚኾንበት ምክንያት መሥዋዕቱ ልዩ በመኾኑ ነው፡፡ መሥዋዕቱ በቀራንዮ ዐደባባይ ዓለም ለማዳን ሥጋውን ቈርሶ፣ ደሙን አፍስሶ የሰጠን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ ቀደም ሲል ያየነው የመላእክት መሥዋዕት ዓለምን ማዳን አልተቻለውም፡፡ የሌዋውያንን መሥዋዕትም አንድ ኀጢአተኛ ሰው ያመጣዋል፡፡ ከመርገም ያልተለየ ካህን ይሠዋዋል፡፡ መሥዋዕቱም ሥጋዊ ይቅርታን ብቻ ያሰጥ ነበር፡፡ መሥዋዕቱ፣ በአቀራረቡም ጉድለት ነበረበት፡፡ ስርየቱ የሚያስገኘውም ላመጣው ሰው ብቻ ነበር፡፡

የሐዲስ ኪዳን መሥዋዕት ግን መሥዋዕቱ ፍጹም ጉድለት የሌለበት ነው፡፡ መሥዋዕቱም፣ አቅራቢውም፣ ተቀባዩም ኢየሱስ ክርስቶስ በመኾኑ ክህነቱም ፍጹም ነው፡፡ ይህን ፍጹም ክህነት ፍጹም የሆነውን መሥዋዕት ለሚያቀርቡ ካህናት ሰጠ፡፡ ክህነቱን አገልግሎቱን በትህትና አሳያቸው አስተማራቸው፡፡ ክህነቱንም መሥዋዕቱንም ሰጣቸው፡፡ በዚህ የተነሳ የሐዲስ ኪዳን ካህናት መላእክት ያልሰዉትን የብሉይ ኪዳን ካህናት ያላቀረቡትን መሥዋዕት የማቅረብ የማገልገል ሥልጣነ ክህነት የተሰጣቸው በመሆኑ ክህነቱ ምጡቅ ምስጢሩ ጥልቅ አገልግሎታቸውም ረቂቅ ነው፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ፣ ‹‹ኢተአምሩኑ ከመ መላእክተ ጥቀ ንኴንን ኅድጉሰ ዘዝ ዓለም፤ የዚህን ዓለም ዳኝነት ተዉትና በመላእክት ስንኳን እንድንፈርድ አታውቁምን?›› ሲል እንደ ጠቀሰው፤ መምህራነ ቤተ ክርስቲያንም ‹‹ዘኢተገብረ ለመላእክት ተገብረ ለካህናት፤ ለመላእክት ያልተደረገ ለካህናት ተደረገ›› በማለት እንደሚያስተምሩን (፩ኛ ቆሮ. ፮፥፲፫)፡፡

የብሉይ ኪዳን ካህናት ሰዉን ከእግዚአብሔር ጋር ለማስታረቅ አልተቻላቸውም፡፡ የሐዲስ ኪዳን ካህናት ግን የጠብ ግድግዳ ከፈረሰ፣ ልጅነት ከተመለሰ፣ ጸጋ ከተገኘ፣ ሰውና እግዚአብሔር ከተገናኘ በኋላ ስለ ተሾሙ ክህነታቸው ልዩ፣ መሥዋዕታቸው ልዩ፣ ክብራቸው ልዩ ነው፡፡ ምድራውያን ናቸው፤ ነገር ግን ሰማያዊ ሥልጣን አላቸው፡፡ የተሾሙትም ሰማያዊውን ርስት ለመስበክ፣ ሰውን ከምድራዊ ግብር ለይተው ሰማያዊ ጸጋ አሰጥተው መንግሥተ ሰማያትን ለማውረስ ነው፡፡ አምላክ ይህን ያደረገው በመልእክት አይደለም፤ ሰው ኾኖ መጥቶ ሥርዓቱን ሠርቶ አሳይቶ ሥልጣኑን ሰጥቶ አገልግሎቱን መሥርቶ ነው፡፡ ‹‹ወአልቦ ዘይነስእ ክብረ ለርዕሱ ዳዕሙ ዘጸውዖ እግዚአብሔር በከመ አሮን፤ በቃሁ ነቃሁ ብሎ ክብረ ክህነትን ለራሱ የሚያደርግ የለም፡፡ እግዚአብሔር እንደ አሮን ነው እንጂ (እንደ አሮን በእግዚአብሔር ከተጠራ በቀር ማንም ክብርን ለራሱ የሚወስድ የለም፤››) እንዳለ (ዕብ. ፭፥፬)፡፡

ማጠቃለያ

በአጠቃላይ ሥልጣነ ክህነት በጳጳሳት እጅ የሚሰጥ ሥልጣን ነውና ማቃለል አይገባም፡፡ ካህናት የእግዚአብሔር ዓይኖች ናቸውና፡፡ እግዚአብሔር ኀጢአተኛውን የሚያየው፣ የሚጐበኘውና ኀጢአቱን ይቅር የሚለው በእነርሱ በኩል ነው፡፡ ‹‹ሒድ ራስህን ለካህን አሳይ›› (ማቴ. ፰፥፬) ተብሎ እንደ ተጻፈ ካህን አየን ማለት እግዚአብሔር አየን ማለት ነው፡፡ ካህን የእግዚአብሔር ዓይን ነውና፡፡ የእግዚአብሔር ልጅ የምንኾነውም በካህናት ተጠምቀን ነውና (ማቴ. ፳፰፥፲፱)፡፡ በዚህ መሠረት ያለ ካህን እና ያለ መሥዋዕት የሚፈጸም አገልግሎት የለም፡፡ ቢኖርም አገልግሎቱ የውሸት ነው፡፡ ሕሙማን በክህነት አገልግሎት ይድናሉ፡፡ ‹‹ከእናንተ የታመመ ሰው ቢኖር በቤተ ክርስቲያን ያሉ ቀሳውስትን ወደ እርሱ ይጥራና ይጸልዩለት፡፡ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም የተጸለየበትንም ዘይት ይቅቡት የሃይማኖት ጸሎት ድውዩን ይፈውሰዋል፡፡ እግዚአብሔርም ያስነሣዋል፤ ኀጢአትንም ሠርቶ እንደ ኾነ ይሰረይለታል፤›› እንዲል (ያዕ. ፭፥፲፫-፲፮)፡፡

ካህናት ይህን ዂሉ የማድረግ ሥልጣን የተሰጣቸው የቤተ ክርስቲያን አባቶች ናቸው፡፡ በትረ ክህነት የጨበጡ፣ በእግዚአብሔር የተመረጡ፣ አጋንንትን የሚቀጡ፣ ኀጢአትን እንደ ሰም አቅልጠው የሚያጠፉ ናቸው፡፡ ሰውን ወደ እግዚአብሔር ያቀርባሉ፤ የእግዚአብሔርን መንጋ ምእመናንን ይጠብቃሉ፡፡ በለመለመ መስክ በጠራ ውኃ ያሠማራሉ፡፡ ማለት ያልተበረዘ ያልተከለሰ ከሐዋርያት የተገኘ ንጹሕ ወንጌልን ያስተምራሉ፡፡ ‹‹ነዋ በግዑ ለእግዚአብሔር ዘየአትት ወያሴስል ኃጢአተ ዓለም፤ እነሆ የዓለምን ኀጢአት የሚያስወግድ የእግዚአብሔር በግ›› እያሉ ሰውን ዂሉ ወደ እግዚአብሔር መንግሥትና ወደ ዘለዓለማዊ ሕይወት የሚያቀርቡ የድኅነት በር ናቸው (ዮሐ. ፩፥፳፱)፡፡

የኤልያስ መንፈስ በኤልሳዕ፤ የሙሴ መንፈስ በኢያሱ እንዳደረ የሐዋርያት መንፈስ ያደረበት እግዚአብሔር የመረጠው የገለጠው ክህነት በአበው ጳጳሳት ቅባትና ጸሎት አማካይነት ይታደላል፡፡ አባቶች ጳጳሳት በአንብሮተ እድ ባርከው በንፍሐት እፍ ብለው በእግዚአብሔር ስም ክህነቱን ካላሳደሩበት በቀር ማንም ካህን መኾን አይችልም፡፡ እግዚአበሔር የሾመው ሐዋርያትን ብቻ አይደለም፤ ጳጳሳትንም የሾመው እርሱ ነውና፡፡ ‹‹በገዛ ደሙ የዋጃትን የእግዚአብሔርን ቤተ ክርስቲያን ትጠብቁአት ዘንድ መንፈስ ቅዱስ እናንተን ጳጳሳት አድርጎ ለሾመባት ለመንጋው ዂሉና ለራሳችሁ ተጠንቀቁ፤›› ተብሎ እንደ ተጻፈ (ሐዋ. ፳፥፳፰)፡፡ ጌታችን ‹‹እውነት እላችኋለሁ፤ በምድር የምታስሩት ዂሉ በሰማይ የታሰረ ይኾናል፡፡ በምድርም የምትፈቱት ዂሉ በሰማይ የተፈታ ይኾናል›› በማለት ለቅዱሳን ሐዋርያት የማሰር የመፍታት ሥልጣን እንደ ሰጣቸው በማያሻማ ኹኔታ በቅዱስ ወንጌል ተቀምጧል (ማቴ. ፲፰፥፲፰፤ ሉቃ. ፳፬፥፶፤ ዮሐ. ፳፥፳፪-፳፬፤ ሐዋ. ፱፥፲፯፤ ፩ኛ ጢሞ. ፬፥፲፭)፡፡

ስለዚህ ክህነት በእግዚአብሔር ጥሪ የሚፈጸም በእግዚአብሔር ሰጭነት የሚከናወን መኾኑን ማወቅ ያስፈልጋል፡፡ ለዚህ ሥልጣን እግዚአብሔር መጀመሪያ የመረጠው ቅዱሳን ሐዋርያትን ነው፡፡ የመጀመሪያዎቹ የሐዲስ ኪዳን ካህናት ሐዋርያት ናቸው፡፡ የመረጣቸው፣ የጠራቸው፣ የሾማቸውም እርሱ ራሱ ነው (ማቴ. ፲፥፩)፡፡ ሥልጣኑን ያገኙት ከባለቤቱ ከኢየሱስ ክርስቶስ መኾኑን ልብ ማለት ያስፈልጋል፡፡ ሥልጣነ ክህነት ሐዋርያት ተቀብለውት የሚቀር ሳይኾን ለተመረጡ ሰዎች ሊሰጡት እንደሚችሉ መጽሐፍ ቅዱስ ምስክር ነው (ሐዋ. ፩፥፳፬)፡፡ በዚህ መልኩ የሚሾሙ ካህናት የእግዚአብሔር አገልጋዮች የሐዋርያት ተከታዮች ሐዋርያት ናቸው፡፡ ለእነርሱ የተሰጠውን ሥልጣን ማመን፣ መቀበልና መጠቀም ይገባል፡፡ ከዚህ ውጪ በየፌርማታው ነቢይ ነኝ ካህን ነኝ ከሚሉት መጠንቀቅ ያሻል፡፡ ክህነት ዝም ብሎ በየመንገዱ የሚታፈስ አይደለም፡፡ ማንም እየተነሣ የሚዘግነው የእድር ቆሎም አይደለምና፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡