«የአሮጊቷ ሣራ» ወለደች ዐዋጅ ተሐድሶ ዘመቻ የጥፋት ፈትል እንደማጠንጠኛ
በመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት በብሉያትና በሐዲሳቱም የምትነሣው ሣራ አበ ብዙኃን ሥርወ ሃይማኖት የምንለው የአብርሃም ሚስት ነች፡፡ እግዚአብሔር ለአብርሃም የብዙዎች አባት እንዲሆን ቃል ኪዳን ሳይገባለት በፊት፣ በመካንነት ታዝን፣ ተስፋም አጥታ ትተክዝ በነበረችበት ጊዜ ሦራ ትባል ነበር፡፡
ሦራ ሙቀት ልምላሜ ከተለያት በኋላ ልጅ እንደምትወልድ ከአብርሃም በኩል እግዚአብሔር ቃል ኪዳን ከገባላት፣ ተስፋም ከተሰጣት በኋላ ሣራ ተብላለች፡፡ እግዚአብሔርም ስለእርሷ ለአብርሃም «የሚስትህን የሦራን ስም ሦራ ብለህ አትጥራ፤ ስምዋ ሣራ ይሆናል እንጂ፤ እባርካታለሁ፤ ደግሞም ከእርሷ ልጅ እሰጥሃለሁ፤ እባርካትማለሁ፤ የአሕዛብ እናት ትሆናለች፤ የአሕዛብ ነገሥታት ከእርሷ ይወጣሉ» በማለት ተናገረው /ዘፍ. 17፥15/፡፡