እኛ የምናመልከው አምላክ ኪሚነደው ከእሳቱ እቶን ያድነን ዘንድ ይችላል፡፡ ት.ዳን.3፥17
ታኅሣሥ 18 ቀን 2005 ዓ.ም.
በዲ/ን ኀይለ ኢየሱስ ቢያ
ንጉሡ ናቡከደነጾር በዱራ ሜዳ ላቆምኩት የወርቅ ምስል ካልሰገዳችሁ ከእጄ የሚያድናችሁ አምላክ ማን ነው? ብሎ በኀይልና በዛቻ በጠየቃቸው ጊዜ ሠለስቱ ደቂቅ በልበ ሙሉነት፥ በፍጹም እምነት፥ መልስ የሰጡበት ኀይለ ቃል ነው፡፡ ከኀይለ ቃሉ ቅዱስ ዳዊት አመንኩ በዘነበብኩ /በተናገርሁት አመንሁ፤ እንዳለ መዝ.115፥1 ፍጹም እምነታቸውንና ታማኝነታቸውን፣ ጽናታቸውን እንረዳለን፡፡ ዛሬ የምናከብረው የሊቀ መላእክት የቅዱስ ገብርኤል በዓል ሠለስቱ ደቂቅን ከባቢሎን እሳት ያዳነበት ነው፡፡ ታሪኩ የተፈጸመው በብሉይ ኪዳን ዘመን ከ605-562 ቅድመ ልደተ ክርስቶስ በነገሠው በናቡከደነጾር ዘመን ነው፡፡ በብሉይ ኪዳን ዘመን ከጣዖት አምላኪና አስመላኪ ኀያላን ነገሥታት መካከል አንዱ ናቡከደነጾር ነበር፡፡ ምስሉ የቆመው በ587 ቅ/ል/ክ እንደሆነ መተርጎማን ያስረዳሉ፡፡ ዳን.3፥1 ናቡከደነጾር እስራኤላውያንን በማረከበት ዘመን ዳንኤልንና ሦስቱን ሕፃናት በልዩ ሁኔታ አክብሯቸው ነበር፡፡