የዓለሙ ፍጻሜ ምልክቱ ምንድን ነው? – ክፍል አንድ

በአባ ዘሚካኤል ደሬሳ

መጋቢት ፱ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

በዐቢይ ጾም ውስጥ ካሉት ሳምንታት ደብረ ዘይት አምስተኛው ሳምንት ላይ ይውላል፡፡ ደብረ ዘይት ትርጕሙ ‹‹የወይራ ዛፍ፣ ተራራ›› ማለት ሲኾን፣ ይህም በኢየሩሳሌም በሚገኘው በደብረ ዘይት ተራራ ቅዱሳን ሐዋርያት ‹‹የዓለሙ ፍጻሜ ምልክቱ ምንድን ነው?›› /ማቴ.፳፬፥፫/ ብለው ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን በጠየቁት ጊዜ እርሱም የማይቀረውን የዓለም ፍጻሜና አስቀድመው የሚፈጸሙ ምልክቶችን አስረድቷቸዋል፡፡

ቤተ ክርስቲያንም ይህንኑ በደብረ ዘይት ሳምንት ታስበዋለች፤ በቅዱሳት መጻሕፍት የተጠቀሱትን የትንቢት ምልክቶች ከተግባራዊ የዓለም ክንዋኔዎች አንጻር በማገናዘብ ለምእመናኑ ታስተምራለች፡፡ በመኾኑም በቤተ ክርስቲያናችን በደብረ ዘይት ሳምንት ምጽአትን የሚመለከቱ ምሥጢራት በሰፊው ይነገራሉ፡፡ በዚህ ዝግጅት በዓለም እየተከሠቱ ያሉ ወቅታዊ ምልክቶችን ከቅዱሳት መጻሕፍት ቃል ጋር በማገናዘብ መጠነኛ ትምህርት ይዘን ቀርበናል፤

የሰው ልጅ ሲፈጠር ጀምሮ ስለ ራሱ መጨረሻና ስለ ዓለም ፍጻሜ ምንነት ማወቅን እንደሚሻ ቅዱሳት መጻሕፍት ያስረዱናል፡፡ ከእነዚህም በተለይ በደብረ ዘይት ዕለት ቤተ ክርስቲያን የምታስተምረው፤ ቅዱሳን ሐዋርያት ‹‹የዓለሙ ፍጻሜ ምልክቱ ምንድን ነው?›› በማለት የጠየቁት ጥያቄ ቅድሚያ ይሰጠዋል፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለሐዋርያት ከመለሰላቸው ዋነኛውና ቀዳሚው የምጽአቱ ምልክት የሐሳዊ መሲሕ መምጣት ነው፡፡ ሐሳዊ መሲሕ ማለት በቀጥታ ትርጕሙ ‹‹ሐሰተኛ የኾነበኢየሱስ ክርስቶስ (በአምላክ) ስም የሚመጣ የክርስቶስ ተቃዋሚ›› ማለት ነው፡፡

ትርጕሙን አስፍተን ስንመለከተው ደግሞ ከሃይማኖት ጋር ተያያዥነት ያላቸውም ኾነ የሌላቸው፣ በዓለም ላይ እየተከናወኑ የሚገኙ ጉዳዮችንና የጥፋት መንገዶችን ያጠቃልላል፡፡ የሐሳዊ መሲሕ የጥፋት ሥራዎች በማወቅም ይኹን ባለማወቅ በዓለማውያንና በክፉ መናፍስት ተከታዮች እየተፈለሰፉ ናቸው፡፡ ከእግዚአብሔር የተገኙ የሃይማኖት፣ የሥነ ተፈጥሮ፣ የጋብቻና የመሳሰሉ ድንበሮች ማፍለስን ዓላማ ያደረጉ፤ እንደዚሁም ሰብአዊ ክብር፣ መንፈሳዊና አገራዊ ባህል አገራዊ እንዲጠፋ የሚሠሩ አካላት ዅሉ ከሐሳዊ መሲሕ መደብና ከዓለም ፍጻሜ ምልክት አንጻር የሚታዩ ናቸው፡፡ ጉዳዩን ለማብራራት ያህል የሚከተሉት ነጥቦችን እንመልከት፤

፩. የሃይማኖት ድንበርን ማፍለስ

እግዚአብሔር በመጻሕፍቱ ‹‹አባቶችህ ያኖሩትን (የሠሩትን) የቀድሞውን የድንበር ምልክት አታፋልስ›› /ምሳ.፳፪፥፳፰/ በማለት ያዘዘውን ትምህርት መጣስ ማለትም የሃይማኖት ድንበርን ማፍለስ ከሐሳዊ መሲሕ ተግባር ውስጥ የሚመደብ ነው፡፡ አፈጻጸሙም ሰዎች የእግዚአብሔርን ማንነት እንዳያውቁ ከማድረግ ይጀምራል፡፡ ከዚህም አንዱ ሐሳዊ መሲሕ በእግዚአብሔር ስም በተለያየ ኹኔታና መንገድ መገለጥ ነው፡፡ ‹‹‹እኔ ክርስቶስ ነኝ› እያሉ ብዙ ሰዎች በእኔ ስም ይነሣሉ›› /ማቴ. ፳፬፥፭/፡፡

ይህም እንደ መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ትምህርትና የቅዱሳን ሐዋርያት ስብከት መሠረት ኢየሱስ ክርስቶስ የእግዚአብሔር የባሕርይ ልጁ እንደ ኾነ የማይሰብክ ዅሉ ከሐሳዊ መሲሕ ትምህርት ይመደባል፡፡ ቅዱስ ዮሐንስም በመልእክቱ ‹‹ኢየሱስ ክርስቶስም በሥጋ እንደ መጣ የማይታመን መንፈስ ዅሉ ከእግዚአብሔር አይደለም፤ ይህም የክርስቶስ ተቃዋሚው መንፈስ ነው፡፡ ይህም እንደማመጣ ሰምታችኋል፤ አሁንም እንኳ በዓለም አለ፤›› በማለት በእነዚህ ሐሳውያን ላይ ይመሰክርባቸዋል /፩ኛዮሐ. ፬፥፫/፡፡

በመኾኑም ከዚህ በፊት ያለፉ፣ አምላክ ነን ብለው እንደ ተነሡት ቴዎዳስ ዘግብጽና ይሁዳ ዘገሊላ /ሐዋ. ፭፥፴፮-፴፯/፤ ከዚያም በኋላ በየጊዜው እንደ ተነሡ መናፍቃን በዚህ ዘመንም ‹‹ኢየሱስ ነኝ … ኢየሱስ በእኛ ዘንድ አለ …›› እያሉ የዋሁን ሕዝብ የሚያጭበረብሩ ሐሳውያን መሲሖች መጥተዋል፡፡ ከዚህም ሌላ ክርስቶስን ከአብ የሚያሳንሱ (ሎቱ ስብሐት)፣ ነቢይ ነው ብለው የሚያምኑ፣ በመናፍስት አሠራር የሚጠነቁሉ፣ በማቴሪያሊስት (ቁሳዊነት) ወይም በኢቮሉሽን (በዝግመተ ለውጥ) ትምህርት አምነው አምላክ የለም የሚሉ፣ ወዘተ. ዅሉ የሐሳዊው መሲሕ አካላት ናቸው፡፡

አሁንም ቅዱስ ዮሐንስ በመልእክቱ ‹‹ልጆች ሆይ! መጨረሻው ሰዓት ነው፤ የክርስቶስም ተቃዋሚ ይመጣ ዘንድ እንደ ሰማችሁ አሁን እንኳ ብዙዎች የክርስቶስ ተቃዋሚዎች ተነሥተዋል፡፡ ስለዚህም መጨረሻው ሰዓት እንደ እናውቃለን፤›› ይለናል /፩ኛዮሐ. ፪፥፲፰/፡፡ ከዚህ ቃል የምንረዳው የክርስቶስ ተቃዋሚ መምጣት የምጽአት ጊዜው መቃረብ ምልክት መኾኑን ነው፡፡ በተጨማሪም የምጽአትን መቅረብ ከሚያመለክቱ፣ ከሐሳዊው መሲሕ እና ከእርሱ ጋር ተዛማጅ የኾኑ ወቅታዊ ጉዳዮችን ለመረዳት የሚከተሉትን ትንቢቶች እንመልከት፣

‹‹የአውሬው ምስል ሊናገር እንኳ ለአውሬውም ምስል የማይሰግዱለትን ዅሉ ሊያስገድላቸው፣ ለአውሬው ምስል ትንፋሽ እንዲሰጠው ተሰጠው። ታናናሾችና ታላላቆችም፣ ባለ ጠጋዎችና ድሆችም፣ ጌታዎችና ባሪያዎችም ዅሉ በቀኝ እጃቸው ወይም በግምባራቸው ምልክትን እንዲቀበሉ፤ የአውሬውም ስም ወይም የስሙ ቍጥር ያለው ምልክት የሌለበት ማንም ሊገዛ ወይም ሊሸጥ እንዳይችል ያደርጋል። ጥበብ በዚህ አለ። አእምሮ ያለው የአውሬውን ቍጥር ይቍጠረው፤ ቍጥሩ የሰው ቍጥር ነውና፡፡ ቍጥሩም ስድስት መቶ ስድሳ ስድስት ነው፤›› /ራእ. ፲፫፥፲፮-፲፰/፡፡

ይህ የቅዱስ ዮሐንስ ራእይ ከሚመሠጠርበት ትርጕም ውስጥ አንዲት ቅንጣት ብቻ ከዘመኑ አንጻር ብናይ ‹‹የሚናገር የአውሬው ምስል›› ማለት ለእርሱ ያልተገዙትን ወይም ቁጥሩን ያልያዙትን የሚናገርባቸው፤ ‹‹ምልክቱን ያልተቀበሉትን ሊገዙና ሊሸጡ እንዳይችሉ ያደርግል›› ማለት መኖር፣ መሥራት፣ መሸጥ፣ መለወጥ ወዘተ የሚያግዳቸው ሲል ነው፡፡ ይህም አሁን ባለው የዚህ ዓለም አኗኗር አንጻር ሲታይ ተመሳሳይ ጉዳዮች አሉ፡፡ ለምሳሌ መታወቂያ ወረቀት፣ ፓስፖርት፣ ቪዛ፣ የመኖሪያ ፈቃድ ወዘተ በዓለም አጠቃላይ አሠራር እና ባንድ ሰው የመኖር ማንነት ሚና ላይ ተጽዕኖ የሚያደርጉ ነገሮች ናቸው፡፡ እነዚህ መታወቂያ ወረቀቶች የሌሉት ሰው ካለበት የትም መንቀሳቀስ አይችልም፡፡

ከዚህም በላይ ጉዳዩን ስናሰፋው በሠለጠኑት ዓለማት አሠራር የእያንዳንዱ ሰው የጣት አሻራ በዘመናዊ (ኮምፒውተራይዝድ) መንገድ የተደራጀ በመኾኑ፣ ከዚህ አደረጃጀት ውስጥ ካልተካተተ በቀር ማንም ሰው በዚያች አገር ሊኖር፣ ሊዘዋወር፣ ሊሠራ፣ ሊነግድ ወዘተ. አይችልም፡፡ በዚህ የኮምፒውተር ድር አደረጃጀት ውስጥ ያለ አንድ ሰው ወደየትኛውም ዓለም ቢንቀሳቀስ በጣቱ አሻራ ይታወቃል፡፡ ወንጌላዊው ዮሐንስ በትንቢቱ፡- ‹‹አእምሮ ያለው የአውሬውን ቍጥር ይቍጠረው፤ ቍጥሩ የሰው ቍጥር ነውና፤ ቍጥሩም ስድስት መቶ ስድሳ ስድስት ነው፤››  የሚለውም ይህን ጉዳይ የሚያደራጀው ሌላ አካል ሳይኾን የሰው ልጅ መኾኑን የሚያመለክት ነው፡፡ ‹‹ስድስት መቶ ስድሳ ስድስት›› የሚለው ቍጥር የሰው ልጅ የጅማት ቁጥር ነውና፡፡

ሌላው የምጽአት መቃረብ ምልክት የሐሳዊው መሲሕ ዘመቻን አውቀው በድፍረት፣ ላላወቁት በረቀቀ መንገድ እግዚአብሔርን ያመለኩ አስመስለው የእግዚአብሔርን ስም፣ እመቤታችንን ቅድስት ድንግል ማርያምን፣ በአጠቃላይ ቅዱሳንን መስደብ ነው፡፡ እነዚህ በልዩ ልዩ ዘመናት ሲፈጸሙ የቆዩ ተግባራት ዛሬም ተጠናክረው በመፈጸም ላይ ይገኛሉ፡፡ ሩቅ ሳንሔድ ዛሬ ቤተ ክርስቲያናችንን እየተፈታተነ ያለው የተሐድሶአውያን መናፍቃን ትልቁ ሤራ የእግዚአብሔር ወልድን አምላክነት፤ የድንግል ማርያምን ክብርና አማላጅነት፤ የታቦትንና የመስቀልን ክብር፤ የቅዱሳንን ቅድስና እና አማላጅነት መቃወም ነው፡፡ የተሐድሶ ኑፋቄ እንቅስቃሴ በሥራው የአውሬው መንፈስ አራማጅና መንገድ ጠራጊ መኾኑን ቅዱስ ዮሐንስ በራእዩ እንዲህ በማለት ያረጋግጥልናል፤

‹‹ለዘንዶውም ሰገዱለት፤ ለአውሬው ሥልጣንን ሰጥቶታልና፡፡ ለአውሬውም ‹አውሬውን ማን ይመስለዋል? እርሱንስ ሊዋጋ ማን ይችላል?› እያሉ ሰገዱለ፡፡ ታላቅንም ነገርና ስድብን የሚናገርበት አፍ ተሰጠው፡፡ በዐርባ ሁለት ወርም እንዲሠራ ሥልጣን ተሰጠው፡፡ እግዚአብሔርንም ለመሳደብ ስሙንና ማደሪያውንም በሰማይም የሚያድሩትን ሊሳደብ አፉን ከፈተ። ቅዱሳንንም ይዋጋ ዘንድ ድልም ያደርጋቸው ዘንድ ተሰጠው፡፡ በነገድና በወገንም በቋንቋም በሕዝብም ዅሉ ላይ ሥልጣን ተሰጠው። ከዓለምም ፍጥረት ጀምሮ በታረደው በግ ሕይወት መጽሐፍ ስሞቻቸው ያልተጻፉ በምድር የሚኖሩ ዅሉ ይሰግዱለታል፤›› /ራእ. ፲፫፥፬-፰/፡፡

ሌላኛው በዓለም ላይ የሚታየው በሰዎች ዘንድ ክብርን፣ ዝናንና ታዋቂነትን ለማግኘት ሲባል ራስን ከፍ ማድረግና እንደ አማልክት መቍጠር ከሐሳዊው መሲሕ ጋር ያስመድባል፡፡ በተመሳሳይ መልኩ ሊቀ ነቢያት ሙሴ እንደ ገለጸው የሰናዖር ሰዎችን ኀጢአት ስናስተውል የተነሡበት ዋነኛው ነጥብ ‹‹ስማችንን እናስጠራ›› የሚለው ነበር፡፡ ‹‹‹ኑ! ለእኛ ከተማና ራሱ ወደ ሰማይ የሚደርስ ግንብ እንሥራ፤ በምድር ላይ ሳንበተንም ስማችንን እናስጠራው› አሉ፤›› ተብሎ እንደ ተጻፈ /ዘፍ. ፲፩፥፬/፡፡ በዚህ እኩይ አሳብ ምክንያት ነው እግዚአብሔር ቋንቋቸውን የደባለቀባቸው፡፡ የሰናዖር ሰዎች ያሰቡትና የተመኙት ትውልዱ እግዚአብሔርን ማድነቅ ትቶ፣ ለዘለዓለም ስማቸውን ሲጠራና ሥራቸውን ሲያደንቅ እንዲኖርላቸው ነበር፡፡ ዛሬም ብዙዎቹ ይህንን የሰናዖርን ኀጢአትና የጥፋት ጉዞ እንደ ዓላማ ይዘው በመንቀሳቀስ ላይ ይገኛሉ፡፡

፪. የሥነ ተፈጥሮ ሕግመጣስ

እግዚአብሔር አምላካችን የፈጠረው ፍጥረት ፍጹም በመኾኑ ይህ ቀረህ፤ ይህ ይጨመርልህ የሚባል አይደለም፡፡ ነገር ግን በዚህ ወቅት ሰው ልዩ ልዩ ጥቅማጥቅም ለማግኘት ሲል ዝርያቸው የተለያየ ፍጥረታትን (እንስሳትና ተክሎችን) ማዳቀልንና ማደበላለቅን ተያይዞታል፡፡ በተቃራኒውም የሰውን ቍጥር ለመቀነስ የማያደርገው ሩጫ የለም፡፡ የሰውን ቍጥር ለመቀነስ በሚደረጉ ሕክምናዎች ምክንያትም ሰዎች ለተለያዩ በሽታዎች ተዳርገዋል፡፡ ከዚህም ሌላ በዚህ መሰሉ ድጋፍና ማበረታቻ በተለይ በሠለጠኑ የዓለም ክፍሎች ብዙዎቹ የግብረ ሰዶም ፈጻሚና አስፈጻሚ ኾነዋል፡፡

ይህም አምላክ የሠራውን የፍጥረት ሕግ በማጣጣልና በመጣስ ሰው ላሻሽል ወደሚል ያዘነበለ መኾኑንና የሰውን ልጅ ቅጥ ያጣ ድፍረት ያሳያል፡፡ እግዚአብሔር ግን ሥነ ፍጥረቱን እንዲያደባልቁበት አይፈልግም፡፡ ለዚህም ነው ሊቀ ነቢያት ሙሴን፡- ‹‹ሥርዓቴን ጠብቁ። እንስሳህ ከሌላ ዓይነት ጋር አይደባለቅ፤ በእርሻህም ሁለት ዓይነት ዘር አትዝራ፤›› ሲል ያዘዘው /ዘሌ. ፲፱፥፲፱/፡፡ ግብረ ሰዶምን በተመለከተም ‹‹ማናቸውም ሰው ከሴት ጋር እንደሚተኛ ከወንድ ጋር ቢተኛ ሁለቱ ጸያፍ ነገር አድርገዋል፤ ፈጽመው ይገደሉ፡፡ ደማቸው በላያቸው ነው፤›› ተብሎ ተጽፏል /ዘሌ. ፳፥፲፫/፡፡

፫.  ጋብቻን ማፍረስ (ማፋታት)

አውሬው (አስማንድዮስ የሚባለው ርኵስ መንፈስ) የጋብቻ ጠላት ኾኖ ነግሦአል፡፡ ስለዚህም ተጋቢዎች ፈተናውን መቋቋም አልቻሉምና በአንድ መኖራቸውን ጠልተው ይለያያሉ (ይፋታሉ)፡፡ አስማንድዮስ (ርኵስ መንፈስ) ከጋቻ ይልቅ ግብረ ሰዶምን እያበረታታ በአንዳንድ አገሮች እንደሚታየው ወንድን ከወንድ፣ ሴትን ከሴት ጋር እያቆራኘ በማምለኪያ ሥፍራዎቻቸው ሳይቀር ጋብቻቸውን እስከ መፈጸም አድርሷቸዋል፡፡ ይህንን ኀጢአት በሚመለከትም ቅዱስ ጳውሎስ እንዲህ ይላል፤

‹‹ስለዚህ እርስበርሳቸው ሥጋቸውን ሊያዋርዱ እግዚአብሔር በልባቸው ፍትወት ወደ ርኵሰት አሳልፎ ሰጣቸው፤ ይህም የእግዚአብሔርን እውነት በውሸት ስለ ለወጡ በፈጣሪም ፈንታ የተፈጠረውን ስላመለኩና ስላገለገሉ ነው፡፡ እርሱም ለዘላለም የተባረከ ነው፤ አሜን። ስለዚህ እግዚአብሔር ለሚያስነውር ምኞት አሳልፎ ሰጣቸው፡፡ ሴቶቻቸውም ለባሕርያቸው የሚገባውን ሥራ ለባሕርያቸው በማይገባው ለወጡ፡፡ እንዲሁም ወንዶች ደግሞ ለባሕርያቸው የሚገባውን ሴቶችን መገናኘት ትተው እርስ በርሳቸው በፍትወታቸው ተቃጠሉ፡፡ ወንዶችም በወንዶች ነውር አድርገው በስሕተታቸው የሚገባውን ብድራት በራሳቸው ተቀበሉ። እግዚአብሔርን ለማወቅ ባልወደዱት መጠን እግዚአብሔር የማይገባውን ያደርጉ ዘንድ ለማይረባ አእምሮ አሳልፎ ሰጣቸው፡፡ ዓመፃ ዅሉ፣ ግፍ፣ መመኘት፣ ክፋት ሞላባቸው፡፡ ቅናትን፣ ነፍስ መግደልን፣ ክርክርን፣ ተንኰልን፣ ክፉ ጠባይን ተሞሉ፡፡ የሚያሾከሹኩ፣ ሐሜተኞች፣ አምላክን የሚጠሉ፣ የሚያንገላቱ፣ ትዕቢተኞች፣ ትምክህተኞች፣ ክፋትን የሚፈላለጉ፣ ለወላጆቻቸው የማይታዘዙ፣ የማያስተውሉ፣ ውል የሚያፈርሱ፣ ፍቅር የሌላቸው፣ ምሕረት ያጡ ናቸው፡፡ ‹እንደነዚህ ለሚያደርጉት ሞት ይገባቸዋል› የሚለውን የእግዚአብሔርን ሕግ እያወቁ እነዚህን ከሚያደርጉ ጋር ይስማማሉ እንጂ አድራጊዎች ብቻ አይደሉም፤›› /ሮሜ.፩፥፳፬ እስከ ፍጻሜው/፡፡

 ይቆየን

‹‹ሰው የለኝም››

በመምህር ኃይለሚካኤል ብርሃኑ

መጋቢት ፬ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

ኃይለ ቃሉን የተናገረው በደዌ ዳኛ ተይዞ የአልጋ ቁራኛ ኾኖ ይኖር የነበረው መጻጕዕ ነው፡፡ መጻጕዕ ማለት በሽተኛ ማለት ነው፡፡ መጻጕዕ ይህንን የኀዘን ሲቃ የተሞላበት ተስፋ የመቁረጥ ምልክት የኾነውን ‹‹ሰው የለኝም›› የሚለውን አቤቱታ ያቀረበው ሳይንቅ ለጠየቀው፣ አይቶ በቸልታ ላላለፈው፣ የሰውን ድካሙን ለሚረዳ ለጌታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡

ወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስ እንደተረከው በኢየሩሳሌም በበጎች በር አጠገብ በዕብራይስጥ ቋንቋ ‹‹ቤተ ሳይዳ›› የምትባል አንዲት መጠመቂያ ነበረች፡፡ አምስትም መመላለሻ ነበረባት፡፡ ቤተ ሳይዳ ማለት ቤተ ሣህል (የይቅርታ ቤት) ማለት ነው፡፡ አምስት መመላለሻ የሚለውን ትርጓሜ ወንጌል እርከን ወይም መደብ ይለዋል፡፡ በእርከኑ ወይም በመደቡ ብዙ ድውያን ይተኛሉ፡፡ ከእነሱም ውስጥ የታወሩ፣ አንካሾች፣ የሰለሉ፣ ልምሹ የኾኑ፣ የተድበለበሉ በየእርከን እርከኖች ላይ ይተኛሉ፡፡ የእግዚአብሔር መልአክ ውኃውን ለመቀደስ በየዓመቱ በሚወርድ ጊዜ ድምፁ እስኪያስተጋባ ድረስ ውኃው ይናወጣል፡፡ ድውያኑም በዚያ ሥፍራ ተኝተው የውኃውን መናወጥ ይጠባበቃሉ፡፡ ምክንያቱም በዓመት አንድ ጊዜ ብቻ ውኃው ሲናወጥ ቀድሞ ወደ ውኃው የገባ አንድ ሰው ከደዌው ይፈወስ ነበርና፡፡

ፈውሱ በየጊዜው ከዓመት አንድ ጊዜ ይደረግ የነበረው የእግዚአብሔር ተአምራት በአባቶቻችን ጊዜ ነበር እንጂ አሁንማ የለም ብለው ድውያኑ ከማመን እንዳይዘገዩ ሲኾን፣ የድውያኑ መፈወስ አለመደጋገሙም (በዓመት አንድ ጊዜ ብቻ መፈጸሙም) በኦሪት ፍጹም ድኅነት እንዳልተደረገ ለማጠየቅ ነው፡፡ በዚያም ከሠላሳ ስምንት ዓመት ጀምሮ የታመመ አንድ ሰው ነበረ፡፡ ከአልጋው ላይ ተጣብቆ ይኖር ነበር፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ወደዚያ ሰው ቀርቦ አየው፡፡ ጌታችን ክብር ይግባውና ተጨንቀን እያየ ዝም የማይለን፣ ስንቸገርም የሚረዳን ቸር አምላክ ነውና መጻጕዕ በደዌ ዳኛ በአልጋ ቁራኛ ተይዞ ለብዙ ዓመታት እንደተሰቃየ፣ ደዌው እንደጸናበት መከራውም እንደበረታበት አውቆ በርኅራኄ ቃል ‹‹ልትድን ትወዳለህን?›› አለው፡፡ ፈቃዱን መጠየቁ ነው፡፡

አምላካችን ልዑል እግዚአብሔር ፍትሐዊ ነውና ለማዳን የእያንዳንዳችን ፈቃደኝነት ይጠይቃል እንጂ ሥልጣን ስላለው፣ ክንደ ብርቱና ዅሉን ማድረግ የሚቻለው ስለኾነ ብቻ ያለ ፈቃዳችን የሚገዛን አምላክ አይደለም፡፡ በእኛ ላይ የሚያደርገውን የማዳኑን ሥራ ‹‹ልትነጻ ትወዳለህን፣ ምን እንዳደርግልህስ ትሻለህ?›› በማለት ከጠየቀ በኋላ ‹‹እንደእምነትህ ይኹንልህ፤ እንደእምነትሽ ይኹንልሽ›› እያለ በነጻነት እንድንመለላለስ ነጻነታችን ያወጀልን የፍቅር አምላክ ነው፡፡ መጻጕዕንም ‹‹ልትድን ትወዳለህን?›› ባለው ጊዜ እሱ ግን የሰጠው ምላሽ እጅግ የሚያሳዝን ነበር፡፡ ‹‹ጌታ ሆይ ውኃው በተናወጠ ጊዜ በመጠመቂያው ውስጥ የሚያኖረኝ ‹ሰው የለኝም› ነገር ግን እኔ ስመጣ ሳለሁ ሌላው ቀድሞኝ ይወርዳል›› ብሎ መለሰለት፡፡ መጻጕዕ፣ ሰዎች ባጣ ጊዜ እንደሸሹት፣ በታመመ ጊዜ እንደተጸየፉት፣ ‹‹እንዴት ዋልኽ? እንዴት አደርኽ?›› የሚለው ሰው እንዳጣ፣ ወገን አልባ እንደኾነ እና ተስፋ እንደቆረጠ ለጌታችን ተናገረ፡፡

ጌታችን የልብን የሚያውቅ አምላክ ሲኾን ‹‹ልትድን ትወዳለህን?›› ብሎ የጠየቀበት ምክንያት አላዋቂ ሥጋን እንደተዋሐደ ለማጠየቅ ነው፡፡ አልዓዛር በሞተ ጊዜ ‹‹መቃብሩን አሳዩኝ ወዴት ነው የቀበራችሁት?›› እንዳለው ዅሉ፡፡ መጻጕዕም በምላሹ ‹‹ሰው የለኝም›› ማለቱ ኢየሱስ ክርስቶስን ሲያየው የሠላሳ ዓመት ጎልማሳ ነውና የውኃውን መናወጥ ተጠባብቆ ያወርደኛል ብሎ በማሰቡ ነው፡፡ አንድም አምስት ገበያ ሰው ይከተለው ነበርና አንዱን ሰው ያዝልኛል ብሎ ነው፡፡

ብዙዎቻችን የሕይወታችን ዋልታ በሰው እጅና በሰው ርዳታ ያለ ይመስለናል፡፡ ሰዎች ካልረዱን፣ ካልደጎሙን፣ አይዟችሁ ካላሉን፣ ከጎናችን ካልኾኑና በሰዎች ካልታጀብን ነገር ዅሉ የማይሳካልን ይመስለናል፡፡ ለዚህም ነው በሰዎች ትከሻ ላይ እንወድቅና ክንዳቸውን ተመርኩዘን እነሱ ሲወድቁ አብረን የምንወድቀው፡፡ ሲጠፉም አብረን ለመጥፋት የምንዳረገው፡፡ እስኪ ከሚደክመው ከሰው ትከሻ፣ ከሚዝለው ከሰው ክንድ እንውረድና በማይዝለውና በማይደክመው በአምላክ ክንድ ላይ እንደገፍ፡፡ እርሱ መታመኛ ነው፤ ያሳርፋል፡፡ የማይደክምም ብርቱ መደገፊያ ነው፡፡

መጻጕዕ ዅሉ ነገሩ በሰዎች እጅ ላይ ነው ብሎ ስላሰበና የሰዎች ርዳታ ስለቀረበት ተስፋ ቆርጦ ነበር፡፡ የተማመነባቸው ሰዎችም ሲርቁት ሕይወቱ ጨልሞበት ነበርና ‹‹ሰው የለኝም›› አለ (ዮሐ.፭፥፯)፡፡ የተቸገረውን ለመርዳት፣ ድሃውን ባዕለ ጸጋ ለማድረግ፣ የተጨነቀችቱን ነፍስ ለማጽናናት አማካሪ የማይሻው አምላክ ግን ወዲያውኑ ‹‹ተነሣና አልጋህን ተሸክመህ ሒድ›› አለው፡፡ ሰውዬው (መጻጕዕ) ወዲያውኑ ዳነ፡፡ አልጋውንም ተሸክሞ ሔደ፡፡ ቀነ ቀጠሮ ሳይሰጥ፣ ይህን ያህል ክፈል ሳይል ብቻ መሻቱን ተመልክቶ በአምላካዊ ቃሉ ፈወሰው፡፡

በዮሐንስ ወንጌል ትርጓሜ እንደተገለጸው የእግዚአብሔር መልአክ የቀሳውስት፣ ውኃው የጥምቀት፣ አምስቱ እርከን የአምስቱ አዕማደ ምሥጢር፣ አምስቱ ድውያን የአምስቱ ፆታ ምእመናን ማለትም የአዕሩግ፣ ወራዙት፣ አንስት፣ ካህናት፣ መነኮሳት ምሳሌዎች ናቸው፡፡ እነዚህንም ሰይጣን የሚዋጋበት ለእያንዳንዱ እንደየድካሙ ሊያጠቃው ይሞክራልና ያንን ድል የሚነሱበትን ምሥጢር እንደሚያድላቸው ያጠይቃል፡፡ አዕሩግን በፍቅረ ንዋይ፣ ወራዙትን በዝሙት ጦር፣ አንስትን በትውዝፍት (የምንዝር ጌጥ)፣ ካህናትን በትዕቢት፣ መነኮሳትን በስስት ጦር ሰይጣን ይዋጋቸዋል፡፡ እነርሱም በጥምቀት ባገኙት ኃይል (የልጅነት ሥልጣን) ድል ያደርጉታልና የዚያ ምሳሌ ነው፡፡ ለመጻጕዕ መፈወስ የዘመድ ጋጋታ፣ የሰዎች ርዳታ አላስፈለገውም፡፡ በእግዚአብሔር ቃል ብቻ ተፈውሷል፡፡ ለዚህም ነው ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት በመዝሙሩ ‹‹ችግረኛውን ከቀማኛው እጅ፤ ረዳት የሌለውንም ምስኪን ያድነዋልና፤›› (መዝ.፸፪፥፲፪) ሲል የተቀኘው፡፡ ጻድቁ ኢዮብም እንዲሁ ‹‹ረዳት (ኃይል) የሌለውን ምንኛ ረዳኸው፤›› (ኢዮ.፳፮፥፪) በማለት የእግዚአብሔርን አዳኝነት መስክሯል፡፡

የድንግል ማርያም ልጅ ኢየሱስ ክርስቶስ በሕይወቱ የደረሰለት ሰው እንዲህ ይባረካል፡፡ ስለዚህ ሰው የለኝም፣ ገንዘብ የለኝም፣ ሥልጣን የለኝም፣ ወገን የለኝም፣ ረዳት የለኝም በማለት ተስፋ የቆረጥን ሰዎች እግዚአብሔር ከሰውም፣ ከሥልጣንም፣ ከገንዘብም በላይ ነውና እርሱን ተስፋ አድርገን ዅል ጊዜ በስሙ መጽናናት እና የሚያስጨንቀንን ዅሉ በእርሱ ላይ መጣል እንደሚገባን መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡ ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት ‹‹አቤቱ የሚፈልጉህ ዅሉ በአንተ ደስ ይበላቸው፤ ሐሴትም ያድርጉ፡፡ ዅልጊዜ ማዳንህን የሚወዱ ዘወትር እግዚአብሔር ታላቅ ይኹን ይበሉ፤›› (መዝ.፵፥፲፮) እንዳለው ዅሉ ዅል ጊዜም በአምላካችን እግዚአብሔር ደስተኞች እንኹን፡፡

   ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ዐቢይ ጾም

በሊቀ ጉባኤ ቀለመወርቅ ውብነህ

የካቲት ፳፰ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

ጾም ማለት መተው መከልከል ማለት ነው፡፡ ጾም በእግዚአብሐር የተቀደሰ ተግባር ስለኾነ ወደ ቅድስና ጎዳና የሚመራ ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያናችንም ሥርዓት ሠርታ ጾመን ከአምላካችን ጋር ኅብረት እንዲኖረን፤ መንፈሳዊ ኃይል እንድናገኝ ታደርጋለች፡፡ በጾም ወራት ከመባልዕት መከልከል ብቻ ሳይኾን ዐይን ክፉ ከማየት፣ አንደበት ክፉ ከመናገር፣ ጆሮ ክፉ ከመስማት መቆጠብ እንደሚገባው በቅዱሳት መጻሕፍት ተጽፎአል፡፡ ‹‹ይጹም ዐይን ይጹም ልሳን እዝንኒ ይጹም እምሰሚዓ ኀሡም በተፋቅሮ›› እንዲል ቅዱስ ያሬድ /ጾመ ድጓ/፡፡ በጾም ወራት ላምሮት፣ ለቅንጦት የሚበሉ ወይም ለመንፈሳዊ ኃይል ተቃራኒ የኾኑ ሥጋዊ ፍትወትን የሚያበረታቱ፣ ሥጋንና የሚያሰክሩ መጠጦችን /ዳን.፲፥፪-፫/፣ ቅቤና ወተትን ከመጠቀም መታቀብ እንደሚገባ ታዟል /መዝ.፻፰፥፳፬፣ ፩ቆሮ.፯፥፭፤ ፪ቆሮ.፮፥፮/፡፡

በብሉይ ኪዳን ጾም ከፍተኛ ቦታ ነበረው፡፡ የብሉይ ኪዳን ነቢያት ከእግዚአብሔር በሚገናኙበት ወራት እህልና ውኃ በአፋቸው አይገባም ነበር /ዘፀ.፴፬፥፳፰/፡፡ አስቴር አስቀድማ ሦስት ቀን ጾማ ጸልያ በእስራኤል ላይ የመጣውን መቅሠፍት እንዲመለስ አድርጋለች /አስቴር ፬፥፲፭-፲፮/፡፡ በዘመኑ በኃጢአት ብዛት የታዘዘው የእግዚአብሔር መዓት የሚመለሰውም ሕዝቡ በጾም ሲለምኑትና ሲማልዱት ነበር  /ዮናስ ፪፥፯-፲/፡፡ በሐዲስ ኪዳንም ጾም ሰው ሠራሽ ሕግ ሳይኾን ራሱ ክርስቶስ የሠራው ሕግ ነው /ማቴ.፬፥፪፤ ሉቃ.፬፥፪/፡፡ ቅዱሳን ሐዋርያትም በየጊዜው ከመንፈስ ቅዱስ ትእዛዝ የሚቀበሉት በጾም በጸሎት ላይ እንዳሉ ነበር /ሐዋ.፲፫፥፪/፡፡ ለስብከተ ወንጌል የሚያገለግሉ ዲያቆናትና ቀሳውስትም የሚሾሙት በጾምና በጸሎት ነው /ሐዋ.፲፫፥፫፤ ፲፬፥፳፫/፡፡ እንደ ቆርነሌዎስ ያሉ ምእመናን ያላሰቡትን ክብር ያዩና ያገኙ የነበረውም በጾምና በጸሎት ፈጣሪያቸውን በመማጸን ነው /ሐዋ.፲፥፴/፡፡

ዐቢይ ጾም ጌታችን ከተጠመቀ በኋላ ዐርባ ቀን የጾመው፤ እኛም እንድንጾማቸው በቤተ ክርስቲያናችን ከታዘዝናቸው ሰባቱ የአዋጅ አጽዋማት አንዱ ነው፡፡ ምእመናን ጌታችን ያደረገውን ምሳሌ ተከትለን ጾሙን በየዓመቱ እንጾመዋለን፡፡ ዐቢይ ጾም ስምንት ሳምንታት (፶፭ ቀኖች) አሉት፡፡ በውስጡ ስምንት ቅዳሜዎች፣ ሰባት እሑዶች ይገኛሉ፡፡ ይኸውም ዐሥራ አምስት ቀን ማለት ነው፡፡ እነዚህ ቀናት ከጥሉላት እንጂ ከእኽል ውኃ ስለማይጦሙ የጦሙ ወራት ዐርባ ቀን ብቻ ይኾናል፡፡

ጾሙ በተለያዩ ስሞች ይጠራል፤ አንደኛ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከተጠመቀ በኋላ የጾመው በመኾኑ፣ እንደዚሁም ‹‹ዐቢይ እግዚአብሔር ወዐቢይ ኀይሉ ዐቢይ እግዚአብሔር ወብዙኅ አኰቴቱ›› /መዝ.፵፯፥፩፤ መዝ.፻፵፮፥፭/ የተባለ ጌታችን የጾመው ጾም ስለኾነ ‹‹ዐቢይ ጾም›› ይባላል፡፡ ሁለተኛ ‹‹ሁዳዴ ጾም›› ይባላል፡፡ ይህም የመንግሥት እርሻ ወይም ማንኛውም የሕዝብ ብዛት ያለበት ሥራ ሁዳድ ስለሚባል ሲኾን፣ ዐቢይ ጾምም ከአጽዋማት ዅሉ ብዙ ቀናት ስለሚጾምና ኃያሉ አምላካችን ስለጾመው ነው /አሞ.፯፥፩/፡፡ ሦስተኛ ‹‹በአተ ጾም›› ይባላል፡፡ የጾም መግቢያ፣ መባቻ ማለት ነው፡፡ አራተኛ ‹‹ጾመ ዐርባ›› ይባላል፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የጾመው ፵ ቀን ስለኾነ /ማቴ.፬፥፩/፡፡ አምስተኛ ‹‹ጾመ ኢየሱስ›› ይባላል፡፡ ጌታችን እርሱ ጾሞ፣ ጹሙ ብሎ ስላዘዘን፡፡ ስድስተኛ ‹‹ጾመ ሙሴ›› ይባላል፡፡ ቅዱስ ያሬድ በዘወረደ ጾመ ድጓው ‹‹ከመዝ ይቤ ሙሴ እስመ ለዓለም ሙሴኒ ይቤ በውስተ ኦሪት›› እያለ ስለዘመረ /የሰኞ ዕዝል/፡፡

ከዐቢይ ጾም ሳምንታት መካከል የመጀመሪያው ሳምንት ‹‹ዘወረደ (ዘመነ አዳም)›› ይባላል፡፡ ዘወረደ ማለት ከላይ የመጣ፣ የወረደ ማለት ነው፡፡ ይህም አምላካችን አዳምንና ልጆቹን ከሞት ለማዳን ሲል ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሰው መኾኑንና የፈጸመውን የማዳን ሥራ ያመለክታል፡፡ ‹‹ከሰማይ ከወረደው በቀር ወደሰማይ የወጣ የለም›› ካለው ከጌታችን ከመድኃኒታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ቃል በመነሣት ሊቁ ቅዱስ ያሬድ ‹‹ዘወረደ እምላዕሉ አይሁድ ሰቀሉ ወሚመ ኢያእመሩ እግዚአ ኵሉ ዘየሐዩ በቃሉ›› በማለት በጾመ ድጓው መጀመሪያ ላይ ይህን ዕለት ገልጾታል፡፡ ትርጕሙም ‹‹አዳምን ለማዳን ከሰማይ የወረደውን አምላክ አይሁድ ሰቀሉት፤ የሰማይ ሥልጣን ያለው የዅሉ ጌታ እንደኾነም ምንም አላወቁም›› ማለት ነው፡፡ ይህም ድርሰት በቤተ ክርስቲያናችን የጾም መጀመሪያ የኾነው ዕለተ ሰንበት ዋዜማ፣ መግቢያ (መሐትው) ኾኖ ከዋዜማ በፊት ምንጊዜም በየዓመቱ ይቆማል፤ ይዘመራል፤ ይመሰገናል፡፡

በዚህ ሳምንት በተለይም እሑድና ሰኞ የሚነገሩት ውዳሴያት ከመጻሕፍተ ኦሪትና ነቢያት የተወሰዱ ናቸው፡፡ ሁለተኛም ሳምንቱ ‹‹ሙሴኒ›› በመባል ይታወቃል፡፡ እግዚአብሔር አምላክ አዳምን ለማዳን ከሰማይ መውረዱንና በመስቀል መሰቀሉን ስለሚያወሳ ነው፡፡ በተጨማሪም ይህ የመጀመሪያው ሳምንት ‹‹ጾመ ሕርቃል›› ይባላል፡፡ ሕርቃል (ኤራቅሊየስ) የቤዛንታይን ንጉሥ ነበር፡፡ ይህ ሳምንት በስሙ የተጠራበት ምክንያት በዘመኑ ፋርሶች ኢየሩሳሌምን ወርረው፣ የጌታችንን መስቀል ማርከው ወስደውት ነበር፡፡ እርሱ ወደ ፋርስ ዘምቶ መስቀሉን ከእነርሱ ነጥቆ ይዞ ወደ ኢየሩሳሌም ተመልሷል፡፡

ሕርቃል ከፋርሶች ጋር ከመዋጋቱ በፊት ሐዋርያት በሲኖዶሳቸው ‹‹ነፍስ የገደለ ሰው እስከ ዕድሜ ልኩ ይጹም›› ብለው ሥርዓት ሠርተዋልና ጾሙን ፈርቶ ስለነበር በኢየሩሳሌም የነበሩ ምእመናን አሳቡን ደግፈው ‹‹አንተ ጠላታችንን አጥፋልን፤ መስቀሉን አስመልስልን እንጂ የአንድ ሰው ዕድሜ ቢበዛ ሰባ፣ ሰማንያ ዓመት ነው፡፡ ጾሙን አምስት አምስት ቀን ተከፋፍለን እኛ እንጾምልሃለን›› ብለው ጾመውለታል፡፡ ይህንን መሠረት በማድረግ ያላወቁት አንድ ጊዜ ጾመው ትተውታል፡፡ ያወቁት ግን ቀድሞም ሐዋርያት ጾመውታል ብለው ሥርዓት አድርገው በዓመት በዐቢይ ጾም መጀመሪያ ላይ ጾመ ሕርቃል እያሉ የሚጾሙት ኾነዋል፡፡ ቤተ ክርስቲያናችን ይህንን ሥርዓት መሠረት በማድረግ ከጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጾም የመጀመሪያውን ሳምንት ጾመ ሕርቃል በሚል ስም ሰይማ እንዲጾም አድርጋለች (የመጋቢት ፲ ቀን ስንክሳርን ይመልከቱ)፡፡

በቅዱስ ያሬድ ጾመ ድጓ ዘወረደ እየተባለ የሚታወቀው፣ በጾመ ዐርባው ወቅት በተለይም በመጀመሪያው ሳምንት የሚገኘው ድርሰት በነግህ በሠለስት፣ በቀትርና በሠርክ እንደዚሁም ቅዳሜና እሑድ በሌሊት የሚዘመር ነው፡፡ በውስጡም የያዘው ፍሬ ሐሳብ የጾምን፣ የጸሎትን፣ የምጽዋትንና የፍቅርን ጠቃሚነት አጕልቶ የሚያስተምር ነው፡፡ ሊቁ ቅዱስ ያሬድ በዘወረደ ጾመ ድጓው ‹‹አዘዞ እግዚአብሔር ለሙሴ ወይቤሎ ሰብእከ ወላህምከ ወኵሉ ቤትከ ያዕርፉ በሰንበት፤ እግዚአብሔር ሙሴን ሕዝብህ የከብትህ መንጋህ ቤተሰብህ ዅሉ በሰንበት ቀን ከድካማቸው ይረፉ በማለት አዘዘው፤›› በማለት ሰንበት ለሰው ልጆች ብቻ ሳይኾን፣ ሕይወት ላለው ነገር ዅሉ ጸጥታና ሰላም የሰፈነባት የዕረፍት ቀን ስለመኾኗ ተናግሯል /ዘፀ.፳፥፲፤ ፳፫፥፲፪/፡፡ በዚህም ወቅቱ ‹‹ዘመነ ጾም›› ወይም ‹‹ጾመ ሙሴ›› ይባላል፡፡

በአጠቃላይ ጾምን መጾም የፈቃድ ብቻ ሳይኾን የትእዛዝም ነው፡፡ ነቢዩ ኢዩኤል ‹‹ቀድሱ ጾመ ወስብኩ ምሕላ …፤ ጾምን ያዙአጽኑ፡፡ ምሕላንም ዐውጁ፡፡ ሸማግሌዎቹን ከፈጣሪያችን ቤት ሰብስባችሁ በአንድነት ኾናችሁ ወደ እግዚአብሔር ጩኹ (ለምኑ)፤›› ብሏል /ኢዩ.፩፥፲፩፤ ፪፥፲፪፤ ፲፪፥፲፭-፲፮/፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስም ‹‹ወኩኑ ላእካነ ለእግዚአብሔር በጾም ወበንጽሕ፤ በጾም፣ በንጽሕና ተወስናችሁ እግዚአብሔርን አገልግሉ፤›› ብሏል /፪ቆሮ.፮፥፬-፮/፡፡ ጾም ባያስፈልግ ኖሮ ጌታችን ‹‹በምትጾሙበት ጊዜ እንደ ግብዞች አትኹኑ … ስለ ጽድቅ የሚራቡ የሚጠሙ ንዑዳን ክብራን ናቸው፤›› ባላለም ነበር /ማቴ.፭፥፮-፲፮/፡፡ ነቢዩ ዳዊትም ‹‹ጕልበቶቼ በጾም ደከሙ፤ ሥጋዬም ቅባት በማጣት ከሳ፤›› /መዝ.፻፰፥፳፬/ ማለቱ የጾምን አስፈላጊነት ያስረዳል /ዳን. ፱፥፫-፬፤ ፲፬፥፭/፡፡ በቁራኝነት አብሮ የሚኖር መንፈስ ርኩስ (ሰይጣን) እንኳን በጾም የሚወገድ መኾኑን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተናግሮአል /ማቴ.፲፯፥፳፩፤ ማር.፱፥፪/፡፡

ቅዱሳን ሐዋርያት ‹‹ሙሽራውን ከእነሱ ለይተው የሚወስዱበት ጊዜ ይመጣል፡፡ ያን ጊዜ ይጾማሉ፤›› ያለውን የጌታን ቃል መሠረት በማድረግ ጌታችን ሞቶ ከተነሣ እና ካረገ በኋላ ጾመዋል፤ የጾምንም ሕግ ሠርተዋል /ሐዋ.፲፫፥፫/፡፡ ሠለስቱ ምዕትም ‹‹ሐዋርያት የጾሙትንና እንዲጾም የወሰኑትን መጾም ይገባል›› ብለው አጽዋማትን እንድንጾም መወሰናቸው ይህን የጌታችንን ቃል መሠረት በማድረግ ነው፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ሠራዔ ሕግ እንደመኾኑ ዐርባ ቀን ዐርባ ሌሊት ጾሞ እንጂ ዝም ብሎ ጾሙ አላለንም፡፡ ስለዚህ ጾም ትእዛዝ (ሕግ) መኾኑን ተገንዝበን ዅላችንም መጾም አለብን፡፡ ጾመን ለማበርከት ያብቃን!

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ኪዳነ ምሕረት

%e1%8a%aa%e1%8b%b3%e1%8a%95

በዲያቆን ኃይለ ኢየሱስ ቢያ

የካቲት ፲፭ ቀን ፳፻፱ .

‹‹ኪዳን›› የሚለው ቃል ‹‹ተካየደ – ተዋዋለ፤ ቃል ኪዳን ተጋባ፤ ተማማለ›› ከሚለው የግእዝ ግስ የተገኘ ሲኾን፣ ትርጕሙም ኪዳን፣ ውል፣ መሐላ፣ ቃል ኪዳን፣ የውል ቃል ማለት ነው /ዘዳ.፳፱፥፩፤ ኤር.፴፩፥፴፩-፴፫፤ መዝ.፹፰፥፫/፡፡ በሌላ በኩል ኪዳን የጸሎት ስም ሲኾን፣ ጌታችን ሞትን ድል አድርጎ ከተነሣ በኋላ፣ ከማረጉ በፊት ለሐዋርያት ያስተማራቸው ጸሎት ኪዳን ይባላል፡፡ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ከልጇ ከወዳጇ ከጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የምሕረት ቃል ኪዳን (ውል፣ ስምምነት) የተቀበለችበት ዕለት (የክብረ በዓል ስም) ደግሞ ኪዳነ ምሕረት ይባላል፡፡

በየዓመቱ የካቲት ፲፮ ቀን የምናከብረው ይህ በዓል እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በጎልጎታ በልጇ በመቃብር ላይ ኾና ‹‹ኦ ወልድየ ወፍቁርየ እስእለከ በእንተ ዘተሰባእከ እምኔየ ወበማኅፀንየ ዘጾረተከ፤ ልጄ ወዳጃ ሆይ ከሥጋዬ ሥጋ፣ ከነፍሴ ነፍስ ነሥተህ ሰው ስለመኾንህ፤ ዘጠኝ ወር ከአምስት ቀን ስለቻለችህ ማኅፀኔ፤ ከአንተ ጋር ከአገር ወደ አገር ስለመሰደዴ መጥተህ ልመናዬን ትሰማኝ ዘንድ እለምንሃለሁ›› እያለች ስትጸልይ ጌታ እልፍ አእላፍ መላእክቱን አስከትሎ ወደእርሷ መጥቶ ‹‹ሰላም ለኪ ማርያም እምየ፤ እናቴ ማርያም ሰላም ላንቺ ይኹን! እንዳደርግልሽ የምትለምኚኝ ምንድን ነው?›› አላት፡፡ እመቤታችንም በስሟ የሚማጸኑትንና መታሰቢያዋን የሚያደርጉትን፣ ለችግረኛ የሚራሩትን፣ ቤተ ክርስቲያን የሚያንጹትን፤ ዕጣን ዘይትና መብአ ለቤተ ክርስቲያን የሚሰጡትን፤ ለእመቤታችንና ለሃይማኖታቸው ካላቸው ፍቅር የተነሣ ልጆቻቸውን በስሟ የሰየሙትን ዅሉ እንዲምርላትና ከሞተ ነፍስ እንዲያድንላት ጠየቀችው፡፡

ጌታችንም ‹‹ይህን ዅሉ እንዳደርግልሽ መሐልኩ ለኪ በርእስየ ወበአቡየ ወበመንፈስ ቅዱስ ሕያው፤ በራሴ፣ በአባቴ እና በመንፈስ ቅዱስ ማልኩልሽ›› ብሎ ቃል ኪዳን ገብቶላት ወደ ሰማይ ዐርጓል፡፡ ለዚህም ነው ቅዱስ ያዕቆብ ዘሥሩግ በቅዳሴው ‹‹… ዳግመኛም በእናትህ በማርያም ተማፅነናል፤ ይህችውም አንተን በመውለድ እመቤታችንና የባሕርያችን መመኪያ ናት፡፡ አንተ ‹መታሰቢያሽን ያደረገ፣ ስምሽንም የጠራ፣ የዘለዓለም ድኅነትን ይድናል› ብለሃታልና …፤›› በማለት የሚማጸነው፡፡

በተአምረ ማርያም መጽሐፍ እንደተመዘገበው በዚህ ዕለት የሚታሰቡ ሁለት ተአምራት አሉ፤ ከእነዚህም አንደኛው የስምዖን ታሪክ ነው፡፡ ስምዖን የሚባል እንግዳ ተቀባይ ደግ ሰው ነበር፡፡ ሰይጣን ለምቀኝነት አያፍርምና ከዕለታት አንድ ቀን በእንግድነት ከቤቱ ገብቶ ‹‹ልጅህን አርደህ ካላበላኸኝ ሌላ ምግብ አልበላም›› አለው፡፡ በዚህ ጊዜ ስምዖን ሲያወጣና ሲያወርድ ቆየና ‹‹አብርሃም ልጁን ሰውቶ ነው የእግዚአብሔር ሰው የተባለው›› በማለት፣ ‹‹የእግዚአብሔርን እንግዳ›› ላለማሳዘን ሲል ልጁን አርዶ አቀረበለት፡፡ እንግዳ መሰሉ ሰይጣንም ሥጋውን ቅመስልኝ ብሎ ግድ አለው፡፡ ስምዖንም (በላዔ ሰብእ) አርዶ ያዘጋጀውን የልጁን ሥጋ በቀምሰ ጊዜ ሰይጣን ስላደረበት (ስለተዋሐደው) ከዚያች ሰዓት ጀምሮ ቤተሰቦቹን፣ ጎረቤቶቹንና መንገደኛውን ዅሉ ይበላ ጀመር፡፡ በአጠቃላይ ፸፰ ሰዎችን ከበላ በኋላ አንድ በቍስል የተመታ ሰው አገኘና ሊበላው ሲል ‹‹ውኃ አጠጣኝ›› ብሎ በሥላሴ፣ በቅዱስ ሚካኤል፣ በቅዱስ ገብርኤል ስም ለመነው፤ እርሱም ዝም አለው፡፡

በመጨረሻም ‹‹በድንግል ማርያም ስም›› አለው፡፡ ስምዖን የእመቤታችንን ስም በሰማ ጊዜም ወደ ልቡናው ተመልሶ ‹‹እስኪ ቃሉን ድገመው›› አለው፤ በሽተኛውም መልሶ ‹‹ስለ ድንግል ማርያም ውኃ አጠጣኝ›› ብሎ ለመነው፡፡ ያን ጊዜ ‹‹ይህችስ እንደምታስምር በልጅነቴ ሰምቻለሁ›› ብሎ ጥቂት ውኃ ሰጠው፤ ውኃው ጕሮሮውን እንኳን ሳያርስለት ‹‹ጨረስህብኝ›› ብሎ ነጥቆት ሔደ፡፡ በሌላ ቦታም አንድ ገበሬ አግኝቶ ሊበላ ሲል ገበሬው ‹‹በላዔ ሰብ የምትባል አንተ ነህ?›› ባለው ጊዜ ‹‹ለካስ አመሌን ሰው ዅሉ አውቆብኛል›› ብሎ ዋሻ ገብቶ በመጸጸት በዚያው ሞተ፡፡ ነፍሱንም መላእክተ ጽልመት መጥተው ሲወስዷት እመቤታችን ‹‹ልጄ በማይታበል ቃልህ ይህችን ነፍስ ማርልኝ?›› አለችው፡፡ ጌታችንም ‹‹ሰባ ስምንት ነፍስ ያጠፋ፣ ፈጣሪውን የካደ ሰው ይማራልን?›› አላት፡፡ እመቤታችንም ‹‹በስሜ የተጠማውን ውኃ አጥጥቶ የለምን?›› ብላ ስምዖንን (በላዔ ሰብእን) አስምራዋለች፡፡ ነፍሱንም መላእክተ ብርሃን መጥተው ወደ ገነት አስገብተዋታል፡፡

ሁለተኛው ተአምር ደግሞ ከብሮ ከኖረ በኋላ ለድህነት በተጋለጠ አንድ ምእመን ላይ የተደረገ ነው፤ ከክርስቲያን ወገን የኾነ ሀብት አግኝቶ ያጣ አንድ ሰው ነበር፡፡ ከዕለታት አንድ ቀን ‹‹ከብሬ በኖርኹበት አገር ተዋርጄ አልኖርም›› ብሎ ጓዙን ጠቅልሎ ከአገሩ ወጥቶ ሲሔድ ሰይጣን ያዘነ ሰው መስሎ ደንጊያውን በምትሐት ወርቅ አስመስሎ ‹‹ሥላሴን፣ ጻድቃንን፣ ሰማዕታትንን፣ መላእክትን ካድልኝና ይህን ወርቅ እሰጥሃለሁ›› አለው፡፡ ዅሉንም ካደለትና ወርቁን ተቀብሎ ዞር ሲል ‹‹ምእመናን የሚመኩባት ድንግል ማርያምየአምላክ እናት አይደለችም› ብለህ ካድልኝ›› አለው፡፡ ሰወየውም ‹‹እርሷንስ አልክድም›› ስላው በደንጊያ ቀጥቅጦ ገደለው፡፡ መላእክተ ጽልመት የሟቹን ነፍስ ሊወስዱ ሲሉ መላእክተ ብርሃንም አብረው ቀረቡ፡፡ እመቤታችንም ጌታችንን ‹‹ልጄ ይህችን ነፍስ ማርልኝ?›› አለችው፡፡ እርሱም ‹‹ከልብኑ ይትመሐር እምየ፤ እናቴ፣ ውሻ ይማራልን?›› አላት፡፡ እመቤታችንም፡- ‹‹‹ስምሽን የጠራውን፣ መታሰቢያሽን ያደረገውን እምርልሻለሁ› ያልኸው ቃል ይታበላልን?›› አለችው፡፡ በዚህ ጊዜ ‹‹ምሬልሻለሁ›› አላት፡፡

እግዚአብሔር አምላካችን ‹‹ከመረጥኳቸው ጋር ቃል ኪዳን አደረግሁ›› ባለው መሠረት ከቅዱሳን ጋር ያደረጋቸው ቃል ኪዳኖች ብዙዎች ናቸው፡፡ ከእነዚህም መካከል ከላይ በተአምራቱ እንደተመለከትነው አንዱ ለእመቤታችን የሰጠው የአማላጅነት ኪዳን ነው፡፡ ማማለድ ማለት ስለሌላው መጸለይ፣ መለመን፣ የደረሰውን ችግር እንዲወገድ ማድረግ፣ ማስማር (ይቅርታ ማሰጠት) ማለት ነው፡፡ በዚሁ መሠረት ከእግዚአብሔር በታች ከቅዱሳን ዅሉ በላይ ከፍ ከፍ ያለችና የከበረች እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ከእግዚአብሔር በተሰጣት የማማለድ ሥልጣን ‹‹ሰአሊ ለነ ቅድስት፤ ቅድስት ሆይ ለምኚልን›› እያሉ ለሚለምኗት ዅሉ ከእግዚአብሔር እያማለደችና እየለመነች ምሕረትን እንደምታሰጥ ቀናውንና የተመሰገነውን ሃይማኖት የምንከተል ምእመናን ዅሉ እናምናለን፡፡ ምክንያቱም ቅድስት ድንግል ማርያም የእግዚአብሔር እናትና አገልጋይ እንደመኾኗ ከዅሉም ቅዱሳን በበለጠ ለእግዚአብሔር ቅርብ ናትና፡፡ በእግዚአብሔር ዘንድም ኾነ በሰው ዘንድ ባለሟልነትን ማግኘት ወይም ቅርብ መኾን ደግሞ አንድን ጉዳይ በቀላሉ ለማስፈጸም ይጠቅማል፡፡ ለምሳሌ፡-

  • መልአኩ ቅዱስ ገብርአል በእግዚአብሔር ፊት የሚቆም ባለሟል በመኾኑ የድኅነትን ምሥጢር አብሣሪ ኾኗል /ሉቃ. ፩፥፲፱-፳፮/፡፡
  • አስቴር የንጉሡ አርጤክስስ ሚስት በመኾኗ በወገኖቿ አይሁድ የታወጀውን የሞት አዋጅ አስለውጣለች /መጽሐፈ አስቴር ፫፥፲/፡፡
  • ነቢዩ ሙሴ በእግዚአብሔር ፊት ባለሟል በመኾኑ ‹‹ይህንን ኀጢአታቸውን ይቅር በላቸው፤ ያለዚያ ግን እኔን ከጻፍከው መጽሐፍህ እባክህ ደምስሰኝ?›› በማለት ለእስራኤላውያን ምሕረትን አሰጥቷል /ዘፀ.፴፪፥፲፬/፡፡

ስለዚህ የቅድስት ድንግል ማርያም አማላጅነትም እንደ ፀሐይ የበራ ሐቅ ነው፡፡ ይህንን እውነት ቅዱስ ያሬድ ሲመሰክር፡- ‹‹ወታስተሠርዪ ኀጢአተ ሕዝብኪ ተበውሀ ለኪ እምአብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ ወከመ ትኩኒ ተንከተመ ለውሉደ ሰብእ ለሕይወት ዘለዓለም፤ ለሕዝብሽ፣ ለወገኖችሽ የኃጢአት ይቅርታን ታሰጪ ዘንድ፤ ዘለዓለማዊ ሕይወትንም ለሚወርሱ ዅሉ መሸጋገሪያ ድልድይ ትኾኚ ዘንድ ከአብ ከወልድ ከመንፈስ ቅዱስ ዘንድ ሥልጣን አግኝተሻል›› በማለት አመስግኗታል /አንቀጸ ብርሃን/፡፡ አባ ጽጌ ድንግልም በማኅሌተ ጽጌ ድርሰታቸው፡- ‹‹ሶበሰ ኪዳንኪ ምክንያተ ድኂን ኢሀሎ ፈለገ እሳት ወደይን እም አሰጠመ ኩሎ፤ የድኅነት ምክንያት ቃል ኪዳንሽ ባይኖር ኖሮ የጥፋት እሳት፣ መርገም (ኀጢአት) ባጠፋን ነበር›› ብለዋል፡፡ አባ ሕርያቆስም በቅዳሴው፡‹‹ጥፋትን ያይደለ ይቅርታን አሳስቢ፡፡ መዓትን ያይደለ ምሕረትን አሳስቢ፡፡ ለጻድቃን ያይደለ ለኀጥአን አሳስቢ፡፡ ለንጹሐን ያይደለ ለተዳደፉት አሶስቢ፤›› ሲሉ ይማጸኗታል /ቅዳሴ ማርያም ቍ.፻፷፭-፻፸፩/፡፡

ስለዚህም ዘወትር በሥርዓተ ቅደሴአችን፡- ‹‹ድኅነትን የምንለምንሽ ክብርን የተመላሽ ቅድስት ሆይ ደስ ይበልሽ፡፡ ዅል ጊዜ ድንግል የምትኾኚ አምላክን የወለድነሽ የክርስቶስ እናት ሆይ ኀጢአታችንን ያስተሠርይልን ዘንድ ወደ ልጅሽ ወደ ወዳጅሽ ወደ ላይ ጸሎታችንን አሰርጊልን፡፡ በእውነት የጽድቅ ብርሃን የሚሆን አምላካችንን ክርስቶስን የወለድሽልን ንጽሕት ሆይ ደስ ይበልሽ፡፡ ንጽሕት ድንግል ሆይ ለነፍሳችን ይቅርታን ያደርግ ዘንድ፤ ኀጢአታችንንም ያስተሠርይልን ዘንድ ወደ ጌታችን ለምኚልን፡፡ በእውነት ለሰው ወገን አማላጅ የምትሆኝ አምላክን የወለድሽ ንጽሕት ቅድስት ድንግል ማርያም ሆይ ደስ ይበልሽ፡፡ የኀጢአታችንን ሥርየት ይሰጠን ዘንድ በልጅሽ በክርስቶስ ፊት ለምኝልን፡፡ በእውነት ንግሥት የምትኾኚ ንጽሕት ድንግል ሆይ ደስ ይበልሽ፡፡ የባሕርያችን መመኪያ ሆይ ደስ ይበልሽ፡፡ አምላካችን አማኑኤልን የወለድሽልን ሆይ ደስ ይበልሽ፡፡ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ፊት እውነተኛ አስታራቂ ሆነሽ ታስቢን ዘንድ እንለምንሻለን፡፡ ለነፍሳችን ይቅርታን ያደርግልን ዘንድ ኀጢአታችንንም ያስተሰርይልን ዘንድ፤›› በማለት እመቤታችንን እንማጸናታለን፡፡

በአጠቃላይ ‹‹ኪዳነ ተካየድኩ ምስለ ኅሩያንየ፤ ከመረጥኋቸው ጋር ቃል ኪዳን አደረግሁ፤›› በማለት በነቢዩ ቅዱስ ዳዊት አድሮ ራሱ እግዚአብሔር ከመረጣቸው አበው ነቢያት፣ ጻድቃን፣ ቅዱሳንና ሰማዕታት ጋር ቃል ኪዳን እንደ ገባ፣ እንደሚገባ ተናግሯል /መዝ.፹፰፥፫/፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስም ‹‹እንግዲህ እርሱ ራሱ ካጸደቀ እግዚአብሔር የመረጣቸውን ሰዎች የሚቃወማቸው ማን ነው?›› በማለት እግዚአብሔር ሰዎችን እንደሚጠራ፣ እንደሚያከብር፣ እንደሚቀድስና ቃል ኪዳን እንደሚሰጥ ነግሮናል /ሮሜ.፰፥፴፫/፡፡ ቅዱስ ዳዊት ‹‹ነኪር ነገሩ በእንቲአኪ ሀገረ እግዚአብሔር፤ የእግዚአብሔር ከተማ ሆይ ስለ አንቺ የተነገረው ነገር ድንቅ ነው፤›› /መዝ.፹፮፥፫/ በማለት እንደተናገረው እግዚአብሔር አምላካችን ለእመቤታችን ለቅድስት ድንግል ማርያም የገባው ቃል ኪዳን ከቅዱሳን ቃል ኪዳን ዅሉ ልዩ ነው፡፡ ይህም እንደምን ነው ቢሉ፡-

  • ለአምላክ እናትነት የተመረጠች ልዩ እናት በመኾኗ፤
  • አምላክ ከሥጋዋ ሥጋ፣ ከነፍሷ ነፍስ ነሥቶ ከእርሷ በመወለዱ፤
  • ከመለለዷ በፊት፣ በወለደች ጊዜ፣ ከወለደች በኋላ ምን ጊዜም ድንግል በመኾኗ፤
  • በሁለቱም ወገን (በአሳብም በገቢርም) ድንግል በመኾኗ፤
  • አማላጅነቷ የወዳጅነት ሳይኾን የእናትነት በመኾኑ፤
  • ዓለም ይድን ዘንድ የድኅነት ምክንያት አድርጎ አምላክ ስለመረጣት ነው፡፡

ስለዚህ ብዙ ከንቱ አሳቦችን ትተን፣ እንደበላዔ ሰብእ በቃል ኪዳኗ ተጠቅመን፣ ንስሐ ገብተን፣ ቅዱስ ሥጋውን ክቡር ደሙን ተቀብለን፣ የስሙ ቀዳሽ፣ የመንግሥቱ ወራሽ ለመኾን ያብቃን፡፡ የእግዚአብሔር ቸርነት፣ የእመቤታችን አማላጅነት፣ የቅዱሳን ተራዳዒነት አይለየን፡፡

ዋቢ መጻሕፍት፡-

  • መጽሐፈ ስንክሳር
  • መዝገበ ታሪክ
  • ተአምረ ማርያም
  • አማርኛ መዝገበ ቃላት
  • ክብረ ቅዱሳን

ልደተ ስምዖን ነቢይ

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

የካቲት ፰ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

የተወደዳችሁ የድረ ገጻችን ተከታታዮች! ጥር ፭ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ‹‹በዓለ ግዝረት›› በሚል ርእስ ባቀረብነው ትምህርታዊ ጽሑፍ ነቢዩ ስምዖን ጌታችንን እንደ ታቀፈውና ከእርግናው እንደ ታደሰ፤ ከክርስቶስ ቤዛነት ጋር የተያያዘ ትንቢት እንደ ተናገረ፤ ነቢዪት ሐናም የክርስቶስን የማዳን ሥራ ለሕዝቡ ዅሉ እንደ መሰከረች መግለጻችን ይታወሳል፡፡ ኾኖም ግን ይህ ታሪክ የሚነገረው ጌታችን ሥርዓተ ግዝረትን በፈጸመበት ዕለት (ጥር ፮ ቀን) ሳይኾን ጌታችን ወደ ቤተ መቅደስ በገባበት ዕለት (የካቲት ፰ ቀን) መኾኑን እንድትገነዘቡልን በትሕትና እያሳሰብን ወደ ዛሬው ዝግጅታችን እንወስዳችኋለን፤

በቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን በየዓመቱ የካቲት ፰ ቀን ከሚከበሩ በዓላት መካከል የጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ቤተ መቅደስ መግባት፣ የነቢዩ ስምዖን ልደት (መታደስ) እና የነቢዪት ሐና ዕረፍት በስፋት ይነገራል፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በተወለደ በስምንተኛው ቀን (ጥር ፮ ቀን) በኦሪቱ ሕግ መሠረት ሥርዓተ ግዝረትን ፈጽሟል፡፡ በተወለደ በዐርባኛ ቀኑ (የካቲት ፰ ቀን) ደግሞ ወደ ቤተ መቅደስ ገብቷል፡፡ (ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከተወለደበት ከታኅሣሥ ፳፱ ቀን ጀምረን ስንቈጥር  የካቲት ፰ ዐርባኛው ቀን ነው፡፡)

በቅዱስ ወንጌል እንደ ተመዘገበው ከሕርስ ደም የሚነጹበት ጊዜ ሲደርስ ‹‹የእናቱን ማኅፀን የሚከፍት ወንድ (የበኵር ልጅ) ዅሉ ለጌታ የተቀደሰ ይባላል›› ተብሎ እንደ ተጻፈ እንደ ኦሪቱ ሥርዓት እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም እና ጠባቂዋ ጻድቁ ዮሴፍ ለመሥዋዕት የሚቀርቡ እንስሳትን ይዘው ጌታችንን በዚህች ዕለት ወደ ቤተ መቅደስ ወሰዱት፡፡ ‹‹ከሕርስ ደም የሚነጹበት ጊዜ ሲደርስ›› ሲልም በሌሎች ሴቶች ልማድ ለመናገር ነው እንጂ በእመቤታችንስ ይህ ዅሉ ጣጣ የለባትም፡፡ ከሴቶች ተለይታ የተመረጠች ቅድስት የአምላክ እናት እንደ መኾኗ ለድንግል ማርያም ርስሐት በፍጹም አይስማማትም፡፡ በሌላ በኩል ‹‹ከሕርስ ደም የሚነጹበት ጊዜ ሲደርስ›› ማለት ከሰው የሚለዩበትን ጊዜ ያመለክታል፡፡ ወንዶች በተወለዱ በዐርባ፣ ሴቶች በሰማንያ ቀናቸው ከሰው ይለያሉና፡፡

ጌታችን ወደ ቤተ መቅደስ በሔደ ጊዜም አረጋዊው ነቢዩ ስምዖን ታቅፎት ሰውነቱ ታድሷል፡፡ ይህ ዕለት (የካቲት ፰ ቀን) ‹‹ልደተ ስምዖን›› እየተባለ የሚጠራውም ዕለቱ ነቢዩ ጌታችንን ታቅፎ ከእርግናው (ሽምግልናው) የታደሰበት፤ ከደዌው የተፈወሰበት፤ አምላኩን በሥጋ ያየበት በአጠቃላይ ዳግም የተወለደበት ዕለት በመኾኑ ነው፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ ‹‹ስምዖን›› በሚለው ስም ከሚጠሩ ቅዱሳን መካከል ነቢዩ ስምዖን አንዱ ነው፡፡ የነቢዩን ታሪክ ለማስታዎስ ያህል አባታችን አዳም በተፈጠረ በአምስት ሺሕ ሁለት መቶ ዓመት በንጉሥ በጥሊሞስ ዘመነ መንግሥት የኦሪት መጻሕፍትን ከዕብራይስጥ ወደ ጽርዕ (ግሪክ) ቋንቋ እንዲተረጕሙ ከታዘዙ ሰብዓ ሰዎች (ሊቃናት) መካከል አንዱ ነቢዩ ስምዖን ነው፡፡

ይህ ነቢይ ትንቢተ ኢሳይያስ ደረሰውና እየተረጐመ ሳለ ‹‹እነሆ ድንግል ትፀንሳለች፤ ወንድ ልጅንም ትወልዳለች፡፡ ስሙንም ዐማኑኤል ትለዋለች፤›› ከሚለው ኀይለ ቃል በደረሰ ጊዜ በቀጥታ ቢተረጕመው ንጉሡ እንደማይቀበለው በማሰቡ፤ እርሱም ‹‹ይህ እንዴት ሊኾን ይችላል?›› ብሎ በመጠራጠሩ ‹‹ድንግል›› የሚለውን ቃል ‹‹ወለት›› (ሴት ልጅ) ብሎ ተረጐመው፡፡ ተኝቶ በነቃ ጊዜም ‹‹ወለት›› የሚለው ቃል ተፍቆ ‹‹ድንግል›› ተብሎ ተጽፎ አገኘና እርሱም ‹‹ድንግል››ን ፍቆ ‹‹ወለት›› ብሎ ይጽፋል፡፡ ዳግመኛም ለሁለተኛና ጊዜ ተኝቶ ሲነቃ ቃሉ እንደ ነበረ ኾኖ ያገኘዋል፡፡ ለሦስተኛ ጊዜ ቃሉን እፍቃለሁ ሲልም የእግዚአብሔር መልአክ ተገልጦ ‹‹የተጠራጠርኸውን፣ ከድንግል የሚወለደው ክርስቶስን እስከምታየውና እስከምትታቀፈው ድረስ ሞትን አትቀምስም፤›› ብሎታል፡፡

‹‹መሲሑን ሳታይ አትሞት›› የተባለው ነቢዩ ስምዖን አርጅቶ ከአልጋ ተጣብቆ ለሦስት መቶ ዓመታት ያህል ከኖረ በኋላ ትንቢቱ ተፈጽሞ፣ ዘመኑ ደርሶ ክርስቶስ ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በተወለደ በዐርባኛው ቀን ወደ ቤተ መቅደስ እስከ በገባበት ዕለት መንፈስ ቅዱስ አነሳሥቶ ወደ ምኵራብ ወሰደው፡፡ በዚያም ጌታችንን ከእመቤታችን ተቀብሎ ለመታቀፍ ታድሏል፡፡ ‹‹የምትጠብቀው ሕፃን ይህ ነው›› ብሎ እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ በነገረው ጊዜም ታውረው የነበሩ ዓይኖቹ ተገልጠዋል፤ ሰውነቱም ታደሷል፡፡

ነቢዩም የእግዚአብሔርን ማዳን በዓይኑ በማየቱ፣ ከደዌው በመፈወሱ እና ከእርጅናው በመታደሱ በአጠቃላይ በተደረገለት ድንቅ ተአምር ዅሉ በመደሰቱ እግዚአብሔርን አመስግኗል፡፡ ‹‹አቤቱ ባሪያህን ዛሬ አሰናብተኝ፤ ዓይኖቼ ትድግናህን አይተዋልና፤›› በሚለው ትንቢታዊ መዝሙሩም ‹‹የእግዚአብሔርን ማዳን በዓይኔ ስላየሁ እንግዲህስ ልረፍ›› በማለት ሞቱን ተማጽኗል፡፡ በመንፈስ ቅዱስ ተቃኝቶም የክርስቶስን የዓለም ቤዛነትና ክርስቶስ በሥጋው በሚቀበለው መከራ እመቤታችን መራራ ኀዘን እንደሚደርስባት፤ እንደዚሁም ጌታችን ለሚያምኑበት ድኅነትን፣ ለሚክዱት ደግሞ ሞትን የሚያመጣ አምላክ እንደ ኾነ የሚያስገነዝብ ትንቢት ተናግሯል፡፡

የቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት ለነቢዩ ስምዖን የተደረገለትን ታላቅ ሥራ ሲያደንቁ እንዲህ ይገልጹታል፤ ‹‹ሰላም እብል እንዘ እዌድሶ ወእንዕዶ፤ መዝሙረ ማኅሌት በአስተዋድዶ፤ ክብረ ስምዖን ነቢይ ለክብረ ሱራፌል ዘይፈደፍዶ፤ እስመ ሐቀፈ መለኮተ ወገሠሠ ነዶ፤ እኤምኅ ሕፅኖ ወእስዕም እዶ፤ የማኅሌት መዝሙርን በማዘጋጀት እያከበርሁትና እያደነቅሁት ከሱራፌል ክብር ለሚበልጠው ለስምዖን ክብር ሰላም እላለሁ፡፡ እርሱ መለኮትን በእጁ ታቅፏል፤ እሳቱንም ዳሷልና እቅፎቹን እጅ እነሳለሁ፤ እጆቹንም እስማለሁ፤›› /መጽሐፈ ስንክሳር፣ የየካቲት ፰ ቀን አርኬ/፡፡ የዚህ አርኬ መልእክት ኪሩቤል፣ ሱራፌል (ሰማያውያን መላእክት) በእጃቸው የማይነኩት፣ ከግርማው የተነሣ የሚንቀጠቀጡለት፣ እሳተ መለኮቱ የሚቃጥል እግዚአብሔር ወልድን ነቢዩ ስምዖን በክንዱ ለመታቀፍ በመታደሉ ክብሩ ከመላእክት እንደሚበልጥ፤ ለክብሩም የጸጋ ምስጋና እና እጅ መንሻ ማቅረብ እንደሚገባ የሚያስገነዝብ ነው፡፡

በተመሳሳይ መልኩ የነቢዪት ሐና ዕፍትም በዛሬው ዕለት ይታሰባል፡፡ ይህቺ ቅድስት ከአሴር ነገድ የተገኘች ደግ እናት ስትኾን አባቷም ፋኑኤል ይባላል፡፡ ክብረ ንጽሕናዋን ጠብቃ በድንግልና ኾና ዐሥራ አምስት ዓመት ሲሞላት ባል አግብታ ሰባት ዓመት ከባሏ ጋር ቆይታለች፡፡ ከባሏ ጋር ከተፋታች በኋላ ራሷን ጠብቃ ቀንም ሌትም ከምኵራብ ሳትወጣ በጾም በጸሎት ተወስና በሚቻላት ዅሉ እግዚአብሔርን እያገለገለች ሰማንያ አራት ዓመት ኖራለች፡፡ ይህቺ የአንድ መቶ ስድስት ዓመቷ አረጋዊት ጌታችን ወደ ቤተ መቅደስ በገባበት ዕለት በምኵራብ ተገኝታ አምላኳን በዓይኗ ለማየት በማታደሏ በክርስቶስ የእግዚአብሔር ልጅነት እና የዓለም ቤዛነት አመነች፡፡ ለዚህ ቀን ያደረሳትን እግዚአብሔርንም አመሰገነች፡፡ በመንፈስ ቅዱስ ተቃኝታም የክርስቶስን ሥራ እያደነቀች የሰውን ድኅነት በተስፋ ለሚጠባበቁ ለኢየሩሳሌም ሕዝቦች አዳኝነቱን መሰከረች /ሉቃ.፪፥፴፮-፴፱/፡፡ በመጨረሻም በዛሬው ዕለት ዐርፋለች፡፡

ምንጭ፡-

መጽሐፈ ስንክሳር፣ የካቲት ፰ ቀን፡፡

የሉቃስ ወንጌል አንድምታ ትርጓሜ፣ ሉቃ.፪፥፳፪-፴፱፡፡

ከዚህ ታሪክ ከምንገነዘባቸው በርካታ ቁም ነገሮች መካከል ጥቂቱን ለመጥቀስ ያህል ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሦስቱ አካላት (አብ ወልድ መንፈስ ቅዱስ) አንዱ (ወልድ) ነው፡፡ እንደ አምላክነቱ በዅሉም ቦታ የመላ ነውና መሔድ መምጣት፣ መራብ መጠማት የባሕርዩ አይደለም፡፡ ስለዚህም ‹‹ሔደ፤ መጣ፤ ተራበ፤ ተጠማ፤ ተገረዘ፤ ወደ ቤተ መቅደስ ሔደ፤ ወዘተ.›› የመሳሰሉ ለፍጡራን የሚስማሙ ቃላት አይነገሩለትም፡፡ ነገር ግን መድኀኒታችን ክርስቶስ መገረዝ፣ መሔድ፣ መምጣት፣ መራብ፣ መጠማት የሚስማማው ሥጋን ለብሷልና የሰውነቱን ሥራ ይፈጽም ዘንድ በመጽሐፍ ቅዱስ በተቀመጠው ሕግ መሠረት በተወለደ በስምንተኛው ቀን ለመገረዝ፤ በዐርባኛው ቀን ደግሞ ለመቀደስ (መሥዋዕት ለማቅረብ) ወደ ቤተ መቅደስ ሔዷል፡፡ ከዚህም እርሱ አምላክ ነኝ እና በተአምራቴ የማዳን ሥራዬን ልፈጽም ሳይል ከኀጢአትና ከፈቃደ ሥጋ በስተቀር በሰው ሥርዓት ማደጉን፤ እንደዚሁም የትሕትና ጌታ መኾኑን እንማራለን፡፡ ዛሬም ምእመናን ልጅ ሲወልዱ ወንዶችን በዐርባ፤ ሴቶች ደግሞ በሰማንያ ቀን ወደ ቤተ ክርስቲያን በመውሰድ ክርስትና የሚያስነሡት በዚህ ሥርዓት መሠረት ነው፡፡

ከነቢዩ ስምዖን ታሪክም በመጀመሪያ እግዚአብሔር አምላክ የማይፈጽመውን የማይናገር፤ የተናገረውንም የማያስቀር የእውነት ባለቤት እንደ ኾነ፤ እንደዚሁም እኛ አይደረግም ያልነው ከባድ የሚመስለን ምሥጢር ጊዜውን ጠብቆ መፈጸሙ እንደማይቀር፤ በተጨማሪም እግዚአብሔር በጥበብ የሚገሥፅ፣ የሚያስተምር የፍቅር አምላክ እንደ ኾነ እንገነዘባለን፡፡ ከዚሁ ዅሉ ጋርም በሥርዓተ ጋብቻ እስኪወሰኑ ድረስ ወንድሞችም እኅቶችም ክብረ ንፅሕናቸውን ጠብቀው መቆየት እንዳለባቸው፤ ከጋብቻ በኋላ ከሁለቱ ጥንዶች አንዱ በሞት ቢለይ ፈቃደ ሥጋቸውን መግታትና ሰውነታቸውን መቈጣጠር የሚቻላቸው ከኾነ እስከ ምድራዊ ሕይወታቸው ፍጻሜ ራሳቸውን ጠብቀው እግዚአብሔርን ሲያመሰግኑ ቢኖሩ በጸጋ ላይ ጸጋን፤ በበረከት ላይ በረከትን እንደሚታደሉ ከነቢዪት ሐና ታሪክ የምናገኘው ትምህርት ነው፡፡

በእርግጥ በሞት ወይም በዝሙት ምክንያት ከትዳር አጋሮቻችን ጋር የተለያየን ምእመናን ፈቃደ ሥጋችንን መቋቋም የማይቻለን ከኾነ በሥርዓተ ቍርባን በድጋሜ ጋብቻ መመሥረት እንደምንችል በቀኖና ቤተ ክርስቲያን ተደንግጓል፡፡ እናም በሞት ለተለያዩ ጥንዶች ሁለተኛ ጋብቻ ባይከለከልም ሳያገቡ እንደ ነቢዪት ሐና ራሳቸውን ጠብቀው መኖር ለሚፈልጉ ግን አለማግባት ይቻላል፡፡ ራስን ጠብቆ መኖር በእግዚአብሔር ለተመረጡ ሰዎች እንጂ ለዅላችን አይቻለንምና፡፡ ‹‹… እያንዳንዱ እግዚአብሔር እንደ አደለው ጸጋ ይኑር፤ ግብሩ እንዲህ የኾነ አለና፡፡ ገብሩ ሌላ የኾነም አለና፡፡ ነገር ግን ያላገቡትንና አግብተው የፈቱትን እንደ እኔ ኾነው ቢኖሩ ይሻላቸዋል እላቸዋለሁ፡፡ በፍትወት ከመቃጠል ማግባት ይሻላልና …፤›› እንዳለ ቅዱስ ጳውሎስ /፩ኛ ቀሮ.፯፥፯-፱/፡፡

ነቢዪት ሐና በድንግልና ከመኖሯ እና ሁለተኛ ባል ካለማግባቷ ባሻገር ዓለማዊ ተድላና ደስታን ንቃ፣ ሰውነቷን ጠብቃ፣ ከምኵራብ ሳትወጣ ሰማንያ ዓመት ሙሉ እግዚአብሔርን ስታገለግል መኖሯ ከእርሷ የምንማረው ሌላኛው ቁም ነገር ነው፡፡ እኛም እንደ ነቢዪቷ ሙሉ ጊዜአችንን ለቤተ ክርስቲያን መስጠት ባይቻለን እንኳን ከሥጋዊው ሥራችን ጎን ለጎን ወደ ቤተ ክርስቲያን እየሔድን ትምህርተ ወንጌል ብንሰማ፣ ብንጸልይ፣ ብንሰግድ፣ ከምሥጢራት ብንሳተፍ፤ እንደዚሁም ለአቅማችን በሚመጥን ልዩ ልዩ መንፈሳዊ ተልእኮ ብናገለግል የእግዚአብሔር ጸጋ በእኛ ላይ ይበዛል፤ እጥፍ ድርብም ይኾናል፡፡ ከዅሉም በላይ በምድራዊው ሕይወታችን የክርስቶስ ቤተ መቅደስ የኾነውን ሰውነታችንን ከኀጢአት ለይተን፣ ራሳችንን ለጽድቅ ሥራ አስገዝተን፣ በመንፈሳዊ ምግባር ጸንተን፣ ስንበድል ተጸጽተን (ንስሐ ገብተን)፣ ቅዱስ ሥጋውን በልተን፣ ክቡር ደሙን ጠጥተን ብንኖር የማያልፈውን መንግሥቱን ለመውረስ እንበቃለን፡፡

የጌታችን የመድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋ፣ የነቢዩ ስምዖን እና የነቢዪት ሐና፣ የሌሎችም ቅዱሳን በረከት ይደርብን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ጾመ ሰብአ ነነዌ

በርእሰ ደብር ብርሃኑ አካል

ጥር ፳፮ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

ጾመ ነነዌ ከሰባቱ የአዋጅ አጽዋማት አንዷ ስትኾን የምትጾመውም ለሦስት ቀናት ነው፡፡ ይህቺ ጾም የምትጀመርበት ዕለትም ልክ እንደ ዐቢይ ጾም ሰኞን አይለቅም፡፡ ጾሟ የምትጀመርበት ቀን ሲወርድ ወይም ወደ ኋላ ሲመጣ እስከ ጥር ፲፯ ቀን ድረስ ነው፡፡ ቀኑ ሲወጣ ወይም ወደ ፊት ሲገፋ ደግሞ እስከ የካቲት ፳፩ ቀን ይረዝማል፡፡ ጾመ ነነዌ በእነዚህ ፴፭ ቀናት ውስጥ ስትመላለስ (ከፍ እና ዝቅ ስትል) ትኖራለች፤ ከተጠቀሱት ዕለታት አትወርድም፤ አትወጣም፡፡ በዚህ ዓመትም (፳፻፱ ዓ.ም) ጥር ፳፱ ቀን ትጀመራለች፡፡

‹‹ጾመ ሰብአ ነነዌ፤ የነነዌ ሰዎች ጾም›› የሚለው የጽሑፋችን ርእስ እንደሚያስረዳው ይህቺን የሦስት ቀን ጾም የጾሟት በነነዌ ይኖሩ የነበሩ ሰዎች ናቸው፡፡ ከተማዋም (ነነዌ) በጤግሮስ ወንዝ ዳርቻ የምትገኝ ስትኾን መሥራቿም ናምሩድ ነው /ዘፍ.፲፥፲፩-፲፪/፡፡ ጥንታዊቷ የነነዌ ከተማ ለአሦር መነሻ የኾነች፤ እጅግ ሰፊና ያማረች፤ የቅጥሯ ርዝመትም ፲፪ ኪሎ ሜትር የሚሸፈን ነበር፡፡ በከተማዋ ንጉሡ ሰናክሬም ብዙ ሕንጻዎችን ገንብቶባት ነበር /ዮናስ ፬፥፲፩/፡፡ በዚያ ዘመን የነበሩ የነነዌ ሰዎች ኀጢአታቸው በዝቶ እግዚአብሔር ሊያጠፋቸው ሲል ቸርነትና ምሕረቱ የማያልቅበት እግዚአብሔር መክሮ፣ ዘክሮ እንዲመልሳቸውና ንስሐ እንዲገቡ ነቢዩ ዮናስን ወደ ነነዌ ሕዝብ ላከው /ሉቃ.፲፩፥፴/፡፡

ዮናስ የስሙ ትርጕም ‹ርግብ› ማለት ነው፡፡ በዳግማዊ ኢዮርብዓም ዘመነ መንግሥት የነበረ ነቢይ ነው፡፡ ይህ ነቢይ መኖሪያው በገሊላ በጋትሔፌር ድንበር ከተማ ነበረ፡፡ አባቱም አማቴ ይባላል፡፡ ኢዮርብዓም ሶርያውያንን አባሮ የእስራኤልን ድንበር እንዲመልስ ነቢዩ ዮናስ ትንቢትን ተናግሯል /፪ኛነገ.፲፬፥፳፭፤ ዮናስ ፩፥፩/፡፡ ነቢዩ ኤልያስ ያስነሣው የሰራጵታዋ መበለት ሕፃን ነቢዩ ዮናስ እንደ ኾነ የቤተ ክርስቲያን ታሪክ ያስረዳል /፩ኛነገ.፲፯፥፲፱/፡፡ መድኀኒታችን ክርስቶስም የዮናስን ከዓሣ ኾድ መውጣት የራሱ ትንሣኤ ምሳሌ አድርጎ ነግሮናል /ማቴ.፲፪፥፲፱-፵፪፤ ሉቃ.፲፩፥፴-፴፪/፡፡

እግዚአብሔር ‹‹ሔደህ በነነዌ ላይ ስበክ›› ባለው ጊዜ ነቢዩ ዮናስ ‹‹አንተ መሐሪ ነህ፤ ልትጠፉ ነው ብዬ ተናግሬ ብትምራቸው ሐሰተኛ ነቢይ እባላለሁ›› ብሎ ላለመታዘዝ እስራኤልን ለቆ በመርከብ ወደ ተርሴስ ሸሸ፡፡ እግዚአብሔርም ታላቅ ነፋስን አስነሥቶ መርከቧ በማዕበል እንድትመታ አደረገ፡፡ ከዮናስ ጋር በመርከቧ ተሳፍረው የነበሩ ነጋድያንም ያላቸውን ሀብት ወደ ባሕሩ መጣል ሲጀምሩ ነቢዩ ዮናስ ጥፋቱን ተገንዝቦ ‹‹ማዕበሉ በእኔ ምክንያት የመጣ ስለ ኾነ ንብረታችሁን ሳይኾን እኔን ወደ ባሕር ጣሉኝ›› ብሎ ተማጸናቸው፡፡ እነርሱም ‹‹ስለዚህ ሰው ነፍስ እንዳንጠፋ፣ ንጹሕም ደም በእኛ ላይ እንዳይደረግብን አይኾንም›› አሉ፡፡

ወደ ባሕሩ ለመጣል ዕጣ በተጣጣሉ ጊዜም ዕጣው በዮናስ ላይ ስለ ወጣ ነጋድያኑ ዮናስን ወደ ባሕሩ ጣሉት፡፡ ወዲያውኑ ከእግዚአብሔር ዘንድ የታዘዘ ታላቅ ዓሣ አንበሪ ዮናስን በአፉ ተቀብሎ ሦስት ቀንና ሦስት ሌሊት አሳድሮ ወደ ነነዌ አደረሰው፡፡ እግዚአብሔር የቅል ተክልን ምሳሌ በማድረግ ቅጠሉ በመድረቁ ዮናስ ባዘነ ጊዜ ‹‹አንተ ላልደከምክበት እና በአንድ ቀን በቅሎ ላደገ ቅል ስታዝን እነሆ በታላቂቱ ነነዌ ከተማ ያሉ ከአንድ መቶ ሃያ ሺሕ በላይ ሕዝብና እንስሳቱ የእጄ ፍጥረቶች ስለ ኾኑ ያሳዝኑኛል›› በማለት ነቢዩ ዮናስም ውሸታም ላለመባል መኮብለሉ ስሕተት መኾኑን አስረድቶታል፡፡

ዮናስም ነነዌ መሬት ላይ መድረሱን ባወቀ ጊዜ ከእግዚአብሔር መሸሽ አለመቻሉን ተረዳ፤ የነነዌ ሰዎችንም ‹‹ንስሐ ግቡ›› እያለ መስበክ ጀመረ፡፡ የነነዌ ሰዎችም ንስሐ በገቡ ጊዜ እግዚአብሔር ይቅር ብሎ ከጥፋት አድኗቸዋል፡፡ ሐሰት እንዳይባልም እሳቱ እንደ ደመና ኾኖ ከላይ ታይቶአል፡፡ የታላላቁ ዛፍ ቅጠል እስኪጠወልግ ድረስ አድርቆ ለሕዝቡ አሳይቷቸዋል፡፡ ንስሐቸው በከንቱ እንዳልቀረ አስረድቷቸዋል /ትንቢተ ዮናስን በሙሉ ይመልከቱ/፡፡ ታኅሣሥ ፭ ቀን የሚነበበው የመጽሐፈ ስንክሳር ክፍል ‹‹ወበልዐ አሐደ ኀምለ›› በማለት ንስሐ ያልገቡ አንድ አገር ያህል ሰዎች በእሳቱ እንደ ጠፉ ይነግረናል፡፡

ጾመ ነነዌ የሦስት ቀን ሱባኤ ናት፤ በሦስት ቀናት ጾምና ጸሎት ንስሐ የገቡ የነነዌ ሰዎች ከጥፋት እንደ ዳኑ ዅሉ፣ በብሉይ ኪዳን አስቴር ሦስት ቀን ጾማ፣ ጸልያ በእስራኤል ላይ የመጣውን መቅሠፍት እንዲመለስ አድርጋለች /አስ.፬፥፲፭-፲፮/፡፡ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምም ከበዓል ስትመለስ ሕፃኑ ልጇ ኢየሱስ ክርስቶስ መንገድ ላይ ጠፍቶአት ከሦስት ቀን ፍለጋ በኋላ በቤተ መቅደስ አግኝታዋለች /ሉቃ.፪፥፵፮/፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ለሄሮድስ በሰጠው ምላሽ መልስ ሦስት ቀን የሱባኤ ፍጻሜ መኾኑን ገልጿል /ሉቃ.፲፫፥፴፪/፡፡

ጾመ ነነዌ የእግዚአብሔርን ቸርነትና መሐሪነት የምናስታውስበት ጾም ነው፡፡ ይኸውም እኛ ፍጡራኑ በበደልን ጊዜ ፈጽሞ ከማጥፋት ይልቅ ምክንያት ፈልጎ እንድንድን ያደርገናል፡፡ ዮናስ ለስብከት ፈቃደኛ ባይኾን እንኳን እግዚአብሔር በተለየ ጥበቡ እንዲሔድ አድርጎታል፡፡ በእርግጥ እግዚአብሔር ሌላ የሚልከው ነቢይ አጥቶም አይደለም፤ እርሱንም ጭምር ሊያስተምረው ስለ ፈለገ እንጂ፡፡ የነነዌ ሰዎች የተነሳሕያን ምሳሌ ናቸው፡፡ ይህም ማለት ሰው ጥፋቱን አምኖ ንስሐ ከገባ እግዚአብሔር ይቅር ማለቱን አይተውም፡፡ ለዚህም ነው ዮናስን ‹‹አንተ ላልደከምክበት እና በአንድ ቀን በቅሎ ላደገ ቅል ስታዝን እነሆ በታላቂቱ ነነዌ ከተማ ያሉ ከአንድ መቶ ሃያ ሺሕ በላይ ሕዝብና እንስሳቱ የእጄ ፍጥረቶች ስለ ኾኑ ያሳዝኑኛል›› ያለው፡፡

ቀደምት የቤተ ክርስቲያን አባቶቻችን ይህን እና ሌሎች አጽዋማትን እንድንጾም የወሰኑልን ያለ ምክንያት አይደለም፡፡ ሕጉ የተዘጋጀልን እንደ ነነዌ ሰዎች እኛም ጾመን፣ ጸልየን ከኀጢአታችን እንነጻ ዘንድ ነው፡፡ ዛሬ ዓለማችን በኀጢአት ማዕበል እየተናወጠች ባለችበት ወቅት እኛም እንደ ነነዌ ሰዎች ከበደላችን ብንመለስ እና ንስሐ ብንገባ ቸሩ ፈጣሪያችን እግዚአብሔር ይቅርታና ምሕረት የባሕርይ ገንዘቡ ስለ ኾነ ‹‹ወደ እኔ ተመለሱ፤ እኔም ይቅር እላችኋለሁ፤›› ይለናል፡፡

ስለኾነም በነቢዩ ዮናስ ላይ የተደረጉ ተአምራትንና ካለመታዘዝ የሚመጣ ቅጣት ቀላል አለመኾኑን በማስተዋል፣ ለነነዌ ሰዎች የወረደውን ምሕረት በመገንዘብ ለእግዚአብሔርም ኾነ ለሃይማኖት አባቶች እና ለወላጆቻችን መታዘዝ ይገባናል፡፡ ስንጾምም እግዚአብሔር አምላካችን መዓቱን በምሕረት፣ ቍጣውን በትዕግሥት መልሶ በኀጢአት ለጠፋው ዓለም ይቅርታውን ይልካል፡፡ በመጾማችን ራሳችን ከመዓትና ከመቅሠፍት ከመዳናችን ባሻገር በእኛ በደል ምክንያት አገራችን፣ ዕፀዋቱና እንስሳቱም ሳይቀር ከድርቅና ከቸነፈር ይተርፋሉና፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

አስደናቂው የድንግል ማርያም ሞት

%e1%88%9e%e1%89%b3-%e1%88%88%e1%88%9b%e1%88%ad%e1%8b%ab%e1%88%9d

በዲያቆን ታደለ ፋንታው

ጥር ፳ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

እግዚአብሔር አምላካችን ፍጥረቱንና ዓለሙን ለማዳን የመረጠው ጊዜ በደረሰ ጊዜ አስቀድሞ በመልአኩ አፍ እንዳናገረ ከድንግል ማርያም በድንግልና ተወለደ፤ ክብሩም በእርሷ ላይ ተገለጠ /ኢሳ.፷፥፪/፡፡ ማኅፀኗን ከተማ አድርጎ ዘጠኝ ወር ከአምስት ቀን በእርስዋ አደረ፡፡ ይህም ያነጻቸው፣ ይቀድሳቸው ዘንድ በሥጋም በነፍስም መርቶ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ያገባቸው ዘንድ በነቢያት በሐዋርያት ላይ እንዳደረው ዓይነት ማደር አይደለም፤ ከሦስቱ አካል አንዱ አካል እግዚአብሔር ወልድ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሥጋዋ ሥጋን፤ ከነፍስዋ ነፍስን ተዋሕዶ ፍጹም ሰው፣ ፍጹም አምላክ ኾነ እንጂ፡፡ ቅዱስ ሉቃስ ይህን ዘለዓለማዊ እውነት ‹‹መንፈስ ቅዱስ በአንቺ ላይ ይመጣል፤ የልዑል ኃይልም ይጸልልሻል፡፡ ስለዚህ ከአንቺ የሚወለደው ቅዱስ የእግዚአብሔር ልጅ ይባላል፤›› በማለት ገልጾታል /ሉቃ.፩፥፵፭/፡፡

በእግዚአብሔር፣ በመላእክቱና በሰው ፊት የከበረ ሰው መታሰቢያው ለዘለዓለም ነው፡፡ በቤቱ፣ በቅፅሩ የማይጠፋ የዘለዓለም ስምን ይቀበላልና /ኢሳ.፶፭፥፫/፡፡ ይህንን ታላቅ በረከት እንደሚሰጣቸው የተናገረውም የማይዋሸው እግዚአብሔር አምላክ ነው፡፡ ከእግዚአብሔር ወልድ እናት ከድንግል ማርያም የበለጠ በሰውና በእግዚአብሔር ዘንድ የከበረ ማንን ልንጠራ እንችላለን? ከእርሷ ሊከብር የሚችል፣ በቅድስና ሕይወት ያለፈ ማን ይኖራል? እግዚአብሔር አምላክ ዘለዓለማዊ ኃይሉንና አምላክነቱን ለዓለም ከገለጸባቸው ሥራዎቹ መካከል በእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ላይ የገለጸው ተዋሕዶ በቤተ ክርስቲያን ታሪክ ቀዳሚውን ሥፍራ ይይዛል፡፡

ይህንን ኹኔታም ‹‹ብርቱ የኾነ እርሱ ታላቅ ሥራን በእኔ አድርጓል፤ ስለዚህም ምክንያት ፍጥረት ዅሉ ያመሰግኑኛል፤›› በማለት ድንግል ማርያም ገልጻዋለች /ሉቃ.፩፥፵፱/፡፡ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል እመቤታችንን ‹‹ከሴቶች መካከል ተለይተሽ የተባረክሽ ነሽ፤›› ብሏታል /ሉቃ.፩፥፳፰/፡፡ ቅድስት ኤልሳቤጥም ‹‹የጌታዬ እናት›› ብላታለች /ሉቃ.፩፥፵፫/፡፡ ቅዱስ ዳዊት ‹‹ልጄ›› ይላታል /መዝ.፵፬፥፱/፡፡ ጠቢቡ ሰሎሞንም ‹‹እኅቴ›› ይላታል /መኃ.፭፥፩/፡፡ ለወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስም እናት ኾና ተሰጥታዋለች /ዮሐ.፲፱፥፳፮/፡፡

ቅዱስ አግናጥዮስ ዘአንጾኪያ ለኤፌሶን ክርስቲያኖች በጻፈው መልእክቱ እንደ ገለጸው የቅድስት ማርያም ዘለዓለማዊ ድንግልና፤ አማኑኤልን መውለዷ እና የማይሞተው ጌታ ሞት እነዚህ ሦስቱ ከዚህ ዓለም ጥበበኞችና ገዢዎች የተሰወሩ ምሥጢራት ናቸው፡፡ ‹‹እነዚህ ድንቅ ምሥጢራት በራሳቸው ከንግግርና ከቋንቋዎች ዅሉ በላይ ኾነው የሚነገሩ በእግዚአብሔር የዝምታ መጐናጸፊያ የተጠቀለሉ ድብቅና ጣፋጭ ምሥጢሮች ናቸው፤›› ይላል ቅዱስ አግናጥዮስ፡፡

ምስጋናዋ የበዛለት ቅዱስ ኤፍሬም ሶርያዊም ‹‹አቤቱ መሰንቆ ልቡናዬን አነቃቃ፤ የልቤንም እንዚራ፡፡ ድምፁን ከፍ አድርጎ የዳዊት ልጅ የኾነችውን የጌታውን እናት ድንግል ማርያምን ያመሰግናት ዘንድ፡፡ ለዓለም ሕይወት የሚሰጠውን የወለደች እናቱ የኾነች እርሷን ከፍ ከፍ ያደርጋት ዘንድ፤›› በማለት ለምስጋናዋ ይዘጋጃል፡፡ በሌላ አንቀጽም ‹‹ከሕሊናት ዅሉ በላይ ለኾነ ለዚህ ነገር አንክሮ ይገባል፤ ምድራዊት ሴት ፈጣሪዋን ወለደችው፡፡ እርሱም እናቱን ፈጠረ፤›› ይላል፡፡

ኢትዮጵያዊው ሊቅ አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫም በመጽሐፈ አርጋኖን ድርሰቱ ‹‹ከሚያሰጥመው ባሕር ሞገድ የተነሣ የማትነቀነቅ፤ መልኅቆቿም በሦስቱ ሥላሴ ገመድ የተሸረቡ ናቸው፡፡ ይህቺ ደግሞ ከነፋሳት ኃይል የተነሣ የማትናወጥ በጭንጫ ላይ ያለች የዕንቈ ባሕርይ ምሰሶ ናት፡፡ እርሷን የተጠጋ መውደቅ፣ መሰናከል የለበትም፤›› የሚላት እመቤታችን ሞት ሥጋ ለለበሱ ዅሉ አይቀርምና እርሷም እንደ ሰው የምትሞትበት ጊዜ ደረሰ፡፡

እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በአባት በእናቷ ቤት ሦስት ዓመት፤ በቤተ መቅደስ ዐሥራ ሁለት ዓመት፤ ከልጇ ጋር ሠላሳ ሦስት ዓመት ከሦስት ወር፤ ከጌታችን ስቅለት በኋላ ደግሞ ዐሥራ አምስት ዓመታት በምድር ኖራለች፡፡ ጌታን የፀነሰችበትን ወራት ስንጨምር በዚህ ዓለም በሥጋ የቆየችበት ጊዜ ስድሳ አራት ዓመት ይኾናል፡፡ ያረፈችውም ጥር ፳፩ ቀን ነው፡፡ እመቤታችን ባረፈች ጊዜ ሐዋርያት ሊቀብሯት ሲሹም ከአይሁድ ክፋት የተነሣ ልጇ ሌላ ክብርን ደረበላት፡፡ ከጌቴሴማኒ ሥጋዋ ተነጥቆ በገነት በዕፀ ሕይወት ሥር እስከ ነሐሴ ፲፮ ቀን ለሁለት መቶ አምስት ቀናት ቆይታለች፡፡

ልጇ ወዳጇ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሞትን በሥልጣኑ እንዳሸነፈ ዅሉ እርሷንም በእርሱ መለኮታዊ ኃይል ሞትን አሸንፋ እንድትነሣ አድርጓታል፡፡ ቅድስት ድንግል ማርያም የኃያሉ እግዚአብሔር እናቱ፣ መቅደሱ፣ ታቦቱ፣ መንበሩ ኾና እያለ ሞትን መቅመሷ በራሱ የሚያስገርም ምሥጢር ነው፡፡ ከቤተ ክርስትያን ወገን ሞትን እንዳያዩ የተወሰዱ ቅዱሳን ሄኖክ፣ ኤልያስ፣ ሌሎችም አበው እንዳሉ ቅዱሳት መጻሕፍት ይናገራሉ፡፡

ይህ ከሕሊናት ዅሉ በላይ የኾነው የእመቤታችን ዕረፍት ርቀቱ በመጽሐፈ ዚቅ እንዲህ ተብሏል፤ ‹‹ለምንት ይዜኃር ኃያል በኃይሉ ወባዕል በብዝኃ ብዕሉ ኢያድለወ  ሞተ ክርስቶስ ለሥጋ አባሉ ሞትሰ ለመዋቲ ይደሉ ሞታ ለማርያም የዐፅብ ለኵሉ፡፡ ኃይለኛ በኃይሉ ለምን ይታጀራል? ባለ ጸጋም በሀብቱ ብዛት፡፡ ክርስቶስ ለአካሉ አላደላም፤ ሞትስ ለሟች ይገባዋል፡፡ የእመቤታችን የቅድስት ማርያም ሞት ግን አስደናቂ ነው፡፡››

የቤተ ክርስቲያን ትውፊት የድንግል ማርያም ሞት በሚከተሉት ምክንያቶች እንደ ኾነ ያስረዳል፤ የመጀመሪያው ‹‹ለመለኮት ማደርያ ለመኾን የበቃችው ኃይል አርያማዊት ብትኾን ነው እንጂ እንደ ምድራዊት ሴትማ እንደምን ሰማይና ምድር የማይችለውን አምላክ ልትሸከመው ይቻላታል?›› የሚሉ ወገኖች ነበሩና እግዚአብሔር ወልድ የተዋሐደው የሰው ልጆችን ሥጋ መኾኑን ለማጠየቅ ነው፡፡

ቅዱስ ጳውሎስ ይህንን ሲያስረዳ ‹‹እንግዲህ ልጆቹ በሥጋና በደም ስለሚካፈሉ፣ እርሱ ደግሞ በሞት ላይ ሥልጣን ያለውን በሞት እንዲሽር፣ ይኸውም ዲያብሎስ ነው፡፡ በሕይወታቸው ዅሉ ስለ ሞት ፍርሃት በባርነት ይታሠሩ የነበሩትን ዅሉ ነጻ እንዲያወጣ፣ በሥጋና በደም እንዲሁ ተካፈለ፡፡ የአብርሃምን ዘር ይዟል እንጂ የያዘው የመላእክትን አይደለም፤›› አለ /ዕብ.፪፥፲፬-፲፭/፡፡ በዚህም ድንግል ማርያም የአዳም ዘር መኾኗ ታወቀ፡፡ ሁለተኛውም ቅዱስ ያሬድ እንደ ተናገረው ጌታችን በፍርዱ አድልዎ የሌለበት አምላክ መኾኑ ይታወቅ ዘንድ ነው፡፡ ሥጋ የለበሰ ዅሉ ሞትን ይቀምስ ዘንድ የግድ ነውና፡፡

ጠቢቡ ሰሎሞን ‹‹ወዳጄ ሆይ ተነሺ፤ ውበቴ ሆይ ነዪ፡፡ እነሆ ክረምት አለፈ፤ ዝናሙም አልፎ ሔደ፡፡ አበቦች በምድር ላይ ተገለጡ፤ የዜማም ጊዜ ደረሰ፡፡ የቍርዬም ቃል በምድር ላይ ተሰማ፤›› /መኃ.፪፥፲-፲፬/ በማለት የተናገረው ትንቢት እመቤታችን የዚህ ዓለም ድካሟ ዅሉ መፈጸሙን ያስረዳል፡፡ ልጇን ይዛ ከአገር ወደ አገር በረሀብና ጥም የተንከራተተችበት ጊዜ አሁን አለፈ፡፡ ታናሽ ብላቴና ሳለች ልጇን አዝላ በግብጽ በረሃ የተቀበለችው መከራ ዅሉ ፍጻሜ አገኘ፡፡

ከእግረ መስቀል ሥር ወድቃ የልጇን የቈሰለ ገላ እየተመለከተች የደረሰባት ልብ የሚሰነጥቅ ኀዘን ወደ ደስታ ተለወጠ፡፡ ልጇ ሲንገላታ፣ ሲሰደድ፣ ሲገረፍ፣ ሲሰቀል፣ ሲቸነከር ያየችበት ዓለም አለፈ፡፡ ‹‹በነፍሷ ሰይፍ ያልፋል›› ተብሎ የተነገረው ልብ የሚሰነጥቅ መከራ የሚቀጥልበት ጊዜ ተፈጸመ፡፡ ሊቁ ቅዱስ ያሬድ ‹‹ለዛቲ ብእሲት ሠረቀ ላዕሌሃ ብዕለ ጸጋሁ ለአብ ወአግዓዛ እምእኩይ ውስተ ሠናይ እሞት ውስተ ሕይወት፤ በድንግል ማርያም ላይ የአብ የባለጸግነቱ ብዛት ተገለጠ፡፡ ከሞት ወደ ሕይወት፣ ከክፉ ዓለም ወደ በጎ ዓለም አሸጋግሯታልና፤›› ሲል የተነጋረውም ይህንኑ ምሥጢር የሚገልጽ ነው፡፡

እመቤታችን አሁን የልጇን ልዕልና ከሚያደንቁ ጋር ታደንቃለች፤ ከፍ ከፍ ከሚያደርጉት ጋር ታከብረዋለች፡፡ ይኸውም ከገቡ የማይወጡበት፤ ኀዘን፣ መከራ፣ ችግር የሌለበት ሰማያዊ አገር ነው፡፡ በእግዚአብሔር መንግሥት ስደት፣ መከራ፣ ኀዘን፣ ሰቆቃ፣ መገፋት፣ መግፋትም የለም፡፡ ቅዱሳን ሩጫቸውን ጨርሰው የድል አክሊልን የሚቀዳጁበት ሥፍራ ነው፡፡ በዚህም ከፍጡራን ኹሉ ከፍ ባለ በታላቅ ክብርና ጸጋ ለዘለዓለም እንደምትኖር እናምናለን፡፡ ልመናዋ፣ ክብሯ፣ ፍቅሯ፣ አማላጅነቷ፣ የልጇም ቸርነት በኹላችን ላይ አድሮ ይኑር፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ዘመነ አስተርእዮ

በርእሰ ደብር ብርሃኑ አካል

ጥር ፲፱ ቀን ፳፻፱ .

አስተርእዮ ቃሉ የግእዝ ቃል ሲኾን መታየት መገለጥ ማለት ነው፡፡ ገሃድ የሚለው ቃልም በጾምነቱ ሌላ ትንታኔ ሲኖረው ትርጕሙ ያው መገለጥ ማለት ነው፡፡ በግሪክ ‹‹ኤጲፋኒ›› ይሉታል፡፡ የእኛም ሊቃውንት ቃሉን በቀጥታ በመውሰድ ‹‹ኤጲፋኒያ›› እያሉ በዜማ መጻሕፍቶቻቸው ይጠሩታል፡፡ ትርጕሙም ከላይ ከጠቀስናቸው ጋር ተመሳሳይ ነው፡፡ አስተርእዮ የሚለው ቃል ‹‹አስተርአየ›› ከሚለው ግሥ ራሱን ችሎ ሳይለወጥ በአምስቱ አዕማድ የሚፈታ ብቸኛ ግሥ ነው፡፡ ይህም ማለት፡- አስተርአየ፤ ታየ፤ ተያየ፤ አሳየ፤ አስተያየ፤ አየ ተብሎ ይፈታል ማለት ነው፡፡

ዘመነ አስተርእዮ ሲያጥር ከጥር ፲፩ ቀን እስከ ጥር ፴፤ ሲረዝም ደግሞ ከጥር ፲፩ ቀን እስከ መጋቢት ፫ ቀን ይኾናል፡፡ በዚህም መሠረት ቀናቱ ሲያጥር ፳፤ ሲረዝም ፶፫ ይኾናሉ ማለት ነው፡፡ ጌታችን ለሐዋርያት ሕጽበተ እግር ካደረገበት ቀን (ከጸሎተ ሐሙስ) እስከ ጰራቅሊጦስ ቢቈጠር ቀናቱ ፶፫ ስለሚኾኑ የእነዚህ ምሳሌዎች ናቸው፡፡ ዮሐንስ በጥምቀት ዕለት ለልዕልና (ጌታ ሰውን ምን ያህል እንዳከበረው) ለማሳየት እጁን ከጌታችን ራስ በላይ ከፍ እንዳደረገ ጌታችንም ለትሕትና እጁን ከሐዋርያት እግር በታች ዝቅ አድርጎ እግራቸውን አጥቧቸዋልና ነው፡፡

ጥምቀት የሕጽበት አምሳል ሲኾን፣ ሕጽበት (መታጠብ) ደግሞ በንባብ አንድ ኾኖ ሁለት ምሥጢራት አሉት፡፡ የመጀመሪያው፡- ምእመናን የእንግዳ እግር እንዲያጥቡ ጌታችን ትምህርት ማስተማሩ ሲኾን፣ ሁለተኛውም ለሐዋርያት ጥምቀታቸው መኾኑ ነው፡፡ ሐዋርያት በጸሎተ ሐሙስ ቢጠመቁም መንፈስ ቅዱስ የተቀበሉት የጰራቅሊጦስ ዕለት ነውና፡፡ ቅዱስ ጎርጎርዮስ ዘኑሲስ ስለ ቅዱሳን ሐዋርያት ጥምቀት ቅዱስ ባስልዮስ ዘቂሣርያን እንደ ጠየቀውና ጥምቀታቸው ሕጽበተ እግር መኾኑን እንደ መለሰለት፡፡

በሌላ በኩል ከዘመነ ልደት እስከ ጥምቀት ተወልደ፤ ተሠገወ (ሰው ኾነ) ይባላል እንጂ አስተርአየ (ተገለጠ) አይባልም፡፡ ከጥምቀት በኋላ ግን አብሮ፣ ተባብሮ ተጠምቀ፤ ተወልደ፤ ተሠገወ፤ አስተርአየ ይባላል፡፡ ከጥምቀት በፊት አስተርእዮ ለመባሉ በሦስት ነገሮች ነው፡፡ የመጀመሪያው፡- የማይታየው ረቂቅ አምላክ በበረት ተወልዶ፣ በጨርቅ ተጠቅልሎ ቢታይ፤ እንደ ሕፃን ሲያለቅስ ቢሰማም ሰው ዅሉ ሠላሳ ዓመት ሲሞላው ሙሉ ሰው ይኾናል እንደሚባለው፣ አምላክ ነኝ ብሎ በአንድ ቀን ሳያድግ በጥቂቱ ማደጉንና ስደት እንደ ውርደት ኾኖ እንዳይቈጠር ለሰዎች ስደትን ባርኮ (ጀምሮ) ለመስጠት፤ ሄሮድስም ሊገድለው ይፈልገው ስለ ነበር ወቅቱ የሚሰደድበት እንጂ የሚታይበት ስላልነበረ ነው፡፡

ሁለተኛው፡- ሰው በተፈጥሮም ኾነ በትምህርት አዋቂ ቢኾን ለሚመለከተው ሥራና ደረጃ እስከ ተወሰነ ጊዜ ይህ ሕፃን ለእንዲህ ያለ ማዕረግ ይኾናል አይባልም፤ ተንከባክባችሁ አሳድጉት ይባላል እንጂ፡፡ ሕፃኑ አዋቂ ነው አይባልም፤ ያውቃል ተብሎም ለትልቅ ደረጃ አይበቃም፡፡ በየትኛውም ሓላፊነት ላይ አይሰጥም፤ ራሱን በመግዛት ይጠበቃል እንጂ፡፡ ጌታችንም በመንፈስም በሥጋም ባለ ሥልጣን ቢኾንም ፍጹም ሰው ኾኗልና አምላክ ነኝ፤ ዅሉን በዕለቱ ልፈጽም ሳይል በየጥቂቱ ማደጉን እናያለን፡፡

የሰውን ሥርዓት ከኀጢአት በቀር ለመፈጸም በየጥቂቱ አደገ፡፡ ‹‹በበሕቅ ልሕቀ›› እንዲል፡፡ ሰው ዅሉ ፴ ዓመት ሲኾነው ሕግጋትን ለመወከል፣ ለመወሰን እስከ ፴ ዓመት መታገሡም ስለዚሁ ነው፡፡ ከሠላሳ ዓመት በኋላ ሰው ቢመቸው ይወፍራል፤ ቢከፋው ይከሳል እንጂ ቁመት አይጨምርም አይቀንስም፡፡ ጌታችን ሰው ሙሉ፣ አእምሮው የተስተካከለለት ጐልማሳ በሚኾንበት ዕድሜ በ፴ ዓመት በግልጽ በመታየቱ ወቅቱ ‹‹ዘመነ አስተርእዮ›› ተብሏል፡፡

ሦስተኛው፡- በ፴ ዓመት እርሱ ሊጠመቅበት ሳይኾን የመጀመሪያ መንፈሳዊ ሕግና ሥርዓት መሠረት የኾኑ ጥምቀትንና ጾምን ሠርቶ በመሳየትና መመሪያ አድርጎ ለምእመናን በመስጠት እሱ ሙሉ ሰው ኾኖ ተገልጾ የቃሉን ትምህርት ለመስማት፤ የእጁን ተአምራት ለማየት ይከተለው ለነበረው አምስት ገበያ ያህል ሕዝብ  ትምህርት፣ ተአምራት ያደረገበት፤ ሥራዬ ብሎ የመጣበት መንፈሳዊ ሕግና ሥርዓት የፈጸመበት ዘመን በመኾኑ ነው፡፡ የታየውም ወልድ ብቻ አይደለም፤ አብ ‹‹ይህ የምወደው ልጄ ነው›› ሲል፤ መንፈስ ቅዱስም በእርግብ አምሳል ሲወርድ ረቂቁ አምላክ የታየበት፤ የሥላሴ የአንድነትና ሦስትነት ምሥጢር የተገለጠበት ዕለት ስለ ኾነ ይህ ወቅት ዘመነ አስተርእዮ ተብሏል፡፡

በአስተርእዮ ሌሎች በዓላትም ይጠሩበታል፡፡ ለምሳሌ ድንግል ማርያም ጥር ፳፩ ቀን ነፍሷ ከሥጋዋ ተለይቶ በደመና ተነጥቃ ወደ ገነት በመግባት ለጻድቃን እና ለመላእክት በሰማይና በምድር የተሰጣት ጸጋ፣ ክብር የተገለጸበት ዕለት ስለኾነ በዓሉ ‹‹አስተርእዮ ማርያም›› ይባላል፡፡ የኢትዮጵያ ሊቃውንት በዚህ ቃል ሐሳባቸውን ያስተባብራሉ፡፡ ሊቁ ቅዱስ ያሬድ አምላክ በሥጋ ከድንግል መወለዱንና በዚህ አካለ መጠንም ለዓለም መገለጡን አስተርእዮ ብሎ ሲናገር፤ አባ ጽጌ ብርሃን ደግሞ በማኅሌተ ጽጌ ድርሰቱ ‹‹እግዚአብሔር ጽጌ ትንቢት ለቢሶ ሥጋኪ ሥጋ ዚአነ፤ አመ አስተርአየ በምድር ወተአምረ ለነ፤ ንዌድሰኪ እንዘ ንብል ምክሐ ዘመድነ፤ ዮም በፍሥሓ ለማርያም እምነ፤ አስተርእዮ በሰማይ ኮነ፡፡ – የትንቢት አበባ እግዚአብሔርእኛ ሥጋ የኾነውን የአንቺን ሥጋ ለብሶ ለእኛ እንዲታወቅ በምድር እንደ ተገለጠ፤ የወገናችን መመኪያ ድንግል ሆይ፣ዛሬ ለእናታችን ለማርያም በሰማይ ፍጹም በደስታ መገለጥ ኾነ› እያልን እናመሰግንሻለን፤›› ሲል ገልጾታል፡፡ ነቢዩ ዳዊትም፡- ‹‹በከመ ሰማዕነ ከማሁ ርኢነ፤ በነቢያት ይወለዳል ሲባል የሰማነው በበረት ተጥሎ፤ በጨርቅ ተጠቅልሎ በግዕዘ ሕፃናት ሲያለቅስ ሰማነው፡፡ በዮርዳኖስ ሲጠመቅ አየነው፤›› በማለት የአምላካችንን መገለጥ ተናግሯል /መዝ.፵፯፥፮/፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ዝክረ በዓለ ጥምቀት

timk

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ጥር ፲፮ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም  

በዓለ ጥምቀት ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን እንደ በዓለ መስቀል በዐደባባይ የምታከብረው ልዩ በዓል ነው፡፡ በዓሉ ከሃይማኖታዊ ትውፊቱ ባሻገር አገራዊ ቅርስም ነው፡፡ በዓሉ ከመድረሱ አስቀድሞ በአዲስ አበባ ከተማ የሚስተዋለው ደማቅ መንፈስ ከተማዋን ታላላቅ እንግዶችን በቤቷ ለመቀበል ሽር ጉድ የምትል አንዲት ወይዘሮን አስመስሏታል፡፡ በየቦታው በተዘጋጁ ድንኳኖች የሚሰሙ ኦርቶዶክሳውያን መዝሙራት፤ ነጭ ልብስ ለብሰው የሚንቀሳቀሱ ምእመናን፤ በየቤቱ የነበረው ባህላዊ ዝግጅት ልዩና ማራኪ ነበር፡፡ ይህ ልዩ በዓል እንደ አሁን በፊቱ ዅሉ በዘንድሮው ዓመትም በመላው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አብያተ ክርስቲያናት በደማቅ መንፈሳዊ ሥርዓት ተከብሮ ውሏል፡፡ በአዲስ አበባ ከተማ፣ በጊዜያዊው የጥምቀት ቤተ መቅደስ በጃንሜዳ የበርካታ አብያተ ክርስቲያናት ታቦታት በተሰባሰቡበት በቅዱስ ፓትርያርኩ ቡራኬ የተከበረው የ፳፻፱ ዓ.ም በዓለ ጥምቀት ከዋይዜማው ጀምሮ መንፈሳዊ ቀልብን በሚገዙ፤ ልቡናን በሚመስጡ፣ ሕሊናን በሚማርኩና ነፍስን በሚያስደስቱ ሥርዓታት ተውቦ ነበር፡፡

በትምህርተ ወንጌል፣ በዝማሬ፣ በዕልልታ፣ በጸሎተ ቅዳሴ፤ በቦታው የተገኙ የቤተ ክርስቲያችን አባቶች (ቅዱስ ፓትርያርኩ፣ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ መምህራን፣ ቀሳውስትና ዲያቆናት)፤ እንደዚሁም የአኃት አብያተ ክርስቲያናት ተወካዮች፤ ከየአጥቢያው ታቦታቱን በዝማሬ አጅበው የመጡ የሰንበት ት/ቤት እና የማኅበረ ቅዱሳን መዘምራን፤ የበዓሉን ሥርዓት ለመመልከት ከውጪ አገር እና ከአገር ውስጥ የመጡ ጐብኚዎች፤ በበዓሉ ለመታደም በነቂስ ከየቤታቸው ወጥተው በጃን ሜዳ የተሰባሰቡ በመቶ ሺሕ የሚቈጠሩ የአዲስ አበባ ከተማ እና የአካባቢው ምእመናን ጃን ሜዳን ክርስቶስ ዳግም ሲመጣ ፍርድ የሚሰጥበት ዐውደ ምሕረትን አስመስለውታል፡፡

pp

እኛም በጃን ሜዳ ተገኝተን በዓሉን አክብረናል፡፡ ቅዱስ ፓትርያርኩ በዋይዜማው (የከተራ ዕለት) በጃንሜዳ ተገኝው ስለ ጌታችን ጥምቀት ካስተማሩት ቃለ እግዚአብሔር በተጨማሪ በዕለቱም ‹‹ወይርአይ ኵሉ ዘነፍስ አድኅኖቶ ለእግዚአብሔር፤ ነፍስ ዅሉ የእግዚአብሔርን ማዳን ይይ፤›› /ሉቃ.፫፥፮/፣ በሚል ኃይለ ቃል በሰጡት ቃለ ምዕዳናቸው የሰውን ልጅ ለሞት ያበቃው ኀጢአት በጥምቀተ ማይ እና በልደተ መንፈስ ቅዱስ መወገዱን ማስተማራቸውም አንዱ የበዓሉ በረከት ነበር፡፡

ቅዱስነታቸው በቃለ ምዕዳናቸውም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በየጎዳናው፣ በየመንደሩ፣ በየወንዙ ቅዱስ የኾነውን የእግዚአብሔርን የቃል ኪዳን ታቦት ይዛ በመዝሙር፣ በጭብጨባ፣ በሆታ፣ በዕልልታ፣ በውዳሴ፣ በማኅሌት፣ በቅኔ፣ በስብከተ ወንጌል፣ በጸሎት የከበረውን ውኀ ባርኮ በመርጨት ልዩና በኾነ የአምልኮ ጉዞ ሃይማኖታዊና ማኅበራዊ አስተምህሮን አጉልቶ ሊያሳይ በሚያስችል መልኩ በዓለ ጥምቀት እንዲከበር በማድረጓ ለአገራችን ኢትዮጵያ ልዩ የኾነ ግርማ ሞገስን አጐናጽፋ እንደምትገኝ አስረድተዋል፡፡ ከ፶ ሚሊየን በላይ የሚኾን ሕዝበ ክርስቲያን በነጻነት፣ በአንድነት፣ በደስታና በፍቅር ከቤተ ክርስቲያኑ አንሥቶ እስከ ባሕረ ጥምቀቱ፤ ከባሕረ ጥምቀቱ እስከ ቤተ ክርስቲያኑ ድረስ ምንም መለያየት ሳይኖር፣ ጥላቻ ሳያጋጥም፣ በየቋንቋውና በየባህሉ ፈጣሪውን እያመሰገነ እንደ ዓባይ ወንዝ የእግዚአብሔር ሠራዊት ኾኖ ከዳር እስከ ዳር እየተመመ በዓለ ጥምቀትን ማክበሩ ዅሉን የሚገዛ የእግዚአብሔር ኀይል መገለጫ መኾኑን ቅዱስ ፓትርያኩ አስገንዝበዋል፡፡

img_0513

‹‹ይህ በዓል የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የቅድስና ሕይወትና የሥራ ፍሬ ምስክር ነው፡፡ ይህ በዓል የኢትዮጵያውያን ቅዱሳን አበው የማይፈርስ ጽኑዕ ግንብ ነው፡፡ ይህ በዓል የኢትዮጵያ እና የእግዚአብሔር የኾነ ጽኑዕ የቃል ኪዳን ትስስርን የሚያረጋግጥ ማስረጃ ነው፤›› ያሉት ቅዱስ ፓትርያርኩ የኢትዮጵያን ሕዝብ እርስበርስ ከማቀራረብና ከማስተሳሰር አኳያ ከበዓለ ጥምቀት የሚበልጥ በዓል እንደሌለ ጠቅሰው ኢትዮጵያውያን ይህንን ጸጋ እግዚአብሔርና ግርማ ሞገስ የተሞላ በዓል እስከ መጨረሻው ሊጠብቁትና ሊንከባከቡት፤ ሊያሳድጉትና ሊያበለጽጉት፤ ለዓለምም ሊያስተዋውቁት እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ እንድርያስ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት ጉባኤ ሰብሳቢ እና የመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል የበላይ ጠባቂ እንደዚሁ በበዓለ ጥምቀት ዋይዜማ ከሰጡት ትምህርተ ወንጌል በተጨማሪ በዕለቱም ‹‹ተሣሃልከ እግዚኦ ምድረከ ወሜጥከ ፄዋሁ ለያዕቆብ ወኀደገ ኀጢአቶሙ ለሕዝብከ፤ አቤቱ ምድርህን ይቅርል አልኽ፡፡ የያዕቆብን ምርኮ መለስህ፡፡ የሕዝብህን ኀጢአት ይቅር አልህ፤›› /መዝ.፹፬፥፩/ በሚል ኃይለ ቃል እግዚአብሔር አምላካችን አዳምን ከዘለዓለማዊ ሞት ማዳኑን እና ለሕዝቡ ያደረገውን ይቅርታ የሚያስገነዝብ ትምህርተ ወንጌል ሰጥተዋል፡፡

img_0506

በበዓሉ ከታደሙ ከፍተኛ የመንግሥት ባለ ሥልጣናት መካከል የኢትዮጵያ ባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር ሚኒስትር ዶክተር ኂሩት ወልደ ማርያም ያስተላለፉት መልእክት ደግሞ ሌላው የጥምቀት ትውስታ ነው፡፡ ሚኒስትሯ በዚህ መንፈሳዊ በዓል ላይ ተገኝተው መልእክት ለማስተላለፍ በመቻላቸው የተሰማቸውን ልባዊ ደስታ ገልጸው ኢትዮጵያውያን የብዙ ሀብት ባለቤት የኾነች አገር ስላለችን ዕድለኞች እንደ ኾንን እና አገራችን ካሏት ልዩ ልዩ የሚዳሰሱና የማይዳሰሱ ሀብታት መካከል በዓለ መስቀል አንዱ መኾኑን ጠቅሰው ይህንን የማይዳሰስ ሃይማኖታዊ ሀብት ጠብቀው ለትልድ ያቆዩ ቀደምት ኢትዮጵያውያንን አመስግነዋል፡፡ ዶ/ር ኂሩት አያይዘውም ከልዩ ልዩ የዓለም ክፍሎች የሚመጡ ጐብኚዎች በአንክሮ እና በተደሞ ኾነው የበዓሉን ሥርዓት እንዲከታተሉ ያደረጋቸው በዓለ ጥምቀት በሌላው ዓለም የማይገኝ፤ ኢትዮጵያውያን በአንድነት ኾነው ደስታቸውን የሚገልጹበት ልዩ በዓል በመኾኑ ነው ብለዋል፡፡

በዓለ ጥምቀት በዓለም አቀፉ የትምህርት፣ ሳይንስና ባህል ድርጅት እንዲመዘገብ መንግሥት ከፍተኛ ጥረት በማድረግ ላይ እንደሚገኝ የገለጹት ሚኒስትሯ ለዚህም ቤተ ክርስቲያንና መላው ሕዝበ ክርስቲያን ድጋፍ እንዲያደርጉ ጠይቀዋል፡፡ አብያተ መዝክራትን በማስፋፋት መንፈሳዊ ቅርሶችን የመጠበቅ ጉዳይ በቤተ ክርስቲያኗ ትኩረት ሊሰጠው እንደሚገባ ያሳሰቡት ዶ/ር ኂሩት ወልደ ማርያም በመጨረሻም ‹‹በበዓለ ጥምቀት አከባበር ላይ የሚታየው የኢትዮጵያውያን መንፈሳዊ ኅብረት በማኅበራዊ ሕይወታችንም ተጠናክሮ እንዲቀጥል አደራ›› በማለት መልእክታቸውን አጠቃለዋል፡፡ የአዲስ አበባ ከተማ ባህልና ቱሪዝም ቢሮ ሓላፊ አቶ ገብረ ጻድቅ ሀጎስ እንደዚሁ በዓለ ጥምቀት የኢትዮጵያን መልካም ገጽታ የሚገነባ እና ለዓለም የሚያስተዋውቅ በዓል ከመኾኑ ባሻገር ለአገሪቱ የቱሪዝም ገቢ ዕድገት ከፍተኛ አስተዋጽዖ እንዳለው መናገራቸውም አይዘነጋም፡፡

img_0514

በመላው ዓለም በሚገኙ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በበዓለ ጥምቀት ወቅት አባቶች ካህናት ከዋይዜማው ጀምሮ ከምግብ ተከልክለው፤ እንቅልፍ አጥተው በቅዳሴ፣ ታቦት በማክበርና በመሳሰሉ ተልእኮዎች መሰማራታቸው፤ የየአድባራቱና ገዳማቱ ሊቃውንት፣ የየሰንበት ት/ቤቶችና የማኅበረ ቅዱሳን መዘምራን በከበሮ፣ በጸናጽል፣ በመሰንቆ፣ በዋሽንት፣ በበገና ታግዘው የሰሚዎችን ልቡና በሚማርክ ያሬዳዊ ዝማሬ ታቦታን ማጀባቸው፤ ብዙ ምእመናን ሥርዓት ባለው (ክርስቲያናዊ በኾነ) አለባበስ አጊጠው በዕልልታና በጭብጨባ እየዘመሩ በበዓሉ መታደማቸው፤ በተለይ እንደ አዲስ አበበባ ባሉ ሰፋፊ ከተሞች ወጣቶች የክብር ምንጣፍ ለታቦታቱ ለመዘርጋት መፋጠናቸው የብዙዎችን ቀልብ የሚስቡና የሚያስደስቱ የአገልግሎት ክፍሎች ናቸው፡፡

መለዮ ሹራብ ለብሰው ለታቦታቱ የክብር ምንጣፍ ለመዘርጋት ወዝ እስኪወጣቸው ድረስ የሚሽቀዳደሙ ወጣቶች አቤት ሲያስቀኑ! በእውነት በእግዚአብሔር ጥሪ ለመልካም አገልግሎት የተሰማሩ የተዋሕዶ ፍሬዎች ናቸው፡፡ እነዚህን ወንድሞችና እኅቶች ስንመለከት ‹‹በጕብዝናህ ወራት ፈጣሪህን አስብ፤›› /መክብብ ፲፪፥፩/ የሚለው የጠቢቡ ሰሎሞን ምክር በአእምሯችን ድቅን ይላል፤ የወጣቶቹ ርብርብ ምክሩ በተግባር ላይ እንደ ዋለ የሚያመላክት መንፈሳዊ አገልግሎት ነው፡፡ ወጣቶቹ የሚያገለግሉት ምንጣፍ በመዘርጋት ብቻ አይደለም፤ በየከተሞች በሚገኙ መንገዶችና ዐደባባዮች በረጅሙ የተዘረጉ ሰንደቅ ዓላማዎችና ጌጣጌጦች፤ በሙዚቃና በሐራ ጥቃ ‹‹መዝሙራት›› የተዋጡ አካባቢዎችን ነጻ ያወጡ መንፈሳውያን የሲዲ ዝማሬዎች በየዓመቱ የሚከናወኑ የወጣቶቹ ተጨማሪ ተልእኮዎች ናቸው፡፡

img_0524

ታቦታትን አጅበው ለሚጓዙ፣ በፀሐይ ለደከሙ ምእመናን ጠበል ጸሪቅ እና የሚጠጣ ውኀ በየመንገዱ ማቅረብም ሌላኛው ተግባራቸው ነበር፡፡ ይህ መልካምና አርአያነት ያለው የወጣቶቹ ተልእኮ ተጠናክሮ እንዲቀጥል የሚመለከትን አካላት ዅሉ ወጣቶቹን በገንዝብ፣ በጕልበት፣ በሐሳብና በሌላም ልዩ ልዩ መንገድ መደገፍና መከባከብ ይገባናል፡፡ እኛም እንደ ዝግጅት ክፍል እነዚህን ወንድሞችና እኅቶችን ‹‹እግዚአብሔር መጨረሻችሁን ያሳምርላችሁ!›› እንላቸዋለን፡፡ ለታቦተ ሕጉ ምንጣፍ በዘረጉ እጆቻችን የሰው ንብረት እንዳንወስድ፤ የሰው ባል ወይም ሚስት እንዳናቅፍ፤ ሰውን እንዳንደበድብ፤ ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት በተሸቀዳደምንባቸው እግሮቻችን ወደ ኀጢአት መንገድ እንዳንሔድባቸው፤ ደሃ ወገኖቻችንን እንዳንረግጥባቸው እግዚአብሔር የዅላችንንም መጨረሻ ያሳምርልን፡፡

በቃና ዘገሊላ መድኀኒታችን ክርስቶስ ውኀውን ወደ ወይን ጠጅ በቀየረበት ዕለት የሰርግ ቤቱ አጋፋሪ ወይኑን በቀመሰ ጊዜ እንደ ተደነቀ በቅዱስ ወንጌል ተጽፏል /ዮሐ.፪፥፱/፡፡ ቅዱስ ያሬድም በድርሰቱ ‹‹ጥዒሞ አንከረ ሊቀ ምርፋቅ በረከተ ዘአምላክ ገብረ›› በማለት ይህንኑ ምሥጢር ጠቅሶታል፡፡ የቃናው ወይን ጠጅ የቀመሱትን ዅሉ ያስደነቀበት ምክንያት በክርስቶስ ተአምር የተገኘ ንጹሕ መጠጥ በመኾኑ ነው፡፡ እኛም የእግዚአብሔር የእጁ ሥራዎች ከመኾናችን ባሻገር በቅዱስ ሥጋው እና በክቡር ደሙ ቤዛነት ለመንግሥቱ የጠራን ልጆቹ ነን፡፡ ስለዚህ የእኛን መንፈሳዊ ኅበረት፣ ክርስቲያናዊ ፍቅር እና የአምልኮ ሥርዓት የሚመለከቱ ሰዎች ይደነቃሉ፡፡ ይህ መንፈሳዊ ሥርዓት ግን በበዓላት ላይ ብቻ የሚፈጸም ተግባር መኾን የለበትም፡፡ ክርስትናችንን ከዓመት አንድ ጊዜ ብቻ ሳይኾን በየቀኑ መኖር ይጠበቅብናልና፡፡

img_0534

አንድ ጊዜ መንፈሳዊ፤ ሌላ ጊዜ ዓለማዊ በኾነ የተቀላቀለ ሥርዓት ከኖርን ግን እንኳን የውጮቹ ሊደነቁብን የውስጦቹ ወገኖቻችንም በእኛ የማስመሰል ክርስትና ሊደናገሩብን፤ ‹‹እነዚህ እንደዚህ ሲያደርጉ የተመለከትናቸው አይደሉም እንዴ?›› በሚል የጥርጣሬ መንፈስም ሊሰናከሉብን ይችላሉ፡፡ ለሌሎች መሰናክል ከመኾን ይልቅ የወፍጮ ድንጋይ በአንገታችን ታስሮ ወደ ጥልቅ ባሕር መስጠም እንደሚሻለን ደግሞ ጌታችን በወንጌል ተናግሯል /ማቴ.፲፰፥፮/፡፡ ጌታችን እንደ ተነናገረው ምግባራችን ለእኛም ለሌሎችም የማይጠቅም ኢ ክርስቲያናዊ ከኾነ እንደ አጥፍቶ ጠፊ ሞቶ መግደል መገለጫችን ይኾናል ማለት ነው፡፡ እናም ራሳችንን አጥተን ለሰዎችም መጥፋት ምክንያት እንዳንኾን እንጠንቀቅ መልእክታችን ነው፡፡

ከዚህ ላይ ይህን ሐሳብ ያነሣነው ያለ ምክንያት አይደለም፡፡ እንደ በዓለ ጥምቀት ባሉ ልዩ በዓላት ወቅት በየከተማው የሚስተዋሉ ኢ ክርስቲያናዊ ተግባራት እንዲስተካከሉ ለመሳሰብ ነው፡፡ ጥቂቶቹን ለመጠቆም ያህል በዓሉን ተገቢ ላልኾነ የተቃራኒ ጾታ መቀጣጠሪያ ማድረግ፤ በየመጠጥ ቤቱ መተላለፊያ መንገዶችን በመዝጋት፣ በጩኸትና በሁካታ አካባቢን እየረበሹ መጠጥ መጠጣትና መስከር እኛንም ሃይማኖታችንንም የሚያስነቅፍ ድርጊት ነውና እናስብበት፡፡ መጠጥ ቢያምረን እንኳን ከዘመዶቻችን ጋር ኾነን በቤታችን ተሰባስበን፣ ጸሎት አድርገን፣ በሥርዓትና በአግባቡ መጠጣት እንችላለን፡፡ በክርስትናችን መስከር (አብዝቶ መጠጣት) እንጂ አልኮል መቅመስ አልተከለከለምና፡፡ ሲበዛና ከሥርዓት ውጪ ሲኾን ግን እንሰክርና በኀጢአት ላይ ኀጢአት ለመፈጸም እንገፋፋለን፡፡ ይህም በቅጣት ላይ ቅጣትን ያመጣብናል፡፡

ttt

በበዓላት ወቅት ለሥጋዊ ጉዳይ የምንቀሽዳድም ክርስቲያኖች ጥቂቶች አይደለንም፡፡ ይህም ሊስተካከል ይገባዋል፡፡ መንፈሳውያን በዓላትን ከዓለማዊ ግብር ለይተን ልናይ ያስፈልጋል፡፡ ይህ ብቻም አይደለም፤ በዓሉን ስናከብር ለጥላቻ፣ ለድብድብ፣ ለግብረ ዝሙትና ለመሳሰለው ኀጢአት የምንገዛ ወገኖች ይህ የክርስቲያኖች መገለጫ አይደለምና ከዚህ ልማድ እንቈጠብ፡፡ ይህ ልማድ በበዓላት ወቅት በተለይ በበዓለ ጥምቀት ጎልቶ ስለሚታይ በዚህ ዝግጅት አነሣነው እንጂ በሌላ ጊዜ ኀጢአት መሥራት ይቻላል ለማለት አይደለም፡፡ ቀደም ሲል እንደ ጠቀስነው በክርስቲያናዊ ምግባር ጸንቶ መኖር የዅልጊዜ ተግባራችን ሊኾን የግድ ነውና፡፡ በእርግጥ ተሳስተን ልንሰናከል እንችላለን፤ በዕቅድና በዓላማ ለስካርና ለሌችም የኀጢአት ዘሮች ተገዢ መኾን ግን ከእኛ የሚጠበቅ ተግባር አይደለም፡፡

img_0574

ከዚሁ ዅሉ ጋርም በየመንገዱና በየዐደባባዩ የምናስቀምጣቸው ቅዱሳት ሥዕላት ጉዳይ ከቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ አንጻር ሊታይ ይገባል፡፡ ምክንያቱም ሥዕላቱ ንዋያተ ቅድሳት እንደ መኾናቸው ለአምልኮ እና ለጸሎት በተመረጠ ልዩና ንጹሕ ቦታ መቀመጥ ሲገባቸው ለፀሐይ፣ ለአቧራና ለነፋስ በሚጋለጡባቸውና በሚቀደዱባቸው መንገዶች ላይ፣ ጭራሽ በቆሻሻ መጣያ ሥፍራዎች በዘፈቀደ መቀመጣቸው ተገቢ አይደለም፡፡ በአንዳንድ የአዲስ አበባ መንገዶች ስንዘዋወር ሥዕላቱ ከተቀመጡበት ቦታ የሚያነሣቸው ጠፍቶ በነፋስ ተቀዳደው ሲወድቁ ዅሉ ተመልክተናል፡፡ የተወደዳችሁ ምእመናን በተለይ ወጣት ክርስቲያኖች ሆይ! ይህ ጉዳይ ትኩረት ሊያገኝ ይገባዋል፡፡

img_0575

ከዚህ ላይ የወጣቶቹን ተልእኮ እየነቀፍን እንዳልኾነ ግን ለማስገንዘብ እንወዳለን፡፡ እርግጥ ነው፤ ወጣቶቹ ይህን የሚያደርጉት ለተንኮል ሳይኾን ለሃይማኖታቸው ካላቸው ቀናዒነትና በዓሉ ድምቀት እንዲኖረው ከማሰባቸው የተነሣ መኾኑ አይካድም፡፡ ዳሩ ግን ጥሩ የሠራን መስሎን የምናከናውናቸው ተግባራት ከሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን ጋር ተቃርኖ እንዳይኖራቸው፤ እንደዚሁም ‹‹መክፈልት ሲሹ መቅሠፍት›› እንደሚባለው ለበረከት ያልነው ተልእኮ ለጥፋት እንዳይዳርገን የሥዕላቱን ኦርቶዶክሳዊ ይዘት ከማስገምገም ጀምሮ እስከምናስቀምጥበት ቦታ ድረስ ከአባቶች ጋር መመካከርና መመርያ መቀበል ያስፈልጋል፡፡

በተጨማሪም በየመንገዱ የምንከፍታቸው ዝማሬያት ያሬዳዊነትም አብሮ ቢታሰብበት መልካም ነው፡፡ በአጭሩ ቅዱሳት ሥዕላቱን በየመንገዱ ከማስቀመጣችን በፊት (አስፈላጊነቱ በአባቶች ከታመነበት) ሥዕላቱን ከምንመርጥበት መሥፈርትና ከምናስቀምጥበት ቦታ ጀምሮ እስከ አቀማመጠጥ ሥርዓቱ ድረስ፤ እንደዚሁም ከምንከፍታቸው መዝሙራት ያሬዳዊነት አኳያ ዅሉም በሥርዓት ይኾን ዘንድ ጥንቃቄ ማድረግ እንደሚገባን አንርሳ፡፡ ቤተ ክርስቲያናችን የሊቃውንት ችግር የለባትም፡፡ የትኞቹን ሥዕላትና መዝሙራትን መጠቀም እንደሚገባን ጠጋ ብለን መምህራንን ብንጠይቅ በቂ ትምህርት ይሰጡናል፡፡

img_0570

እንደሚታወቀው በዓለ ጥምቀት ከሃይማኖታዊ ይዘቱ በተጨማሪ አገራዊ ሀብታችን ስለኾነ ዓለም አቀፋዊ እውቅና ሊገኝ እንደሚገባው እሙን ነው፡፡ ስለዚህም በዓሉን በዓለም አቀፉ የትምህርት፣ ሳይንስና ባህል ድርጅት በቅርስነት ለማስዝገብ ቤተ ክርስቲያናችን ከመንግሥት ጋር በመኾን ጥረት በማድረግ ላይ ትገኛለች፡፡ በዓለ ጥምቀት በቅርስነት እንዲመዘገብ የሚያደርገው በዐደባባይ የሚከበር በዓል መኾኑ ብቻ ሳይኾን የአከባበር ሥርዓቱ መንፈሳዊነትና ውበት ነው፡፡ የታቦታቱ ዑደት፣ የሊቃውንቱና የሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶች ዝማሬ፣ የምእመናኑ አለባበስና የወጣቶቹ ሱታፌ፣ ከበዓሉ በፊትም ኾነ ከበዓሉ በኋላ የምናደርጋቸው ሌሎች እንቅስቃሴዎች ዅሉ የበዓሉ አካላት ናቸው፡፡

የእኛ የአከባበር ዅኔታ ነው በዓሉን በዓል የሚያስብለው፡፡ በሥርዓት ካከበርነው በዓለም እንደ ተደነቀ ይቀጥላል፤ መንፈሳዊ ሥርዓቱን ካጎደልን ግን በዓልነቱም ይረሳል፡፡ ስለዚህ በዐቢይነት ከክርስቶስ ጸጋና በረከት እንሳተፍ ዘንድ፤ በሁለተኛ ደረጃ ደግሞ በዓሉ በቅርስነት እንዲመዘገብ የሚደረገው ጥረት ይሳካ ዘንድ ለወደፊቱ ዅላችንም ክርስቲያናዊ ሥርዓቱን በጠበቀ መልኩ በዓለ ጥምቀትን ለማክበር እንዘጋጅ እያልን ጽፋችንን አጠቃለልን፡፡ በዘንድሮው በዓለ ጥምቀት ያከናወናቸውን መልካም ተግባራት አሳድገን፤ ያጎደልናቸውን ደግሞ አሻሽለን በዓሉን በመንፈሳዊ ሥርዓት እንድናከብር አምላካችን ዕድሜ ለንስሐ ሰጥቶ በሚቀጥለው ዓመት በበዓለ ጥምቀቱ ይሰብስበን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

አስተርእዮ

በመምህር  ለማ በእርሱፈቃድ

ጥር ፲ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

አስተርእዮ ማለት መታየት፣ መገለጥ  የመሳሰሉትን ፍች ይይዛል፡፡ ቃሉ አስተርአየ ታየ፤ ተገለጠ ከሚለው የግእዝ ግሥ የተገኘ ነው፡፡ የጥር ወር በሙሉ ዘመነ አስተርእዮ በመባል ይታወቃል፡፡ ምክንያቱም ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በገባው ቃል ኪዳን መሠረት በሥጋ የተገለጠበት (የታየበት) ወቅት በመኾኑ ከልደት በዓል እስከ ጥር መጨረሻ ያለው ጊዜ ዘመነ አስተርእዮ ይባላል፡፡ ይህ ብቻም ሳይኾን የእግዚአብሔር አንድነት፣ ሦስትነት የተገለጠው በዚሁ ወር ነውና ወቅቱ ዘመነ አስተርእዮ ተብሎ ይጠራል፡፡ በዚህ ጽሑፍ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሰውን ልጅ ሥጋ ለብሶ የመታየቱ (የመገለጡ) ዋና ዋና ምክንያቶችን ምንድን ናቸው የሚሉ ነጥቦችን በአጭሩ እንመለከታለን፤

፩. የገባውን ቃል ኪዳን ይፈጽም ዘንድ

እግዚአብሔር አምላካችን ሰውን በምሳሌው ፈጥሮ የሚያስፈልገውን ዅሉ አዘጋጅቶ በክብር ይኖር ዘንድ ገነትን አወረሰው፡፡ በማየት የሚደሰትበትና የሚማርበትንም ሥነ ፍጥረትን ፈጠረለት፤ የሚበላውንና የማይበላውንም ለይቶ ሰጠው፡፡ ነገር ግን አትብላ የሚለውን አምላካዊ ትእዛዝ ሳይጠብቅ የተከለከለውን ዕፀ በለስ በመብላቱ ምክንያት ከገነት ተባረረ /ዘፍ.፪፥፲፮/፡፡ በዚያን ጊዜ ነው ርኅራኄ የባሕርዩ የኾነ አምላካችን ‹‹ከአምስት ሺሕ አምስት መቶ ዘመን በኋላ ከልጅ ልጅህ ተወልጄ አድንሃለው›› የሚለውን የተስፋ ቃል ኪዳን ለአዳም የሰጠው /ሲራ.፳፬፥፮/፡፡

ነቢያቱም ‹‹ጌታ ራሱ ምልክትን ይሰጣችኋል፤ እነሆ ድንግል ትፀንሳለች፤ ወንድ ልጅም ትወልዳለች፡፡ ስሙንምአማኑኤል› ብላ ትጠራዋለች፤›› እያሉ ትንቢት ሲናገሩ ቆይተዋል /ኢሳ.፯፥፲፬/፡፡ አዳምም ከነልጆቹ ለአምስት ሺሕ አምስት መቶ ዘመናት ይህንን ቃል ኪዳን ሲጠባበቅ ኖሯል፡፡ ‹‹ቁጣው እስኪያልፍ ድረስ ጥቂት ጊዜ ተሸሸግ፤›› ተብሎ እንደ ተጻፈው /ኢሳ.፳፮፥፳/፣ ይህችን ቃል ኪዳን ይፈጽማት ዘንድ ወልደ አምላክ ኢየሱስ ክርስቶስ በተለየ አካሉ በሥጋ ተገለጠ ማለት ሥጋን ተዋሐደ፡፡

፪. የዲያብሎስን ሥራ ያፈርስ ዘንድ

‹‹ወዘሰ ይገብራ ለኀጢአት እምነ ጋኔን ውእቱ እስመ ቀዳሚሁ ለሰይጣን አበሰ ወበእንተ ዝንቱ አስተርአየ ወልደ እግዚአብሔር ከመ ይስዐር ግብሮ ለጋኔን፤ ኀጢአትን የሚሠራትም ከዲያብሎስ ወገን ነው፡፡ ጥንቱንም ሰይጣን በድሎአልና ስለዚህ የእግዚአብሔር ልጅ በሥጋ ተገለጠ፡፡ የዲያብሎስን ሥራ ይሽር ዘንድ፤›› በማለት ሐዋርያው እንደ ገለጸው /፩ኛዮሐ.፫፥፰/፣ ሰይጣን የሰውን ልጅ እግዚአብሔርን ያህል ጌታ፣ ገነትን የመሰለ ቦታ እንዲያጣ፤ ከደስታ ወደ ዘለዓለም ኀዘን፣ ከነጻነት ወደ ግዞት፣ ከብርሃን ወደ ጨለማ እንዲገባ ረቂቅ ሥራ ሠርቶ ነበርና ይህንን የዲያብሎስን ሥራ ያፈርስ ዘንድ እግዚአብሔር በሥጋ ተገለጠ፡፡

ዲያብሎስ በሥጋ ከይሲ (በእባብ ሥጋ) ተሰውሮ ነገት ገብቶ አዳምና ሔዋንን እንዳሳተ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም የሰውን ልጅ ሥጋ ተዋሕዶ የዲያብሎስን ሥራ አፍርሶበታል፡፡ ዲያብሎስ አዳምና ሔዋንን አስቶ የግብር ልጆቹ ይኾኑ ዘንድ ‹‹አዳም ገብሩ ለዲያብሎስ ሔዋን አመቱ ለደያብሎስ›› ብለው የፈረሙትን ደብዳቤ፣ በዮርዳኖስና በሲዖል የቀበረውን የጥፋት የተንኮል ሥራውን ያፈርስ ዘንድ አምላክ ሰው ኾኖ ተገለጠ፡፡

ይህንን የዲያብሎስ ሥራም በዮርዳኖስ ባሕር የተቀበረውን በጥምቀቱ፤ በሲዖል የተቀበረውን በስቅለቱ፣ በሞቱ ደምስሶበታልና ‹‹ወነሰተ ዐረፍተ ማእከል እንተ ጽልዕ በሥጋሁ፤ በመካከል የነበረውን የጥል ግድግዳ በለበሰው ሥጋ አፈረሰው፤›› በማለት ሐዋርያው እንደ ተናገረው /ኤፌ.፪፥፲፬/፣ የዲያብሎስን ክፉ ሥራ የጥል ግድግዳ ያፈርስ ዘንድ ክርስቶስ በሥጋ ተገለጠ፡፡

፫. አንድነቱን፣ ሦስትነቱን ይገልጥ ዘንድ

የምሥጢረ ሥላሴ ትምህርት በብሉይ ኪዳን ዘመን በግልጥ አይታወቅም ነበር፡፡ የተገለጠ፣ የታወቀ፣ የተረዳ የአንድነቱን፣ የሦስትነቱን ትምህርት በሚገባ ለማስተማር የተቻለው ጌታችን ሥጋ ለብሶ ከተጠመቀ ጊዜ ጀምሮ ነው፡፡ ‹‹ወርእየ መንፈሰ እግዚአብሔር እንዘ ይወርድ በአምሳለ ርግብ ወናሁ መጽአ ቃል እምሰማይ ዘይብል ዝንቱ ውእቱ ወልድየ ዘአፈቅር ዘቦቱ ሠመርኩ፤ የእግዚአብሔር መንፈስ በርግብ አምሳል በራሱ ላይ ሲቀመጥ አየ፡፡ እግዚአብሔር አብ በደመናየምወደው፣ ለመሥዋዕትነት የመረጥኩት ልጄ ይህ ነው› አለ፤›› ተብሎ እንደ ተጻፈ /ማቴ.፫፥፲፯፤ ሉቃ.፫፥፳፩/፣ ጌታችን የአዳምና የሔዋንን የዕዳ ደብዳቤ ለመሻር በዮርዳኖስ ወንዝ በተጠመቀ ጊዜ የአንድነት እና ሦስትነት ምሥጢር ተገልጿል፡፡ ይህ ምሥጢር ከጥንተ ዓለም ጀምሮ በግልጽ ሳይታወቅ፣ ሳይገለጥ ተሰውሮ ይኖር ነበር፡፡ ‹‹በእንተ ኢየሱስ ክርስቶስ ዘኅቡእ ኅርመቱ እምቅድመ ዓለም፤ ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ ዓለም ሳይፈጠር ተሰውሮ ነበር፡፡ ከነቢያት ቃል የተነሣ በዚህ ዘመን ተገለጠ፤›› እንዲል /ሮሜ.፲፮፥፳፬/፡፡

፬. ፈጽሞ እንደ ወደደን ለመግለጽ

እግዚብሔር ሰውን ምን ያህል እንደ ወደደው ለመረዳት እግዚብሔር ዓለምን ከፈጠረበት ጥበቡ ይልቅ ዓለምን ያዳነበት ጥበቡን በሚገባ መረዳት ያስፈልጋል፡፡ ምክንያቱም ዓለምን ከፈጠረበት ጥበቡ ይልቅ ያዳነበት ጥበቡ እጅግ ዕፁብ ድንቅ ነውና፡፡ ማንም ሳያስገድደው፤ ሰው ኹን ብሎ ሳይጠይቀው በገባው ቃል ኪዳን መሠረት ዘመኑን ጠብቆ እግዚአብሔር ሰው ኾኖ ከኀጢአት በስተቀር ዅሉን ፈጽሞ፣ በገዛ ፈቃዱ መከራ ሥጋን ተቀብሎቈ ሥጋውን ቈርሶ፣ ደሙን አፍሶ የዘለዓለም ሕይወትን ለሰው ልጅ በመስጠቱ ምን ያህል ፍጹም ፍቅሩን እንደ ገለጸልን እንረዳለን፡፡ ‹‹አልቦ ዘየዐቢ እምዝ ፍቅር ከመ ዘቦ ዘይሜጡ ነፍሶ ህየንተ አእርክቲሁ፤ ስለ ወዳጆቹ ሕይወቱን አሳልፎ የሚሰጥ ያለ እንደ ኾነ ከዚህ የሚበልጥ ፍቅር የለም፤›› እንዳለ ወንጌላዊው /ዮሐ.፲፭፥፲፪/፡፡

በደል የሠራው የሰው ልጅ ይሰቀል ይሙት ሳይል እኔ ልሙት ማለቱ የእግዚአብሔር የፍጹም ፍቅሩ መገለጫ ነው፡፡ ሰው ሰውን የሚወደው ገንዘቡንና የመሳሰሉትን እስከ መስጠት ሊኾን ይችላል፡፡ ሕይወቱን እስከ መስጠት የሚወድ ማንም የለም፤ አልነበረም፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የወደደውን የሰውን ሥጋ ለብሶ መኪራ ሥጋን ተቀብሎ ሰውን በሞቱ ያድን ዘንድ ሞትን የሞተው ፈጽሞ እንደ ወደደን ለመግለጥ ነው /፩ኛዮሐ.፬፥፱/፡፡ ይህም ፍቅሩ ይቃወቅ ዘንድም በሥጋ ተገለጠ፡፡ ስለዚህም ሊቃውንቱ ይህንን ወቅት ‹‹አስተርእዮ›› በማለት ሰይመውታል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ማስገንዘቢያ፡- ይህ ትምህርት ጥርቀን ፳፻፭ .ም በድረ ገጻችን ቀርቦ ነበር፡፡