ሆሣዕና በአርያም

በዲያቆን ሚክያስ አስረስ

መጋቢት ፳፱ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

ሰውን ከወደቀበት የበደል ጉድጓድ ያወጣው ዘንድ እግዚአብሔር ክንዱን ወደ ዓለም ላከ፡፡ ሰው ኾኖ የተገለጠው የእግዚአብሔር ክንድ በትሕትና ሁለተኛ አዳም ኾኖ በለበሰው ሥጋ በጉድጓድ ተጥሎ፤ በሥጋ፣ በነፍስ፣ በውስጥ፣ በአፍአ ቈስሎ የነበረ አዳምን ከሞተ ነፍስ አድኖታል፡፡ ከእርሱ አስቀድሞ ሰውን ከሞት ወደ ሕይወት፤ ከባርነት ወደ ነጻነት የሚያመጣ ባለመኖሩ ዅሉን የፈጠረ፣ ዅሉን የሚያኖር እግዚአብሔር በለበሰው ሥጋ ሞቶ ለሰው ልጅ መድኃኒት ኾነ፡፡ በዚህም ‹‹መድኃኒተ ፈነወ እግዚአብሔር ለሕዝቡ፤ እግዚአብሔር ለሕዝቡ መድኃኒትን ላከ፤›› ተብሎ በነቢዩ የተነገረው ትንቢት ተፈጸመ (መዝ. ፻፲፥፱)፡፡

ክርስቶስ ባለ መድኃኒት ኾኖ በኃጢአት ለታመሙ ደቂቀ አዳም ዅሉ ሕይወትን ይሰጥ ዘንድ ወደዚህ ዓለም መጣ፡፡ በምድራዊ ሥርዓት እንደምናየው መድኃኒትና ባለ መድኃኒት እንደሚለያዩት አይደለም፡፡ እርሱ በመምጣቱ (ሰው በመኾኑ) ሁለቱንም ፈጸመ እንጂ፡፡ መድኃኒት አድርጎ ሥጋውን ደሙን የሰጠ እርሱ ነው፡፡ በካህናት አድሮ ሰው በንስሐ ሲመለስ መድኃኒት ወደ ኾነው ወደ ራሱ የሚመራም እርሱ ነው፡፡ በእመቤታችን ማኅፀን የተጀመረው የክርስቶስ መድኃኒትነት እና ፍቅሩ ፍጻሜውን ያገኘው በሕማሙ እና በሞቱ ነው፡፡ መሐሪ ንጉሥ እርሱ መኾኑን ይገልጥ ዘንድም በፈቃዱ ወደ ኢየሩሳሌም መጣ፡፡

ጌታችን ወደ ኢየሩሳሌም ከመግባቱ አስቀድሞ ከኢየሩሳሌም ፲፮ ያህል ምዕራፍ በምትርቀው በቤተ ፋጌ ከደቀ መዛሙርቱ ጋር ነበር፡፡ ከደቀ መዛሙርቱም ሁለቱን ማለትም ጴጥሮስን እና ዮሐንስን ‹‹በፊታችሁ ወዳለችው መንደርዱ፤ ወደ እርሷ ገብታችሁ ከሰው ማንም ገና ያልተቀመጠበትን ውርንጫ ታስሮ ታገኛላችሁ፤ ፈትታችሁ አምጡልኝ፤›› በማለት አዘዛቸው (ማር. ፲፩፥፪)፡፡ ሰው ወዳልገባባት የተዘጋች የምሥራቅ ደጅ ወደ ምትባል ወደ ድንግል መጥቶ ዘጠኝ ወር ማኅፀኗን ከተማ አድርጎ እንደ ኖረ፤ ማኅየዊት ከምትኾን ሕማሙ በኋላም ሰው ባልተቀበረበት መቃብር እንደ ተቀበረ፤ አሁንም ጌታችን ወደ ኢየሩሳሌም ለመግባት ማንም ሰው ያልተቀመጠባቸውን፣ አህያንና ውርንጫን እንዲያመጡ ደቀ መዛሙርቱን አዘዘ፡፡

የፍጥረት ዅሉ ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ በልደቱ እስትንፋሷን የገበረችለትን አህያ አሁን ደግሞ በፈቃዱ ስለ ሰው ዅሉ ሊሞት ሲል ንጉሥነቱን ሊያስመሰክርባት ወደደ፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እስከ ኢየሩሳሌም ድረስ ካለው ፲፮ ምዕራፍ ዐሥራ አራቱን በአህያ ላይ ሳይቀመጥ በእግሩ ተጓዘ፡፡ ከዚያም ሁለቱን ምዕራፍ በአህያ ጀርባ ላይ ተቀምጦ ከሔደ በኋላ የኢየሩሳሌምን መቅደስ ሦስት ጊዜ በውርጫዋ ላይ ኾኖ ዞረ፡፡ በዚህም ሕግ በተሰጣቸው አይሁድ እና ሕግ ባልተሰጣቸው አሕዛብ ላይ እኩል ቀንበርን መጫን እንዳይገባ አጠየቀ፡፡

ወደ ኢየሩሳሌም ሲሔድም እርሱን የሚከተሉት ሰዎች ሆሣዕና በአርያም› እያሉ ያመሰግኑት ነበር፡፡ ይኸውም በሰማይ በልዕልና ያለ፤ ከሰማይ የመጣ መድኃኒት› ማለት ነው፡፡ ብዙ ሰዎችም ልብሳቸውን እና ቅጠሎችን በመንገድ ላይ አነጠፉ፡፡ ‹‹ሆሣዕና በጌታ ስም የሚመጣ የተባረከ ነው›› እያሉም ጌታችንን አመሰገኑ (ማር. ፲፩፥፰-፲)፡፡ ዛሬም እኛ ክርስቲያኖች ‹‹ቡሩክ ስሙ ለእግዚብሔር ወቡሩክ ዘይመጽእ በስመ እግዚአብሔር፤ የእግዚአብሔር ስሙ ምስጉን ነው፡፡እግዚአብሔር ነኝ› ብሎ በእግዚአብሔር ስም የሚመጣ እርሱ ክርስቶስም ምስጉን ነው፤›› በማለት የአብ እና የወልድ መለኮታዊ አንድነትን ገልጸን እግዚአብሔርን እናመሰግነዋለን፡፡

በክርስቶስ ሕማም እና ሞት የእግዚአብሔር ፍቅሩ እና መሓሪነቱ ተገልጧል፡፡ ክርስቶስ የተቀበለው መከራም የእርሱን አምላክነት እና ንጉሥነት አልሸሸገውም፡፡ እንዳውም ዙፋኑን መስቀል በማድረግ ንጉሥነቱን በመድኃኒትነቱ ገልጿል እንጂ፡፡ በማእከለ ምድር ተሰቅሎ በመድኃኒትነቱ ንጉሥነቱን መግለጡንም ነቢዩ፡- ‹‹እግዚአብሔርሰ ንጉሥ ውእቱ እምቅድመ ዓለም ወገብረ መድኃኒተ በማእከለ ምድር፤ እግዚአብሔር ከዓለም አስቀድሞ ንጉሥ ነው፤ በምድር መካከልም መድኃኒትን አደረገ፤›› በማለት የተናገረው ቃል ያመለክታል (መዝ. ፸፫፥፲፪)፡፡ በሌላ የመዝሙር ክፍልም፡- ‹‹አንሰ ተሰየምኩ ንጉሠ በላዕሌሆሙ በጽዮን በደብረ መቅደሱ፤ እኔ በተቀደሰው ተራራ ላይ ንጉሥ ኾኜ ተሾምኹ፤›› በማለት ነቢዩ ክርስቶስ በመስቀል ላይ መንገሡን ተናግሯል (መዝ. ፪፥፮)፡፡ ይህንም ‹‹እነርሱ (አይሁድ) ‹ሰቀልነው፤ ገደልነው፤ በኋላ ፈርሶበስብሶ ይቀራል፤› ይሉኛል እንጂ እኔስ ደብረ መቅደስ በሚባል መስቀል ላይ ነግሻለሁ›› ብለው ኦርቶዶክሳውያን አበው ይተረጕሙታል፡፡

የጌታችን ሕማሙ እና ሞቱ ንግሥናው፣ ክብሩ የተገለጠበት ምሥጢር እንጂ ክብሩን የሚሸሽግ ውርደት አይደለም፡፡ ሊቁ ዮሐንስ አፈወርቅ፡- ‹‹ይትባረክ እግዚአብሔር ዘሰመየ ሕማማተ ወልዱ ክብረ ወስብሐተ፤ የልጁን ሕማማት ክብርና ምስጋና አድርጎ የሰየመ እግዚአብሔር ይመስገን!›› ያለውም ስለዚህ ነው፡፡ የክርስቶስ ሕማሙ እኛን ያከበረበት በመኾኑ ክብርና ምስጋና እንደ ተባለ እናስተውል፡፡

ከጌታችን በስተቀኝ በኩል ተሰቅሎ የነበረው ወንበዴም፡- ‹‹አቤቱ በመንግሥትህ በመጣህ ጊዜ አስበኝ?›› በማለት ንጉሥነቱን መስክሮለታል (ሉቃ. ፳፫፥፵፪)፡፡ ጌታችን ወደ ኢየሩሳሌም በምስጋና መግባቱ መድኃኒትነቱን እና ንጉሥነቱን ያሳያል ማለታችንም ስለዚህ ነው፡፡ ዳግመኛም ዅሉን የያዘ ጌታ በአህያ ላይ መቀመጡ ትሕትናውን ያስረዳል፡፡ ሊቁ ቅዱስ ያሬድ፡- ‹‹ዘይነብር ዲበ ኪሩቤል ዲበ ዕዋለ አድግ ነበረ›› በማለት ሰማያዊው አምላክ ልዑል እግዚአብሔር በትሕትና በአህያ ጀርባ እንደ ተቀመጠ ተናገረ፡፡

ጌታችን በመድኃኒትነቱ ድንቅ የኾኑ ተአምራትን ለሰዎች አሳየ (ገለጠ)፡፡ ‹‹እምሆሣዕናሁ አርአየ ተአምረ ወመንክረ›› እንዳለ ቅዱስ ጎርጎርዮስ ዘኑሲስ በቅዳሴው፡፡ ይህም ክርስቶስ በአህያ ተጭኖ ወደ ኢየሩሳሌም በገባ ጊዜ አእምሮ፣ ጠባይዕ ያልቀናላቸው ሕፃናት ዕውቀት ተገልጾላቸው ‹‹ሆሣዕና በአርያም›› እያሉ ማመስገናቸውን ያጠይቃል፡፡ መናገር የማይችሉ ድንጋዮች እርሱ በከሃሊነቱ ዕውቀት ሰጥቷቸው መናገር ችለው ጌታችንን አመስግነዋልና፡፡ መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የባሕርይ አምላክ መኾኑን፤ ቀድሞ በአዳም በደል ምክንያት ለሰው ከመገዛት ውጪ የነበሩ ፍጥረታት የሰውን ሥጋ ለብሶ በተገለጠው በክርስቶስ አማካይነት ዳግመኛ ለሰው መገዛታቸውን ከዚህ ምሥጢር እንረዳለን፡፡

ዳግመኛም ጌታችን በመድኃኒትነቱ የሥላሴ ልጅነት ማግኘትን እና ተአምራት ማድረግን ገለጠ፡፡ ‹‹እምሆሣዕናሁ አርአየ ጸጋ ወኃይለ›› እንዲል (ቅዳ. ጎርጎ. ዘኑሲስ)፡፡ የእርሱ የማዳን ሥራ ከሰው ተወስዶ የነበረውን የጸጋ ልጅነት እንዲመለስ ከማድረጉ ባሻገር በልጅነት ላይ ተአምራትን ለማድረግ አስችሏል፡፡ ይኸውም እርሱ በረድኤት አድሮባቸው ድንቅ ተአምራትን ለሚያደርጉ ቅዱሳን መሠረት ነው፡፡ በተጨማሪም የበደሉትን ያከብራቸው ዘንድ፤ ኃጥአንን ከኃጢአታቸው ያነጻቸው ዘንድ፤ እንደዚሁም የሳቱትን ይመልሳቸው ዘንድ ለንስሐ የሚኾን ዕንባን ሰጠ፡፡ ‹‹እምሆሣዕናሁ ወሀበ ፈልፈለ አንብዕ ለኃጥአን›› እንዲል (ቅዳ. ጎርጎ. ዘኑሲስ)፡፡

በተመሳሳይ ምሥጢር ጌታችን በመድኃኒትነቱ ለዕውራን ብርሃንን ሰጥቷል፡፡ ይኸውም ለጊዜው በዐይነ ሥጋ የታወሩትን በመፈወስ ዐይናቸውን እንዳበራላቸው፤ ለፍጻሜው ግን ዕውቀትን ከማጣት የተነሣ ታውረው ለነበሩ ዅሉ ዕውቀትን፣ ጥበብን ማለትም አንድነቱን፣ ሦስትነቱን፣ አምላክነቱንና የዓለም መድኃኒት መኾኑን የሚረዱበትን ጥበብ እንደ ገለጠላቸው የሚያመለክት ነው፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ሆሣዕና

በመ/ር ኃይለ ማርያም ላቀው

መጋቢት ፳፱ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

‹ሆሣዕና› የሚለው ቃል ‹ሆሼዕናህ› ከሚለው የዕብራይስጥ  ቃል የተወሰደ ሲኾን፣ ትርጕሙም እባክህ አሁን አድን› ማለት ነው፡፡ ‹‹አቤቱ እባክህ አሁን አድን፤ አቤቱ እባክህ አሁን አቅና፡፡ በእግዚአብሔር ስም የሚመጣ ቡሩከ ነው፤›› ተብሎ እንደ ተጻፈ (መዝ. ፻፲፯፥፳፭-፳፮)፡፡ የሆሣዕና በዓል ጌታችን አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በአህያ ጀርባ ተቀምጦ ወደ ኢየሩሳሌም ሲገባ አዕሩግም ሕፃናትም ‹‹ሆሣዕና ለዳዊት ልጅ፣ በጌታ ስም የሚመጣ የተባረከ ነው፣ ሆሣዕና በአርያም›› እያሉ ጌታችንን በክብር መቀበላቸው የሚታወስበት በዓል ነው፡፡

በሌላ አገላለጽ ይህ በዓል ‹የጸበርት እሑድ› (Palm Sunday) ይባላል፡፡ ታሪኩም የመልካም ምኞትና የድል አድራጊነት መገለጫ ኾኖ ከደገኛው አባታችን ይስሐቅ ልደት ጋር ተያይዞ የመጣ ነው፡፡ ሣራ ልማደ እንስት ከተቋረጠባት በኋላ ዅሉን ቻይ አምላክ ይስሐቅን በሰጣት ጊዜ ዘመዶችዋ የተሰማቸውን ደስታ ለመግለጽ የዘንባባ ዝንጣፊ በመያዝ እግዚአብሔርን አመስግነዋል፡፡ እስራኤል ከአስከፊው የግብጻውያን አገዛዝ ተላቀው ባሕረ ኤርትራን በደረቅ ሲሻገሩ የተሰማቸውን እጥፍ ድርብ ደስታ በገለጡ፣ እንደዚሁም ዮዲት የተባለች ንግሥተ እስራኤል ሆሎፎርኒስ የተባለ አላዊ ንጉሥን ድል ባደረገች ጊዜ ቤተ እስራኤል እንደ ሰንደቅ ዓለማ የዘንባባ ዝንጣፊ በመያዝ ወደ አደባባይ ወጥተው የተሰማቸውን ደስታ ገልጸዋል፡፡

በዘመነ ሐዲስም መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሰውን ዘር ከዲያብሎስ ቁራኝነት፣ ከሲኦል ባርነት ነጻ ለማውጣት ወደ ዙፋን መስቀሉ በተጓዘ ጊዜ ሕፃናት እና አዕሩግ ነጻ የሚወጡበት ቀን መድረሱን እግዚአብሔር አመላክቷቸው ዘንባባ በመያዝ ዘምረዋል (ሉቃ. ፳፪፥፲፰)፡፡ በዚህ ዕለት በቤተ ክርስቲያን ዘንባባ እየተባረከ ለሕዝቡ ይታደላል፡፡ እስራኤል ዘሥጋ ዘንባባ በመያዝ እግዚአብሔርን እንዳመሰገኑ እኛ እስራኤል ዘነፍስም ዘንባባ (ጸበርት) በግንባራችን በማሰር በዓሉን እናከብራለን፡፡ በዕለተ ሆሣዕና አዕሩግና ሕፃናት ‹‹ለዳዊት ልጅ መድኃኒት መባል ይገባዋል›› እያሉ ዘምረዋል፡፡

ይህ ዅሉ በአንድ ወገን የነበረው የአቀባበል ሥነ ሥርዓት ሲኾን፣ በሌላ በኩል የነበረው አቀባበል ደግሞ እጅግ የሚያሳዝን ነበር፡፡ ሥርዓተ ኦሪትን፣ ትንቢተ ነቢያትን በሚገባ እንከተላለን ይሉ የነበሩ ጸሐፍት ፈሪሳውያን ጌታችንን ‹‹ደቀ መዛሙርትህን ገሥፃቸው›› ነበር ያሉት፡፡ ጌታችንም መልሶ፡- ‹‹እነዚህ ዝም ቢሉ ድንጋዮች ይጮኻሉ›› በማለት ሕያዋን ሰዎች ብቻ ሳይኾኑ ግዑዛን ፍጥረታትም እርሱን እንደሚያመሰግኑ አስረድቷቸዋል፡፡ ቅናት አቅላቸውን ያሳታቸው ፈሪሳውያን የሕዝቡን ምስጋና ወደ ጥላቻ እንዲለወጥ በማድረጋቸው በዕለተ ሆሣዕና ዘንባባ ይዘው ይዘምሩ የነበሩ ጭምር በዕለተ ዓርብ ‹‹ይሰቀል!›› እያሉ በጌታችን ላይ ጮኸዋል፡፡

መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በአህያ ጀርባ ላይ ተቀምጦ ወደ ኢየሩሳሌም ሲገባ በነቢዩ ዘካርያስ፡- ‹‹እነሆ ንጉሥሽ ጻድቅና አዳኝ ነው፤ ትሑትም ኾኖ በአህያም፣ በአህያዪቱ ግልገል በውርንጫዪቱ ላይ ተቀምጦ ወደ አንቺ ይመጣል፤›› ተብሎ የተነገረው ትንቢት ተፈጽሟል (ዘካ. ፱፥፱፤ ማቴ. ፳፩፥፬፤ ማር. ፲፩፥፩-፲፤ ሉቃ. ፲፱፥፳፰-፵፤ ዮሐ. ፲፪፥፲፭)፡፡ ጌታችን በአህያ ጀርባ ተቀምጦ ወደ ኢየሩሳሌም መግባቱ የሰላም ንጉሥ መኾኑን ያመለክታል፡፡ እስራኤል ዘመነ ምሕረት ሲኾንላቸው አባቶቻቸው በአህያ ጀርባ ተቀምጠው ይታዩ ነበር፡፡ ጌታም እውነተኛ ሰላም ይዤላችሁ መጣሁ ሲለን በአህያ ጀርባ ወደ ቤተ መቅደስ ሕይወታችን ተጉዟል፡፡

መድኃኒታችን ክርስቶስ መላእክት በዕለተ ልደቱ ‹‹በሰማይ ለእግዚአብሔር ምስጋና ይገባዋል፤ በምድርም ሰላም ለሰዉ ዅሉ ይሁን›› እያሉ የዘመሩለት የሰላም ባለቤት ነው (ሉቃ. ፪፥፲፫)፡፡ በመዋዕለ ትምህርቱም ‹‹ሰላሜን እሰጣችኋለሁ›› ብሎ አስተምሮናል (ዮሐ. ፲፬፥፳፯)፡፡ ሰላሙን የሚሰጥበት ዕለት መቃረቡን ለማመልከት ጌታችን በአህያ ጀርባ ተቀምጦ ወደ ቤተ መቅደስ መጣ፡፡ በሌላ በኩል በአህያ ጀርባ መቀመጡ ኅቡዕ ምሥጢር አለው፡፡ በአህያ ጀርባ የተቀመጠ ሰው ሌላውን አሳድዶ አይዝም፤ እርሱም ሮጦ አያመልጥም፡፡ በዚህም ጌታችን በእምነት ለሚፈልጉት የሚገኝ፣ ለማይፈልጉት ግን የማይገኝ አምላክ መኾኑን አስተምሯል፡፡

ለታሰሩት መፈታትን ሊሰብክ ሰው የኾነው ጌታችን ከማሰሪያዋ በተፈታች አህያ እንደ ተቀመጠ ዅሉ ዛሬም ከኃጢአት እስራት በተፈታ ሕይወት አድሮ የሕሊና ሰላምን ይሰጣል፡፡ የአህያን ጀርባ ያልናቀ ጌታችን ትሑት ሰብእና እና የተሰበረ ልቡና ወዳለው ሰው ዘወትር ይጓዛል፡፡ እርሱ የተዋረደውንና የተሰበረውን ልብ አይንቅምና (መዝ. ፶፥፲፯፤ ኢሳ. ፷፮፥፪)፡፡ ስለዚህ የእግዚአብሔር ቤተሰቦች ፀሐይ ዕድሜአችን ሳትጠልቅ በእምነት እግዚአብሔርን እንፈልገው፡፡ ሰላሙን ይሰጠን ዘንድም ንስሐ ገብተን ‹‹ሆሣዕና በአርያም›› እያልን እናመስግነው፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ምንጭ፡- ሐመር ዘኦርቶዶክስ ተዋሕዶ፣ መጋቢት/ሚያዝያ ፲፱፻፺፮ ዓ.ም፡፡

ኒቆዲሞስ – የክርስቲያኖች ፊደል  

መጋቢት ፳፮ ቀን ፳፻፱ .

ጌታችን ወደዚህ ምድር መጥቶ የምሥራቹን ቃል ሲያውጅ እስራኤላውያን የተቀበሉት በተደበላለቀ ስሜት ነበር፡፡ በአንድ በኩል ለብዙ ዘመናት በባርነት ሲገዙ ስለ ነበር ከሮማውያን ቅኝ ግዛት ነጻ የሚያወጣቸው መሲሕ ይፈልጋሉ፤ በሌላ በኩል ደግሞ ለብዙ ዘመናት በባርነት ቀንበር ስለ ደከሙ ተስፋ በመቁረጥ ተዳክመው ነበር፡፡ መሲሕ ቢመጣ እንኳ ይመጣል ብለው የሚጠብቁት ጦር ይዞ፣ ሠራዊት አስከትሎ ነው ብለው ያምኑ ነበር፡፡ ስለዚህም ነው የክርስቶስን መሲሕነት ያልተቀበሉት፡፡ አብዛኛው እስራኤላዊ የክርስቶስን መሲሕነት ቢጠራጠርና ባይቀበለውም፣ በፍጹም እምነት እስከ መጨረሻው  የተከተሉትም  ነበሩ፡፡ ለዚህም  ትልቅ ማሳያ የሚኾነን ከፈሪሳውያን ወገን የኾነው ኒቆዲሞስ ነው፡፡ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ይህን  ታላቅ ሰው ለማዘከር የዐቢይን ጾም ሰባተኛ እሑድ በስሙ ሰይማ ታከብረዋለች፡፡ ተከታዮቿ ምእመናንም የእርሱን አሠረ ፍኖት እንዲከተሉ ትመክራለች፤ ታስተምራለችም፡፡

ኒቆዲሞስ ማነው?

ኒቆዲሞስ ፈሪሳዊ ነው (ዮሐ. ፫፥፩)

የእስራኤላውያን ለብዙ ዘመን በባርነት መኖር የሕዝቡን የአኗኗር ኹኔታ ቀይሮታል፡፡ በግዞት ጊዜ ከአሕዛብ የቀሰሟቸው አጉል ትምህርቶች በእምነትም በአስተሳሰብም እጅግ እንዲለያዩና እንዲራራቁ ምክንያት ኾነዋል፡፡ አይሁዳውያን፣ ሳምራውያን፤ ከአይሁዳውያንም ሰዱቃውያን፣ ጸሐፍት፣ ፈሪሳውያን፣ ወዘተ. ተብለው እንዲከፋፈሉ ከዚህም እጅግ ወርደው ገሊላዊ፣ ናዝራዊ እንዲባባሉ ያበቃቸው ከአሕዛብ ጋር የነበራቸውን ግንኙነት ፈር አለማስያዛቸው ነበር፡፡

ከአይሁድ ቡድኖች መካከል ፈሪሳውያን ሕግን በማጥበቅ ሕዝቡን የሚያስመርሩ፤ ቀሚሳቸውን በማስረዘም እነርሱ የማይፈጽሙትን ሕግ በሕዝብ ላይ የሚጭኑ፤ ራሳቸውን ከሌሎች በላይ ከፍ ከፍ የሚያደርጉ ‹‹አባታችን አብርሃም ነው›› እያሉ የሚመጻደቁ፤ የአባታቸው የአብርሃምን ሥራ ግን የማይፈጽሙ የአይሁድ ቡድን ክፍሎች ናቸው (ዮሐ. ፰፥፴፱)፡፡ ኒቆዲሞስም ራሱን ከዚህ ሕዝብ ለይቶ በፍጹም ልቡ ክርስቶስን ፍለጋ የመጣ ፈሪሳዊ ነው፡፡ ቀድሞ አባታችን አብርሃምን ‹‹ከቤተሰብህ ተለይተህ እኔ ወደማሳይህ ምድር ሒድ›› ያለው አምላክ ኒቆዲሞስን ከፈሪሳውያን ለይቶ ጠራው (ዘፍ. ፲፪)፡፡

ኒቆዲሞስ የአይሁድ አለቃ ነው (ዮሐ. ፫፥፩)

ሮማውያን ሕዝቡን የሚያስተዳድሩት ከላይ ያለውን ሥልጣን ተቆናጠው ታች ያለውን ሕዝብ ባህላቸውን በሚያውቅ፣ ቋንቋቸውን በሚጠነቅቅ አይሁዳዊ ምስለኔ ያስገዙ ነበር፡፡ አውሮፓውያንም አፍሪካን ለመቀራመት የተጠቀሙበት ስልት ይህን ዓይነት ነበር፡፡ ኒቆዲሞስ ምንም እንኳ ፈሪሳዊ ቢኾን አለቃ እንዲኾን በሮማውያን የተሾመ ባለ ሥልጣን ነው፡፡

ኒቆዲሞስ መምህረ እስራኤል ነው (ዮሐ. ፫፥፭)

ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለኒቆዲሞስ ምሥጢረ ጥምቀትን በገለጸለት ጊዜ ሲደናገር አይቶ «አንተ የእስራኤል መምህር ስትኾን ይህን አታውቅምንብሎታል፡፡ ይህ ጥያቄ የሚጠቁመን ኒቆዲሞስ አለቅነትን ከመምህርነት የያዘ፤ በአይሁዳውያን ዘንድ የታፈረና የተከበረ ሰው እንደ ነበረ ነው፡፡ መምህር ቢኾንም ‹‹የሚቀረኝ ያላወቅሁትያልጠነቀቅሁት ብዙ ነገር አለ›› በማለት የመምህርነቱን ካባ አውልቆ፣ የተማሪነትን ዳባ ለብሶ ከክርስቶስ ሊማር መጣ፡፡

ኒቆዲሞስ ምሁረ ኦሪት ነው (ዮሐ. ፫፥፯)

አንዳንዴ ሳያውቁ አወቅን ሳይማሩ እናስተምር የሚሉ ደፋር መምህራን አይጠፉም፡፡ ኒቆዲሞስ ግን ከዚህ በተለየ አለቅነትን ከመምህርነት፣ መምህርነትን ከምሁርነት አስተባብሮ የያዘ፤ ዕውቀትን ከትሕትና፣ ምሁርነትን ከመንፈሳዊነት ጋር አስማምቶ የኖረ ሰው ነበር፡፡ የኦሪት ምሁር መኾኑን የሚጠቁመን ደግሞ ከካህናት አለቆች ጋር ያደረገው ክርክር ነው፡፡

ኒቆዲሞስ ምን አደረገ?

ለምሥጢረ ጥምቀት መገለጥ ምክንያት

የአይሁድ የፋሲካ በዓል እየቀረበ ሲመጣ ጌታችን አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቀኑ እንደ ደረሰ ለሐዋርያቱ ተናግሮ ወደ ኢየሩሳሌም መጣ፡፡ እንደ ሰውነቱ ሰለቸኝ ደከመኝ ሳይል ሕዝቡን ቀንና ሌሊት በትምህርትና በተአምራት ያገለግል ነበር፡፡ በዚህ ሰዓት ነው ኒቆዲሞስ በሌሊት ገስግሶ ወደ ጌታችን የመጣው፡፡ በፊቱ ቀርቦም «መምህር ሆይ» ብሎ የእርሱን አላዋቂነት፣ የክርስቶስን ማእምረ ኅቡዓትነት (የተሰወረን አዋቂነት) መሰከረ፡፡ ጌታችንም አመጣጡ ከልብ መኾኑን አውቆ ምሥጢረ ጥምቀትን (ዳግም ልደትን) ገለጸለት፡፡ ምሥጢሩም የኦሪት ምሁር ለነበረው ኒቆዲሞስ ለጆሮ የከበደ፣ ለመቀበል የሚቸግር ኾነበት፡፡ የከበደውን የሚያቀል፣ የጠበበውን የሚያሰፋ አምላክ ምሥጢሩ ለኒቆዲሞስ  እንደ ከበደው ስላወቀ ቀለል አደረገለት፡፡ ዳግም ልደት ከእናት ማኅፀን ሳይኾን ከውኃ እና ከመንፈስ ቅዱስ እንደ ኾነ አብራራለት፡፡

 አዋቂ ነን የሚሉትን አሳፈራቸው

ወቅቱ የአይሁድ የፋሲካ በዓል የቀረበበት፤ ጻፎችና የካህናት አለቆች ጌታን ለመያዝ፣ እንደ ሙሴም ሕግም ሊያስፈርዱበት የተቻኮሉበት ጊዜ ነበር፡፡ ጌታችን የሙሴ ፈጣሪ መኾኑን አላወቁምና፡፡ የካህናት አለቆች ተሰብስበው ክርስቶስን ለመያዝ በሚመካከሩበት ጊዜ ከሙሴ መጽሐፍ ሕግ ጠቅሶ ሊቃውንተ ኦሪትን አፍ ያስያዛቸው ኒቆዲሞስ ነበር፡፡ በዚህም የተነሣ ሳይስማሙ ወደየቤታቸው እንዲበታተኑ ምክንያት የኾነ ታላቅ ሰው ነው – ኒቆዲሞስ፡፡

ጌታን ለመገነዝ በቃ (ዮሐ. ፲፱፥፴፰)

ጌታችን በቀራንዮ አደባባይ ራሱን ለዓለሙ ቤዛ አድርጎ ሲሰጥ እስከ ሞት ከአንተ አንለይህም ያሉት ደቀ መዛሙርቱ ከዮሐንስ በቀር ሲበታተኑ፣ በዘጠኝ ሰዓት ቀራንዮ ላይ የነበረው ኒቆዲሞስ ነበር፡፡ ከአርማትያሱ ዮሴፍ ጋር ኾኖ የክርስቶስን  ስጋ ከአለቆች ለምኖ የገነዘው፤ ወደ ሐዲስ መቃብር ያወረደውም ኒቆዲሞስ ነበር፡፡

ከኒቆዲሞስ ምን እንማር?

አትሕቶ ርእስ (ራስን ዝቅ ማድረግ)

ብዙዎቻችን ባለን የኑሮ፣ የዕውቀት እና የሥልጣን ደረጃ ራሳችንን ከፍ ከፍ አድርገን የመማር አቅም ያጣን፤ ቁጭ ብሎ መማር ለደረጃችን የማይመጥን የሚመስለን ስንቶቻችን እንኾን? በአንድ ወቅት አባ መቃርስ ከሕፃናት እንቆቅልሽ ለመማር ቁጭ እንዳሉ፣ በእንቆቅልሹም ልባቸው ተነክቶ እያነቡ ወደ በዐታቸው እንደ ተመለሱ እያወቅን እኛ ግን ከአባቶች የመማር አቅም አጣን፡፡ ኒቆዲሞስ ፈሪሳዊ፣ የአይሁድ አለቃ፣ መምህረ እስራኤል፣ ምሁረ ኦሪት ቢኾንም ራሱን ዝቅ አድርጎ ከጌታ እግር ሥር ቁጭ አለ፡፡ ሕዝብን ከመምራትና ከማስተማር ይልቅ ቁጭ ብሎ መማር ምንኛ መታደል ነው!

ጌታችንም በትምህርቱ «ማርያምም  መልካም ዕድልን መርጣለችከእርሷም አይወሰድባትም» ያለው ስለዚህ አይደል? (ሉቃ. ፲፥፵፪)፡፡ በቅዱስ ወንጌል ላይ በተደጋጋሚ የምናገኘው የፈሪሳውያንን ግብዝነትና የጌታችንን ተግሣፅ ነው፡፡ ትሑት የሚያሰኘው ሳያውቁ አውቃለሁ ማለት ሳይኾን፣ እያወቁ አላውቅም ማለት ነው፡፡ ሳይማሩ ተምሬያለሁ ማለት ሳይኾን ተምረውም ልክ እንደ ኒቆዲሞስ ለመማር ራስን ዝቅ ማድረግ ነው፡፡ ከፈሪሳዊው ይልቅ የቀራጩ ጸሎት ተቀባይነትን ማግኘቱም ለዚህ አንዱ ማስረጃ ነው (ሉቃ. ፲፰፥፲፩-፲፮)፡፡

 ጎደሎን ማወቅ

በአብዛኞቻችን ዘንድ የሚታየውና ክርስትናችንን፣ አገልግሎታችንን እና ቤተ ክርስትያናችንን እየተፈታተነ ያለው ችግር ጎደሎዎቻችንን አለማወቃችንና ምሉዕ እንደ ኾነን ማሰባችን ነው፡፡ ነገር ግን ምንም  እንዳልኾኑ አውቆ ራስን ለክርስቶስ እና ለቤተ ክርስቲያኑ አሳልፎ መስጠት ምንኛ መታደል ነው! ኒቆዲሞስ ያለውን ሳይኾን ያጣውን፤ የሞላለትን ሳይኾን የጎደለውን ፍለጋ ወደ ክርስቶስ መጣ፡፡ ዕውቀት ብቻውን ምሉዕ አያደርግም፡፡ አለቅነትም ቢኾን ገደብ አለው፡፡ ኒቆዲሞስ ምሁረ ኦሪት እንጅ ምሁረ ሐዲስ አይደለም፤ መምህረ እስራኤል ዘሥጋ እንጅ መምህረ እስራኤል ዘነፍስ አይደለም፡፡ የሕይወቱን ክፍተት ሊሞላ የሚችል አንድ ክርስቶስ ብቻ ነውና ኒቆዲሞስ ጉድለቱን አምኖ ጎደሎውን ሊያስሞላ ወደ ክርስቶስ መጣ፡፡ ‹‹የሚጎድለኝ ምንድን ነው?›› ብሎ እንደ ጠየቀው እንደዚያ ሰው ጎደሎን ማመን ምንኛ ታላቅ ነገር ነው!

አልዕሎ ልቡና (ልቡናንን ከፍ ማድረግ)

ኒቆዲሞስ ይዞ የመጣው ሥጋዊ ሕዋሳቱን ነበር፡፡ ጌታችን ግን አመጣጡ ለመልካም እንደ ኾነ አውቆ ለሥጋዊ ዕውቀት እጅግ የሚከብደውን ምሥጢረ ጥምቀትን ገለጸለት፡፡ መጀመሪያ ይህን ምሥጢር ለመቀበል አልተቻለውም ነበር፡፡ መድኃኔ ዓለም ክርስቶስ ምሥጢሩን ፍንትው አድርጎ ሲያብራራለት ግን ልቡናው ምሥጢሩን ለመቀበል ተዘጋጀ፡፡ ምሥጢራትን ለመቀበል ልቡናን ከፍ ከፍ ማድረግ ይገባል፡፡ የእምነታች መሠረት በሥጋ ዓይን ማየት፣ በሥጋ ጆሮ መስማት፣ በሥጋ እጅ መዳሰስ ብቻ ከኾነ እምነታችን ልክ እንደ እንቧይ ካብ ኾነ ማለት ነው፡፡ ትቂት የፈተና ነፋስ ሲነፍስበት፣ ጠቂት የመከራ ተፅዕኖ ሲደርስበት መፈራረስ፣ መናድ ይጀምራል፡፡ ኒቆዲሞስም ምሥጢሩ መጀመሪያ ቢከብደውም ቅሉ በኋላ ልቡናውን ወደ ሰማያዊው ምሥጢር ከፍ ስላደረገ ምሥጢሩን በቀላሉ ተረዳ፡፡ ቤተ ክርስቲያንን ሲፈታተኗትና እየተፈታተኗት ያሉ አካላት በሙሉ የስሕተታቸው ምንጭ እንደ ግያዝ ከአካባቢያቸውና ከምናየው አካል (ቁሳዊ ዓለም) ውጭ መመልከት አለመቻል ነው (፪ኛ ነገ. ፮፥፲፯)፡፡ ለዚህም ነው ካህኑ በሥርዓተ ቅዳሴ ጊዜ የቍርባኑ ምሥጢር እንዲገለጽልን «አልዕሉ አልባቢክሙልቦናችሁን ከፍ ከፍ አድርጉ» የሚሉን፡፡

ስምዐ ጽድቅ (የእውነት ምስክር) መኾን

ቅዱስ ጳውሎስ፡- «ለእውነት እንጅ በእውነት ላይ ምንም ማድረግ አንችልም» በማለት እንደ ተናገረው (፪ኛ ቆሮ. ፲፫፥፰)፣ ቤተ ክርስቲያን በሰማዕትነት የምትዘክራቸው ቅዱሳን በሙሉ ለእውነት ብለው ራሳቸውን ለክርስቶስ አሳልፈው የሰጡትን አባቶች እና እናቶችን ነው፡፡ በፍርኀትና በሐፍረት፣ በይሉኝታና በሐዘኔታ እውነትን አለመመስከር በክርስቶስ ፊት ያስጠይቃል እንጅ አያስመሰግንም፡፡ ኒቆዲሞስ ያለ ፍርኀትና ያለ ሐፍረት በካህናቱ ፊት እውነትን መስክሯል፡፡ ካህናቱን መጽሐፍ ጠቅሶ እውነትን ተናግሮ አሳፍሯቸዋል፡፡ እውነትንና ፀሐይን ፈርቶ የትም መድረስ አይቻልም፡፡ በመሪዎችና በታላላቅ ባለ ሥልጣናት ፊት እውነትን መመስከር ክርስትናችን የሚያስገድደን ዐቢይ ቁም ነገር ነው (ሉቃ. ፲፪፥፫-፭)፡፡

ትግሃ ሌሊት (በሌሊት ለአገልግሎት መትጋት)

እንደ ሌሊት ለመንፈሳዊ ሕሊና፣ ለተመስጦ የሚመች ጊዜ የለም፡፡ ቀን ለሥጋ ሲራወጥ የነበረ አካልና መንፈስ ሌሊቱን ለነፍስ በመገዛት ሥጋውን ማድከም አለበት፡፡ ለዚህም ነው ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ቀኑን በቅዳሴ፤ ሌሊቱን ደግሞ በማኅሌት፣ በሰዓታት፣ በኪዳን እግዚአብሔርን ስታምሰግን  የምታድረው፡፡ ‹‹ሌሊትስ ጌታን ለማመስገን የተፈጠረ ድንቅ ጊዜ ነው›› እንዳለ ቅዱስ ማር ይስሐቅ፡፡ ጌታችንም ሐዋርያቱን ‹‹ወደ ፈተና እንዳትገቡ ትጉና ጸልዩ›› ብሏቸዋል (ማቴ. ፳፮፥፵፩)፡፡ አሁንም ቤተ ክርስቲያን እንደ ኒቆዲሞስ ለኪዳን፣ ለማኅሌት፣ ለጸሎት በሌሊት የሚገሰግስ ምእመንን ትፈልጋለች፡፡

እስከ መጨረሻ መጽናት

ክርስትና ለጀመሩት ሳይኾን ለጨረሱት፤ ለወጠኑት ሳይኾን ለፈጸሙት የድል አክሊል የምትሰጥ መንገድ ናት፡፡ ስለዚህም የመሮጫ መሙ ጠበበን፤ ሩጫው ረዘመብን ብለው ከመስመሯ ለሚወጡ ዴማሶች ቦታ የላትም (፪ኛ ጢሞ. ፬፥፲)፡፡ ጌታችንን በመዋዕለ ስብከቱ ብዙ ሺሕ ሕዝብ ቢከተለውም እስከ መስቀሉ አብረውት የነበሩ ጥቂቶች ናቸው፡፡ የተወሰነው ሕዝብ ቀድሞም የተከተለው ለምግበ ሥጋ ነበርና ቀራንዮ ላይ አልተገኘም፡፡ ቀራንዮ ላይ ምግበ ነፍስ እንጅ ምግበ ሥጋ የለምና፡፡ ሌሎችም አይሁድን ከመፍራታቸው የተነሣ ከመስቀሉ ሥር አልተገኙም፡፡ ኒቆዲሞስ ግን ክርስቶስ በፈቃዱ ነፍሱን ከሥጋው በለየበት ሰዓት ከአርማትያሱ ዮሴፍ ጋር ኾኖ የክርስቶስን ክቡር ሥጋ ከመስቀል አውርዶ፣ ገነዞ በሐዲስ መቃብር ለመቅበር ታድሏል፡፡

በዚህ የመከራ ሰዓት ከዮሐንስና ከእናቱ ከቅድስት ድንግል ማርያም ውጭ ማንም በሥፍራው አልነበረም፡፡ በመጨረሻው ሰዓት ከመስቀሉ ሥር የተገኙት የቁርጥ ቀን ልጆች ዮሴፍና ኒቆዲሞስ ናቸው፡፡ ይህም ኒቆዲሞስ ፈተናውን ዅሉ ተቋቁሞ እስከ መጨረሻው ለመጽናቱ ምስክር ነው፡፡ በክርስትና ሕይወታችን በምቹ ጊዜ የምናገለግል፣ ፈተና ሲመጣ ግን ጨርቃችን (አገልግሎታችንን) ጥለን የምንሮጥ፣ ሰበብ አስባብ ፈልገን የምናፈገፍግ ብዙዎች ነን (ማር. ፲፬፥፲፭)፡፡ ዕውቀት፣ ሀብት እና ጊዜ ጣኦት ኾኖበት ከመሃል መንገድ የቀረውን፤ ሩጫውን ያቋረጠውን፤ ከቤተ ክርስቲያ አገልግሎት የራቀውን ክርስቲያን ቈጥረን አንጨርሰውም፡፡ ጌታችን በትምህርቱ «ወዘአዝለፈ ትዕግሥቶ ውእቱ ይድኅን፤ እስከ መጨረሻው የሚጸና እርሱ ይድናል» (ማቴ.፳፬፥፲፫) በማለት የድኅነት ተስፋ ሰጥቶናልና ዅላችንም እንደ ኒቆዲሞስ እስከ መጨረሻው በሃይማኖታችን ልንጸና ይገባናል፡፡

በአጠቃላይ ከኒቆዲሞስ ሕይወት ብዙ ቁም ነገሮችን እንማራለን፡፡ የኒቆዲሞስ በሌሊት ገስግሶ መምጣት ለምሥጢረ ጥምቀት ትምህርት መገለጥ ምክንያት እንደ ኾነ ዅሉ፣ ዛሬም በቤተ ክርስቲያን ተገኝተን በቅዳሴው፣ በኪዳኑ፣ በሰዓታቱ፣ በማኅሌቱ ብንሳተፍ ረቂቅ የኾነው ሰማያዊ ምሥጢር ፍንትው ብሎ ይገለጥልናል፡፡ እንደ ኒቆዲሞስ ራሳችንን ዝቅ አድርገን በምሥጢራት በመሳተፍ ለታላቅ ክብር እንበቃ ዘንድ የአምላካችን የልዑል እግዚአብሔር መልካም ፈቃዱ ይኹንልን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ከውኃና ከመንፈስ ያልተወለደ የእግዚአብሔርን መንግሥት አያይም

በአያሌው ዘኢየሱስ

መጋቢት ፳፮ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

‹‹እውነት እውነት እልሃለሁ፤ ሰው ዳግመኛ ከውኃና ከመንፈስ ካልተወለደ የእግዚአብሔርን መንግሥት አያይም፤›› (ዮሐ.፫፥፫)፡፡

ይህ ቃል ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለኒቆዲሞስ ካስተማረው ትምህርት የተወሰደ ኃይለ ቃል ነው፡፡ ኒቆዲሞስ ብዙ የተማረ፤ ብዙ ያወቀ የሃይማኖት ሊቅ ነው፡፡ ከዚህም የተነሣ ሊቅ፣ ምሁር፣ አለቃ ተብሎ ተጠርቶአል፡፡ በጊዜው ከነበሩ ሰዎች ከፍ ያለና የላቀ ዕውቀት የነበረው ሰው ነበር፡፡ በሌሊት ወደ ጌታ እየመጣ ይማር ነበር፡፡ የማታ ተማሪ ነበር፡፡ ቀን፣ ቀን የምኵራብ አስተማሪ ኾኖ ብዙ ሰዎችን ያስተምር ስለ ነበረና እርሱ የሚያስተምራቸው አይሁድ ጌታችንን ስላልተቀበሉ በቀን ለመማር አመቺ ጊዜ አልነበረውም፡፡

በአይሁድ ሕግ ጌታን የሚከተልና የሚቀበል ሰው ከምኵራብ ይባረር ስለ ነበረ እነርሱን ላላማስቀየም ኒቆዲሞስ ማታ፣ ማታ ነበር የሚማረው፡፡ ኒቆዲሞስ፡- ‹‹ከሰው ችሎታ በላይ የኾኑ ተአምራትን ስለምትሠራ እኛን ለማስተማርና ለመምከር ከእግዚአብሔር ዘንድ ተልከህ የመጣህ ነህ›› ብሎ ለጌታችን መስክሮለታል፡፡ ጌታችንም፡- ‹‹እናንተን ለማስተማር እንደ መጣሁ ከተረዳህ ሰው ዳግመኛ ከውኃና ከመንፈስ ካልተወለደ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት አይገባም›› አለው፡፡

ኒቆዲሞስ ስላልገባው ‹‹እኔ አርጅቼአለሁ፤ እንዴት ነው ወደ እናቴ ማኅፀን ተመልሼ የምገባውና ዳግም የምወለደው?›› ብሎ ኢየሱስ ክርስቶስን ጠየቀው፡፡ ጌታችንም፡- ‹‹ሰው ከሰው ከተወለደ ሥጋዊ ነው፤ የሰው ልጅ ነው፡፡ የእግዚአብሔር ልጅ ለመኾን በመንፈስ መወለድ አለበት፡፡ ከእግዚአብሔር መወለድ ነፋስ ከየት ተነሥቶ ወዴት እንደሚነፍስ እንደማይታወቅ ያለ ረቂቅ ምሥጢር ነው›› አለው፡፡ አሁንም ያ ሊቅ፤ ያ አዋቂ ‹‹አልገባኝም›› አለ፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስም፡- ‹‹አንተ የእስራኤል መምህር እና ሊቅ ኾነህ እንዴት ይህን አታውቅም?›› አለው፡፡ ከሰማይ ከወረደው በቀር ወደ ሰማይ የሚወጣ የለም፤ የምናውቀውንም እንናገራለን ካለው በኋላ ጥያቄውን በዚህ ገታ፡፡

ኒቆዲሞስ  ወደ ጌታችን ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ መጥቶ መማሩ የሚያስመሰግነው ተግባር ነው፡፡ አይሁድ ወገኖቹ ጌታን ሳይከተሉት እርሱ ግን ጌታን መውደዱ የሚያስደንቅ ነው፡፡ ኒቆዲሞስ የሚያመሸው ከጌታ ጋር ነበር፡፡ ባለችው ትርፍ ጊዜው ዅሉ ወደ ፈጣሪው ይሔድ ነበር፡፡ ይህ ታላቅ ዕድል ነው፡፡ ቀን ሲያስተምርና ሲደክም ስለሚውል ማታ፣ ማታ ማረፍ ይገባው ነበር፡፡ ኒቆዲሞስ ግን ቤቴ ገብቼ ልረፍ አላለም፡፡ ባለ ሥልጣንና ባለጠጋ ስለ ነበር ደጅ የሚጠናው ሕዝብና መሰል ባልንጀሮቹ ይፈልጉት ነበር፡፡ ይኹን እንጂ ከእነርሱ ጋር አላመሸም፡፡

ከዚህ አባት ታላቅ ትምህርት ልንማር ያስፈልጋል፡፡ እኛ ዛሬ የምናመሸው የት ነው? የምናመሸውስ ከማን ጋር ነው? ምን ስናደርግ ነው የምናመሸው? ኒቆዲሞስ ቤቱ አልነበረም የሚያመሸው፤  ከእውነተኛው መምህር ጋር እንጂ፡፡ ኒቆዲሞስ ጽድቁንና በረከቱን እየያዘ ነበር ወደ ቤቱ ይገባ የነበረው፡፡ እኛ ወደ ቤታችን የምንገባው እየከበርን ነው ወይ? ጸድቀን ነው የምንገባው ወይስ ጐስቁለን?

የዛሬ ዘመን ሰው እየሰከረ፣ እየጨፈረ፣ እየደማ፣ እየቆሰለ አእምሮውን ስቶ ነው ወደ ቤቱ የሚመለሰው፡፡ የሚሞትም አለ፡፡ በቤት ያሉት ወገኖቹም ‹‹እንቅፋት ያገኘው ይኾን? ይሞት ይኾን?›› እያሉ እየተሳቀቁ ነው የሚያመሹት፡፡ ማምሸት እንደ ኒቆዲሞስ ከጌታ ጋር ነው እንጂ! ኒቆዲሞስ ከጌታ ጋር በማምሸቱ ፈጣሪውን አወቀ፡፡ ጌታን ማወቅ ብቻ ደግሞ አይበቃም፡፡ ማወቅማ አጋንንትም ያውቁታል፡፡ ከመንፈስ መወለድ ያስፈልጋል፡፡

የሰው ልጅ ዕፀ በለስን በበላ ጊዜ የእግዚአብሔር ልጅነቱን ተነጥቆ ነበር፡፡ ጌታችን መጥቶ ዳግም ሰው እስከሚያደርገን ድረስ የሰይጣን ልጆች ኾነን ነበር፡፡ ከዚያም በዐርባና በሰማንያ ቀን ከአብራከ መንፈስ ቅዱስና ከማኅፀነ ዮርዳኖስ ተወልደናል፡፡ እግዚአብሔርን አባታችን የምንለውም ስለዚህ ነው፡፡ ከእርሱ ከተወለድንና ልጅነትን ካገኘን፣ እንደ ገና ልጅነታችንን እንዳናጣ አክብረን እንያዘው፡፡ መጀመሪያም አላወቅንበትም ነበር፡፡ አዳም ከገነት የሚወጣ አልመሰለውም ነበር፡፡ ሰይጣን አታሎታል፡፡ እኛም እንደ ገና እንዳንታለል ልጅነታችን እንዳይሰረዝ እንጠንቀቅ፡፡

የብዙዎቻችን ልጅነት ዛሬ እየተወሰደ ነው፡፡ ልጅነታችንን እያስነጠቅነው ነው፡፡ እነኤሳው እየነጠቁን ነው፡፡ ብዙዎች እንደ ያዕቆብ ልጅነታችንን ሊወስዱብን አሰፍስፈዋል፡፡ ሰይጣን እንደ አዳም ሊነጥቀን አሰፍስፏል፡፡ ኒቆዲሞስ አርጅቶ ነበር፡፡ በጥምቀትና በንስሐ ግን አዲስ ሕይወትን አግኝቶአል፤ ታድሷል፡፡ ያረጀው ሕይወቱ ለምልሟል፡፡ እኛም ዛሬ በጣም አርጅተናል፡፡ ያረጀው ሰውነታችንን በሥጋውና በደሙ በንስሐ እናድሰው፡፡ ይህ ከኾነ ነው የእግዚአብሔርን መንግሥት የምንወርሰው፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

  • ብፁዕ አቡነ መልከ ጼዴቅ የከምባታ፣ ሀድያ፣ ጉራጌና ሥልጤ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፤ በአዲስ አበባ የደብረ ብሥራት ቅዱስ ገብርኤል ደብር የበላይ ሓላፊ፤ በዚሁ ደብር በአስተዳዳሪነት ባገለገሉባቸው ዓመታት ካስተማሩት ትምህርተ ወንጌል የተወሰደ (መጋቢት ፳፩ ቀን ፲፱፻፹፭ .ም)፡፡

ኒቆዲሞስ

በመምህር ሳሙኤል ተስፋዬ

መጋቢት ፳፫ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

‹‹ጾምን ቀድሱ፤ ጉባኤውንም ዐውጁ፡፡ ሽማግሌዎችንና በምድር የሚኖሩትን ዅሉ ወደ አምላካችሁ ወደ እግዚአብሔር ሰብስቡ፤ ወደ እግዚአብሔርም ጩኹ፡፡ በጽዮን መለከት ንፉጾምንም ቀድሱ፤›› በማለት የዐዋጅ አጽዋማትን እንድንጾም እግዚአብሔር አምላካችን በነቢዩ ኢዩኤል ላይ አድሮ ነግሮናል (ኢዩ. ፩፥፲፬፤ ፪፥፲፭)፡፡ ከእነዚህ አጽዋማት መካከልም ዐቢይ ጾም አንዱ ነው፡፡

ይህ ጾም የጠፋውን የሰውን ልጅ ለመፈለግ፣ የሞተውን አዳምን ለማስነሣት ሰው ኾኖ ወደዚህ ዓለም የመጣው፣ ወልደ አብ ወልደ ማርያም ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመብል የተጀመረውን የሞት መንገድ ለማጥፋት ሲል የጾመው ጾም ነው፡፡ እኛም አባቶቻችን በሠሩልን ሥርዓት መሠረት በዐቢይ ጾም ወራት ‹ዘወረደ› ብለን ጀምረን በዓለ ትንሣኤን እስከምናከብርበት ዕለት ድረስ ያሉትን ሰንበታት በልዩ ልዩ ስያሜ በመጥራት የተከፈለልንን ዋጋ እያሰብን ቃለ እግዚአብሔር እንማራለን፤ እንዘምራለን፤ እንጸልያለን፡፡ ከእነዚህ ሰንበታት መካከል በሰባተኛው ሳምንት የሚገኘው ወቅት ‹ኒቆዲሞስ› ይባላል፡፡

ኒቆዲሞስ ከፈሪሳውያን ወገን የአይሁድ አለቃ የነበረው ሰው ነው፡፡ የአይሁድ አለቆች አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስን ‹‹ምልክት አሳየን›› እያሉ ይፈታተኑት ነበር፡፡ ጌታችን ስለ ሞቱና ትንሣኤው በምሳሌ እያስረዳ ቢያስተምራቸውም እነርሱ ግን አልገባቸውም ነበር፡፡ ከዚህም አልፎ ጌታችን በተአምራቱ የታመሙትን ሲፈውስ ‹‹ሕጋችን ተሻረ›› ይሉ ነበር፡፡ በዚህ ዅሉ ተአምራትና ትምህርት የአይሁድ አለቆች ክርስቶስን ለመክሰስ በሚፈልጉበት ወቅት ከአይሁድ አለቆች አንዱ ኒቆዲሞስ በቀን እንዳያደርገው አይሁድን ቢፈራ፣ አንድም ጊዜ ባያደርሰው እንደ ባልንጀሮቹ ክርስቶስን ሳይቃወም በሌሊት ወደ ጌታችን ዘንድ እየሔደ ወንጌልን ይማር ነበር፡፡

አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ በነፍስ የታመሙትን በቃሉ፣ በሥጋ የታመሙትን በተአምራቱ ሲፈውስ ኒቆዲሞስ ሰምቶ፣ ተመልክቶ በመምህርነቱ ሳይኮራ አለቅነቱን መመኪያ ሳያደርግ በልቦናው የተሳለውን እውነትን የመፈለግ ስሜት አንግቦ ከጌታው፣ ከመምህሩ ከክርስቶስ ዘንድ በሌሊት ይገሰግስ ነበር (ዮሐ. ፫፥፩)፡፡ ምስክርነቱንም እንዲህ ሲል መስጠት ጀመረ፤ ‹‹መምህር ልታስተምር ከእግዚአብሔር ዘንድ እንደ መጣህ እናውቃለን፡፡ እግዚአብሔር ከእርሱ ጋር ከኾነ በቀር አንተ የምታደርገውን ተአምራት ሊያደርግ የሚችል የለምና፤›› (ዮሐ. ፱፥፳፬፤ ሐዋ. ፲፥፴፰)፡፡

ይህን ምስክርነቱን በሚሰጥበት ጊዜም ጎዶሎን የሚሞላ፤ አላዋቂነት በአዋቂነት የሚለውጥ፤ ከምድራዊ ዕውቀት ወደ ሰማያዊው ምሥጢር የሚያሸጋግር አምላክ ‹‹ዳግመኛ ያልተወለደ የእግዚአብሔርን መንግሥት ለማየት አይችልም፤›› በማለት የአይሁድ መምህር ለኾነው ኒቆዲሞስ ቢያስተምረው ምሥጢሩ አልተገለጠለትም ነበርና ‹‹ሰው ከሸመገለ በኋላ ዳግመኛ መወለድ እንደምን ይቻላል? ዳግመኛ ይወለድ ዘንድ ወደ እናቱ ማኅፀን ተመልሶ መግባት ይችላልን?›› በማለት ጥያቄ አቅርቧል (ዮሐ. ፫፥፮፤ ፩ኛጴጥ. ፩፥፳፫)፡፡ ‹‹እውነት እውነት እልሃለሁ፤ ዳግመኛ ከውኃና ከመንፈስ ቅዱስ ያልተወለደ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ሊገባ አይችልም፡፡ ከሥጋ የተወለደ ሥጋ ነው፡፡ ከመንፈስም የተወለደ መንፈስ ነውና፤›› (ኤፌ. ፭፥፳፮) በማለት አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለኒቆዲሞስ ቢያስረዳውም ምሥጢሩ ከአቅሙ በላይ ስለ ኾነበት እንደምን ይቻላል? በማለት ጠይቋል፡፡

አበ ብዙኃን አብርሃም ከአምላኩ ሞገስን አግኝቶ የሰዶምና ገሞራ ጥፋት እንዳይደርስ ለመማለድ ከእግዚአብሔር ጋር ሲነጋገር እንደ ነበረ፤ ኒቆዲሞስም አላዋቂነቱን አምኖ ያልገባውን ምሥጢር ከአምላኩ በጠየቀ ጊዜ ኢየሱስ ክርስቶስም፡- ‹‹አንተ የእስራኤል መምህራቸው ኾነህ ሳለ ይህን ነገር አታውቅምን? በምድር ያለውን ስንነግራችሁ ካላመናችሁ በሰማይ ያለውን ብንነግራችሁ እንደምን ታምናላችሁ? ከሰማይ ከወረደው ከሰው ልጅ በቀር ወደ ሰማይ የወጣ የለምሙሴምድረ በዳ እባቡን እንደ ሰቀለ የሰው ልጅ እንዲሁ ይሰቀላል፡፡ ያመነበት ዅሉ ለዘለዓለም ሕያው እንዲኖር እንጂ እንዲጠፋ አይደለም ...፤›› እያለ ሰው በመብል ምክንያት የአምላኩን ትእዛዝ አፍርሶ ከእግዚአብሔር ቢለይም የሰው ልጅ ያጣውን ልጅነት ለመመለስ፣ ስመ ክርስትናን፣ ሀብተ ወልድን ለመስጠት ጌታችን መምጣቱን አስረዳው (ዮሐ. ፫፥፲፬)፡፡ ይህን የክርስቶስን የማዳን ሥራና በሥጋ መገለጥም ‹‹ሐወጽከኒ ሌሊተ ወፈተንኮ ለልብየ አመከርከኒ ወኢተረከ ዐመፃ በላዕሌየ ከመ ኢይንብብ አፉየ ግብረ እጓለ እመሕያው፤ ልቤን ፈተንኸው፡፡ በሌሊትም ጐበኘኸኝ፤ ፈተንከኝም፡፡ ምንም አላገኘህብኝም፡፡ የሰውን ሥራ አፌ እንዳይናገር ፈቃዴ ነው፤›› (መዝ. ፲፮፥፫) በማለት ቅዱስ ዳዊት ከኒቆዲሞስ ሕይወት ጋር በማዛመድ አመሥጥሮታል፡፡

በሌሊት ከአምላኩ ተምሮ ምሥጢሩ የተገለጸለት ኒቆዲሞስ ቀድሞ በአደባባይ ሔዶ መማርን ይፈራ እንዳልነበረ ምሥጢሩ ሲገለጽለት ግን አይሁድ ጌታችንን በሰቀሉት ዕለት ፍርኃት ርቆለት ከአርማትያሱ ዮሴፍ ጋር ቅዱስ ሥጋውን ገንዞ ለመቅበር በቃ፡፡ ‹‹ወአልቦ ፍርኃት ውስተ ተፋቅሮትነ፤ ፍጹም ፍቅር ፍርኃትን አውጥቶ ይጥላል›› ተብሎ እንደ ተጻፈ (ማቴ. ፳፯፥፶፰፤ ፩ኛዮሐ. ፬፥፲፰)፡፡ ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ‹‹ያመነየተጠመቀ ይድናል፡፡ ያላመነ፣ ያልተጠመቀ ግን ይፈረድበታል›› (ማር. ፲፮፥፮) በማለት በሰጠን ቃል ኪዳን መሠረት በአምላክነቱ አምነን የመንግሥቱ ወራሾች እንኾን ዘንድ ለኒቆዲሞስ ምሥጢሩን እንደ ገለጸ ለእኛም ይግለጽልን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ክርስቲያናዊ ምግባርን ከገብር ኄር እንማር

በዲያቆን አባተ አሰፋ

መጋቢት ፲፰ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

ታላቁን የጌታችንን ጾም ከጀመርን ስድስተኛው ሳምንት ላይ ደርሰናል፡፡ ይህን ሳምንት ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ‹ገብር ኄር› የሚል ስያሜ ሰጥታዋለች፡፡ ትርጕሙም ‹በጎ አገልጋይ› ማለት ሲኾን የስያሜውን መነሻ የምናገኘው በዕለቱ ሥርዓተ ቅዳሴ ከሚነበበው የወንጌል ክፍል ነው (ማቴ.፳፭፥፲፬-፴)፡፡

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በምሳሌ መስሎ ካስተማራቸው ትምህርቶች መካከል አንዱ የኾነው ይህ የወንጌል ክፍል በርካታ መልእክትታን በውስጡ ይዟል፡፡ በቤተ ክርስቲያን በልዩ ልዩ ሓላፊነት ላይ የሚገኙ ሰዎች ትኩረት ሰጡባቸው የሚገቡ ነጥቦችን ይጠቁማል፡፡ ይህን ለመረዳት ያመቸን ዘንድ ከታሪኩ የመጀመርያ ክፍል በመነሣት ዋና ዋና ነጥቦችን መመርመር ጠቃሚ ነው፤

በዚህ ምሳሌያዊው ታሪክ አንድ ጌታ አገልጋዮቹን ጠርቶ ለእያንዳንዳቸው እንደ ችሎታቸው መጠን ለአንዱ አምስት ለአንዱ ሁለት እንዲሁም ለሌላኛው አንድ መክሊት ነግደው ያተርፉበት ዘንድ እንደ ሰጣቸው ተጠቅሷል፡፡ ከታሪኩ እንደምንረዳው የአገልጋዮቹ ጌታ ለመንገድ ቢዘጋጅም ሀብቱ ግን በተዘጋ ቤት ውስጥ ተቆልፎበት እንዲቀመጥ አልፈለገም፡፡ እንዲያተርፉበት ገንዘቡን ለአገልጋዮቹ ሰጥቷቸዋል፡፡ ሰውዬው ማትረፍ በመፈለጉ ብቻም ገንዘቡን ያለ አግባብ አልበተነም፡፡ ለእርሱ ቀረቤታ የነበራቸውን አገልጋዮቹን ጠርቶ እንደየችሎታቸው መጠን እንዲሠሩበት አከፋፈላቸው እንጂ፡፡

ይህ ጌታ ቅንነትና ርኅራኄ የበዛለት እንደ ኾነ የሚያመላክተን ነገር አለ፡፡ ይኸውም ለአገልጋዮቹ ሓላፊነትን ቢሰጥም እንኳን ከእነርሱ ጋር በነበረው ቀረቤታ ማን ምን መሥራት ይችላል የሚለውን ከግምት ውስጥ በማስገባት ለእያንዳንዳቸው እንደ ሓላፊነት የመሸከም አቅማቸው አምስት፣ ሁለት፣ አንድ እያደረገ መስጠቱ ነው፡፡ የዚህ ጌታ መክሊት አሰጣጥ አድልዎ ያለበት ሊመስለን ይችላል፡፡ ታሪኩን እስከ መጨረሻው ብንከታተለው ግን የባለ መክሊቱን ቅንነት እናስተውላለን፡፡

ይህ ጌታ ለአገልጋዮቹ አትርፉበት ብሎ መክሊቱን ሰጥቷቸው በሔደበት አገር አልቀረም፡፡ ይልቁንም እያንዳንዱ በተሰጣቸው መክሊት ምን እንደ ሠሩበት ሊቆጣጠራቸው ተመልሷል፡፡ ስለዚህ አገልጋዮቹ በሰጣቸው መክሊት ምን እንደ ሠሩ እንደሚጠይቃቸው እያወቀ ከአቅማቸው በላይ የኾነ መክሊትን በመስጠት እንዲጨነቁ አልፈለገም፡፡ በተቃራኒው የምናስተውለው ከአእምሯቸው በላይ ሳይኾን ባላቸው ኃይል ተጠቅመው መሥራትና ማትረፍ የሚችሉትን ያህል መክሊት እንደ ሰጣቸው ነው፡፡

ከብዙ ጊዜም በኋላ የእነዚያ አገልጋዮች ጌታ ሊቆጣጠራቸው ሲመጣ አምስት መክሊት ተቀብሎ የነበረው ሌላ አምስት፣ እንደዚሁም ሁለት መክሊት ተቀብሎ የነበረው ሌላ ሁለት መክሊት አትርፈው ከጌታቸው ፊት እንደ ቆሙ፤ ያ ጌታም በእነዚህ አገልጋዮቹ ታማኝነት ተደስቶ ወደ ደስታ ቦታ እንዳስገባቸው እናያለን፡፡ በተቃራኒው ደግሞ ያ አንድ መክሊት ተቀብሎ የነበረው አገልጋይ ያተርፍባት ዘንድ የተሰጠችውን መክሊት ምድርን ቆፍሮ እንደ ቀበረ፤ ከዚህም አልፎ ‹‹ምን አደረግህባት?›› ተብሎ ሲጠየቅ የዐመፅ ንግግር እንደ ተናገረ፤ በዚህ ያዘነው ጌታውም ያን ክፉ አገልጋይ እንዲቀጣ እንዳደረገው እንረዳለን፡፡ በዚህኛው ክፍል ከተጠቀሰው ታሪክ ሦስቱን አካላት ማለት የመክሊቱን ሰጪ ጌታ፣ በጎ የተባሉ አገልጋዮችን፣ ክፉ እና ሰነፍ የተባለውን አገልጋይ በተናጠል እንመልከታቸው፤

የአገልጋዮቹ ጌታ

ይህ ሰው ለገንዘቡ ጠንቃቃ ከመኾኑ ባሻገር በአገልጋዮቹ ላይ ሙሉ ሥልጣን አለው፡፡ ባለ መታዘዙ ምክንያት በክፉው አገልጋይ ላይ የፈረደበትን ፍርድ (ልቅሶና ጥርስ ማፋጨት ወዳለበት፣ በውጪ ወዳለ ጨለማ አውጡት የሚለው) የጌታው ሙሉ ሥልጣን ያሳያል፡፡ ይህ ጌታ ፍርዱ በእውነት ላይ የተመረኮዘ መኾኑንም በተሰጣቸው መክሊት ላተረፉት ሁለቱ አገልጋዮቹ ከሰጣቸውን ክብር መረዳት ይቻላል፡፡

በጎ እና ታማኝ አገልጋዮች

በአገልጋዮቹ ጌታ በጎ አገልጋዮች የተባሉት አምስት መክሊት የተቀበለውና ሁለት መክሊት የተቀበለው ናቸው፡፡ እነዚህ አገልጋዮች በጎ ለመባል ያበቃቸው አስቀድመው ብዙ ቍጥር ያለው መክሊት በመቀበላቸው አይደለም፡፡ ጉዳዩ የመክሊቱ ብዛት ሳይኾን በተሰጣቸው መክሊት መጠን የሚገባቸውን ያህል ደክመው ማትረፍ መቻላቸው ነው፡፡

ክፉና ሰነፍ አገልጋይ

አንድ መክሊት የተቀበለውን አገልጋይ ከሁለቱ አገልጋዮች ያሳነሰውም ከአንድ በላይ መክሊት አለመቀበሉ ሳይኾን በዚያችው በአንዷ መክሊት እንኳን መሥራት አለመቻሉ ነው፡፡ በአጠቃላይ ይህ አገልጋይ ሦስት መሠረታዊ ስሕተት ፈጽሟል፤

የጌታውን ትእዛዝ በቸልተኝነት መመልከቱ የመጀመርያው ስሕተቱ ነው፡፡ ጌታው ለእያንዳንዳቸው እንደ ችሎታቸው ገንዘቡን ሲሰጣቸው አትርፈው እንዲቆዩት ነው፡፡ እንደ አቅማቸው መስጠቱም አቅማቸው በሚፈቅደው የሥራ ደረጃ እንዲሰማሩ በማሰብ ነበር፡፡ ይህ ሰነፍ አገልጋይ ግን ያደረገው ከታዘዘበት ዓላማ በተቃራኒው መልኩ ነው፡፡ ሊሠራበት የሚገባውን መክሊት ቀበረው፡፡ ይህም ለጌታው ትእዛዝ ያለውን ቸልተኝነት ያሳያል፡፡

ሁለተኛው ስሕተቱ ጌታው መክሊቱን በተቆጣጠረው ጊዜ የዐመፅ ቃል መናገሩ ነው፡፡ ጌታው ከሔደበት ቦታ ተመልሶ በተሰጠው መክሊት ምን እንዳደረገ ይህን አገልጋይ ሲጠይቀው፡- «አንተ ካልዘራህበት የምታጭድ፣ ካልበተንህበትም የምትሰበሰብ ጨካኝ ሰው እንደንህ አውቃለሁ፡፡ ስለ ፈራሁም ሔድሁና መክሊትህን በምድር ውስጥ ቀበርሁ፤» ሲል ነበር የመለሰለት፡፡ ይህ ምላሽ ከዐመፃ ባሻገር የሐሰት ቃልም አለበት፡፡ ምክንያቱም እርሱ እንዳለው ጌታው ካልዘራበት የሚያጭድ ካልበተነበት የሚሰበሰብ ጨካኝ ሰው ቢኾን ኖሮ ምንም መክሊት ሳይሰጠው ከነትርፉ ሁለት መክሊቶችን ይጠይቀው ነበር፡፡ ነገር ግን ተጽፎ የምናነበው ትርፉን ከመጠየቅ በፊት አንድ መክሊት ሰጥቶት እንደ ነበረ ነው፡፡ ይህ ማለት ደግሞ አስቀድሞ ገንዘቡን ዘርቶ ነበር ማለት ነው፡፡ ስለዚህ ይህ ጌታ ዘርቷልና ማጨድ ይገባዋል፤ በትኗልና መሰብሰብም መብቱ ነው፡፡

ሦስተኛው ስሕተቱ ደግሞ ዕድሉን ለሌሎች አለመስጠቱ ሲኾን፣ ይህ አገልጋይ በተሰጠው መክሊት ነግዶ ማትረፍ ቢሳነው እንኳን ዕድሉን ለሌሎች መስጠት ሲገባው መክሊቱን ቆፍሮ ቀብሮታል፡፡ ይህ ሰው የተሰጠው መክሊት በትርፍ ሊመለስ እንደሚገባው ጠንቅቆ ያውቃል፡፡ ምክንያቱም ገና ሲቀበል ከጌታው የተቀበለው ትእዛዝ ነውና፡፡ ስለዚህ እርሱ መውጣት መውረዱ ቢከብደውም ወጥተው ወርደው ማትረፍ ለሚችሉ ሰዎች አለመስጠቱ ተጨማሪ ጥፋቱ ነው፡፡ ይህን እንዳያደርግ ያሰረው ደግሞ በውስጡ የተቀረፀው የዐመፅ መንፈስ ለመኾኑ ለጌታው የሰጠው ረብ የሌለው ምላሽ ማስረጃችን ነው፡፡

የአገልጋዮቹ ጌታ የእግዚአብሔር ምሳሌ እንደ ኾነ፤ ሦስቱ አገልጋዮች ደግሞ በተለያየ ደረጃ ያሉ ምእመናንን እንደሚወክሉ የቤተ ክርስቲያን መተርጕማን ያስተምራሉ፡፡ ከተጠቀሰው ታሪክ ከምንማራቸው ቁም ነገሮች መካከልም ሁለቱን እንመልከታለን፤

ለእያንዳንዳችን ከእግዚአብሔር የተሰጠን ጸጋ እንዳለ እንረዳበታለን

እግዚአብሔር አምላካችን እያንዳንዳችን በሃይማኖታችን ፍሬ እንድናፈራ ይፈልጋል፡፡ ፍሬ ማፍራት የምንችልበትን ኃይልና ጸጋ ደግሞ እርሱ ይሰጠናል፡፡ ከእግዚአብሔር ዘንድ የተቀበልናቸው ስጦታዎች በቍጥር እጅግ ብዙ ቢኾኑም በዓይነታቸው ግን በሁለት መክፈል እንችላለን፡፡ የመጀመሪያው እያንዳንዱ ክርስቲያን ዳግመኛ በመወለድ ምሥጢር ያገኘው የእግዚአብሔር ልጅነት ጸጋና ከልጅነት ጋር በተያያዘ የሚሰጠን ስጦታ ነው (ዮሐ.፫፥፫)፡፡ ሁለተኛው ደግሞ እንደ እግዚአብሔር ፈቃድና እንደየአቅማችን ለመንፈሳዊ አገልግሎታችን ማስፈጸሚያ ይኾነን ዘንድ የሚሰጠን ስጦታ ነው፡፡ ለምሳሌ ትንቢት መናገር፣ በልዩ ልዩ ልሳናት መናገር፣ አጋንንትን ማስወጣት፣ ወዘተ. የመሳሰሉት ጸጋዎች (ስጦታዎች) ከዚህኛው ዓይነት ስጦታ የሚመደቡ ናቸው (፩ኛቆሮ.፲፪፥፬)፡፡

በመጀመሪያውም ይኹን በሁለተኛው ዓይነት ስጦታ በእኛ በተቀባዮች ዘንድ ብዙ የሚያሳዝኑ ችግሮች አሉ፡፡ ዳግመኛ በመወለድ ምሥጢር (በጥምቀት የሥላሴን ልጅ መኾን) ስላገኘው የልጅነት ጸጋ የሚያስብና በዚህም የሚደሰት ክርስቲያን ማግኘት አዳጋች ነው፡፡ ለዓመት በዓላት (ለመስቀል ደመራ፣ ለጥምቀት፣ ለፋሲካ፣ ወዘተ) ካልኾነ በስተቀር ክርስትናችን ትዝ የማይለን ክርስቲያኖች ጥቂቶች አይደለንም፡፡ እንደዚሁም ዘመዶቻችን ወይም ራሳችን ከዚህ ዓለም በሞት ስንለይ ካልኾነ በስተቀር በሕይወት ዘመናችን ወደ ቤተ ክርስቲያን ደጅ የማንደርስ ብዙዎች ነን፡፡ እግዚአብሔር ለእኛ የልጅነትን ጸጋ በመስጠቱ ለእኛ ያለውን ጥልቅ ፍቅሩን አሳይቶናል፡፡ ምክንያቱም ልጅነታችን ዋጋ ተከፍሎበታልና፡፡ እንዲሁ በቀላሉ አይደለም ልጆች የተባልነው፡፡

እኛ ልጅነትን እንድንቀበል አምላክ መከራን ተቀብሏል፡፡ የጥምቀታችን ውኃ የፈሰሰውም በጦር ከተወጋው ከጌታች ጎን ነው (ዮሐ.፲፱፥፳፬)፡፡ ወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስ ይኼንን ዅሉ ምሥጢር ሲያመለክት ‹‹የእግዚአብሔር ልጆች ተብለን ልንጠራ አብ እንዴት ያለውን ፍቅር እንደ ሰጠን እዩ፤›› በማለት ያደንቃል (፩ኛ ዮሐ.፫፥፩)፡፡ እኛ ልጆቹ እንኾን ዘንድ እግዚአብሔር ካሳየን የአባትነት ፍቅሩ ባሻገር ልጆቹ በመኾናችን መንግሥቱን እንድንወርስ መፍቀዱም ከአእምሮ በላይ ነው፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ለገላትያ ምእመናን በላከው መልእክቱ ‹‹እንኪያስ እናንተ ልጆች ናችሁ እንጂ ባሮች አይደላችሁም፡፡ ልጆች ከኾናችሁ በኢየሱስ ክርስቶስ የእግዚአብሔር ወራሾች ናችሁ፤›› በማለት የሚነግረንም ይህንኑ ተስፋ ነው (ገላ.፬፥፯)፡፡

ትልቁ ችግር ተጠማቂው ሰው ይህን የልጅነት ክብር አለመረዳቱ ነው፡፡ የልጅነቴን ክብር ተረድቻለሁ እያለ የሚያወራውም ቢኾን የልጅነቱን መክሊት በልቡናው ውስጥ ቀብሮ አንድም ፍሬ ሳያፈራ ስለ ማንነቱ ለማውራት ቃላት ሲመርጥ ጊዜውን ያባክናል፡፡ አብዛኞቻችን ክርስቲያን የክርስትና እምነት ደጋፊዎች እንጂ ተከታዮች አይደለንም፡፡ የእግዚአብሔር ልጅነት ሊገለጥ የሚገባው ግን በምናሳየው የደጋፊነት (የቲፎዞነት) ስሜት አይደለም፡፡ ደጋፊነት የሚያስፈልገው በጊዜ እና በቦታ ለተወሰነ ያውም ኃላፊ ለኾነ ድርጊት ነው፡፡ ክርስትና ግን በማንኛውም ቦታና ጊዜ ልንኖርበት የሚገባ ዘለዓለማዊ የሕይወት መስመር ነው፡፡ ስለዚህ የመጀመሪያው መክሊታችን ልጅነታችን መኾኑን በሚገባ መረዳት ያስፈልገናል፡፡ በዚህ መክሊታችንም የታዘዝናቸውን ምግባራት ፈጽመን የሚጠበቅብንን ፍሬ ማፍራት አለብን፡፡ ካለዚያ መክሊቱን እንደ ቀበረው ሰው መኾናችን ነው፡፡

እያንዳንዱ ስጦታ እንደሚያስጠይቅ እንገነዘብበታለን

እግዚአብሔር ያለ አንድ ዓላማ በሓላፊነት ለሰዎች ስጦታን አልሰጠም፤ አይሰጥምም፡፡ ማንም ከእግዚአብሔር የተቀበለ ሰው የተሰጠው ስጦታ ለዓላማ ነውና ጥያቄ አለበት፡፡ ጠያቂው ደግሞ የስጦታው ባለቤት ራሱ እግዚአብሔር ነው፡፡ መንጋውን እንዲጠብቁለት ልዩ ልዩ የአገልግሎት ሰጦታዎችን እግዚአብሔር የሰጣቸው አሉ (ዮሐ. ፳፩፥፲፭፤ ገላ. ፩፥፲፭-፲፮)፡፡ ኾኖም ግን የተሰጣቸው ሓላፊነት የሚያስጨንቃቸው፤ ከልባቸው በትሕትና የሚተጉ ክርስቲያኖች የመኖራቸውን ያህል የሚያገለግሉበትን ስጦታ ከእግዚአብሔር መቀበላቸውን፣ ጸጋቸው የሚያስጠይቃቸው መኾኑን የዘነጉና መንገዳቸውን የሳቱም በርካታ ናቸው፡፡

በእግዚአብሔርና በሰዎች መካከል እንደ ድልድይ ኾነው ያገለግሉበት ዘንድ በተሰጣቸው ሥልጣን እግዚአብሔርን የሚያሳዝን ተግባር የሚፈጽሙ አገልጋዮች ለዚህ ጥሩ ምሳሌዎች ናቸው፡፡ ሕዝበ ክርስቲያኑን ወደ እግዚአብሔር ከመምራት ይልቅ የነሱ ደጋፊ፣ ስለ ክብራቸው ተሟጋች እንዲኾን፤ እርስበርስ ጎራ እንዲፈጥርና ‹‹የጳውሎስ ነኝ፤ የአጵሎስ ነኝ›› በሚል ከንቱና የማይጠቅም ሐሳብ እንዲከፋፈል የሚያደርጉ ሰባኪዎችም አይታጡም፡፡ በአጠቃላይ ዅላችንም በተሰጠን መክሊት ባለቤቱ ከፊቱ አቁሞ ስለሚጠይቀን ከገብር ኄር ታሪክ በጎ አገልጋይነትን ተምረን፣ በክርስቲያናዊ ምግባር ጸንተን፣ እንደየአቅማችን መልካም ፍሬን ማፍራት ይጠበቅብናል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

እንደ ገብር ኄር ታማኝ አገልጋዮች እንኹን

በአያሌው ዘኢየሱስ 

መጋቢት ፲፰ ቀን ፳፻፱ .

ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመዋዕለ ሥጋዌው ለሕዝቡና ለደቀ መዛሙርቱ ትምህርቱን ቃል በቃል ወይም በሰምና ወርቅ ወይም በምሳሌ አስተምሮአቸዋል፡፡ ሲያስተምርም በተለያዩ የሙያ ዘርፎች ላይ የተለያዩ ምሳሌዎችን በማቅረብና ምሥጢሩን በማስረዳት ነበር፡፡ ስለዚህም ቃሉን ለገበሬዎች በዘርና በእንክርዳድ፤ እንደዚሁም በሰናፍጭ ቅንጣት፤ ለእናቶች በእርሾ፤ ለነጋዴዎች በመዝገብና በዕንቍ፤ ለዓሣ አጥማጆች በመረብ፤ ወዘተ. እየሰመሰለ ያስተምራቸው ነበር፡፡ በተመሳሳይ መልኩ በዐሥሩ ቆነጃጅት፤ በሰርግ ቤት፤ በበግና በፍየል፤ ወዘተ. እየመሰለ ስለ መንግሥቱ በስፋት አስተምሯል፡፡ ጌታ ትምህርቱን በምሳሌ ያስተምር የነበረው አስቀድሞ፡- «አፌን በምሳሌ እከፍታለሁ፤ ከቀድሞ ጀምሮ ያለውንም ተምሳሌት እናገራለሁ፤» ተብሎ በነቢዩ ዳዊት እንደ ተነገረ (መዝ.፸፯፥፪)፣ ቃሉን የሚሰሙት ዅሉ ትምህርቱ ሳይገባቸው እየተጠራጠሩ ወደ ቤታቸው እንዳይመለሱና ምሥጢሩ ግልጽ እንዲኾንላቸው ለማድረግ ነበር፡፡

በዐቢይ ጾም ስድስተኛ ሳምንት በቤተ ክርስቲያን የሚቀርበው ንባብ፣ ስብከትና መዝሙር የሚያስረዳን ምሥጢርም ስለ አንድ በጎ እና ታማኝ አገልጋይ በምሳሌ የተነገረውን ትምህርት ነው፡፡ በዚህ የወንጌል ንባብ ውስጥ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመጨረሻው የፍርድ ቀን ሰዎች እንደ ሥራቸው መጠን እንደሚዳኙ በምሳሌ አስተምሯል፡፡ በዚህ ምሳሌ አንድ ጌታ ለሦስት አገልጋዮቹ ለአንዱ አምስት፤ ለአንዱ ሁለት እና ለሌላው ደግሞ አንድ መክሊት ከሰጣቸው በኋላ ነግዱና አትርፉ በማለት እርሱ ወደ ሌላ አገር መሔዱ ተገልጦአል፡፡ አምስት መክሊት የተቀበለው የመጀመሪያው አገልጋይ በተሰጠው አምስት መክሊት ቆላ ወርዶ፣ ደጋ ወጥቶ ከነገደ በኋላ አምስት ተጨማሪ መክሊቶችን በማትረፍ ዐሥር መክሊት አኖረ፡፡ ሁለተኛውም በተሰጡት አምስት መክሊቶች ከነገደ በኋላ ሌሎች ተጨማሪ ሁለት መክሊቶችን አትርፎ አስቀመጠ፡፡ ሦስተኛው ግን እንደ ሁለቱ አገልጋዮች ሳይወጣና ሳይወርድ፣ ሳይደክምና ሳያተርፍ በአቅሙ መጠን በተሰጠው አንድ መክሊት ሥራ ሳይሠራ መክሊቱን በጉድጓድ ቀበረው፡፡

ይህ ዅሉ ከኾነ በኋላ ለእነዚህ ሦስት ባሪያዎች በመጠን የተለያዩ መክሊቶችን ሰጥቶ ወደ ሩቅ አገር ሔዶ የነበረው ጌታቸው ወደ እነርሱ ተመልሶ መጣ፡፡ ከዚያም እያንዳንዳቸውን በየተራ እየጠራ በተሰጧቸው መክሊቶች ምን እንደ ሠሩ ጠየቃቸው፤ ተቆጣጠራቸው፡፡ በዚህ መሠረት አምስት መክሊቶችን የተቀበለው የመጀመሪያው አገልጋይ በጌታው ፊት ቀርቦ በተሰጡት አምስት መክሊቶች አምስት በማትረፍ ዐሥር መክሊቶችን ለጌታው አስረከበ፡፡ ሁለተኛውም እንዲሁ ሌሎች ሁለት መክሊቶችን አትርፎ አራት መክሊቶች ለጌታው አስረከበ፡፡ በዚህ ጊዜ የእነዚህ ሁለት አገልጋዮች ጌታ በእነርሱ ደስ በመሰኘቱ፡- ‹‹አንተ መልካም፣ በጎ እና ታማኝ ባርያ! በጥቂቱ ታምሃልና በብዙ ስለምሾምህ ወደ ጌታህ ደስታ ግባ!›› በማለት ሁለቱንም ወደ መንግሥቱ አስገባቸው፡፡

የተሰጠውን አንድ መክሊት ምንም ሥራ ሳይሠራና ሳያተርፍበት ጉድጓድ ውስጥ የቀበረው ሦስተኛው አገልጋይ ግን፡- ‹‹ጌታ ሆይ፣ ካልዘራህበት የምታጭድ፤ ካልበተንህበት የምትሰበስብ ጨካኝ ሰው መኾንህን ስለማውቅና ስለ ፈራሁ መክሊትህን ጉድጓድ ቆፍሬ በመቅበር አቆይቼልሃለሁና እነሆ ተረከበኝ!›› አለው፡፡ በዚህ ጊዜ ንጉሡ እጅግ ተቆጥቶ፡- ‹‹አንተ ክፉና ሐኬተኛ ባርያ! በእርግጥ እንዲህ ዓይነት ሰው መኾኔን ካወቅህ ገንዘቤን ለሚነግዱበት ወይም ለሚለውጡ ሰዎች በመስጠት እንዲያተርፉበት ማድረግና ተመልሼ ስመጣ ከነትርፉ ከእነርሱ መቀበል እችል ነበር፡፡ አንተ ይህን ሳታደርግ ጭራሹኑ በድፍረት እነዚህን በእውነት ላይ ያልተመሠረቱ ክፉ ቃላትን ስለ ተናገርህ ቅጣት ይገባሃል!›› ሲል መለሰለት፡፡ ከዚያም፡– ‹‹ያለውን መክሊት ውሰዱና ዐሥር መክሊት ላተረፈው ጨምሩለት፤ላለው ይሰጠዋል፤ ይበዛለትማል፡፡ ከሌለው ግን ያው ያለው እንኳ ይወሰድበታል፡፡ ስለዚህ የማይጠቅመውን ባሪያ ወደ ልቅሶና ጥርስ ማፋጨት ወዳለበት ወደ ውጪ አውጡት!›› ብሎ ለወታደሮቹ አሳልፎ ሰጠው፡፡

በዚህ የወንጌል ቃል «ወደ ሌላ አገር የሚሔድ ሰው» ተብሎ የተጠቀሰው ባለጠጋ ቅን ፈራጅ የኾነው የጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ምሳሌ ነው፡፡ በምሳሌው ውስጥ የተጠቀሱት አገልጋዮች የሚወክሉት ምእመናንን ወይም እኛን ነው፡፡ መክሊት የተባለው ደግሞ በጎ የሚያሰኘው መልካም ሥራ ነው፡፡ የመጀመሪያዎቹ ሁለት ባሪያዎች ወይም አገልጋዮች ምግባርን ከሃይማኖት ጋር አስተባብረው በያዙ ጻድቃን ይመሰላሉ፤ መክሊቱን ጉድጓድ በመቆፈር የቀበረው ክፉና ሐኬተኛ አገልጋይ ደግሞ ምግባርና ሃይማኖት የሌላቸው ኃጥአን ምሳሌ ነው፡፡

ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በአጭር ቁመት፣ በጠባብ ደረት ተወስኖ፣ በመካከላችን ተገኝቶ ወንጌለ መንግሥቱን ከሰበከልን በኋላ ለእያንዳንዳችን አንድ፣ ሁለትና አምስት መክሊቶችን በመስጠት ‹‹ለፍርድ እስከምመጣ ደረስ ነግዳችሁና አትርፋችሁ ጠብቁኝ›› ብሎን በዕርገቱ ወደ ቀደመ ክብሩ ተመልሶ  ሔዷል፡፡ ዅላችንም ከእግዚአብሔር የተለያዩ መክሊቶችን ተቀብለናል፤ እንድንነግድባቸውና እንድናተርፍባቸው፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ይህን አስመልክቶ ቃሉን ባስተማረበት መልእክቱ እንዲህ ብሏል፤ ‹‹ለአንዱ ጥበብን መናገር በመንፈስ ይሰጠዋልና፤ ለአንዱም በዚያው መንፈስ ዕውቀትን መናገር ይሰጠዋል፡፡ ለአንዱም በዚያው መንፈስ እምነት፤ ለአንዱም በአንዱ መንፈስ የመፈወስ ስጦታ፤ ለአንዱም ትንቢትን መናገር፤ ለአንዱም መናፍስትን መለየት፤ ለአንዱም በልዩ ዓይነት ልሳን መናገር፤ ለአንዱም በልሳኖች የተነገረውን መተርጐም ይሰጠዋል፡፡ ይህን ዅሉ ግን ያ፣ አንዱ መንፈስ እንደሚፈቅድ ለእያንዳንዱ ለብቻው እያካፈለ ያደርጋል፤» (፩ኛ ቆሮ.፲፪፥፰-፲፩)፡፡

እግዚአብሔር ለልጆቹ የሰጣቸው መክሊት ብዙ ነው፤ ለአንዱ የመስበክ፣ ለሌላው የማስተማር፣ ለሌላው የመቀደስ፣ ለሌላው የመዘመርመ ለሌላው የመባረክ፣ ለሌላው የማገልገል፣ ወዘተ. መክሊቶችን ወይም ልዩ ልዩ ጸጋን ሰጥቶአል፡፡ አንድ ሰው የሚሰጠው አንድ መክሊት ብቻ አይደለም፡፡ ሁለት ወይም ሦስት ወይም ከዚያ በላይ መክሊቶች ሊሰጡት ይችላል፡፡ በፍርድ ቀን ዅሉም ሰው የሚፈረድበትም በተሰጠው መክሊት ትርፍ መሠረት ነው፡፡ በተቀበለው መክሊት የሚያተርፍ ሰው በፍርድ ቀን በኢየሱስ ክርስቶስ፡- ‹‹መልካም፤ አንተ በጎ፣ ታማኝም ባርያ! በጥቂቱ ታምነሃል፤ በብዙም እሾምሃለሁ፡፡ ወደ ጌታህ ደስታ ግባ!›› የሚል ቃል ይሰማል፡፡ መክሊቱን መሬት ቆፍሮ የሚቀብር አገልጋይ ግን በውጪ ባለው ጨለማ ውስጥ ተጥሎ በዚያ በልቅሶና ጥርስ በማፋጨት እንዲቆይ ይደረጋል፡፡

ቅዱስ ጳውሎስ እንደ ተናገረው ዅሉም ከእግዚአብሔር ዘንድ የተለያዩ ስጦታዎችን ወይም መክሊቶችን ተቀብሏል፡፡ ይኹን እንጂ ዅሉም መክሊቱን ቆፍሮ ስለ ቀበረ ለእግዚአብሔር ምንም ሊያተርፍ አልቻለም፡፡ በወንጌል ላይ የተጠቀሰው ክፉና ሐኬተኛ አገልጋይ የተሰጠውን መክሊት ምንም ዓይነት ሥራ ሳይሠራበት ወይም ሳይነግድበት ወይም ሳያተርፍበት በመሬት ውስጥ ቆፍሮ በማስቀመጡና ጌታው ሲመጣ ያለ ትርፍ በማስረከቡ በዚህ ዘመን ከምንገኝ ሰዎች እጅጉን ይሻላል፡፡ ምክንያቱም እኛ መክሊቶቻችንን ጠብቀን በማቆየት ለእግዚአብሔር ማስረከብ እንኳ አልቻልንምና፡፡ ዛሬ መክሊት የተቀበለ ዅሉ መክሊቱን ቀብሯል ወይም ጥሏል ለማለት ያስደፍራል፡፡ አንድ የእግዚአብሔር አገልጋይ በተሰጠው የመቀደስ መክሊት መቀደስ ሲገባው የሚዘፍን ከኾነ መክሊቱን ጥሏል፡፡

አንድ የመዘመር መክሊት የተሰጠው አገልጋይ ለእግዚአብሔር መዘመር ሲገባው የሚዘፍን ወይም ሰዎችን የሚያማ ወይም የሚሳደብ ከኾነ መክሊቱን ጥሏል፡፡ ትክክለኛውን የወንጌል ትምህርት እንዲያስተምርና ሰዎችን በንስሐ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት እንዲያስገባ የማስተማር መክሊት ከኢየሱስ ክርስቶስ የተቀበለ ሰባኬ ወንጌል የኑፋቄ ትምህርት በማስተማር የዋሃንን ወደ ሲኦል የሚመራ ከኾነ መክሊቱን ጥሎታል ወይም አጥፍቶታል እንጂ አልቀበረውም፡፡ በተሰጠው የመባረክ መክሊት ወይም ሥልጣን ምእመናንን መባረክና ኃጢአታቸውን መናዘዝ ሲገባው ለጥንቆላ ሥራ ተቀምጦ እፈርዳለሁ የሚል ከኾነ መክሊት የተባለ ክህነቱን አቃሎአታል፤ አጥፍቷታል እንጂ አልቀበራትም፡፡ በእግዚአብሔር ዐውደ ምሕረት ላይ ወንጌልን መናገር ሲገባው ተራ ወሬ ወይም ፖለቲካ የሚደሰኩር ከኾነ ይህ ሰው መክሊቱን ጥሏል፡፡ ሌሎቹም እንደዚሁ፡፡ ለዚህ ነው በዚህ ዘመን ያለን ሰዎች መክሊቱን ከቀበረው ሰው ያነስን፤ ክፉዎች እና ሐኬተኞች ነን የምንለው፡፡

እግዚአብሔር አምላካችን በወንጌል እንደ ተነገረለት ለጻድቃን ሊፈርድላቸውና በኃጥአን ሊፈርድባቸው ዳግመኛ ወደ ምድር ይመጣል፡፡ ከፍርዱ በፊት ዅላችንንም በሰጠን መክሊቶች መጠን ይቆጣጠረናል፡፡ ስለዚህም አንድ መክሊት የተሰጠን ሁለትና ከዚያ በላይ፤ ሁለት የተሰጠን ሁለት ወይም ከዚያ በላይ፤ አምስት የተቀበልነውም አምስትና ከዚያም የሚበልጡ መክሊቶችን ማትረፍ ይጠበቅብናል፡፡ ለመኾኑ በተሰጠን መክሊት እኛ ያተረፍነው ምንድር ነው? በዕርቅ ፋንታ ጠብን የምናባብስ ከኾንን በመክሊታችን ሰዎችን አጉድለናል እንጂ ማትረፍ አልቻልንም፡፡ በመመረቅ ፋንታ የምንራገም ከኾንን መክሊታችንን ጥለናል፡፡ በመጸለይ ፋንታ ለመደባደብ የምንጋበዝ ከኾነም የተሰጠንን መክሊት አጥፍተናል፡፡ የገብር ኄርን ሰንበት ዛሬ ስናከብር አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተገልጦ እያንዳንዳችንን፡- ‹‹ታተርፉበት ዘንድ የሰጠኋችሁን መክሊት እስከነትርፉ አስረክቡኝ!› ቢለን ምንድር ነው የምናስረክበው? ለጥያቄው የምንሰጠውስ ምላሽ ምን የሚል ይኾን?

በወንጌል የተጠቀሰው ያ፣ ሰነፍ አገልጋይ መክሊቱን መቅበሩ ሳያንሰው ለጌታው የሰጠው ክፉ መልስ ለከፍተኛ ቅጣት ዳርጎታል፡፡ ለጌታው፡- «ካልዘራህበት የምታጭድ፤ ካልበተንህበትም የምትሰበስብ ጨካኝ ሰው መኾንህን አውቃለሁ፤» የሚል ምላሽ ነበር የሰጠው፡፡ በዘመናችን ያሉ አንዳንድ ሰዎችም ከዚህ ሰው ጋር የሚመሳሰል ጠባይ አላቸው፤ እነርሱ ስለ እግዚአብሔር ባሕርይ ምንም ነገር ሳያውቁ የእግዚአብሔርን ጠባይና ዕውቀት በእነርሱ የዕውቀት ሚዛን ለመመዘን ይሞክራሉና፡፡ አንድ ክርስቲያን በጠና ሕመም ሲታመም ወይም ከልጆቹ አንዱ በሞት ሲለይበት ወይም ንብረቱ በእሳት ቃጠሎ ሲወድም ይህን አደጋ ያደረሰበት እግዚአብሔር እንደ ኾነ አድርጎ በማሰብ የማይገቡ ቃላትን በእግዚአብሔር ላይ የሚሰነዝሩ ሰዎች አሉ፡፡ እንደ እነዚህ ዓይነት ሰዎች በእግዚአብሔር ህልውና ላይ በመምጣት «እግዚአብሔር ቢኖር ኖሮ ይህ ሕመም ወይም አደጋ በእኔ ላይ አይደርስም ነበር፤» ይላሉ፡፡ ከዚህ በተጨማሪ «እግዚአብሔር እንደዚህ የጨከነብኝ ምን አድርጌው ነው እያሉ እግዚአብሔርን እንደ ሐኬተኛው አገልጋይ ጨካኝ አምላክ የሚያደርጉት ሰዎችም አሉ፡፡

የጻድቁ የኢዮብ ሚስት በእግዚአብሔር ላይ በልቧ ስትሰነዝራቸው የነበሩ ቃላትን ይደግማቸው ዘንድ «እግዚአብሔርን ስደበውና ሙት» በማለት በእርሱ ላይ ልታነሣሣው ሞክራ ነበር፡፡ ነገር ግን «የለም» ወይም «ጨካኝ ነው» ብሎ በድፍረት እግዚአብሔርን መናገር ጥርስ ማፋጨት ወዳለበት ጨለማ የሚያስገባ ክፉ ቃል መኾኑን እናስተውል፡፡ በመሠረቱ ሊነቀፍ ወይም ሊወገዝ ወይም ሊኮነን የሚገባው ሰይጣን እንጂ እግዚአብሔር አይደለም፡፡ እግዚአብሔር አምላክ ቸር፣ ርኅሩኅ፣ ታጋሽ፣ ይቅር ባይ፣ መዓቱ የራቀ፤ ምሕረቱ የበዛ አምላክ ነው፡፡ እርሱ በዚህ ምድር ላይ ስንኖር ያልዘራነውን የጽድቅ ፍሬ እንድንዘራና እንድናጭድ፤ ያልበተንነውንም መልካም ዘር በመበተን በፍርድ ቀን ምርቱን እንድንሰበስብ የሚፈልግ ጌታ ነው፡፡ እኛ ሠላሳ፣ ስድሳና መቶ ፍሬ በማፍራት የእነዚህ ፍሬዎችን ምርት በመሰብሰብ ሰማያዊ መንግሥቱን እንድንወርስ ይፈልጋል፡፡ እርሱ ለሚያምኑትና ለሚታመኑት ዅሉ ታማኝ ነው፤ የሚያምኑትን የሚክድ ጨካኝ ፈጣሪ አይደለም፡፡ ካልዘራበት የሚያጭድና ካልበተነበት የሚሰበስብ ሰው እንጂ እግዚአብሔር አይደለም፤ ጨካኝ፣ ከሀዲና የማይታመንም ሰው ነው፡፡

ዛሬ እግዚአብሔር በጎ እና ታማኝ አገልጋይ አጥቶአል፡፡ ዛሬ ቤተ ክርስቲያን የሚታመን አገልጋይ አጥታለች፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ፡- «ዅሉ ዐመፁ፤ በአንድነትም ረከሱ፡፡ በጎ ነገርን የሚሠራ የለም፤ አንድም ስንኳ፤» (መዝ ፲፫፥፫) ተብሎ የተነገረው ለዚህ ዘመን አገልጋዮች ነው፡፡ የሰው ልጅ ለእግዚአብሔርና ለቤተ ክርስቲያን ታማኝ አገልጋይ ሊኾን አልቻለም፡፡ ቤተ ክርስቲያን በቃሉ የሚገኝ ሰው ለማግኘት ተቸግራለች፡፡ በጥቂቱ ታምኖ በብዙ ላይ ሊሾም የሚችል ሰው ስለ ጠፋ ቤተ ክርስቲያን ‹‹የሰው ያለህ!›› እያለች ነው፡፡ ለምእመናን መዳንና ወደ እግዚአብሔር መንግሥት መግባት የሚተጉ አገልጋዮች ቍጥር እየቀነሰ ነው፡፡ እግዚአብሔር አምላክ አገልጋዮችን በቤተ ክርስቲያን ላይ የሾማቸውና የሚሾማቸው ግን ራሳቸውን፣ ቤተ ክርስቲያንንና መንጋውን ከጥፋት እንዲጠብቁ ነበር (ሐዋ. ፳፥፳፰)፡፡ ሕዝቡን ለመጠበቅ ተሹሞ የሚያጠፋ ጠባቂ ዕድል ፈንታውና ዕጣ ተርታው ትሉ በማያንቀላፋበትና እሳቱ በማይጠፋበት ዘላለማዊ ሲኦል ውስጥ ነው፡፡ ይህን የሚያደርግ አገልጋይ ቅጣቱ ዘላለማዊ መኾኑን ከወዲሁ ሊያውቅ ይገባዋል፡፡

አምላካችን በዳግም ምጽአቱ እስከሚገለጥ ድረስ መንጋውን በመመገብ፣ ውኃ በማጠጣትና በማሳረፍ ፋንታ ለራሱ ብቻ የሚበላና የሚጠግብ፤ የሚጠጣና የሚሰክር፤ የሚያርፍና የሚዝናና ከኾነ እግዚአብሔር ዕድሉን ልቅሶና ጥርስ ማፋጨት ባለበት ጨለማ ውስጥ ያደርግበታል (ማቴ. ፳፬፥፵፭-፶፩)፡፡ ቤተ ክርስቲያንን በተለያያ መልኩ የሚዘርፍና እግዚአብሔርን የሚያሳዝን አገልጋይም ኾነ ተገልጋይ ከዚህ ጠባዩ ሊቆጠብ ይገባዋል፡፡  የቤተ ክርስቲያን አምላክ ኢየሱስ ክርስቶስ መከራ የተቀበለው ለዚህች ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ነው፡፡ በጥፊ የተመታው፤ ርኩስ ምራቅ የተተፋበት፤ የእሾኽ አክሊል የተቀዳጀው፤ በአጠቃላይ የተንገላታውና የሞተው ለዚህች ቤተ ክርስቲያንና ለምእመናን ነው፡፡ ስለ ኾነም ካህናትም ምእመናንም በጎ እና ታማኝ አገልጋዮች ልንኾን ይገባናል፡፡

የአምላካችን የእግዚአብሔር አብ ፍቅር፣ የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋ እና የመንፈስ ቅዱስ ኅብረት ከእኛ ጋር ይኹን!

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

በእንተ ጾም

በዲያቆን ዘአማኑኤል አንተነህ

መጋቢት ፲፫ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

ጾም ‹‹ጾመ›› ከሚለው የግእዝ ግስ የተገኘ ሲኾን ትርጕሙም መተው፣ መጠበቅ፣ መከልከል ማለት ነው፡፡ ጾም ከምግብ መከልከል ብቻ ሳይኾን ከክፉ ተግባር ዅሉ መቆጠብ ጭምር ነው፡፡ ሠለስቱ ምዕትም፡- ‹‹ጾምሰ ተከልኦተ ብእሲ እመብልዕ በጊዜ ዕውቅ በውስተ ሕግ፤ ጾምስ በታወቀው ሰዓት፣ በታወቀው ዕለት ሰው ከምግብ የሚከለከለው መከልከል ነው›› በማለት የጾምን ትርጕም ያስረዳሉ /ፍትሐ ነገሥት፣ አንቀጽ ፲፭/፡፡

ጾም በብሉይ ኪዳንም ኾነ በሐዲስ ኪዳን የታወቀ፣ በነቢያት የነበረ፣ በክርስቶስ የጸና፣ በሐዋርያት የተሰበከ እና የተረጋገጠ መንፈሳዊ ሕግ፤ ፈጣሪን መለመኛ መንፈሳዊ መሣሪያ ነው፡፡ ጾም ሰው ሠራሽ ሕግ ሳይኾን ልዑል እግዚአብሔር የመሠረተው፣ ከእግዚአብሔር ለሰው ልጅ የተሰጠ የመጀመሪያው ትእዛዝ ነው፡፡ ጌታችን መድኀኒችን ኢየሱስ ክርስቶስም እከብር አይል ክቡር፣ እነግሥ አይል ንጉሥ፣ እጸድቅ አይል ጽድቅ የባሕርዩ የኾነ አምላክ ነው፡፡ ለእኛ አርአያ ቤዛ ሊኾነን፣ እናንተም ብትጾሙ ብትጸልዩ አጋንንትን ድል ትነሳላችሁ ሲለን፣ ጾምን ለመባረክ ለመቀደስ፤ በመብል ምክንያት ስተን ስለ ነበር ስለ እኛ ኀጢአት እና በደል ሲል ዐርባ ቀንና ሌሊት ጾሟል፡፡

ጌታችን ሲጾም ዐርባውን መዓልት እና ሌሊት ሙሉ ምንም እኽል ውኃ አልቀመሰም፡፡ ሊቀ ነቢያት ሙሴም እንደዚሁ ጽላተ ሕጉን ከእግዚአብሔር ሲቀበል እኽል ውኃ አልቀመሰም ነበር፡፡ ምክንያቱም አምላካችን ‹‹በእኔ የሚያምን እኔ የማደርገውን ያደርጋል፤ ከእኔ የበለጠም ያደርጋል›› ብሏልና፡፡ አባቶቻችን ጻድቃንም ከዐሥረኛው ማዕረግ (ከዊነ እሳት) ላይ ሲደርሱ በእርሱ መንፈስ (በመንፈስ ቅዱስ) ኃይል ታግዘው ከእኽል ውኃ ተከልክለው ይጾማሉ፡፡ ይህም በሥጋዊ ዓይን ሲመዘን ፈጽሞ የሚከብድ ነው፡፡ ሃይማኖት ከሳይንስና ከአእምሮ በላይ ነውና፡፡ በዚህም  ሃይማኖት የሚቀበሉት እንጅ የሚጠራጠሩት የሚፈላሰፉት እንዳልኾነ እንረዳለን፡፡

የጾም ሥርዓት

መጽሐፍ ‹‹ተሰአሎ ለአቡከ ወይነግረከ፤ አባትህን ጠይቅ፤ ይነግርህማል፤›› /ዘዳ.፴፪፥፯/ እንዳለ ጾም እንዴት እንደሚጾም አባቶችን መጠየቅ እና የአባቶችን ፈለግ መከተል ያስፈልጋል፡፡ ቅዱስ  ኤጲፋንዮስ ‹‹ቤተ ክርስቲያን እናቱ ያልኾነች ሰው እግዚአብሔር አባቱ አይኾነውም›› በማለት እንደ ተናገረው ያለ ቤተ ክርስቲያን እግዚአብሔርን፤ ያለ እግዚአብሔር ደግሞ ቤተ ክርስቲያንን ማወቅ አይቻልም፡፡ ስለዚህ ዘወትር ወደ ቤተ ክርስቲያን እየሔዱ ቃለ እግዚአብሔር መማር፣ መጸለይ፣ ሥጋውን ደሙን መቀበል መገስገስ ክርስቲያናዊ ግዴታ ነው፡፡ ‹‹ቤተ ክርስቲያን ለክርስቲያን›› እንዲሉ አበው፡፡ በጾም ወቅት ደግሞ ይህንን ተግባር ይበልጥ ማሳደግ ይገባል፡፡

በጾም ወቅት የሥጋ አለቃ ነፍስ ናት፡፡ ነፍስ ፈላጭ፣ ቆራጭ፣ አዛዥ ናት፡፡ ሰው መልካም ሥራ ከሠራ በነፍስ በሥጋው ይቀደሳል፤ ገነት (መንግሥተ ሰማያትን) ይወርሳል፡፡ ክፉ ከሠራ ደግሞ በረከተ ሥጋ በረከተ ነፍስን ያጣል፤ ወደ ሲኦል (ገሃነመ እሳት) ይወርዳል፡፡ ሰው ኀጢአተኛ ነው ሲባል ፈቃደ ሥጋው ሠልጥኖበታል ማለት ነው፡፡ ጻድቅ  ነው ሲባል  ደግሞ ፈቃደ ሥጋውን አሸንፏል (ለፈቃደ ነፍሱ እንዲገዛ አድርጓል) ማለት ነው፡፡ ስለዚህ ሰው ሲቀደስም፣ ሲረክስም የሚኖረው በፈቃደ ሥጋ እና ፈቃደ ነፍስ መካከል ባለው የአሸናፊነትና ተሸናፊነት ትግል ነው፡፡

ጾም ራስን ዝቅ የማድረግ፣ የጸሎት እና የንስሐ ጊዜ እንደኾነ ቅዱሳት መጻሕፍት ይነግሩናል፡፡ /ዕዝ. ፰፥፳፩፤ ነህ. ፩፥፬፤ ዳን.፱፥፫/፡፡ ስለዚህም ራሳችንን ዝቅ በማድረግ (በትሕትና) መጾም ይገባናል፡፡ ነቢየ እግዚአብሔር ኢሳይያስ በምዕራፍ ፶፰ ቍጥር ፭ ላይ ‹‹እኔ የመረጥኩት ጾም ይህ ነውን? ሰውስ ነፍሱን የሚያዋርደው እንደዚህ ባለ ቀን ነውን? በውኑ ራሱን እንደ እንግጫ ዝቅ ያደርግ ዘንድ ማቅንና አመድንም በበታቹ ያነጥፍ ዘንድ ነውን?›› ይላል፡፡ እንግጫ ማለት ባሕር ውስጥ የሚበቅል ሣር ነው፡፡ በቀዳም ሥዑር ካህናት ‹‹ጌታ ተመረመረ፤ ዲያብሎስ ታሰረ፤›› እያሉ ለደስታ መግለጫ የሚሰጡት እና ራስ ላይ የሚታሰር ለምለም ሣር ነው፡፡ እንግጫ (ግጫ – በአንዳንድ አካባቢዎች) ሲያድግ ራሱን ዝቅ ያደርጋል፤ እያደገ ሲሔድ ራሱን ይደፋል (ዝቅ ያደርጋል)፡፡

ነቢዩ ኢሳይያስ ራሳችሁን እንደ እንግጫ (ግጫ) ዝቅ አድርጉ ማለቱ  በጾም ወቅት ‹‹እንደዚህ ነው የምጾመው፤ እስከዚህ ሰዓት ድረስ ነው የምጾመው›› እያልን ውዳሴ ከንቱን መሻት የለብንም ሲል ነው፡፡ ሰው እያወቀ ሲሔድ ራሱን ይደብቃል እንጅ ራሱን ከፍ ከፍ አያደርግም፡፡ የጾም ወቅት ትሕትናን ገንዘብ የምናደርግበትና ይበልጥ የምናሳድግበት ወቅት ነው፡፡ አንድ ክርስቲያን ፈተናን ችሎ በትዕግሥት የሚያሳልፍ፣ እየሰማ የሚተው መኾን አለበት፡፡ ነቢዩ ዕዝራም በመጽሐፈ ዕዝራ ፰፥፳፩ ላይ ‹‹በአምላካችን ፊት ራሳችንን እናዋርድ ዘንድ ከእርሱም የቀናውን መንገድ ለእኛ እና ለልጆቻችን ለንብረታችንም ሁሉ እንለምን ዘንድ በዚያ በአኅዋ ወንዝ አጠገብ ጾም አወጅሁ›› በማለት ራስን ዝቅ በማድረግ ለአምላክ ፈቃድ መገዛት እንደሚገባ ያስተምረናል፡፡

የጾም ሰዓት

ስለ ጾም ሲነገር የጾም ሰዓትም አብሮ ይነሣል፡፡ በዘፈቀደ ሳይኾን በሰዓት የተወሰነ ጾም መጾም እንደሚገባን መጽሐፍ ቅዱስ ያስረዳናል፡፡ ‹‹የእስራኤልም ልጆች ዅሉ ሕዝቡም ዅሉ ወጥተው ወደ ቤቴል መጡ፤ አለቀሱም፡፡ በዚያም በእግዚአብሔር ፊት ተቀመጡ፡፡ በዚያም ቀን እስከ ማታ ድረስ ጾሙ፤›› ተብሎ እንደ ተጻፈ /መሳ.፳፥፳፮/፡፡ የጾም ሰዓትም በፍትሐ ነገሥት አንቀጽ ፲፭ ተዘረዝሯል፡፡ ሠለስቱ ምዕት ‹‹ቢቻላችሁ ከዚህ አብዝታችሁ ጹሙ›› እንደዚሁም ‹‹በጾም ምክንያት ጠብ ክርክር ቢኾን መጾም ይገባል፤ ከመብላት መጾም ይሻላልና፤›› በማለት ከተወሰነው ሰዓት በላይ አብልጦ መጾም እንደሚቻልና ከመብል ይልቅ ለጾም ማድላት እንደሚገባ ነግረውናል /ፍትሐ ነገሥት አንቀጽ ፲፭ ቍጥር ፭፻፹፬/፡፡

ሰው ይረባኛል ይጠቅመኛል ብሎ አብዝቶ ከመጾሙ የተነሣ መላእክትን፣ አባ እንጦንስና አባ መቃርስን እንደሚመስል ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ያስተምራሉ፡፡ አምላካችን ‹‹እናንተን የሚቀበል እኔን ይቀበላል›› የሚል ቃል ኪዳን የሰጣቸው አባቶቻችን መምህራን የምንጾማቸውን አጽዋማት እና የምንጾምበትን የሰዓት ጊዜ ወስነውልናል፡፡ በቅዱሳን አባቶቻችን ላይ አድሮ ሥርዓቱን የሠራልን ራሱ እግዚአብሔር ነው፡፡ ምክንያቱም ካለ እርሱ ፈቃድ እጽፍ፣ እተረጕም ቢሉ አይቻልምና፡፡ ጌታችን በወንጌሉ ‹‹ጌታ ሆይ ጌታ ሆይ የሚለኝ ዅሉ ወደ መንግሥተ ሰማያት የሚገባ አይደለም፤ ትእዛዜን የሚያከብር እንጅ፤›› እንዳለ በመንፈስ ቅዱስ ኀይል ተመርተው አባቶች  የደነገጉትን ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን ማክበር እና መጠበቅ አለብን፡፡

ቅዱስ ጳውሎስ ‹‹በየጥቂቱ ማደግ ይገባል›› እንዳለው ዅሉንም ነገር በአቅም ማድረግ ያስፈልጋል፡፡ ጾምን ስንጾምም አቅምን ማወቅም ተገቢ ነው፡፡ ብዙ ለመጾም ስንወስን ጽናታችንና ልምዳችንን ግምት ውስጥ በማስገባት መኾን ይኖርበታል፡፡ ካለበለዚያ ጥብዓት ጎድሎን፣ ትዕግሥት አንሶን እግዚአብሔርን ልናማርር እንችላለን፡፡ ጾመን የማናውቅ ሰዎች በስሜት ተነሣሥተን በአንድ ጊዜ ቀኑን ሙሉ መጾም አለብን ማለት የለብንም፡፡ ክርስትና የስሜት ጉዞ አይደለምና፡፡ እስከ ሰባት ሰዓት ጹሞ የማያውቅ ክርስቲያን እስከ ዐሥራ ሦስት ሊጾም አይችልም፡፡ በስሜት የሚደረግ ማንኛውም ነገር ፍጻሜ አይኖረውምና ስንጾም አቅማችንን ማወቅ ተገቢ ነው፤ ለዚህ ደግሞ ከንስሐ አባት ጋር መመካከር ይጠቅማል፡፡

ጠቢቡ ሰሎሞን ‹‹እጅግም ድሀ አታድርገኝ፤ እጅግም ሀብት አትስጠኝ›› ይላል፡፡ እኛም ስንጾምም ስንለምንም በአቅማችን መኾን አለበት፡፡ ስለጾምና የሰዓት ገደብ ሲነገር ማስተዋል የሚገባን ቁም ነገር ከእኽል ውኃ ከመከልከል አኳያ ጾም በቍጥርና በጊዜ የተወሰነ ይኹን እንጂ ከክፉ ተግባር ከመራቅ አንጻር ክርስቲያን እስኪሞት ድረስ ጾመኛ ነው፡፡ ምንጊዜም ቢኾን ከክፉ ነገር፣ ከኀጢአት ዅሉ መጾም (መከልከል) ይጠበቅበታልና፡፡ ዅላችንም ይህን ክርስቲያናዊ ሓላፊነት መዘንጋት የለብንም፡፡ ከዚህ ላይ ግን አንድ ሰው በመጾሙ ብቻ አምላክን ያስደስተዋል ማለት አይደለም፡፡ መጾም ያለበትም ለሥራው ኀጢአት ማካካሻ አይደለም፡፡ የኀጢአት ስርየት የሚገኘው ንስሐ በመግባት እንጅ በመጾም ብቻ አይደለምና፡፡ ሌሎችንም የትሩፋት ምግባራት መሥራት ስንችል ነው ኀጢአታችን የሚሰርይልን፡፡ ስለዚህ ራሳችንን ዝቅ በማድረግ፣ ንስሐ በመግባት፣ በመጸለይ፣ በመመጽወት ከጾምን ኀጢአታችን ይሰረይልናል ማለት ነው ‹‹በጾም ወበጸሎት ይሰረይ ኵሉ ኃጢአት፤ በጾም በጸሎት ኀጢአት ዅሉ ይደመሰሳል፤›› እንዲሉ ሊቃውንት፡፡

ጾም እና ፈተና

‹‹ቤተ ክርስቲያን እየሔድኹ፣ እየጾምኹ፣ እየጸለይኹ፣ እፈተናለሁ፤ ለምንድን ነው?›› የምንል ብዙዎች ነን፡፡ ወደ ቤተ ክርስቲያን ስሔድ ፈተና እየበዛብኝ ነው በማለት ከቤቱ የምንርቅም ጥቂቶች አይደለንም፡፡ ብዙ ጊዜ ከመልካም ነገር በስተጀርባ ፈተና አለ፡፡ ከጌታችን የምንማረው ሕይወትም ይኸን ነው፡፡ የማይሾሙት ንጉሥ፣ የማያበድሩት ባለጠጋ፣ ዅሉን የፈጠረ፣ ዅሉን የሚገዛ ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለእኛ ሲል ጾመ፤ ተራበ፤ በሰይጣን ተፈተነ፡፡ በእኛ ላይም ብዙ ፈተና ቢመጣብን ለምን ያስደንቃል? ቅዱስ ዳዊት ‹‹ነፍሴን በጾም አስመረርኋት፤ ለስድብም ኾነብኝ›› ይላል /መዝ.፷፱፥፲/፡፡ በክርስትና ሕይወቱ የሚበረታ ሰው ይሰደዳል፤ ይሸነገላል፤ ፈተና ይበዛበታል፡፡ በዚህ ጊዜ ‹‹ለሚያሳድዱህ ጹምላቸው›› በማለት ቅዱሳን ሐዋርያት እንዳዘዙን ለሚያሳድዱን መጾም መጸለይ ይኖርብናል /ዲድስቅልያ ፩፥፭/፡፡ ክርስትና ሲገፉ መግፋት አይደለምና፡፡ በረከታቸው ይደርብንና ብፁዕ አቡነ በርናባስ ‹‹ከቤተ ክርስቲያንን የተጠጋ እንኳን ሰው ዛፉ ይለመልማል›› ይሉ ነበር፡፡ እግዚአብሔር አባታችን፣ ቤተ ክርስቲያን እናታችን ብሎ የሚኖር ሰው ፈተና በየጊዜው ቢገጥመውም መጨረሻው ያማረ ነው፡፡ እግዚአብሔርን ተከትሎ የወደቀ የለምና፡፡

የጾም ጥቅም

በቅዱሳት መጻሕፍት እንደ ተገለጸው ጾም የሚከተሉት ጥቅሞች አሉት፤

  • የሥጋን ምኞት ያጠፋል፤
  • የነፍስ ቍስልን ያደርቃል፤
  • ፈቃደ ሥጋን ለፈቃደ ነፍስ ያስገዛል /ፍት.ነገ.፲፭፥፭፻፷፬/፤
  • መላእክትን መስሎ ለመኖር ያስችላል፤
  • ልዩ ልዩ መከራን ያቃልላል፤
  • አጋንንትን ያስወጣል /ኢያ.፯፥፮-፱/፤
  • ሰማያዊ ክብር እና ጸጋን ያስገኛል /ኛነገ.፲፱፥፰/፤
  • በመንግሥተ ሰማያት ለመኖር የሚያስችል ምግባርን ያሠራል /ሉቃ.፮፥፳፩/፤
  • ከእግዚአብሔር ዘንድ ይቅርታ እና ምሕረትን ለማግኘት ይረዳል፤
  • አጋንንትና ጠላትን ድል ለማድረግ ያግዛል /ማቴ.፬፥፲፩፤ መጽሐፈ አስቴር ምዕ.፯/፤
  • ፈቃደ እግዚአብሔርን ለመፈጸም ይረዳል /፩ኛነገ.፲፱፥፩/፤
  • ከእግዚአብሔር ቍጣ ለመዳን ያስችላል /ዮናስ ፫፥፩/፤
  • የተደበቀ ምሥጢርን ይገልጣል /ዳን.፲፥፲፬/፤
  • ጸጥታን እና ርጋታን ያስተምራል፤
  • ከቅዱሳን በረከት ያሳትፋል፤
  • ሕይወትን ያድሳል፤
  • መንፈሳዊ ኃይልን ያሰጣል /፩ኛሳሙ.፯፥፭/፤ጥበብን ይገልጣል /ዕዝራ ፯፥፮፤ ዳን.፱፥፪/፤
  • ክህደት ጥርጥርን በማጥፋት እምነትን ለማጠንከር ይረዳል፤
  • ዕድሜን ያረዝማል፤
  • ትዕግሥትን ያስተምራል፤
  • በመላእክት ጠባቂነት ለመኖር ያስችላል /ዘፀ.፲፬፥፲፱. ሐዋ.፲፥፫/፡፡

ጾም ከሚያስገኘው መንሳዊ ጸጋና በረከት ባሻገር በርካታ ሥጋውያን ጥቅሞችም እንዳሉት በጾም ዙሪያ የተደረጉ ልዩ ልዩ ሳይንሳዊ ጥናቶች ያሳያሉ፡፡ በጥናቶቹ መሠረትም ጾም፡-

  • የደምና የስኳር መጠንን ይቆጣጠራል፤
  • የአንጎል እንቅስቃሴ የተቀላጠፈ እንዲኾን ያደርጋል፤
  • የስብ ክምችትን ይቀንሳል፤
  • የምግብ መፍጨት ስርዓታችንን ያስተካክላል፤
  • የካንሰር ሕዋሳት ዕድገትን ይከላከላል፤
  • የጠራ የሰውነት ቆዳ እንዲኖረን ያደርጋል፤
  • በሽታ የመከላከል አቅምን ይጨምራል፡፡

በአጠቃላይ ጾም ሰው ሠራሽ ሕግ አይደለም፤ የመሠረተውም ራሱ ልዑል እግዚአብሔር ነው፡፡ አምላካችን አዳምና ሔዋንን ‹‹ዕፀ በለስን አትብሉ›› ብሎ ባዘዛቸው ጊዜ የጾም ሕግን ሠርቶልናል፡፡ በዚህም ጾም የመጀመሪያ ትእዛዝ ናት እንላለን፡፡ አዳም በመብል ምክንያት ሕገ እግዚአብሔርን በመጣሱ ነው ከክብሩ የወረደው፡፡ እኛም ብንጾም እንጠቀማለን፤ ባንጾም ደግሞ በረከትን እናጣለን፡፡ ቅዱስ ዳዊት ‹‹ሥጋዬ ቅቤ በማጣት ከሳ፤›› /መዝ.፻፱፥፳፬/፤ ነቢዩ ዳንኤልም ‹‹ማለፊያ እንጀራም አልበላሁም፤ ሥጋ እና ጠጅም በአፌ አልገባም፤›› /ዳን.፲፥፫/ ሲሉ እንደ ተናገሩት፣ በጾም ወቅት ከጥሉላት ምግቦች መከልከል አለብን፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ‹‹መብል ግን ወደ እግዚአብሔር አያቀርበንም፤ ባንበላም ምንም አይጎድለንም ብንበላም ምንም አይተርፈንም፤›› ሲል ማስተማሩም ከመብል ተከልክለን መጾማችን ወደ እግዚአብሔር የምንቀርብበት መንገድ መኾኑን ያመላክታል /ሮሜ.፲፬፥፯፤ ፩ኛቆሮ.፰፥፰/፡፡ አበው ‹‹ጾም ገድፎ የወፈረ በዓል ሽሮ የከበረ የለም›› እንደሚሉት በጾም ወቅት በልተን ከምናገኘው ጥቅም ይልቅ ጾመን ከእግዚአብሔር ዘንድ የምንቀበለው በረከት ይበልጣል፡፡

ጾም ቍስለ ነፍስን የምትፈውስ፣ ኃይለ ፍትወትን የምታደክም፣ የበጎ ምግባራት ዅሉ መጀመሪያ፣ ጸጋ እግዚአብሔርን የምታሰጥ፣ ለጽሙዳን ክብራቸው፣ ለደናግል የንጽሕና ጌጣቸው፣ የጸሎት እናት፣ የዕንባ መገኛ ምንጭ፣ አርምሞን የምታስተምር፣ ለበጎ ሥራ ዅሉ የምታነቃቃ፣ ሰውነትን በእግዚአብሔር ፊት በማዋረድ ትሕትናን ገንዘብ ለማድረግ የምትረዳ መድኃኒተ ነፍስ ናት /ማር ይስሐቅ አንቀጽ ፬ ምዕራፍ ፮/፡፡ እንደዚሁም ጾም ዕድሜን ያረዝማል፡፡ በጾም በጸሎት ተወስነው፣ ረጅም ዕድሜ የኖሩ አባቶቻችን ሕይወትም ለዚህ ማስረጃ ነው፡፡ ለምሳሌ ቅዱስ ቄርሎስ ዘአንኮራይት ፻፰፤ ቅዱስ እንጦንስ ፻፭፤ ቅዱስ መቃርስ ዘእስክንድርያ ፻ ዓመት በምድር ላይ ቆይተዋል፡፡ ምእመናንም ጾምን ስንጾም አምላካችን ዕድሜአችንን ለንስሐ ያረዝምልናል፡፡ በጾም ወቅት መጸለይ፣ መመጽወት፣ መስገድ በጾም የምናገኘውን ዋጋ ከፍ ያደርገዋል፡፡ ‹‹ስለ ኀጢአቱ እንደሚጾም፣ እንደሚጸልይ ሰው ኹኑ›› እንዳለ ቅዱስ ያሬድ፡፡

አንድ ክርስቲያን ጾም አልጾምም የማለት ሃይማኖታዊ ሥልጣን የለውም፡፡ ምክንያቱም ጾም ለዅሉም ክርስቲያን ሕግ ኾኖ የተሰጠ የአምላክ ትእዛዝ ነውና፡፡ ነቢየ እግዚአብሔር ኢዩኤል ‹‹ጾምን ቀድሱ፤ ጉባኤውንም አውጁ፤›› በማለት መጾም፣ መጸለይ ክርስቲያናዊ ግዴታ መኾኑን ነግሮናል /ኢዩ.፪፥፲፭/፡፡ ቅዱስ ጳውሎስም ‹‹አገልግሎታችን እንዳይነቀፍ በአንዳች ነገር ማሰናከያ ከቶ አንሰጥም›› ሲል ምክንያት እየፈጠርን ከመንፈሳዊ ሕይወትና ከአገልግሎት ወደ ኋላ ማለት እንደሌለብን አስተምሮናል /፪ኛቆሮ.፮፥፫/፡፡ ብፁዕ አቡነ ሺኖዳ ‹‹በዐቢይ ጾም ሕይወቱን ያልቀየረ ክርስቲያን በሌሎች አጽዋማት ይቀይራል ለማለት ይከብዳል›› ይላሉ፡፡ እንደሚታወቀው በዐቢይ ጾም ከበሮ እና ጸናጽል ዅሉ ይጾማሉ፡፡ ይኸውም የጾሙን ትልቅነት ያረጋግጥልናል፡፡ የዜማ መሣሪያዎች ዐቢይ ጾምን ከጾሙ ለባዊነት ያለን የሰው ልጆችስ (ክርስቲያኖች) ለጾሙ ምን ያህል ዋጋ እንሰጥ ይኾን? ዅላችንም ጾሙን በደስታና በፍቅር ጾመን በረከተ ሥጋ በረከተ ነፍስን እናገኝ ዘንድ የእግዚአብሔር ቸርነት፣ የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም አማላጅነት፣ የቅዱሳን ተራዳዒነት አይለየን!

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

የዐቢይ ጾም ሳምንታት

በመምህር ምሥጢረ ሥላሴ ማናየ

መጋቢት ፲፩ ቀን ፳፻፱ .

ዘወረደ

ትርጕሙ ‹ከሰማየ ሰማያት የወረደ› ማለት ነው፡፡ ከሰማየ ሰማያት የወረደውን፣ ከድንግል ማርያም የተወለደውን በጥንት ስሙ ወልድ፣ ቃል በኋላ ስሙ ኢየሱስ ክርስቶስ፣ አማኑኤል የተባለውን ሰው የኾነውን አምላክ ለማመስገን ርደቱን (ከሰማየ ሰማያት መውረዱን) ለመዘከር የሚጾም ጾም ነው፡፡ ጌታችን ጾመ ከማለት አስቀድሞ ከሰማየ ሰማያት መውረዱን ከድንግል ማርያም መወለዱን መናገር አስፈላጊ ነውና የመጀመሪያው ሳምንት ‹ዘወረደ› ተብሏል፡፡ ‹‹አንተ በሰማይ ወአንተ በምድር ወአንተ በባሕር ወአንተ በየብስ፤ አንተ በሰማይ አለህ፤ በምድር በባሕርም በየብስም አለህ፤›› የተባለውን በሰማይ በምድር ምሉዕ የኾነውን አምላክ ‹ወረደ፤ መጣ› ብሎ መናገር ‹ሰው ኾነ› ማለት ነው፡፡ ሰው ኾኖ መገለጡን ለማስረዳት ነው እንጂ መውረድ መውጣት የሚባሉ ቃላት በዅሉ ምሉዕ ለኾነው መለኮት አይስማሙትም፡፡ ቃላቱ ሰውኛ አነጋገርን የሚያመለክቱ ናቸውና፡፡ መተርጕማን አበው ‹‹‹ዘወረደ› ማለት ‹ሰው የኾነ› ማለት ነው›› ብለው ይተረጕማሉ፡፡ አምላካችን ሰው ከኾነ በኋላ ‹መጣ፤ ሔደ፤ ወረደ፤ ዐረገ› የሚሉ ቃላት ይስማሙታል፡፡ ምልዓቱን ሳይለቅ በሰው አካል ተወስኖ ታይቷልና፡፡ ስለዚህ ‹ወረደ› እግዚአብሔር ሰው ኾኖ መገለጡን፤ ‹ዐረገ› ደግሞ የሰውነቱን ሥራ መፈጸሙን ያሳያል፡፡ ዐረገ ስንልም ቀድሞ በሰማይ የለም ለማለት አይደለም፤ አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመለኮቱ በዓለሙ ዅሉ ምሉዕ ነውና፡፡

ጾሙን ሐዋርያት፣ ስያሜውንና የምስጋናውን ሥርዓት ቅዱስ ያሬድ አዘጋጅተዋል፡፡ ቅዱስ ያሬድ ነቢያትን በንባብ፤ ሐዋርያትን በስብከት፤ ሊቃውንትን በትርጓሜ፤ መላእክትን በዜማ ይመስላቸዋል፡፡ ቅዱስ ያሬድ የመላእክትን የምስጋና ሥርዓት ወደ ምድር አምጥቷል፡፡ የነቢያትን ትንቢት፣ የሐዋርያትን ትምህርት በሚገባ ተርጒሞ፣ አብራርቶ፣ አመሥጥሮ አዘጋጅቶታል፡፡ ሐዋርያት ጾሙን ጾመው የጾም ሕግ ደንግገዋል፤ ቅዱስ ያሬድም ለጾሙ ስያሜ ሰጥቶ ምስጋና ከነሥርዓቱ አዘጋጅቶ አቅርቧል፡፡ቤተ ክርስቲያናችንም የመጀመሪያው የዐቢይ ጾም ሳምንትን (ዘወረደን) ስያሜ እንደ ቅዱስ ያሬድ ከሐዋርያት ተቀብላ ታስተምራለች፡፡ ይህ የመጀመሪያው ሳምንት ‹ጾመ ሕርቃል› እየተባለም ይጠራል፡፡ ሕርቃል (ኤራቅሊዮስ) በ፮፻፲፬ ዓ.ም የነበረ የቤዛንታይን ንጉሥ ነው፡፡ ለክርስቲያኖች ባደረገው ርዳታ ምክንያት አንድ ሳምንት ጾመውለት ነበር፡፡ ያላወቁ ‹ጾመ ሕርቃል› ብለው አንድ ጊዜ ጾመው ትተውታል፡፡ ጥንቱን የቅዱሳን ሐዋርያት መኾኑን ያወቁ ምእመናን ግን ዅልጊዜ በየዓመቱ ይጾሙት ነበር፡፡ ዛሬም ድረስ ጾመ ሕርቃል እየተባለ ይጠራል፡፡ ሙሉ ታሪኩ በፍትሐ ነገሥት ትርጓሜ አንቀጽ ፲፭ ላይ ይገኛል፡፡

ቅድስት

‹ቅድስት› ማለት ‹የተለየች፣ የነጻች፣ የከበረች› ማለት ነው፡፡ ይኸውም ጌታችን ጾም የጀመረባት፣ ልዩ፤ የተቀደሰች፤ የከበረች፤ ልዩ፣ ንጹሕ፣ ክቡር በሚኾን በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተጾመች መኾኗን ያመላክታል፡፡ ይህች ጾም በማቴዎስ ወንጌል ምዕራፍ አራት የተገለጠችው የጌታችን ጾም ስትኾን፣ ስያሜዋና የዕለቷ የምስጋና ሥርዓትም የቅዱስ ያሬድ ነው፡፡ አምላካችን በገዳመ ቆሮንቶስ ዐርባ መዓልትና ዐርባ ሌሊት በጾመበት ጊዜያት እነዚህ ሦስቱን አርእስተ ኃጣውእ ድል አድርጓል፡፡ ሦስቱ አርእስተ ኃጣውእ የሚባሉትም፡- ትዕቢት፣ ስስትና ፍቅረ ንዋይ ናቸው፡፡ በእነዚህ ሦስት ኃጢአቶች ጌታችን በዲያሎስ በተፈተነ ጊዜ በትዕቢት ቢመጣበት በትሕትና፤ በስስት ቢመጣበት በትዕግሥት፤ በፍቅረ ንዋይ ቢመጣባት በጸሊዓ ንዋይ ጌታችን ዲያሎስን ድል አድርጎታል፡፡ ለእኛም እነዚህን ድል ለማድረግ የምንችልበትን ጥበብ – ጾምን ገልጦልናል፡፡ ትዕቢት ያልተሰጠንን መሻት፣ ስስት አልጠግብ ባይነት ስግብግብ መኾን፣ ፍቅረ ንዋይ ለገንዘብ ሲሉ ፈጣሪን መካድ ነው፡፡ አንደ ክርስቲያን ሦስቱን አርእስተ ኃጣውእ ድል ካደረገ ሌሎችን ኃጣውእ በቀላሉ ድል ማድረግ ይቻለዋል፡፡

ምኵራብ

ሦስተኛው የዐቢይ ጾም ሳምንት ‹ምኵራብ› ይባላል፡፡ ምኵራብ አምልኮተ እግዚአብሔር ሲፈጸምበት፣ ሕገ ኦሪት ሲነበብበት የነበረ በአይሁድ የሚሠራ መካነ ጸሎት ነው፡፡ ዘወትር ቅዳሜ ብዙ ሕዝብ ይሰበሰብበት ስለ ነበር ጌታችን ለማስተማር ብዙ ጊዜ በምኵራብ ተገኝቶአል፡፡ ስያሜው የተወሰደው በዮሐንስ ፪፥፲፬ ‹‹ወረከበ በምኵራብ እለ ይሠይጡ አልህምተ ወአባግዐ ወአርጋበ …፤ በመቅደስም በሬዎችን፣ ላሞችን፣ በጎችን፣ ርግቦችን፣ የሚሸጡትን አገኘ …›› ተብሎ ከተገለጸው ኃይለ ቃል ላይ ሲኾን፣ ‹ምኵራብ› የሚለው ቃልም በአማርኛ ‹መቅደስ› ተብሎ ተተርጕሟል፡፡ ምኵራብ የሚባለው ሳምንት ጌታችን ወደ ምኵራብ ገብቶ ማስተማሩ የሚነገርበት፤ ‹‹ቤቴ የጸሎት ቤት ይባላል፤ እናንተ ግን የሌቦች ዋሻ አደረጋችሁት›› ብሎ በምኵራብ ይሸጡ፣ ይለውጡ የነበሩትን የገሠፀበት፤ ቤተ መቅደስን የከብት መንጃ የወርቅና የብር መነገጃ ያደረጉ ሰዎችን ከነሸቀጣቸው ከቤተ መቅደስ ያስወጣበት፤ ቤተ መቅደስ የእግዚአብሔር ማደሪያ፣ የስሙ መጠሪያ፣ የጸሎት ሥፍራ መኾኗን ያስረዳበትና ያወጀበት፤ በቤተ መቅደስ የንግድ ሥራ ማከናወን እንደማይገባ ያረጋገጠበት ዕለት ነው፡፡

መጻጒዕ

አራተኛው የዐቢይ ጾም ሳምንት ‹መጻጒዕ› ይባላል፡፡ ስያሜው በዮሐንስ ወንጌል ፭፥፩ ላይ ከሚገኘው ኃይለ ቃል የተወሰደ ነው፡፡ በዚህ የወንጌል ክፍል ጌታችን በቤተ ሳይዳ ሕሙማንን እንደ ፈወሰ ተነግሮአል፡፡ ብዙ ሕሙማን ፈውስ ሽተው አንዲት የመጠመቂያ ሥፍራን ከበው ይኖሩ ነበር፡፡ በዚያች ሥፍራ ቀድሞ የወረደ እና የተጠመቀ አንድ በሽተኛ ብቻ ይፈወስ ነበር፡፡ ጌታችን በዚህ ሥፍራ ተገኝቶ በሽተኞችን ጐብኝቷል፡፡ በዚያም ልዩ ልዩ ደዌ ያለባቸው አምስት ዓይነት ሕሙማን እንደ ነበሩ ተገልጧል፤ እነዚህም፡- ሰውነታቸው የደረቀ፣ የሰለለና ያበጠ፤ እንደዚሁም ዕውራን እና ሐንካሳን ነበሩ፡፡ ከዚህ አምስት የተለያየ ዓይነት በሽታ ከተያዙ ሰዎች መካከል ደዌው የጸናበት፣ ለሠላሳ ስምንት ዓመታት በደዌ ዳኛ፣ ባልጋ ቍራኛ ተይዞ የኖረው፤ ከደዌው ጽናት የተነሣ ‹መጻጒዕ› ተብሎ የተጠራው በሽተኛ አንዱ ነበር፡፡ መጻጒዕ ስም አይደለም፡፡ ደዌ የጸናበት በሽተኛ ሕመምተኛ ማለት ነው እንጂ፡፡ ሰውየው ከበሽታው ጽናት የተነሣ ስሙ ጠፍቶ በበሽታው ሲጠራ የነበረ ነው፡፡ አምላካችን ይህን ሰው ‹‹አልጋህን ተሸክመህ ሒድ›› ብሎ ሠላሳ ስምንት ዘመን የተኛበትን አልጋ ተሸክሞ ወደ ቤቱ እንዲገባ ማድረጉ የሚነገርበት ወቅት በመኾኑ ሳምንቱ ‹መጻጒዕ› ተብሎ በተፈወሰው በሽተኛ ስም ተሰይሟል፡፡ (ሙሉ ታሪኩን በዮሐንስ ወንጌል ፭፥፩-፲፯ ይመልከቱ)፡፡ ዛሬም ቢኾን በሰዎች ላይ ልዩ ልዩ ደዌያት አሉ፤ የሥጋውን ደዌ ሐኪሞች ያውቁታል፡፡ ከዚህ የከፉ የነፍስ ደዌያት እጅግ ብዙዎች ናቸው፡፡ በኃጢአት ብዛት ልባቸው የደረቀና ያበጠ፤ ሰውነታቸው የሰለለ፤ ዓይነ ሕሊናቸው የታወረ፤ እግረ ልቡናቸው የተሰበረ ብዙዎች ሕሙማን አሁንም አሉ፡፡ ፈውስን ይሻሉ፤ ድኅነትን ይፈልጋሉ፡፡ እንደ መጻጕዕ ቦታቸውን ሳይለቁ እግዚአብሔርን በተስፋ ቢጠብቁት አንድ ቀን ይፈወሳሉ፡፡

ደብረ ዘይት

አምስተኛው የዐቢይ ጾም ሳምንት ‹ደብረ ዘይት› ይባላል፡፡ ስያሜው የተወሰደውም ከማቴዎስ ወንጌል ፳፬፥፫ ካለው ትምህርት ነው፡፡ ደብረ ዘይት ከኢየሩሳሌም በስተምሥራቅ አቅጣጫ የሚገኝ በወይራ ዛፎች የተሸፈነ ትልቅ ተራራ ነው፡፡ ጌታችን ምሥጢራትን በተለያየ ቦታ ገልጧል፡፡ ምሥጢረ ጸሎትን በጌቴሴማኒ፤ ምሥጢረ መንግሥቱን በደብረ ታቦር፤ ምሥጢረ ቊርባንን በቤተ አልዓዛር፤ ምሥጢረ ትንሣኤ ሙታንን በቤተ ኢያኢሮስ፤ ምሥጢረ ምጽአቱን ደግሞ በደብረ ዘይት ገልጧል፡፡ ደብረ ዘይት ጌታችን ዳግም ለፍርድ መምጣቱንና ምሥጢረ ምጽአቱን ለደቀ መዛሙርቱ በሚገባ የገለጠበት ዕለት ነው፡፡ ደብረ ዘይትን ጌታችን በመዋዕለ ስብከቱ ለማደሪያነት ተጠቅሞበታል፡፡ ቀን ቀን በምኲራብ ያስተምራል፤ ሌሊት ሌሊት ደግሞ በደብረ ዘይት ያድራል፡፡ ይህንም ቅዱስ መጽሐፍ እንዲህ በማለት ይመሰክራል፤ ‹‹ዕለት ዕለት በመቅደስ ያስተምር ነበር፡፡ ሌሊት ግን ደብረ ዘይት ወደምትባል ተራራ ወጥቶ ያድር ነበር፡፡ ሕዝቡ ዅሉ ይሰሙት ዘንድ ማልደው በመቅደስ ወደ እርሱ ይመጡ ነበር›› (ሉቃ. ፳፩፥፴፯)፡፡ በዚህ ለማደሪያነት ባገለገለው ተራራ ምሥጢረ ምጽአቱን ስለ ገለጠበት አምስተኛው የዐቢይ ጾም ሳምንት ደብረ ዘይት የሚል ስያሜ ተሰጥተታል፡፡ ደብረ ዘይት ጾሙ እኩል የሚኾንበት፤ አምላካችን በግርማ መንግሥቱ ለፍርድ በመጣ ጊዜ መልካም ለሠሩ ክብርን፣ ክፉ ለሠሩ ቅጣቱን የሚያስተላልፍ መኾኑ የሚነገርበት፤ ስለ ዓለም መጨረሻ እና ስለሚመጣው ሕይወት የምንማርበት የክርስቲያኖች ማስጠንቀቂያ ዕለት ነው፡፡

ገብር ኄር

ስድስተኛው ሳምንት ‹ገብር ኄር› የሚል ስያሜ አለው፡፡ ‹ገብር ኄር› ማለት ‹በጎ፣ ታማኝ አገልጋይ› ማለት ነው፡፡ ስያሜው ከማቴዎስ ወንጌል ፳፭፥፲፬ የተወሰደ ሲኾን፣ ታሪኩም እግዚአብሔር በሰጠው ጸጋ በታማኝነት ማገልገል የሚያስገኘውን ዋጋ ያስረዳል፡፡ አንድ ሰው አገልጋዮቹን ጠርቶ ወጥተው፣ ወርደው፣ ነግደው እንዲያተርፉ ለአንዱ አምስት፤ ለአንዱ ሁለት፤ ለአንዱ ደግሞ አንድ መክሊት ሰጣቸው፡፡ አምስት መክሊት የተቀበለው በተሰጠው መክሊት ነግዶ፣ ሌላ አምስት መክሊት አትርፎ፣ ዐሥር አድርጎ፣ ‹‹ጌታዬ አምስት መክሊት ሰጥተኸኝ ነበር፤ ወጥቼ ወርጄ አምስት አትርፌአለሁ›› ብሎ ለጌታው አቀረበ፡፡ ጌታውም ‹‹አንተ ጎበዝ እና ታማኝ ባሪያ! በጥቂቱ ታምነሃልና በብዙ እሾምሃለሁ፤ ወደ ጌታህ ደስታ ግባ!›› አለው፡፡ ሁለት መክሊት የተቀበለውም ወጥቶ፣ ወርዶ፣ አትርፎ አራት አድርጎ አቀረበ፡፡ እርሱንም ጌታው ‹‹አንተ ታማኝ ባሪያ በጥቂቱ ታምነሃልና ወደ ጌታህ ደስታ ግባ!›› አለው፡፡ አንድ የተቀበለው ሰው ግን መክሊቱን ወስዶ ቀበራት፡፡ ጌታው በተቈጣጠረው ጊዜም የቀበራትን መክሊት አምጥቶ ‹‹አንተ ካልዘራህበት የምታጭድ፣ ካልበተንህበት የምትሰበስብ ጨካኝ እንደ ኾንኽ ዐውቃለሁ፡፡ ስለዚህ ፈራሁና የሰጠኸኝን መክሊት ቀበርኳት፤ እነሆ መክሊትህ!›› ብሎ ምንም ሳያተርፍ መክሊቱን ለጌታው መልሶ አስረከበ፡፡ ጌታውም ‹‹አንተ ክፉና ሐኬተኛ ባሪያ! ወርቄን በጊዜው አታስረክበኝም ነበር? ነግዶ ለሚያተርፍ እሰጠው ነበር፡፡ ይህን ክፉና ሐኬተኛ ባሪያ እጅ እግሩን አስራችሁ ጨለማና ጥርስ ማፋጨት ወዳለበት ሥፍራ ውሰዱት! መክሊቱን ቀሙና ለባለ ዐሥሩ ጨምሩለት!›› ብሎ አዘዘ፡፡

በዚህ ታሪክ እንደምናየው በተሰጠው መክሊት ያተረፈ ሰው (ክርስቲያን) ዋጋ አለው፡፡ በፈጣሪው ዘንድ መልካም፣ በጎ፣ ታማኝ ባሪያ ተብሎ ይሸለማል፡፡ ባያተርፍ ደግሞ ሐኬተኛ ባሪያ (አገልጋይ) ይባላል፤ ቅጣቱንም ይቀበላል፡፡ እንግዲህ እኛም ታማኝ አገልጋይ መኾን ይጠበቅብናል፡፡ ሳምንቱ ይህ መልእክት የሚተላለፍበት ወቅት ነው፡፡ በዚህ ዘመን በመክሊታቸው የሚያተርፉ እንዳሉ ዅሉ፣ መክሊታቸውን (ጸጋቸውን) ዝገት እስከሚያጠፋው ድረስ የሚቀብሩ ብዙዎች ናቸው፡፡ መክሊትን (ጸጋን) መቅበር ዋጋ የማያሰጥ መኾኑን ተገንዝበን በቻልነው መጠን ለማትረፍ መትጋት እና ታማኝ አገልጋይ መኾን እንደሚገባን ከገብር ኄር ታሪክ እንማራለን፡፡

ኒቆዲሞስ

ሰባተኛው ሳምንት ‹ኒቆዲሞስ› የሚል ስያሜ ያለው ሲኾን፣ የስያሜው መነሻም በዮሐንስ ወንጌል ምዕራፍ ፫ የተመዘገበው ኒቆዲሞስ የተባለው የአይሁድ አለቃ ታሪክ ነው፡፡ ኒቆዲሞስ በሦስት መንገድ የአይሁድ አለቃ ነበር፤ በሥልጣን፣ በዕውቀትና በሀብት፡፡ ሰው ሥልጣን ቢኖረው ሀብትና ዕውቀት ላይኖረው ይችላል፡፡ ዕውቀት ቢኖረው ደግሞ ሀብትና ሥልጣን ላይኖረው ይችላል፡፡ ሀብት ቢኖረውም ዕውቀትና ሥልጣን ላይኖረው ይችላል፡፡ ኒቆዲሞስ ግን ሦስቱንም አንድ ላይ አስተባብሮ የያዘ የአይሁድ አለቃ ነበር፡፡ ኒቆዲሞስ ወንጌልን ለመማር ከአይሁድ ዅሉ ቀድሞ በሌሊት ወደ ጌታችን ይሔድ ነበር፡፡ ኒቆዲሞስ ፈሪሳውያን ማመን ባልቻሉበት በዚያን ዘመን ጆሮውን ለቃለ እግዚአብሔር፤ ልቡን ለእምነት የከፈተ ሰው ነው፡፡ ብዙ ሰዎችን እናውቃለን ማለት ከመልካም ነገር ሲከለክላቸው ኒቆዲሞስ ግን ዐዋቂ ሳለ ራሱን ዝቅ አድርጎ፣ እምነት በማጣት የነጠፈችውን የፈሪሳውያንን ኅብረት ጥሎ፣ ሐዋርያትን መስሎ ጌታውን አግኝቶታል፡፡ ጌታችን ዓለምን ለማዳን ቅድስት ነፍሱን ከቅዱስ ሥጋው በለየባት በዚያች አስጨናቂ ሰዓት፤ ሐዋርያት በተበተኑባት አይሁድ በሠለጠኑባት በዕለተ ዓርብ የጌታችንን ቅዱስ ሥጋውን በድርብ በፍታ ገንዞ የቀበረ፣ እሱን ያገኘ ያገኘኛል ሳይል በድፍረት ከእግረ መስቀሉ የተገኘ ሰው ነው – ኒቆዲሞስ፡፡ ስለዚህም ሰባተኛው ሳምንት በእርሱ ስም ተሰይሟል፡፡

ሆሣዕና

‹ሆሣዕና› ስምንተኛው የዐቢይ ጾም ሳምንት ሲኾን፣ የሰሙነ ሕማማት መጀመሪያ ነው፡፡ ሆሣዕና ስያሜው በማቴዎስ ወንጌል ፳፩፥፱ ከሚገኘው ትምህርት የተወሰደ ሲኾን ትርጕሙም ‹መድኀኒት ወይም ‹አሁን አድን› ማለት ነው፡፡ ክብር ይግባውና አምላካችን በአህያ ጀርባ ላይ ተቀምጦ ‹‹ሆሣዕና በአርያም›› የሚሉ የአዕሩግ፣ የሕፃናት ምስጋና እየቀረበለት ወደ ኢየሩሳሌም ቤተ መቅደስ ጉዞ ያደረገበት፤ ትሕትናውን የገለጠበት፤ ይህን ዓለም ከማዕሠረ ኃጢአት መፍታቱን በምሳሌ ያስረዳበት ዕለት ነው፡፡ ‹‹ተጽዕኖ›› ተብሎ ከሚጠራው የዐቢይ ጾም መጨረሻ (ዕለተ ዓርብ) እና ከሰሙነ ሕማማት መግቢያ ጀምሮ ያለው ሳምንት ሆሣዕና ይባላል፡፡ የክርስቶስን ነገረ ሕማሙን፣ ስቅለቱን፣ ሞቱን፣ ትንሣኤውን ሆሣዕና ተብሎ ዓለምን ማዳኑን የሚናገሩ ቅዱሳት መጻሕፍት የሚነበቡበት፤ አምላካችን ለሰው ልጅ መዳን መከራ መቀበሉና የማዳን ሥራው በሰፊው የሚታወጅት፤ በሰሙነ ሕማማት ለሚያርፉ ምእመናን ጸሎተ ፍትሐት የሚደረግበት፤ ወንጌል በአራቱ ማዕዘን የሚሰበክበት ሳምንት ነው – ሆሣዕና፡፡ ከዚያው አያይዞም ሰሙነ ሕማማት ይቀጥላል፤ ወቅቱም የክርስቶስን ነገረ ሕማሙንና ዓለምን ያዳነበት ጥበቡን የምንሰማበት ሳምንት ነው፡፡ በሞቱ ሞታችንን አጥፍቶ መንግሥቱን እንድንወርስ የፈቀደልን ልዑል እግዚአብሔር ስሙ የተመሰገነ ይኹን!

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

‹‹ጾመ እግዚእነ አርአያሁ ከመ የሀበነ፤ አርአያነቱን ይሰጠን ዘንድ ጌታችን ጾመ፤›› (ቅዱስ ያሬድ)፡፡

በመምህር ምሥጢረ ሥላሴ ማናየ

መጋቢት ፲፩ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

ጾም በብሉይ ኪዳንም በሐዲስ ኪዳንም በፈጣሪ መኖር ለሚያምኑ፣ የፈጣሪያቸውን ስም ጠርተው ለሚማጸኑ ዅሉ የተሰጠ አምላካዊ ትእዛዝ ነው፡፡ በብሉይ ኪዳን ለሰዎች ከእግዚአብሔር ጋር መገናኛነት ያገለገሉ፣ በነቢያት የተጾሙ አጽዋማት እንዳሉ መጻሕፍት ይመሰክራሉ፡፡ ‹‹ሙሴም ወደ ተራራው ወጣ ዐርባ መዓልትና ዐርባ ሌሊት ቆየ፤›› (ዘጸ. ፳፬፥፲፰) ተብሎ እንደ ተጻፈው ሙሴ በተራራው የቆየው እየጾመ ነበር፡፡ ነቢያት በጾም ከፈጣሪያቸው ጋር ተገናኝተውበታል፡፡ ምንም እንኳን ድኅነተ ነፍስን ማግኘት ባይችሉም በመጾማቸው አባር፣ ቸነፈርን ከሕዝቡ አርቀዋል፡፡ በብሉይ ኪዳን ያሉ አጽዋማት በሙሉ በፍጡራን የተጾሙ ናቸው፡፡ የሐዲስ ኪዳን ጾም ግን የተጀመረው በጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ የብሉይ ኪዳን አጽዋማት ረድኤተ እግዚአብሔር የሚገኝባቸው፣ ለሐዲስ ኪዳን አጽዋማት መነሻና ምሳሌዎች ናቸው፡፡

ቅዱስ ያሬድ ከላይ በርእሱ በተጠቀሰው ኃይለ ቃል እንደ ገለጸው የጌታችን ጾም የሐዲስ ኪዳን አጽዋማት መጀመሪያ ነው፡፡ ይህ ጾም የአጽዋማት ዅሉ በኵር ነው፡፡ በኃጢአት ብዛትና በመርገም በጠወለገ ሰውነት የተጾሙ አጽዋማትን ጌታችን አድሷቸዋል፤ ቀድሷቸዋልም፡፡ ውኃ ከላይ ደጋውን፣ ከታች ቆላውን እንዲያለመልም፣ የጌታችንም ጾም ከላይ ከመጀመሪያ የነበረ የአበውን ጾም ቀድሷል፤ ጉድለቱንም ሞልቷል፡፡ ጌታችን ጾሞ ከእርሱ በኋላ የተነሡ ሐዋርያትን፣ ጻድቃንን፣ ሰማዕታትን፣ ደናግልን፣ መነኮሳትን በአጭሩ የምእመናን ጾም ቀድሷል፡፡ በአጠቃላይ የጌታችን ጾም እንደ በር ነው፡፡ በር ሲከፈት ከውጭ ያለውን እና ከውስጥ ያለውን ያገናኛል፡፡ የጌታችን ጾምም ከፊት የነበሩትን የነቢያትን አጽዋማት ኋላ ከተነሡ ከሐዋርያት አጽዋማት ጋር ያገናኘ፤ በመርገም ውስጥ የነበሩትንና ከመርገም የተዋጁትን ያስተባበረ ጾም ነው፡፡

‹‹ጌታችን የጾመው ለምን ነው?›› የሚለውን ትልቅ ጥያቄ ‹‹አርአያነቱን ይሰጠን ዘንድ ጾመ›› በማለት ቅዱስ ያሬድ መልሶልናል፡፡ ጌታችን የጾመው እንደ ፍጡራን ክብር ለመቀበል ኃጢአት ኖሮበት ስርየት ለማግኘት አይደለም፡፡ አርአያነቱን አይተን፣ ፍለጋውን ተከትለን ልንጠቀምበት ጾምን ቀድሶ ሰጠን፡፡ ጾም ዲያብሎስን ድል የምንነሣበት ጋሻ፣ ከኃጢአት የምንሰወርበት ዋሻ የመንግሥተ ሰማያት መውረሻ፣ መኾኑን አርአያ ኾኖ ሊያሳየን ጌታችን ጾመ፡፡ የጾምንም ጥቅም በግብር (በተግባር) አስተማረን፤ አስረዳን፡፡ ይህ የጌታችን ጾም – ‹ዐቢይ (ታላቅ) ጾም፣ ሁዳዴ፣ ዐርባ ጾም፣ የጌታ ጾም› እየተባለ ይጠራል፡፡ ዐቢይ ጾም ማለት ከግሱ እንደምንረዳው እጅግ ትልቅ ጾም ማለት ነው፡፡ በእርግጥ የጾም ትንሽ የለውም፤ አንድም ቀን ይሁን ሳምንት ጾም ትልቅ ነው፡፡ የጌታችን ጾም የታላቆች ታላቅ፣ የነገሥታት ንጉሥ፣ የጌቶች ዅሉ ጌታ፣ የፍጥረታት ዅሉ ፈጣሪ ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ ጾመው ነው፤ ስምንት ሳምንታን፣ ኀምሳ አምስት ቀናትን በውስጡ የያዘ፣ በቊጥርም ከአጽዋማት ዅሉ እጅግ ከፍ ያለና የሐዲስ ኪዳን አጽዋማት ዅሉ በኵር ስለ ኾነ ዐቢይ (ታላቅ) ጾም ይባላል፡፡

ሁዳድ (የመንግሥት እርሻ)፡- በአንድ መንግሥት የሚተዳደሩ ሕዝቦች በሙሉ በግዳጅ ወጥተው የሚያርሱበት፣ የሚዘሩበት፣ የሚያጭዱበት መሬት እንደ ኾነ ዅሉ ይህም ጾም የጌታችን የመድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን የመንግሥቱን የምስራች በምትነግር ወንጌል ያመኑ ምእመናን በአዋጅ በአንድነት የሚጾሙት ጾም በመሆኑ ‹ሁዳድ› ተብሎ ይጠራል፡፡ ‹ዐርባ ጾም› የተባለበት ምክንያትም ጌታችን የጾመው ዐርባ መዓልትና ዐርባ ሌሊት ስለ ኾነ ነው፡፡ ‹‹ዐርባ መዓልትና ዐርባ ሌሊት ጾመ›› እንዲል (ማቴ. ፬፥፪)፡፡ ጾሙ ስምንት ሳምንታትን ኀምሳ አምስት ቀናትን ያካተተ ነው ብለናል፡፡ ጌታችን የጾመው ዐርባ ቀን ነው፡፡ ለምን ኀምሳ አምስት ቀናት እንጾማለን? የሚሉ ጥያቄዎች በውስጣችን ሊመላለሱ ይችላሉ፡፡

ጌታችን በጾመው ዐርባ ቀን ላይ ቅዱሳን ሐዋርያት ከመጀመሪያው አንድ ሳምንት ከመጨረሻው አንድ ሳምንት ጨምረውበታል፡፡ በዚህ ምክንያት ጾሙ ከስድስት ወደ ስምንት ሳምንታት፣ ከዐርባ ወደ ኀምሳ አምስት ቀናት ከፍ ሊል ችሏል፡፡ ለምን ብለን ጥያቄ ማንሣት የለብንም፡፡ ምክንያቱን ቀኑን የጨመሩት ከጌታችን ጋር የዋሉ በቃልም፣ በተግባርም ከጌታችን የተማሩት፣ የምሥጢር ደቀ መዛሙርት፣ የሕግ ምንጮች፣ እኛ ወደ ክርስቶስ የምናደርገው ጉዞ መሪዎች ቅዱሳን ሐዋርያት ናቸውና፡፡ እኛ የክርስትና ተቀባዮች እንጂ ጀማሪዎች ወይም መሥራቾች አይደለንም፡፡ በቅዱሳን ሐዋርያት መሠረትነት ላይ ተመሠረትን እንጂ፡፡ ‹‹እናንተስ በነቢያትና በሐዋርያት መሠረትነት ላይ ተመሥርታችኋል›› እንዳለ ቅዱስ ጳውሎስ (ኤፌ. ፪፥፳)፡፡ እናም ሕጋቸውንና ሥርዓታቸውን አምነን ከመቀበል ውጭ መቃወም አይቻለንም፡፡ የብሎኬት ድርድር መሠረት አያስፈልገኝም ሊል አይችልም፡፡ መሠረቱ ከተናደ ድርድሩ የት ሊቆም ይችላል? እኛም የሐዋርያትን ትእዛዝ ካልተቀበልን የማንን ትእዛዝ እንቀበላለን?

ቅዱሳን ሐዋርያት ከመጀመሪያው የጨመሩት የጌታችን ጾም መግቢያ መቀበያ ንጉሥ ሲመጣ በሠራዊት እንዲታጀብ፣ በብዙ ሕዝብ እንዲከበብ፣ ሕዝቡ ከፊት ከኋላ ከበውና አጅበው በክብር እንደሚቀበሉትና እንደሚሸኙት ዅሉ የንጉሣችን የኢየሱስ ክርስቶስ ጾም ሲመጣም እንደ ሕዝብ፣ እንደ ሠራዊት የሚያጅቡ፣ የሚከቡ፣ የሚያከብሩ ሳምንታትንና ዕለታትን ማለትም ከመጀመሪያው ዘወረደን፤ ከመጨረሻው ደግሞ ሕማማትን ጨምረዋል፡፡ ደግሞም መልካም ምግባርንም ኾነ የጾምን ቀን መቀነስ እንጂ መጨመር አያስቀጣም፡፡ በክርስትና ሕይወት የተቀበሉትን መክሊት መቅበር እንጂ አትርፎ ማቅረብ ያስከብራል፤ ገብር ኄር (ታማኝ አገልጋይ) ያሰኛል፤ ያሾማል፤ ያሸልማል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡