በዓለ ትንሣኤን በትንሣኤ ልቡና እናክብር

በገብረ እግዚአብሔር ኪደ

ሚያዝያ ፲፰ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

 ፋሲካ ማለት መሻገር ማለት ነው፡፡ እግዚአብሔር ወልድ እኛን ከወደቅንበት አንሥቶና ተሸክሞ ከዚኽ ምድር ወደ ሰማያት ተሻግሯልና (ተነሥቶ ዐርጓልና)፡፡ ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስ፡- ‹‹እንግዲኽ ከክርስቶስ ጋር ከተነሣችኁ ክርስቶስ በእግዚአብሔር ቀኝ ተቀምጦ ባለበት በላይ ያለውን ሹበላይ ያለውን አስቡ እንጂ በምድር ያለውን አይደለም፡፡ ሞታችኋልና ሕይወታችኁም በእግዚአብሔር ከክርስቶስ ጋር ተሰውሯልና፡፡ ሕይወታችኁ የኾነ ክርስቶስ በሚገለጥበት ጊዜ እናንተ ደግሞ ከእርሱ ጋር በክብር ትገለጣላችኁ፤›› እንዳለን /ቈላ.፫÷፩-፬/፣ በጥምቀት ውኃ ሞቱን በሚመስል ሞት ስንሞት፣ አሮጌው ሰውነታችን እንደ ግብጻውያን ተቀብሮ ቀርቷል፡፡ አዲሱ ሰውነታችን ግን እስራኤላውያን ባሕሩ ተከፍሎላቸው እንደ ተሻገሩ ተሻግሯል (ተነሥቷል)፡፡

ብልየት ያለበት የቀዳማዊ አዳም ሰውነታችን በግብረ መንፈስ ቅዱስ ተቀብሮ አዲሱ ሰውነታችን ሕይወትን አግኝቶ ተነሥቷል፡፡ መሬታዊው ሰውነታችን ሞቶ ሰማያዊው ሰውነታችንን ለብሰን መንፈሳውያን ኾነን ተነሥተናል፡፡ ወደ ጥንተ ተፈጥሯችን ተመልሰናል፡፡ አኹን ከእኛ የሚጠበቀው ይኽ ተፈጥሯችንን ሳናቆሽሽ መጠበቅ ነው፤ እንደ ተነሣን መዝለቅ፡፡ ይኽን ለማድረግም ተራራ መውጣት፣ ምድርን መቆፈር፣ የእሳት ባሕርን መሻገር አይጠበቅብንም፡፡ ይኽን ጠብቀን እንድንቈይ እግዚአብሔር ከእኛ የሚፈልገው አንድ ነገር ብቻ ነው፤ ፈቃዳችንን፡፡ የሚሠራው እርሱ ራሱ ነውና /ዮሐ.፲፭÷፭/፡፡ መጽንዒ (የሚያጸና) መንፈስ ቅዱስን ያደለንም ስለዚኹ ነው፡፡

የምናመልከውን አምላክ መስለን በሕይወት ሳንሻገር የመሻገርን በዓል (ፋሲካን) የምናከብረው ምን ጥቅም እንዲሰጠን ነው? ከጨለማ ሥራ ወደ ብርሃን ሥራ፣ ከፍቅረ ዓለም ወደ ፍቅረ ክርስቶስ ሳንሻገር ፋሲካን የማክበራችን ትርጕሙ ምንድነው? እኛው ሳንነሣ የመነሣት በዓልን ማክበራችን በፍርድ ላይ ፍርድ በበደል ላይ በደል ከመጨመር ውጪ የሚሰጠን ጥቅም ምንድን ነው? የምንነሣውስ መቼ ነው? በዐይናችን ጉድፍ ብትገባ ስንት ደቂቃ እንታገሣታለን? ታድያ በነፍሳችን ላይ የተጫነውን የኃጢአት ግንድ መቼ ነው የምናስወግደው? መቼ ነው ወደ ላይኛው ቤታችን ቀና የምንለው? ብዙዎቻችን በሕይወታችን ሳንሻገር ነው በዓለ ፋሲካን የምናከብረው፡፡ ክርስቲያን ኾኖ በመብልና በመጠጥ ብቻ ፋሲካን ማክበር ኢ ክርስቲያናዊ ተግባር ነው፡፡

አዲሱን ሰውነታችን ለብሰን ከተነሣን በኋላ እንደ ቀድሞ ምልልስ የምንጓዝ ከኾነ ግን ተመልሰን ወድቀናል፤ አዲሱ ሰውነታችንን አውልቀን አሮጌውን ሰውነታችንን በድጋሜ ለብሰነዋል፡፡ በእኛነታችን ውስጥ ፍቅረ ንዋይ፣ ፍቅረ ሲመት፣ ፍትወት፣ ይኽንንም የመሰሉ ዅሉ ካለ አዲሱ ሰውነታችን ከእኛ ጋር የለም፤ ቢኖርም ታሟል፡፡ በኃጢአት የመቃጠል ስሜት፣ ርኵሰትና ክፉ ምኞት ከእኛ ዘንድ ካለ አሮጌ ሰው ኾነናል፤ ትንሣኤ ልቡናን ገንዘብ አላደረግንም፡፡ ስለዚኽ ከልቡና ሞት እንነሣና ፋሲካን እናክብር፡፡ እስከ አኹን በኃጢአት ውስጥ ካለን ወደ ብርሃን ክርስቶስ እንምጣ (እንሻገርና) የመሻገርን በዓል እናክብር፡፡ ከክፉ ሥራ ወደ ጽድቅ ሥራ እንሻገርና የእውነት ፋሲካን እናክብር፡፡ ከኃይል ወደ ኃይል እንሻገርና ፋሲካን እናክብር፡፡ ከሞት ሥራ ወደ ሕይወት ሥራ እንነሣና የመነሣትን በዓል እናክብር፡፡

እግዚአብሔር የሚወዳችሁ አንድም እግዚአብሔርን የምትወዱት ሆይ! እኛን የሚያሰነካክል ደግሞም የሚጥለን ፈርዖን (ዲያብሎስ) ተሰነካክሎ ወድቋልና ከግብጽ ሕይወታችን እንውጣ፡፡ ተነሥተንም እንሻገር፡፡ ተሻግረንም ሰማያዊውን ፋሲካ እናክብር፡፡ በግብጽ የነበሩት እስራኤላውያን የበጉን ደም በጉበኑና በኹለቱም መቃን ሲቀቡት አጥፊው ከቤታቸው እንዳለፈ አንብበናል /ዘፀ.፲፪÷፲፫/፡፡ ይኸውም በጉ በራሱ ያንን የማድረግ ኃይል ስለ ነበረው አይደለም፤ ደሙ የክርስቶስ ደም አምሳል ስለ ነበር ነው እንጂ፡፡ እኛ ግን የአማናዊውን በግ /ዮሐ.፩፡፳፱/ ደም በልቡናችን፣ በአስተሳሰባችንና በሰውነታችን ዅሉ እንቀባና (እንቀበልና) እንሻገር፡፡

ይኽን ስናደረግ በእባቡና በጊንጡ ይኸውም በዲያብሎስና በሠራዊቱ ላይ ሥልጣን ይኖረናል /ሉቃ.፲÷፲፱/፡፡ የምንበላው በግ ራሱ ሕይወት ስለ ኾነ ሞት በእኛ ላይ አይነግሥም /ዮሐ.፲፬÷፮/፡፡ በዚኽ ዓለም ሳለን ከዚኽ ደስታ ተካፋዮች ከኾንን (የመዠመሪያውን ትንሣኤ ልቡና በንስሐ ከተነሣን) በሚመጣው ዓለምም በክብር ላይ ክብር፣ በሹመት ላይ ሹመት እንቀበላለን (ኹለተኛውን ትንሣኤ እንነሣለን) /ሉቃ.፳፪÷፲፭-፲፮/፡፡ ብንወድቅ እንኳን መልሰን በመነሣት ከባሕርይ አባቱ ከአብ፣ ከባሕርይ ሕይወቱ ከመንፈስ ቅዱስ ጋር ክብር፣ የክብር ክብር፣ ጌትነት የባሕርዩ በሚኾን፤ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ሰጭነት በመንግሥተ ሰማያት ጸጋ ክብር እናገኛለንና የጭንቅ ቀን ሳይመጣ በዓለ ትንሣኤን እናክብር፡፡ ለዚህም ሊቁ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ የመከረንን የሚከተለውን ኃይለ ቃል በተግባር ላይ ብናውለው እንጠቀማለን፤

‹‹በምነግራችኁ ነገር እያበሳጨኋችሁና እያሳመምችሁ እንደ ኾነ ይገባኛል? ግን ምን ላድርግ? እኔም እናንተም በምግባር በሃይማኖት የታነጽን እንኾን ዘንድ ብቻ ሳይኾን ከዚያም እናመልጥ ዘንድ ነው፡፡ ነገር ግን በኃጢአት ከመጨማለቃችን የተነሣ እንዴት አድርጌ ላሳምማችኁ እችላለኁ? ብትሰሙኝና ብትለወጡስ እኔም ማረፍ እንኳን በቻልኩ ነበር፡፡ ስለዚኽ እስካልተለወጣችሁ ድረስ እናንተን መገሠንና መምከሬን አላቆምም፡፡ ስለ ገነመ እሳት ተደጋግሞ ሲነገር የሚበሳጭ ሰው ሊኖር ይችላል፡፡ እኔ ግን ከዚኽ የበለጠ ያማረ የተወደደ አስደሳች ትምህርት የለም እለዋለኁ፡፡ እንዴት ይኽ አስደሳች ትምህርት ነው ትለናለህ? ልትሉኝ ትችላላችሁ፡፡ እኔም ወደዚያ መጣል ከደስታ ዅሉ የራቀ ነውናብዬ እመልስላችኋለሁ፡፡ ስለዚኽ ነፍሳችን ከመታሠሯ በፊት የነቃን የተጋን እንኾን ዘንድ ይኽን ደጋግሜ እነግራችኋለሁ፡፡ ስሐ ይግባ እንጂ ማንም እንደ ተወቀሰ አያስብ፤ በንግግሬም የሚቆጣ አይኑር፡፡ ዅላችንም ወደ ጠባቢቱ መንገድ እንግባ፡፡ እስከ መቼስ በስንፍና አልጋ እንተኛለን? ዛሬ ነገ ማለት አይበቃንም ወይ? ሰማያዊ ቪላችንን ቀና ብለን ብንመለከት እኮ በዚኽ ምድር ይኽንን ለመሥራት ባልደከምን ነበር፡፡ እስቲ ንገሩኝ! ሩጫችንን ስንጨርስ ከሬሳ ሳጥንና ከመግነዝ ጨርቅ ውጪ ይዘነው የምንሔድ ነገር ምን አለ? ታድያ ለምን እንከራከራለን?›› (ሰማዕትነት አያምልጣችሁ እና ሌሎች፣ ገጽ ፻፶፮ – ፻፶፯)፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ሰሙነ ፋሲካ (ከዕለተ ትንሣኤ እስከ ዳግም ትንሣኤ)

በሊቀ ትጉሃን ኃይለ ጊዮርጊስ ዳኘ

ሚያዝያ ቀን ፳፻፱ .

ከትንሣኤ እሑድ ቀጥለው ያሉት ዕለታት ‹ሰሙነ ፋሲካ› ወይም ‹ትንሣኤ› እየተባሉ የሚጠሩ ሲኾን፣ የየራሳቸው ምሥጢራዊ ስያሜም አላቸው፡፡ ስያሜአቸውንም በአጭሩ እንደሚከተለው እንመለከታለን፤

ሰኞ

የትንሣኤው ማግሥት ሰኞ ጌታችን በትንሣኤው ነፍሳትን ከሲኦል አውጥቶ ወደ ገነት አሻግሮ ለማስገባቱ መታሰቢያ ሰትኾን፣ ‹ፀአተ ሲኦል› ወይም ‹ማዕዶት› ትባላለች (ዮሐ. ፲፱፥፲፰፤ ሮሜ. ፭፥፲-፲፯)፡፡

በዳግም ትንሣኤው ማግሥት ያለችው ሰኞ ደግሞ ገበሬው፡- ወንዶቹ እርሻ ቁፋሮውን፣ ንግዱን፣ ተግባረ እዱን ዅሉ፤ ሴቶቹ፡- ወፍጮውን፣ ፈትሉን፣ ስፌቱን የሚጀምሩባት ዕለት ስለ ኾነች ‹እጅ ማሟሻ ሰኞ› ትባላለች፡፡

ማክሰኞ 

የትንሣኤው ዕለት እሑድ ማታ ጌታችን በዝግ ቤት ገብቶ ለሐዋርያት ሲገለጽ ሐዋርያው ቶማስ ከእነርሱ ጋር አልነበረም፡፡ በኋላ ከሔደበት ሲመጣ ሌሎቹ ሐዋርያት ትንሣኤውን ቢነግሩት ‹‹እኔ ሳላይ አላምንም›› ብሎ ነበር፡፡ በሳምንቱ ቶማስ በተገኘበት ጌታችን በድጋሜ ለሐዋርያት ተገለጸ፡፡ ስለዚህም ይህቺ ዕለት በሐዋርያው ቶማስ ስም ተሰይማለች (ዮሐ. ፳፥፳፬-፴)፡፡ 

ረቡዕ 

ጌታችን ከሞተና ከተቀበረ ከአራት ቀን በኋላ ከመቃብር ጠርቶ ላስነሣው ለአልዓዛር መታሰቢያ ትኾን ዘንድ፤ በክርስቶስ ሥልጣን የአልዓዛርን ከሞት መነሣት አይተው ብዙ ሕዝብ በጌታችን ስለ አመኑ ዕለቲቱ (ረቡዕ) ‹አልዓዛር› ተብላ ትታሰባለች (ዮሐ. ፲፩፥፴፰-፵፮)፡፡ 

ኀሙስ 

ይህቺ ዕለት ‹‹ከአምስት ቀን ተኩል በኋላ (አምስት ሺሕ ከአምስት መቶ ዓመት ሲፈጸም) ከልጅ ልጅህ ተወልጄ አድንሃለሁ፤›› ተብሎ ቃል የተገባለት የአዳም ተስፋው ተፈጽሞ ከነልጅ ልጆቹ ወደ ቀደመ ክብሩ ለመግባቱ መታሰቢያ ኾና ‹የአዳም ኀሙስ› ወይም ‹አዳም› ተብላ ትከበራለች (ሉቃ. ፳፬፥፳፭-፵፱)፡፡

ዐርብ

ከሆሣዕና ቅዳሜ በፊት ያለችው ዐርብ ደግሞ የጌታችን ዐርባው ጾም የሚፈጸምባት የጾመ ድጓው ቁመትም የሚያበቃባት ዕለት በመኾኗ በቤተ ክርስቲያን ‹ተጽዒኖ› ትባላለች፡፡ የከባድ ሥራ ማቆሚያ (ማብቂያ) ዕለት በመኾኗም በሕዝቡ ዘንድ ‹የወፍጮ መድፊያ፣ የቀንበር መስቀያ› ትባላለች፡፡

ዳግኛም በመጀመርያ የሰው ልጆች አባትና እናት የኾኑት አዳምና ሔዋን ስለተፈጠሩባት፤ በኋላም በሐዲስ ኪዳን ጌታችን ለቤዛ ዓለም ስለ ተሰቀለባትና የማዳን ሥራውን ስለ ፈጸመባት ‹ዕለተ ስቅለት፣ አማናዊቷ ዐርብ› ትባላለች፡፡

የሰሙነ ፋሲካዋ ማለትም የትንሣኤ እሑድ ስድስተኛዋ ዐርብ ደግሞ በክርስቶስ ደም ለተመሠረተችው ቅድስት ቤተ ክርስቲያን መታሰቢያ ትኾን ዘንድ ‹ቤተ ክርስቲያን› ተብላ ትጠራለች (ማቴ. ፳፮፥፳፮-፳፱፤ ሐዋ. ፳፥፳፰)፡፡

ቀዳሚት ሰንበት

በሰሙነ ፋሲካው ያለችው ቀዳሚት ሕዝቡ ከአንዳንዱ በስተቀር ገበያ እንኳን ስለማይገበያይባት ‹የቁራ ገበያ፣ የገበያ ጥፊያ› ስትባል፣ በቤተ ክርስቲያን ግን በዘመነ ሥጋዌው በገንዘባቸውና ጉልበታቸው ላገለገሉት፤ በስቅለቱ ዋይ ዋይ እያሉ እስከ ቀራንዮ ድረስ ለተከተሉት፤ በትንሣኤው ዕለት በሌሊት ወደ መቃብሩ ሽቱና አበባ ይዘው ለገሰገሱት፤ በትንሣኤውም ጌታችን ከዅሉ ቀድሞ ለተገለጸላቸው ቅዱሳት አንስት መታሰቢያ ኾና ‹ቅዱሳት አንስት› ተብላ ትጠራለች (ማቴ. ፳፭፥፩-፲፩፤ ሉቃ. ፳፫፥፳፯-፴፫፤ ፳፬፥፩-፲)፡፡

የዋናው ትንሣኤ ሳምንት እሑድ

በዚህች ሰንበት ከላይ እንደ ተጠቆመው ጌታችን በትንሣኤው ዕለት ማታ በዝግ በር ገብቶ፣ በቅዱሳን ሐዋርያት መካከል ተገኝቶ «ሰላም ለዅላችሁ ይኹን!» ብሎ ትንሣኤውን ሲገልጽላቸው ሐዋርያው ቶማስ አልተገኘም ነበር፡፡

በኋላ ከሔደበት ሲመጣ ጌታችን እንደ ተነሣ እና እንደ ተገለጸላቸው ሐዋርያት በደስታ ሲነግሩት «በኋላ እናንተ ‹አየን› ብላችሁ ልትመሰክሩ፤ ልታስተምሩ፤ እኔ ግንሰምቼአለሁ› ብዬ ልመሰክር፤ ላስተምር? አይኾንም፡፡ እኔም ካላየሁ አላምንም» በማለቱ የሰውን ዅሉ፤ ይልቁንም የመረጣቸው ወዳጆቹን የልብ ሐሳብ የሚያውቀው፣ ቸርነቱ ወሰን የሌለው የባሕርይ አምላክ መድኃኔ ዓለም ክርስቶስ ልክ እንደ መጀመሪያው ትንሣኤ ዕለት አበው ሐዋርያት በተዘጋ ቤት በአንድነት ተሰባስበው እንዳሉ በሩን ሳይከፍት ገብቶ «ሰላም ለዅላችሁ ይኹን!» በማለት በመካከላቸው ቆመ፡፡

ቶማስንም «ያመንህ እንጂ ተጠራጣሪ አትኹን፤ እነሆ የተቸነከሩ እጆቼንና እግሮቼን፣ የተወጋ ጐኔንም ናና እይ፤» ብሎ አሳየው፡፡ እርሱም ምልክቱን በማየቱ፣ በመዳሰሱ ትንሣኤውንና አምላክነቱን እንደ ፍላጎቱ በመረዳቱ «ጌታዬ፣ አምላኬ ብሎ መስክሮ» አመነ፡፡ ስለዚህም ማለትም የትንሣኤው ምሥጢር ለሁለተኛ ጊዜ ለሐዋርያት የተገለጠበት ዕለት በመኾኑ የትንሣኤው ሳምንት እሑድ ‹ዳግም ትንሣኤ› ተብሎ ይጠራል፤ ይከበራል (ዮሐ. ፳፥፳፬-፴)፡፡

በአጠቃላይ በቅድስት ቤተ ክርስቲያን በሰሙነ ፋሲካ የሚፈጸመው መንፈሳዊና ሐዋርያዊ አገልግሎት ዅሉ ልክ እንደ መጀመሪያው የትንሣኤ ሥርዓት ኾኖ ይከናወናል፡፡ ብርሃነ ትንሣኤውን የገለጸልን አምላካችን ለብርሃነ ዕርገቱም በሰላም ያድርሰን!

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

የትንሣኤ በዓል ትርጕሙና አከባበሩ

በሊቀ ትጉሃን ኃይለ ጊዮርጊስ ዳኘ

ሚያዝያ ፲ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

እንኳን ለብርሃነ ትንሣኤው በሰላም አደረሰን!

«ትንሣኤ» የሚለው ቃል የግእዝ ቃል መገኛው ‹ተንሥአ = ተነሣ› የሚለው ግስ ሲኾን፣ ትርጕሙም መነሣት፣ አነሣሥ፣ አዲስ ሕይወትን ማግኘት ማለት ነው፡፡ ‹ትንሣኤ› በየመልኩ፣ በየዓይነቱ ሲተረጐም አምስት ክፍል አለው፤

የመጀመርያው ትንሣኤ ሕሊና ነው፤ ይህም ማለት ተዘክሮተ እግዚአብሔር (እግዚአብሔርን ማሰብ) ነው፡፡

ሁለተኛውም ትንሣኤ ልቡና ነው፤ የዚህም ምሥጢሩ ቃለ እግዘብሔርን መስማትና በንስሐ እየታደሱ በሕይወት መኖር ነው፡፡

ሦስተኛው ትንሣኤ ለጊዜው (በተአምራት) የሙታን በሥጋ መነሣት ነው፡፡ ነገር ግን በድጋሜ ሌላ ሞት ይከተለዋል፡፡

አራተኛው ትንሣኤ ክርስቶስ በሥልጣኑ ሞትን ድል አድርጎ መነሣቱን ያመላክታል፡፡ የርእሰ ትምህርታችን መነሻም ይህ ነው፡፡

አምስተኛውና የመጨረሻው የትንሣኤ ደረጃ የባሕርይ አምላክ የጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ትንሣኤ መሠረት ያደረገ ትንሣኤ ዘጉባኤ ሲኾን፣ ይህም ከዓለም ኅልፈት በኋላ ሰው ዅሉ እንደየሥራው ለክብርና ለውርደት፣ ለጽድቅና ለኵነኔ በአንድነት የሚነሣው የዘለዓለም ትንሣኤ ነው፡፡

ወደ ርእሳችን ስንመለስ የትንሣኤ በዓል በምሥጢሩም፣ በይዘቱም ከኦሪቱ በዓለ ፋሲካ ጋር ስለሚመሳሰል ‹ፋሲካ› ተብሎ ይጠራል፡፡ ‹ፋሲካ› ማለት በዕብራይስጥ ቋንቋ ‹ፌሳሕ›፤ በጽርዕ (በግሪክ) ‹ስኻ› ይባላል፡፡ ይህም ወደ እኛው ግእዝና አማርኛ ቋንቋችን ሲመለስ ፍሥሕ (ደስታ)፣ ዕድወት፣ ማዕዶት (መሻገር፣ መሸጋገር)፣ በዓለ ናእት (የቂጣ በዓል፣ እየተቸኮለ የሚበላ መሥዋዕት) ማለት ነው፡፡ የዚህም ታሪካዊ መነሻው በዘመነ ኦሪት ይከበር የነበረው በዓለ ፋሲካ ሲኾን፣ ይህም እስራኤል ዘሥጋ ከግብጽ የባርነት ቀንበር ወደ ነጻነት የተላለፉበት፤ ከከባድ ኀዘን ወደ ፍጹም ደስታ የተሸጋገሩበት በዓል ነው፡፡ በዚህ ኦሪታዊ (ምሳሌ) በዓል አሁን አማናዊው በዓል በዓለ ትንሣኤ ተተክቶበታል፡፡

ፋሲካ (በዓለ ትንሣኤ) በዘመነ ሐዲስ እስራኤል ዘነፍስ የኾንን ምእመናን የክርስቶስን ትንሣኤ የምናከብርበት ዕለት ነው፡፡ ይህ በዓል ከኃጢአት ወደ ጽድቅ፤ ከውርደት ወደ ክብር፤ ከጠላት ሰይጣን አገዛዝ ወደ ዘለዓለማዊ ነጻነት፤ ከአደፈ፣ ከጐሰቆለ አሮጌ ሕይወት ወደ አዲስ ሕይወት የተሻገርንት ከበዓላት ዅሉ የበለጠ የነጻነት በዓል ነው፡፡ ስለዚህም ክርስቲያኖች በታላቅ ደስታና መንፈሳዊ ስሜት በዓሉን እናከብረዋለን፡፡

መድኃኒታችን ሞትን በሞቱ ድል ነስቶ፣ ሙስና መቃብርን አጥፍቶ፣ በሥልጣኑ የተነሣው መጋቢት ፳፱ ቀን በ፴፬ ዓ.ም እንደ ኾነ ታሪከ ቤተ ከርስቲያን ያስረዳል፡፡ የትንሣኤ በዓል መከበር የጀመረው በቅዱሳን ሐዋርያትና በሰብዐ አርድእት፣ ኋላም በየጊዜው በተነሡ ሊቃውንትና ምእመናን ነው፡፡ ድምቀቱና የአከባበር ሥርዓቱ ይበዛ፣ ይቀነስ እንደ ኾነ እንጂ በዓሉ መከበሩ ተቋርጦ አያውቅም፡፡

በቅብብሎሽ ከዚህ በደረሰው ትውፊት መሠረት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በሰሙነ ሕማማት ግብረ ሕማማቱን ስታነብ ሰንብታ ለትንሣኤ እሑድ አጥቢያ ማታ በ፪ ሰዓት «ለጸሎት ተሰብሰቡ» ስትል የደወል ድምፅ ታሰማለች፡፡ ካህናቱም በቤተ ክርስቲያን ተሰብስበው ሥርዓቱን በጸሎት ይጀምራሉ፡፡ ሕዝቡም በቤተ ክርስቲያን ይሰባሰባል፡፡ ካህናቱ መዝሙረ ዳዊት፣ ነቢያት፣ ሰሎሞንና ውዳሴ ማርያም ከተደረሰ በኋላ «ተፈሥሒ ማርያም ለአዳም ፋሲካሁ» የሚለውን ግጥማዊ የደስታ መዝሙር ይዘምራሉ፡፡

ምንባቡ፣ ጸሎቱና ሌላውም ሥርዓት ከተፈጸመ በኋላ ጸሎተ አኰቴት ተደርሶ ዲያቆኑ ነጭ ልብሰ ተክህኖ ለብሶ፣ አክሊል ደፍቶ፣ መስቀል ይዞ፣ በጌታችን መቃብር በራስጌና በግርጌ በታዩት መላእክት ምሳሌ እንደ እርሱው ነጭ ልብሰ ተክህኖ በለበሱ፣ ድባብ ጃንጥላ በያዙ፣ መብራት በሚያበሩ ሁለት ዲያቆናት ታጅቦ በቅድስት ቆሞ፡- «ወተንሥአ እግዚአብሔር ከመ ዘንቃህ እምንዋም፣ ወከመ ኀያል ወኅዳገ ወይን፣ ወቀተለ ፀሮ በድኅሬሁ፤ እግዚአብሔር ከእንቅልፍ እንደሚነቃ ተነሣ፤ የወይን ስካር እንደ ተወው ኃያል ሰውም ጠላቱን በኋላው ገደለ፤» የሚለውን የዳዊት መዝሙር በረጅም ያሬዳዊ ዜማ ይሰብካል (መዝ. ፸፯፥፷፭)፡፡

ካህናቱም ከበሮ እየመቱና በእርጋታ እያጨበጨቡ ተቀብለው ይዘምራሉ፡፡ ሕዝቡም በጭብጨባና በዕልልታ የደስታ ዝማሬው ተሳታፊ ይኾናል፡፡ ይህ ምስባክ በዲያቆኑና በመላው ካህናት ሁለት ሁለት ጊዜ፤ በዲያቆኑና በመላው ካህናት አንድ ጊዜ (በጋራ) ይዘመራል፡፡ ይህም በድምሩ አምስት መኾኑ አምስት ሺሕ አምስት መቶ ዘመን ሲፈጸም በጌታችን ሞትና ትንሣኤ ዓለም ለመዳኑ ምሳሌያዊ ማስረጃ ነው፡፡ በመቀጠል ካህኑ ትንሣኤውን የሚያበሥር ትምህርት ከማቴዎስ፣ ከማርቆስና ከሉቃስ ወንጌል አውጥቶ ያነባል፡፡ የዮሐንስ ወንጌል በቅዳሴ ጊዜ ይነበባል (ዮሐ. ፳፥፩-፱)፡፡

በማስከተል ከሊቃውንቱ መካከል ሥራው የሚመለከተው ወይም የተመደበው ባለሙያ (መዘምር) መስቀል ይዞ «ትንሣኤከ ለእለ አመነ» የሚለውን እስመ ለዓለም ከቃኘ በኋላ ለበዓሉ ተስማሚ የኾነው አርያም ተመርቶ በመቋሚያ ይዘመማል፡፡ ከዚያም «ዮም ፍሥሐ ኮነ በሰንበተ ክርስቲያን፣ እስመ ተንሥአ ክርስቶስ እሙታን = ክርስቶስ ከሙታን ተለይቶ ተነሥቷልና በሰንበተ ክርስቲያን ዛሬ ደስታ ኾነ …፤» የሚለው አንገርጋሪ በመሪና በተመሪ ይመለጠናል፤ በግራ በቀኝ እየተነሣ ይዘመማል፤ ይጸፋል፡፡

በዚህ ጊዜ «በጨለማ የነበራችሁ ሕዝቦች የትንሣኤውን ብርሃን እዩ፤ ብርሃኑንም ወስዳችሁ የብርሃኑ ተካፋይ ኹኑ፤» እያለች ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ያዘጋጀችውን ጧፍ እያበራች ታድላቸዋለች፡፡ ወዲያውኑም ‹‹ትንሣኤከ ለእለ አመነ ብርሃነከ ፈኑ ዲቤነ = ለአመነው ለእኛ ብርሃንህን ላክልን፤›› የሚለውን እስመ ለዓለም እየዘመሩ፣ መብራት እያበሩ ካህናቱና ሕዝቡ ዑደት ያደርጋሉ (ቤተ ክርስቲያኑን ይዞራሉ)፡፡

መዘምራኑና ካህናቱ ከዑደት ሲመለሱ «ይእቲ ማርያም» የተባለው የኪዳን ሰላም ይጸፋና ኪዳን ተደርሶ ሲያበቃ እንደ ቦታው ደረጃ ፓትርያርክ ወይም ሊቀ ጳጳስ ወይም ቆሞስ ወይም ቄስ ዘለግ ባለ ድምፅ በንባብ «ክርስቶስ ተንሥአ እሙታን = ክርስቶስ ከሙታን ተለይቶ ተነሣ» ሲሉ ካህናቱና መዘምራኑ ‹‹በዐቢይ ኃይል ወሥልጣን = በታላቅ ኃይልና ሥልጣን» ብለው ይቀበላሉ፡፡ አሁንም ካህኑ «አሰሮ ለሰይጣን = ሰይጣንን አሰረው» ባለ ጊዜ መላው ካህናት «አግዐዞ ለአዳም = አዳምን አርነት ነጻ አወጣው» ይላሉ፡፡

በመቀጠል «ሰላም = ሰላም፣ አንድነት፣ ፍቅር» ሲሉ ዅሉም «እምይእዜሰ = ከዛሬ ጀምሮ» ብለው ይቀበላሉ፡፡ ካህኑም «ኮነ ፍሥሐ ወሰላም = ሰላምና ደስታ» ብለው ሦስት ጊዜ አውጀው «ነዋ መስቀለ ሰላም» እያሉ መስቀል ሲያሳልሙ ካህናቱና ሕዝቡም «ዘተሰቅለ ቦቱ መድኃኔ ዓለም» እያሉ ይሳለማሉ፡፡ ካህኑም «እግዚአብሔር ይፍታ» ይላሉ፡፡ ግብረ ሕማማት ሲነበብበት ከሰነበተው ጠበልም ይረጫል፡፡ የተረፈውንም ጠበል ሕዝቡ ለበረከት ወደየቤቱ ይወስደዋል፡፡

ከዚያም ልኡካኑ ለቅዳሴ እየተዘጋጁ መዘምራኑ ምስባክ መወድሱን ካዜሙ በኋላ በመቋሚያ ይዘሙታል፡፡ አያይዞም ይትፌሣሕ› የተባለውን መዝሙር ቃኝተው ከዘመሙ በኋላ «… ወምድርኒ ትገብር ፋሲካ፤ ተኀፂባ በደመ ክርስቶስ = … ምድርም በክርስቶስ ደም ታጥባ ፋሲካውን ታደርጋለች፤» እያሉ ይጸነጽላሉ፡፡ አያይዘውም የመዝሙሩን ሰላም ይጸፋሉ፡፡ መንፈቀ ሌሊት ሲኾንም ቅዳሴ ተቀድሶ ሥርዓተ ቍርባን ይፈጸማል፡፡ ከዚያም ሠርሖተ ሕዝብ = የሕዝብ ስንብት ከኾነ በኋላ ካህናቱም ሕዝቡ ወደየቤታቸው ሔደው እንደየባህላቸው ይፈስካሉ (ይገድፋሉ)፡፡

የመግደፊያ ዝግጅት ለሌላቸው ነዳያንም በየመንደሩ እየተዞረ «እንኳን ለብርሃነ ትንሣኤው በሰላም አደረሳችሁ» እየተባለ ከሥጋውም፣ ከአይቡም፣ ከቅቤውም ከመጣጣሙም፣ ከእርጐውም ይታደላል፡፡ ከትንሣኤ እሑድ ጀምሮ እስከ ዳግም ትንሣኤ ድረስ ሕዝበ ክርስቲያኑ «እንኳን ለብርሃነ ትንሣኤው በሰላም አደረሳችሁ» እየተባባለ በዚህ መልኩ አብሮ እየበላ፣ እየጠጣ፣ እየተደሰተ እግዚአብሔርን ሲያመሰግን ይሰነብታል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ቀዳሚት ሥዑር

በመምህር ቸሬ አበበ

ሚያዝያ ፮ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

ዕለተ ቅዳሜ እግዚአብሔር አምላካችን የሚታዩትንና የማይታዩትን፣ በእግር የሚሔዱትን፣ በክንፍ የሚበሩትን እና በባሕር የሚዋኙትን እንስሳትን፣ በመጨረሻም ሰውን በአርአያውና በአምሳሉ ፈጥሮ ያረፈባት ዕለት ነች፡፡ የመጀመሪያዋ ቅዳሜ ለእግዚአብሔር የዕረፍት ዕለት ናት፡፡ እግዚአብሔርን ፍጥረታትን ፈጥሮ ከፈጸመ በኋላ ስላረፈባት ‹ሰንበት ዐባይ› (ታላቋ ሰንበት) ትባላለች፡፡ ይህቺን ዕለት እስራኤላውያን እንዲያከብሯት ታዟል፡፡ ዕለተ ቀዳሚት (ሰንበት ዐባይ) በዘመነ ሐዲስም የተለየ የደኅነት ሥራ ተከናውኖባታል፡፡ እግዚአብሔር ጥንት ሥነ ፈጥረትን በመፍጠር ዕረፍት እንዳደረገባት ዅሉ፣ የፍጥረት ርእስ የኾነውን አዳምን ለማዳን ሕማምና ሞት የተቀበለው አምላካችን ክርስቶስ በመቃብር አርፎባታል (ማቴ. ፳፯፥፷፩)፡፡

ቀዳሚት ሰንበት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በከርሠ መቃብር አርፎ የዋለባት ዕለት በመኾኗ ‹ቀዳሚት ሥዑር› ወይም ‹ቀዳም ሥዑር› ትሰኛለች፡፡ ‹ሥዑር› የተባለችበት ምክንያትም በዓመት አንድ ቀን ስለምትጾም (የጾም ቀን በመኾኗ) ነው፡፡ የጌታችን እናት ቅድስት ድንግል ማርያም፣ ወዳጆቹ ቅዱሳን ሐዋርያት ጌታችን ተላልፎ ከተሰጠበት ዕለት ጀምሮ ብርሃነ ትንሣኤውን እስኪያዩ ድረስ እኽል ውኃ በአፋቸው አልዞረም፡፡ ይመኩበትና ተስፋ ያደረጉት የነበረ አምላካቸው በመቃብር ስላረፈ ዕለቷን ሞቱን በማሰብና ትንሣኤውን በመናፈቅ በጾም አክብረዋታል፡፡

እመቤታችንና ቅዱሳን ሐዋርያት በማዘን፣ በመጾምና በመጸለይ ዕለቷን እንዳከበሯት ዅሉ የተዋሕዶ ልጆችም የተቻላቸው ከሐሙስ ጀምረው በማክፈል (በመጾም) እኽል ውኃ ሳይቀምሱ ለሁለት ቀናት ያድራሉ፡፡ ያልተቻላቸው ደግሞ ዓርብ ማታ በልተው ቅዳሜን በመጾም ትንሣኤን ያከብራሉ፡፡ በዚህ ዕለት ከሰኞ ከሆሣዕና ማግሥት ጀምረው እስከ ስቅለተ ዓርብ ድረስ በስግደት እና በጾም ያሳለፉ ምእመናን በዕለተ ቅዳሜ በቅጽረ ቤተ ክርስቲያን ይሰበሰባሉ፡፡ የጠዋቱ ጸሎት ሲፈጸምም ካህናቱ ‹‹ገብረ ሰላመ በመስቀሉ፤ በመስቀሉ ሰላምን መሠረተ» እያሉ በቤተ ክርስቲያን ለተሰበሰቡ ምእመናን የምሥራች ቄጠማ ያድላሉ፡፡

ቄጠማው የምሥራች ምልክት ነው፡፡ ቄጠማው የምሥራች ምልክት ተደርጐ የተወሰደው በኖኅ ዘመን ከተፈጸመው ታሪክ ጋር በማቆራኘት ነው፡፡ ቅዱስ መጽሐፍ እንደሚነግረን በጻድቁ ኖኅ ዘመን የነበሩ ሕዝቦች ከሕገ እግዚአብሔር ውጪ ኾነው እጅግ የሚያሳዝን ኃጢአት በሠሩ ጊዜ በንፍር ውኃ ተጥለቅልቀዋል፡፡ በወቅቱ ጻድቁ ኖኅ ወደ መርከብ ይዞአቸው ከገባው እንስሳት መካከል የውኃውን መጉደል ለመረዳት ርግብን በመርከብ መስኮት አሾልኮ ይለቃታል፤ እርሷም ቄጠማ በአፍዋ ይዛ ትመልሳለች፡፡ ኖኅም በዚህ ቄጠማ የውኃውን መድረቅ ተረድቶ ተደስቷል (ዘፍ. ፱፥፩-፳፱)፡፡

ቄጠማ ለጥፋት ውኃ መድረቅ የምሥራች መንገሪያ እንደ ኾነ ዅሉ፣ አሁንም ‹‹በክርስቶስ ሞት ሞተ ነፍስ ከሰው ልጆች ተወገደ፤›› ስትል ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ለልጆቿ ቄጠማ ታድላለች፡፡ ምእመናንም የምሥራች ተምሳሌት የኾነውን ቄጠማ በግንባራቸው ያስሩታል፡፡ የክርስቶስ ተከታዮች ዅሉ ከጨለማ ወደ ብርሃን፤ ከዋዕየ ሲኦል (የሲኦል ቃጠሎ) ወደ ጥንተ ማኅደራቸው ገነት መመለሳቸውን በዚህ አኳኋን እየገለጡ በዓለ ትንሣኤን በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ያከብራሉ፡፡

 ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

‹‹ለምን ትመታኛለህ?›› – ካለፈው የቀጠለ

በዲያቆን ሄኖክ ኃይሌ

ሚያዝያ ፭ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

ጌታችን መጻጕዕን ‹‹ተነሣና አልጋህን ተሸክመህ ሒድ›› ብሎ ሲነግረው ወዲውኑ ድኖ አልጋውን ተሸክሞ ሔደ፡፡ ከዚህ ላይ አባታችን ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እንዳለው የዚህን በሽተኛ እምነት እናደንቃለን፡፡ ራሱን መሸከም የማይችለው መጻጕዕ ‹‹ተነሣና አልጋህን ተሸከም›› ሲባል አልሳቀም፡፡ ‹‹እንዴት አድርጌ ነው ደግሞ አልጋ የምሸከመው?›› ብሎ አልጠየቀም፡፡ በፍጹም እምነት ተነሣና ተሸክሞ ሔደ፡፡ የሠላሳ ስምንት ዓመት ጓደኛውን፣ ሰው ሳይኖረው አብራው የኖረችውን፣ የተሸከመችውን ባለ ውለታ የኾነችዋን አልጋ ተሸከማት አለው – ተሸክሞ ሔደ፡፡

አንድ ሰው እንኳን ለሠላሳ ስምንት ዓመታት ይቅርና ለሠላሳ ስምንት ቀናት እንኳን ቢታመም እንደ ተሻለው ተነሥቶ አልጋ አይሸከምም፡፡ እስከሚያገግም ድረስ በደንብ መንቀሳቀስ አይችልም፡፡ ራሱን ያዞረዋል፤ ይደክመዋል፡፡ የቀረ ሕመም አያጣውም፡፡ መጻጕዕ ግን የተፈወሰው ያለ ተረፈ ደዌ (ያለ ቀሪ በሽታ) ነበር፡፡ ጌታችንም ወዲያው ተነሥቶ አልጋውን እንዲሸከም አዘዘው፡፡ መምህር ኤስድሮስ እንደ ተረጐሙት መጻጕዕ የብረት አልጋውን ተሸክሞ እየሔደ የጌታን ጽንዐ ተአምራት አሳየ፡፡

ጌታችንም ከዚያ በሽታ ያዳነው በነጻ መኾኑን በሚያሳይ ኹኔታ ያችን አንዲት ንብረቱንም ‹‹ተሸክመህ ሒድ›› አለው፡፡ መጻጕዕ የተሸከመችህን አልጋ ተሸከም ተባለ፡፡ እግዚአብሔር የተሸከሙንን እንድንሸከም የሚፈልግ አምላክ ነው፡፡ ውለታ ሳንረሳ የተሸከሙንን ወላጆቻችንን የተሸከመችንን ቤተ ክርስቲያንን፣ የተሸከመችንን አገራችንን እንድንሸከም ይፈልጋል፡፡ አንድ ሊቅም ‹‹ዓለም እንደዚህ ናት፤ እናት ዓለም አልጋ መጻጕዕን ‹እንደ ተሸከምሁህ ተሸከመኝ› አለችው›› ሲሉ አመሥጥረውታል (ዝክረ ሊቃውንት 2)፡፡

ከዚህ ላይ ጌታችን ቤተ ሳይዳ ከመጣ አይቀር ዅሉንም በሽተኞች መፈወስ ሲችል ለምን አንዱን ብቻ ፈውሶ መሔዱ ጥያቄ ሊኾንብን ይችላል፡፡ ጥያቄ የሚያስነሣው ሌላው ጉዳይ ደግሞ ሊቃውንቱ እንደ ጻፉት የቤተ ሳይዳው መጠመቂያ ፈውስ ከዚያ በኋላ ብዙም አለመቆየቱ ነው፡፡ የመልአኩም መውረድ ቆሞአል፡፡ ከዚያ በኋላ በሰባ ዓመተ ምሕረትም ኢየሩሳሌም መቅደስዋ ፈርሶአል፤ ተመሰቃቅላለች፡፡ ወንጌላዊው ዮሐንስም ‹‹በኢየሩሳሌምም በበጎች በር አጠገብ በዕብራይስጥ ‹ቤተ ሳይዳ› የምትባል አንዲት መጠመቂያ ነበረች፤ አምስትም መመላለሻ ነበረባት፤›› ብሎ በኃላፊ ጊዜ ግስ (past perfect tense) ነው የተናገረላት (ዮሐ. ፭፥፪)፡፡

ታዲያ ጌታችን እንዲህ መኾኑን እያወቀ ምነው መጻጕዕን ብቻ ፈውሶት ሔደ? ቢባል የፈወሰው እርሱን ብቻ አይደለም፡፡ እርሱን በሥጋ ቢፈውሰውም ተአምራቱን አይተው በማመናቸው በነፍሳቸው የተፈወሱ ይበዛሉ፡፡ ‹‹ሕሙማነ ሥጋን በተአምራት ሕሙማነ ነፍስን በትምህርት እየፈወሰ›› እንዲሉ አበው፡፡ በዚያ ሥፍራ በሥጋ ታመው በነፍሳቸው አምነው የዳኑ ብዙዎች ናቸው፡፡ የጌታችንና የእርሱ አካል የኾነች ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ዋነኛ ሥራዋ ነፍስን መፈወስ እንጂ ሥጋዊ በሽታን መፈወስ ብቻ አይደለም፡፡ ለዚህ ነው እንጂ ጌታችን ሰው ኾኖ ይህችን ምድር በእግሩ ሲረግጥ በሽታ እንዳይኖር ያደርግ የነበረው፡፡

ቅዱስ ባስልዮስ ‹‹በመስቀል ላይ በቈሰልኸው ቍስል ከኃጢአቴ ቍስል አድነኝ›› ብሎ እንደ ጸለየ እኛም የዘወትር ልመናችን ለሚከፋው ለነፍሳችን በሽታ ነው፡፡ የጌታችን ወደ ምድር መምጣት ዋነኛ ዓላማም ለነፍሳችን ድኅነትን ለመስጠት ነው፡፡ ይህ ማለት ግን ለሥጋ አልመጣም ማለት አይደለም፡፡ ጌታችን ‹‹ኃጢአተኞችን ለንስሐ ልጠራ መጣሁ እንጂ ጻድቃን ልጠራ አልመጣሁም … ከእስራኤል ቤት በቀር ለአሕዛብ አልተላክሁም›› ሲል መናገሩ ለጻድቃን አይገደኝም፤ ለአሕዛብ አላስብም ለማለት እንዳልኾነ ዅሉ፣ ለነፍስ ድኅነት ቅድሚያ ሰጥቶአል ማለትም ለሥጋ አይገደውም ማለት አይደለም፡፡

በመጻጕዕ ታሪክ ውስጥ የምንማራቸው ብዙ ነጥቦች ቢኖሩም ሁለት ነገሮችን ብቻ እናንሣና ይህችን አጭር ጽሑፍ እንግታ፤ ይህ ሰው ተፈውሶ አልጋውን ተሸክሞ ሲሔድ ሰንበት ለሰው ድኅነት እንደ ተፈጠረች ያልተረዱ አይሁድ በቍጣ ነደዱ፡፡ ‹‹ሰንበት ነው፤ አልጋህን ልትሸከም አልተፈቀደልህም፤›› አሉት፡፡ አስተውሉ! ይህ ሰው በቤተ ሳይዳ ሠላሳ ስምንት ዓመታት ሙሉ ሲማቅቅ እንደኖረ የሰውን ገመና አዋቂ ነን ባዮቹ አይሁድ ይቅሩና ቤተ ሳይዳን የረገጠ ሰው ዅሉ ያውቃል፡፡ ለሠላሳ ስምንት ዓመታት ወደዚያች የመጠመቂያ ሥፍራ ሲሔዱ፣ ያም ባይኾን በጎች ታጥበው ተመርጠው በሚገቡበት የበጎች በር ሲያልፉ ይህን በሽተኛ በአልጋው ተጣብቆ ሳያዩት አይቀሩም፡፡

አሁን ግን ከአልጋው ተነሥቶ የተሸከመችውን አልጋ ተሸክሞ በአደባባይ ሲያዩት የጠየቁትን ጥያቄ ተመልከቱ፤ ‹‹እንኳን ለዚህ አበቃህ! ዛሬ የእግዚአብሔር መልአክ ወደ ውኃው ወረደ ማለት ነው? እሰይ ልፋትህን ቈጠረልህ!›› ያለው ሰው የለም፡፡ የተናገሩት አንድ ዐረፍተ ነገር ብቻ ነው፤ ‹‹ሰንበት ነው አልጋህን ልትሸከም አልተፈቀደልህም›› የሚል ብቻ፡፡ በአይሁድ ዘንድ መጻጕዕ ድኖ ሠላሳ ስምንት ዓመት የተኛበትን አልጋ ተሸክሞ ከመሔዱ ይልቅ ሰንበትን መሻሩ የሚያስደንቅ ትልቅ ዜና ነው፡፡ መጻጕዕም ‹‹ያዳነኝ ያ ሰው አልጋህን ተሸከም አለኝ›› አላቸው፡፡ እነርሱም ‹‹አልጋህን ተሸክመህ ሒድ ያለህ ሰው ማን ነው?›› ብለው ጠየቁት፡፡ እነዚህ ሰዎች ይህን በሽተኛ ፈጽሞ አያውቁትም ነበር ቢባል ‹‹ያዳነኝ ሰው›› ሲላቸው ‹‹ከምንድን ነው የምትድነው? ምን ኾነህ ነበር? ከየት ነው የመጣኸው?›› ይሉ ነበር፡፡

ነገር ግን መዳኑን ማየት አልፈለጉም እንጂ ማን እንደ ኾነ ጠንቅቀው ያውቁታል፡፡ እስኪ ጥያቄና መልሱ ውስጥ ያለውን ሽሽት እንመልከት፤ ‹‹ያዳነኝ ሰው አልጋህን ተሸከም አለኝ›› ለሚለው ምላሽ ተከታዩ ጥያቄ ‹‹ማን ነው ያዳነህ?›› የሚል መኾን ነበረበት፡፡ እነርሱ ግን የጌታን የማዳን ሥራ ላለመስማት ጆሮአቸውን ደፍነው ‹‹አልጋህን ተሸከም ያለህ ማን ነው?›› አሉ፡፡ እንግዲህ የማዳኑን ሥራ እያዩ ከማመን ይልቅ መከራከር፣ ከማድነቅ ይልቅ የትችት ሰበብ መፈለግ ጌታን የሰቀሉ የአይሁድ ጠባይ ነው፡፡

የመጨረሻው ቁም ነገር መጻጕዕ ከዚህ በኋላ ወደ አይሁድ ሔዶ ጌታን መክሰሱና ለጌታ ሞት የመማከራቸው ምክንያት መኾኑ ነው፡፡ ይህ ሰው ‹‹ከዚህ የሚብስ እንዳይገጥምህ ደግመህ ኃጢአትን አትሥራ›› ብሎ ጌታ ቢያሳስበውም አልሰማም፡፡ ጌታ በተያዘበት በምሴተ ሐሙስ ለሊቀ ካህናቱ አግዞ ጌታችንን በጥፊ መታው፡፡ ጌታችንም ‹‹ክፉ ተናግሬ እንደ ኾነ ስለ ክፉ መስክር፤ መልካም ተናግሬ ከኾነ ግን ስለምን ትመታኛለህ?›› አለው (ዮሐ.፲፰፥፳፫)፡፡ ጌታችን ‹‹‹አልጋህን ተሸክመህ ሒድ› ከማለት በቀር ክፉ ቃል ተናግሬህ ከኾነ መስክርብኝ፤ የተናገርኩህ መልካም ኾኖ ሳለ ስለ ምን ትመታኛለህ?›› ማለቱ ነበር፡፡

በማግስቱ ያ ዅሉ ጅራፍና ግርፋት በጌታችን ላይ ሲደርስበት አንድም ጊዜ ‹‹ለምን ትመታኛለህ?›› ብሎ አልተናገረም፡፡ የመጻጕዕ ጥፊ ይህን ያህል ዘልቆ የተሰማው ለምንድር ነው? ለዚህም የመጀመሪያው ምክንያት ከቤተ ሳይዳ ከበጎች በር ጋር የተያያዘ ምሥጢር አለው፡፡ ጌታችን የዓለምን ኃጢአት የሚያስወግድ የእግዚአብሔር በግ ነው፡፡ በበጎች በር አልፎ የመጣውም ንጹሐ ባሕርይ እንደ ኾነ ለማስረዳት ነበር፡፡ ለዚህም ንጽሕናው ዋነኛው ምስክር ፈውስን የሰጠው ይህ በሽተኛ ነበር፤ እሱ ግን መታው፡፡ ‹‹በቤተ ሳይዳ ክፉ ቃል ተናግሬህ ከነበር መስክርብኝ›› ማለቱ ‹‹ነውር የሌለብኝ፣ ለመሥዋዕት የተዘጋጀሁ በግ ነኝ ለምን ትመታኛለህ?›› ሲል ነው፡፡ ሁለተኛው ምክንያት ደግሞ ከሮማውያን ግርፋት በላይ ለጌታ ዘልቆ የሚሰማው ባዳነው ሰው መመታቱ ስለ ኾነ ነው፡፡

ውድ አንባብያን! መጻጕዕ ከሠላሳ ስምንት ዓመታት በሽታ ብቻ ዳነ፤ እኛ ግን የዳንነው ከአምስት ሺህ አምስት መቶ ዓመታት በሽታ ነው፡፡ ጌታችን እኛን ያስነሣን ከሲኦል አልጋ ነው፡፡ በሰሙነ ሕማማት ያን ዅሉ መከራ ዝም ብሎ የተቀበለ ጌታ መጻጕዕ በጥፊ በመታው ጊዜ ግን ‹‹ለምን ትመታኛለህ?›› ሲል ጠየቆታል፡፡ ከሌላው ሰው ይልቅ የእኛ ከዘለዓለም ሞት ያዳነን ክርስቲያኖች ዱላ ለእግዚአብሔር ይሰማዋልና፡፡ ይህም ዱላ ኃጢአታችን ነው፡፡ እናም እግዚአብሔር ዛሬም ድረስ እያንዳንዳችንን ይጠይቀናል – ‹‹ለምን ትመታኛለህ?›› እያለ፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

‹‹ለምን ትመታኛለህ?›› – ክፍል አንድ

በዲያቆን ሄኖክ ኃይሌ

ሚያዝያ ፭ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከተጠመቀ በኋላ የአይሁድ ፋሲካ ለሦስት ጊዜ ተከብሯል፡፡ የመጀመሪያው ፋሲካ ጌታችን ቤተ መቅደሱን ያጸዳበትና በቤተ መቅደስ ሲሸጡ ሲለውጡ የነበሩትን ያስወጣበት ሲኾን፣ በመጨረሻው የፋሲካ ሰሙንም እንደዚሁ ለሁለተኛ ጊዜ ቤተ መቅደሱን አንጽቶ ጌታችን በፋሲካው ማግስት ተሰቅሏል፡፡ በሁለቱ ፋሲካዎች መካከል በነበረው ፋሲካ ነው ጌታችን ወደ ቤተ ሳይዳ የመጣው፡፡ ቤተ ሳይዳ የመጠመቂያው ሥፍራ ስም ሲኾን ከአጠገቡ ደግሞ የበጎች በር ነበር፡፡ (የበጎች በር በአሁኑ ሰዓት የቅዱስ እስጢፋኖስ በር እና የአንበሳ በር ተብሎ ይጠራል)፡፡

እንደሚታወቀው ዘመነ ኦሪት በግ መሥዋዕት ኾኖ የሚቀርብበት ዘመን ነበር፡፡ መሥዋዕት ኾነው የሚቀርቡ በጎች የሚገቡት በዚህ በር ነበር፡፡ በሩ በጎቹ ነውር እንደሌለባቸው ማለትም ቀንዳቸው እንዳልከረከረ፣ ጥፍራቸው እንዳልዘረዘረ፣ ፀጕራቸው እንዳላረረ የሚጠኑበት፤ የአንድ ዓመት ተባዕት (ወንድ) መኾናቸው የሚታይበት ሥፍራ ነው፡፡ ይህን መሥፈርት አሟልተው ያለፉ በጎች ለመሥዋዕትነት ሲቀርቡ ለዚህ ብቁ ያልኾኑትን ግን ለይተው፣ በአለንጋ እየገረፉ ያስወጡአቸዋል፡፡

በቤተ ሳይዳ የጌታ መልአክ ወደ መጠመቂያዪቱ ወርዶ ውኃውን አንዳንድ ጊዜ ያናውጠው ነበር፡፡ ይህ መልአክ በሰው ቍስል፣ በበሽታም ዅሉ ላይ የተሾመ የስሙ ትርጓሜም ‹‹እግዚአብሔር ፈዋሽ ነው›› ማለት የኾነ ከሰባቱ ሊቃነ መላእክት አንዱ ቅዱስ ሩፋኤል ነው፡፡ መልአኩ ውኆችን ለመቀደስ፣ ጸሎትን ከሰው ወደ ፈጣሪ ለማድረስ ወደ ውኃው ይወርድ ነበር፡፡ ይህም በየትኛውም ውኃ መዳን ባይቻለንም ቅዱሳን መላእክት የነኩት ውኃ በረከትና ፈውስ እንደሚያሰጥ የሚያስረዳ ነው፡፡ ውኃው ከተነዋወጠ በኋላ ከደዌው መዳን የሚችለው በመጀመሪያ የሚገባ በሽተኛ ነበር፡፡ በዚህ የጠበል ሥፍራ በነበሩ አምስት መመላለሻዎች በሽተኞች በተለይ አንካሶች፣ ዕውሮችና እግራቸው የሰለለ ብዙ ሰዎች ይተኙ ነበር፡፡

ከሌሎች በሽተኞች በተለየ እነዚህ የውኃውን መናወጥ አይተው ለመግባት፣ በዓይናቸውም ለማየት አይቻላቸውም፡፡ ገብተውም እንኳን ቢኾን ድንገት ከእነሱ ቀድሞ የገባ ሰው በመፈወስ ስለሚቀድማቸው ሳይፈወሱ ይመለሳሉ፡፡ ስለዚህም ከውኃው መልሶ የሚያወጣቸውም ሰው ያስፈልጋቸዋል፡፡ የሚያወጣቸው አጥተው ሊቸገሩም ይችላሉ፡፡ ምናልባትም በእንደዚህ ዓይነት ችግር ለባሰ ነገር የተዳረገ በሽተኛም ሊኖር ይችላል፡፡ ከእነርሱ ቀድሞ የሚድነው እንግዲህ ሁለት ዓይነት ሰው ነው፤ አንደኛው በሽታው ለመንቀሳቀስ የማያግደው ኾኖ እያለ የእነሱ ይብሳል ብሎ ሳያዝን የሚገባ ነው፡፡

እንኳን ቀድሞ የገባ ሰው ብቻ በሚድንበት ሥፍራ ቀርቶ በማንኛውም ሰዓት ቢገባ በሚዳንበት የጠበል ሥፍራ ‹‹ከእኔ በሽታ የእገሌ ይብሳል፤ እስኪ ቅድሚያ ልስጠው›› የሚል ሰው ብዙ ጊዜ አይታይም፡፡ ስለዚህ እነዚህን ደካሞች ቀድመው የሚገቡ በሽተኞች ብዙ ናቸው፡፡ በአንጻሩ ደግሞ ወደ መጠመቂያው ሊያስገቡት የሚጠባበቁ ዘመዶች ያሉት፣ አለዚያም ዘመድ የሚያፈራበት ገንዘብ ያለው በሽተኛ ደግሞ ሌላው ቀድሞ ወደ መጠመቂያው የሚገባ ነው፡፡ በዚህ ሥፍራ ለሠላሳ ስምንት ዓመታት ያህል የተኛ በሽተኛ (በግእዙ መጻጕዕ) ነበር፡፡ እንግዲህ ሠላሳ ስምንት ዓመት ማለት የጕልምስና ዕድሜ ነው፡፡

መጻጕዕ የመጣው በዐሥር ዓመቱ ነው እንኳን ብንል ዐርባ ስምንት ዓመት ይኾነዋል፡፡ ይህ ሰው ከመታመሙ በፊት ለዚህ ጽኑ ደዌ የሚዳርግ ኃጢአት ለመሥራት የሚችልበት ዕድሜ ላይ መድረሱን ጌታችን ከፈወሰው በኋላ ‹‹ከዚህ የሚብስ እንዳይደርስብህ ደግመህ ኃጢአትን አትሥራ›› ብሎ በማስጠንቀቁ እንረዳለን፡፡ መቼም ክፉ ደግ በማያውቅበት ሕፃንነቱ በድሎ ‹‹የልጅነቱ መተላለፍ ታስቦበት ታመመ›› ብሎ መናገር ይከብዳል፡፡ ብቻ ይህ ሰው የአንድ ጐልማሳ ዕድሜ ያህል በአልጋ ላይ ኾኖ በቤተ ሳይዳ ተኝቶአል፡፡ ጠበል ሊጠመቅ ሲጠባበቅ በፀጕሩ ሽበት፣ በግንባሩ ምልክት አውጥቶአል፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በቤተልሔም ግርግም ውስጥ ሲወለድም ይህ በሽተኛ በዚሁ መጠመቂያ ሥፍራ ነበረ፡፡

ድንግል ማርያም የወለደችውን ሕፃን በበረት ውስጥ ስታስተኛው ይህ በሽተኛ አልጋው ላይ ከተኛ ስድስት ዓመት ደፍኖ ነበር፡፡ ከዅሉ የሚያሳዝነው ደግሞ ይህ ሰው አልጋው ላይ ኾኖ እጅግ ብዙ ሰዎች ቀድመውት ሲፈወሱ ሲመለከት መኖሩ ነው፡፡ ከእርሱ በኋላ መጥተው ከእሱ በፊት ድነው የሚሔዱ ሰዎችን ማየት እንዴት ይከብደው ይኾን? እንደ እርሱ ብዙ ዘመን የቆዩት ሲድኑ ሲያይ ተስፋው ሊለመልም ይችላል፡፡ በመጡ በአጭር ጊዜ ውስጥ ዘመደ ብዙ በመኾናቸው ብቻ የሚድኑ ሰዎችን ሲያይ ግን ልቡ በሐዘን ይሰበራል፡፡ ዓመቱ በረዘመ ቍጥር ተስፋ ቈርጦ ቤተ ሳይዳን ቤቴ ብሎ ከመኖር በስተቀር ምንም የሚታየው ነገር አይኖርም፡፡

እግዚአብሔርን በመከራው ውስጥ ተስፋ እያደረገ ይጽናናል እንዳንል ደግሞ እንደ ጻድቁ ኢዮብ ወይም እንደ በሽተኛው አልዓዛር ከእግዚአብሔር ጋር የጠበቀ ግንኙነት አልነበረውም፡፡ እንደዚያ ቢኾን ኖሮ መቼ ለዚህ በሽታ የሚዳርገው ኃጢአት ይሠራ ነበር? በቃለ እግዚአብሔር ይጽናናል ማለትም ያስቸግራል፡፡ ያም ኾነ ይህ መጻጕዕ በበሽታው እጅግ ተሰቃይቶ ነበር፡፡ ጌታችን የዚህን ሰው ችግር ብቻ ሳይኾን ብዙ ዘመን እንደዚህ እንደነበረ ያወቀው ማንም ሳይነግረው ነበር፡፡ በሽታውን ከነመንሥኤው አስቀድሞ ያውቃልና ወደዚህ የብዙ ዓመታት በሽተኛ መጣና ‹‹ልትድን ትወዳለህን?›› አለው፡፡ ጌታችን የሚፈልገው ይህንን ሰው መፈወስ እንጂ የራሱን ማንነት ማሳየት ስላልነበረ ‹‹ላድንህ ትወዳለህን?›› አላለውም፡፡ በዚያውም ላይ ይህ ሰው የጌታን ማንነት አያውቅም፡፡

ይህ በሽተኛ ‹‹ልትድን ትወዳለህን?›› ሲባል የሰጠው ምላሽ እጅግ የሚያስገርም ነው፡፡ እንደሚታወቀው በሽታ አመል ያጠፋል፡፡ በሽታው በቆየ ቍጥር ደግሞ መራር ያደርጋል፡፡ ሰዎች በበሽታ ሲፈተኑ በሰው በፈጣሪም ላይ ብዙ የምሬት ንግግር ሊናገሩ ይችላሉ፡፡ ጌታችን ‹‹ልትድን ትወዳለህን?›› ብሎ ሲጠይቀው ምንም የምሬት እና የቍጣ ቃል ሳይናገር በጨዋ ሰው ሥርዓት ‹‹ጌታ ሆይ …›› ብሎ ነው የመለሰለት፡፡ በዚህ ኹኔታው መጻጕዕ ትሑት ሊባል ይችላል፡፡ ነገር ግን የመለሰው የተጠየቀውን አልነበረም፡፡ ጥያቄው ‹‹ልትድን ትወዳለህን?›› የሚል ከኾነ ምላሹ ‹‹አዎን፤ መዳን እወዳለሁ፤›› አለዚያም ‹‹አይ መዳን አልፈልግም›› የሚል ብቻ መኾን ነበረበት፤ እርሱ ግን ‹‹ጌታ ሆይ! ውኃው በተናወጠ ጊዜ በመጠመቂያይቱ ውስጥ የሚያኖረኝ ሰው የለኝም፡፡ ነገር ግን እኔ ስመጣ ሳለሁ ሌላው ቀድሞኝ ይወርዳል›› የሚል ምላሽ ነበር የሰጠው፡፡

መጻጕዕ የጌታችንን ማንነት ባይረዳውም ጌታችን በወቅቱ ሠላሳ ሁለት ዓመቱ ነበርና ምናልባት ወደ መጠመቂያው ሊጨምረኝ አስቦ ይኾናል ያም ባይኾን ግን ከተከተሉት ሰዎች አንዱን አደራ ሊልልኝ ይኾናል ብሎ አስቦ ነበር፡፡ ‹‹ሰው የለኝም›› ብሎ የሠላሳ ስምንት ዓመታት ብሶቱን ተናገረ፡፡ ‹‹ሌላው ቀድሞኝ ይወርዳል›› ብሎ እየቀደሙት ሲፈወሱ የነበሩ ሰዎችን አስታወሰ፡፡ ጌታችንም ‹‹ተነሣና አልጋህን ተሸክመህ ሒድ›› አለው፡፡ ባላሰበው፣ ባልጠበቀው መንገድ ፈወሰው፡፡ ይህ ሰው ሠላሳ ስምንት ዓመት ሙሉ ሲጠባበቃት የነበረችውን የቤተ ሳይዳ ጠበል ሳያገኝ፣ በመልአኩ መውረድ ሳይኾን በመላእክት ፈጣሪ ቃል ተፈወሰ፡፡

ገባሬ መላእክት ክርስቶስ ራሱ መጥቶ አዳነው፡፡ ይህ ሰው ‹‹ለመዳን የሚያስፈልገው ምንድን ነው?›› ተብሎ ቢጠየቅ የሚመልሰው ‹‹ወደ ውኃው የሚጨምር ሰው እና የቤተ ሳይዳ ውኃ›› ብሎ ነበር፡፡ እግዚአብሔር በዚህች ጠበል ካልኾነ በቀር በሌላ በምንም መንገድ ያድናል ብሎ አስቦም አልሞም አያውቅም ነበር፡፡ ጌታችን መጻጕዕ ለሠላሳ ስምንት ዓመታት ተስፋ ያደረጋትን ጠበል ወይም ደግሞ ወደ ጠበሉ የሚጨምሩትን ሰዎች ሳይጠቀም አምላካችን ፈወሰው፡፡ እግዚአብሔር ያለ ጠበልም እንደሚያድን ማመን ካልቻልን እምነታችን ሙሉ አይደለም፡፡

ይህ ሰው ወደ ውኃው ገብቶ ቢድን ኖሮ ‹‹ጌታዬ አዳነኝ›› ከማለት ይልቅ ‹‹መዳን ይነሰኝ? ሠላሳ ስምንት ዓመት እኮ ነው የጠበቅኩት …›› እያለ ልፋቱን ያወራርድ ነበር እንጂ ፈጣሪውን አያመሰግንም ነበር፡፡ ጌታችንም ‹‹ስታምኑብኝ ብቻ ነው የምፈውሳችሁ›› የሚል አምላክ አይደለም፣ ለዅሉም ፀሐይን የሚያወጣ፣ ዝናምን የሚያዘንም አምላክ ይህንን ሰውም ለመፈወስ እስኪያምነው አልጠበቀም፡፡ ጌታችን ጠበል ቦታ ያገኘውን ያለ ጠበል ፈወሰው ሲባል መቼም ጠበል መጠመቅ የማይወዱ ወይም በጠበል የማያምኑ ሰዎች ደስ ሊላቸው ይችላል፡፡

‹‹እኛስ ምን አልን? ጌታ እኮ ይህን በሽተኛ ጠበል ቦታ አግኝቶ እንኳን የፈወሰው ያለ ጠበል ነው›› ብለው ባቀበልናቸው በትር ሊመቱን ይፈልጉ ይኾናል፡፡ ኾኖም በዮሐንስ ወንጌል በዘጠነኛው ምዕራፍ ላይ ዕውር ኾኖ የተወለደውን ሰው ጠበል በሌለበት ሥፍራ አግኝቶት እኛ እመት (እምነት) የምንለውን አፈር በምራቁ ለውሶ ከቀባው በኋላ ‹‹ሒድና በሰሊሆም መጠመቂያ ታጠብ›› ብሎ ልኮታል፡፡ ጠበል ምንም የማያስፈልግ ቢኾን ኖሮ ዓይነ ስውሩን ሰው ወደ ወንዝ ወርደህ ተጠመቅ ብሎ አይልከውም ነበር፡፡ ዛሬ ለታመሙ ሰዎች ‹‹ጠበል ሒዱ›› ብለን ስንመክር ክርስትና ያልገባን፣ ክርስቶስን የማናውቅ የሚመስለው ይኖራል፡፡

አሁን ባየነው ታሪክ ውስጥ ግን ለበሽተኛው ‹‹ሔደህ ጠበል ተጠመቅ›› ብሎ የመከረው ራሱ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ መፈወስ የሚቻለው ክርስቶስ ‹‹ጠበል ተጠመቅ›› ብሎ ከተናገረ፤ የታመመን መፈወስ የማንችለው እኛ ኃጢአተኞቹ ከንፈር ከመምጠጥ ይልቅ ‹‹ሔደህ ተጠመቅ›› ብንል ምን አጥፍተናል? ጌታችን ሲያደርግ ያየነውን ነው፡፡ ‹‹እኔን ምሰሉ›› ብሎን የለ እንዴ? (ዮሐ. ፱፥፯)፡፡ በእነዚህ ሁለት ታሪኮች አምላካችን ሲፈልግ በጠበል፣ ሲፈልግ ያለ ጠበል፣ አልያም በሕክምና፤ ሲያሻው በምክንያት ሲያሻው ያለ ምክንያት፤ ሲፈልግ በቃሉ፣ ሲፈልግ በዝምታ፤ ሲፈልግ በቅዱሳን መላእክቱ፣ ሲፈልግ ያለ ቅዱሳን መላእክቱ ማዳን እንደሚቻለው እንረዳለን፡፡

ይቆየን

ዓርብ ስቅለት (የድኅነት ቀን)

በሊቀ ማእምራን ብርሃነ መስቀል አጠና (የሊቃውንት ጉባኤ አባል)

ሚያዝያ ፭ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

ዓርብ ስቅለት የዕዳ ደብዳቤያችን በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ለመጨረሻ ጊዜ የተደመሰሰበት፤ ከአጋንንት አገዛዝ ነጻ የወጣንበት ዕለት ስለኾነ ‹የድኅነት ቀን› ይባላል፡፡ ጌታችን ከተያዘባት ሰዓት አንሥቶ አይሁድ ከቀያፋ ወደ ሐና፣ ከሐና ወደ ቀያፋ ሲያመላልሱት አደሩ፡፡ ሲነጋ ከቀያፋ ወደ ጲላጦስ አደባባይ አስረው ወሰዱት (ማቴ. ፳፯፥፩-፶፯)፡፡ አይሁድ ይህን አጥፍቶአል የሚሉት ነጥብ ሳይኖራቸው ነውና ጌታችንን ለፍርድ ያቀረቡት ጲላጦሰ እነርሱ ወደ ተሰባሰቡበት ቦታ ወጥቶ ‹‹ይህን ሰው ወደ እኔ ያመጣችሁበት በደል ምንድን ነው?›› ሲል በጠየቃቸው ጊዜ በቂ ምላሽ አላቀረቡም፡፡

‹‹ክፉ የሠራ ባይኾንስ ወደ አንተ ባላመጣነውም ነበር›› በሚል የሸፍጥ ቃል ሲያጕረመርሙ ጲላጦስ መልሶ ‹‹እኔ ምንም ጥፋት አላገኘሁበትም፤ እናንተወስዳችሁ እንደ ሕጋችሁ ፍረዱበት፤›› አላቸው፡፡ አይሁድም ኦሪት ‹‹ኢትቅትል ብእሴ ጻድቀ ወኀጥአ ኢታኅዩ፤ ጻድቅን ሰው አትግደል፤ ኀጥኡንም ከፍርድአታድን፤›› ትላለችና ‹‹እኛስ ማንንም ልንገድል አልተፈቀደልንም፤›› ብለዋል (ዮሐ. ፲፰፥፳፰-፴፩)፡፡ ይኸውም መንፈስ ቅዱስ ‹‹በሕጋችን ጻድቀ ባሕርይክርስቶስን መግደል አይገባንም ሙሉ በሙሉ ጥፋተኞች ነን፤›› ሲያሰኛቸው ነው፡፡ በኋላም እርሱ ሞቶ ዓለም ይድን ዘንድ ወደ ምድር መጥቷልና ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ያለ ጥፋቱ ሞት ተፈረደበት፡፡ ስለዚህም ገርፈው ሰቀሉት፡፡

ጌታችን ሲሰቅልም የሚከተሉት ሰባት ተአምራት ተፈጽመዋል፤

፩. ፀሐይ ጨለመ፤

፪. ጨረቃ ደም ኾነ፤

፫. ከዋክብት ረገፉ፤

፬. የቤተ መቅደስ መጋረጃ ተቀደደ፤

፭. አለቶች ተፈረካከሱ፤

፮. መቃብራት ተከፈቱ፤

፯. ሙታን ተነሡ (ማቴ. ፳፯፥፶፩-፶፬)፡፡

ጌታችን በመስቀል ላይ ሳለ የሚከተሉትን ሰባት ዐበይት ቃላት አሰምቶ ተናግሯል፤

፩. ‹‹ኤሎሄ ኤሎሄ ላማ ሰበቅታኒ (አምላኪየ አምላኪየ ለምን ተውኸኝ?)››፤

፪. ‹‹እውነት እውነት እልሃለሁ፤ ዛሬ ከእኔ ጋር በገነት ትኖራለህ››፤

፫. ‹‹አባት ሆይ የሚያደርጉትን አያውቁትምና ይቅር በላቸው››፤

፬. እመቤታችንን ‹‹ሴትዮ ሆይ፣ እነሆ ልጅሽ›› ደቀ መዝሙሩንም ‹‹እናትህ እነኋት›› በማለት የቃል ኪዳን እናትነትና ልጅነት ማከናወኑ፤

፭. ‹‹አባት ሆይ በአንተ እጅ ነፍሴን አደራ እሰጣለሁ››

፮. ‹‹ተጠማሁ››

፯. ‹‹ዅሉ ተፈጸመ›› (ማቴ. ፳፯፥፵፭-፵፮፤ ሉቃ. ፳፫፥፵፫-፵፮፤ ዮሐ. ፲፱፥፲-፴)፡፡

ከስድስት ሰዓት እስከ ዘጠኝ ሰዓት ጨለማ ኾኖ ከቈየ በኋላ ከዘጠኝ እስከ ማታ እንደ ተለመደው ብርሃን ኾኖአል፡፡ ‹‹ወፍና ሠርክ ይበርህ ብርሃነ ፀሐይ›› እንዲል (ዘካ. ፲፬፥፯)፡፡ በዚህ ዕለት ሰባት መስተፃርራን (ጠበኞች) ታረቁ፤ ተስማሙ፡፡ እነዚህም፡- ሰውና እግዚአብሔር፣ ሰውና መላእክት፣ ሕዝብና አሕዛብ፣ ነፍስና ሥጋ ናቸው (ኤፌ. ፪፥፲፤ ቈላ. ፩፥፳)፡፡ ጌታችን ጠዋት በሦስት ሰዓት ተገረፈ፤ በስድስት ሰዓት ተሰቀለ (ማቴ. ፳፯፥፩-፴፯፤ ሉቃ. ፳፫፥፩-፵፬፤ ዮሐ. ፲፱፥፩)፡፡

በዘጠኝ ሰዓት ጌታችን በውኃው ተጠምቀን፣ ደሙን ተቀብለን የእግዚአብሔር ልጆች እንኾን ዘንድ ከቀኝ ጎድኑ ጥሩ ውኃ፣ ትኩስ ደም አፈሰሰልን (ዮሐ. ፲፱፥፴፬)፡፡ በዐሥራ አንድ ሰዓት ዮሴፍና ኒቆዲሞስ ከመስቀል አውርደው ሽቶ እየረበረቡ በድርብ በፍታ ገንዘው ቀበሩት (ሉቃ. ፳፫፥፶-፶፬፤ ዮሐ. ፲፱፥፴፰-፵፪)፡፡ ቅድስት ነፍሱ ወደ ሲኦል ወርዳ ነፍሳትን ነጻ አወጣች (፩ኛ ጴጥ. ፫፥፲፱)፡፡ በዚህ ጊዜ በርሃነ መለኮቱ በሲኦል ተገለጠ፡፡ ስለዚህም ‹‹ንሴብሖ ለእግዚአብሔር›› እየተባለ ይዘመራል፡፡ ከሆሣዕና አንሥቶ ተከልክሎ የነበረው ኑዛዜ ይናዘዛል፤ ጸሎተ ፍትሐት ይደረጋል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ጸሎተ ሐሙስ

ሚያዝያ ፬ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

ጸሎተ ሐሙስ በብሉይ ኪዳን

ጸሎተ ሐሙስ በብሉይ ኪዳን ለፋሲካ ዝግጅት ተደርጎበታል (ማቴ. ፳፮፥፯-፲፫)፡፡ ‹ፋሲካ› ማለት ማለፍ ማለት ነው፡፡ ይኸውም እስራኤላውያን በግብጽ ምድር ሳሉ መልአኩን ልኮ እያንዳንዱ እስራኤላዊ የበግ ጠቦት እንዲያርድና ደሙን በበሩ ወይም በመቃኑ እንዲቀባ ለሙሴ ነገረው፡፡ ሙሴም የታዘዘውን ለሕዝቡ ነገረ፤ ዅሉም እንደ ታዘዙት ፈጸሙ፡፡ በኋላ ከእግዚአብሔር ዘንድ መቅሠፍት ታዞ መልአኩ የደም ምልክት የሌለበትን የግብጻውያንን ቤት በሞተ በኵር ሲመታ፤ የበጉ ደም ምልክት ያለበትን የእስራኤላውያንን ቤት ምልክቱን እያየ አልፏል፡፡ ፋሲካ መባሉም ይህን ምሥጢር ለማስታወስ ነው (ዘፀ. ፲፪፥፩-፳)፡፡

በዚህ መነሻነት በየዓመቱ እስራኤላውያን በመጀመሪያው ወር በዐሥራ አራተኛው ቀን በግ እያረዱ የፋሲካን በዓል ያከብራሉ፡፡ አገራችን ኢትዮጵያም አስቀድማ ብሉይ ኪዳንን የተቀበለች አገር እንደ መኾኗ ይህን ሥርዓት ትፈጽም ነበር፡፡ በሐዲስ ኪዳንም የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ትንሣኤ ‹ፋሲካ› ተብሎ የተጠራበት ምክንያት ጌታችን በዚህ በፋሲካ በዓል ራሱን የተወደደ ምሥዋዕት አድርጎ ደሙን ስላፈሰሰልን ነው፡፡ በደሙ መፍሰስም ሞተ በኵር የተባለ ሞተ ነፍስ ርቆልናል፡፡ ስለዚህም ክርስቶስን ‹ፋሲካችን› እንለዋን (፩ኛ ቆሮ. ፭፥፯፤ ፩ኛ ጴጥ. ፩፥፲፰-፲፱)፡፡

የጸሎተ ሐሙስ ስያሜዎች

ጸሎተ ሐሙስ በቤተ ክርስቲያን በርካታ ስያሜዎች አሉት፡፡ የዓለም መድኃኒት ኢየሱስ ክርስቶስ ሥጋን የተዋሐደ አምላክ መኾኑን ለመግለጥና ለአርአያነት ጠላቶቹ መጥተው እስኪይዙት ድረስ ሲጸልይ ያደረበት ቀን ነውና ‹ጸሎተ ሐሙስ› ይባላል (ማቴ. ፳፮፥፴፮-፶፮)፡፡ ጌታችን በዚህ ዕለት የደቀ መዛሙርቱን እግር በፍጹም ትሕትና ዝቅ ብሎ አጥቧል፡፡ ይህም ኢየሱስ ክርስቶስ የዓለምን ዅሉ ኃጢአት ለማጠብ የመጣ የንጽሕና፣ የቅድስና አምላክ መኾኑን ያጠይቃል፡፡ ስለዚህም ዕለቱ ‹ሕጽበተ ሐሙስ› ይባላል፡፡ ይህን ለማስታወስ ዛሬም ሊቃነ ጳጳሳትና ቀሳውስት ‹‹በመካከላችን ተገኝተህ የእኛንና የሕዝብህን ኃጢአት እጠብ፤ እኛም የአንተን አርአያነት ተከትለን የልጆቻችንን እግር እናጥባለን፤›› ሲሉ በቤተ ክርስቲያን የተገኙ ምእመናንን እግር በወይንና በወይራ ቅጠል ያጥባሉ፡፡

ከሰባቱ ምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን አንዱ ምሥጢረ ቍርባን በዚህ ቀን ተመሥርቷልና ዕለቱ ‹የምሥጢር ቀን› ይባላል፡፡ ይኸውም ጌታችን ኅብስቱንና ጽዋውን አንሥቶ ‹‹ይህ ስለ እናንተ በመስቀል ላይ የሚቈረሰው ሥጋዬ ነው፡፡ እንካችሁ፤ ብሉ፡፡ ይህ ስለ እናንተ ነገ በመስቀል ላይ የሚፈስ ደሜ ነው፤ ከእርሱም ጠጡ፤›› በማለት እርሱ ከእኛ፤ እኛም ከእርሱ ጋር አንድ የምንኾንበትን ምሥጢር ከጠላት ዲያብሎስ ሰውሮ፣ ለደቀ መዛሙርቱ የገለጠበት ቀን በመኾኑ የተሰጠ ስያሜ ነው፡፡ በዚህ ዕለት ክርስቲያን የኾነ ዅሉ በንስሐ ታጥቦ ቅዱስ ሥጋውንና ክቡር ደሙን ለመቀበል ይዘጋጃል፡፡

መድኃኒታችን ክርስቶስ መሥዋዕተ ኦሪት ማለትም በእንስሳት ደም የሚቀርበው መሥዋዕት ማብቃቱን ገልጦ፣ ለድኅነተ ዓለም ራሱን የተወደደ መሥዋዕት አድርጎ ያቀረበበት ዕለት በመኾኑ ይህ ዕለት ‹የሐዲስ ኪዳን ሐሙስ› ይባላል (ሉቃ. ፳፪፥፳)፡፡ ‹ኪዳን› ማለት በሁለት ወገን መካከል የሚደረግ ውል፣ ስምምነት፣ መሐላ ማለት ነው፡፡ በዚህ መሠረት ጌታችን ለአዳምና ለልጆቹ ዅሉ ዘለዓለማዊውን ቃል ኪዳን በራሱ ደም የፈጸመበት ዕለት ስለ ኾነ ሐሙስ ‹የሐዲስ ኪዳን ሐሙስ› ተባለ፡፡

ይህ ዕለት ለኃጢአትና ለዲያብሎስ ባሪያ ኾኖ መኖር ማብቃቱ የተገለጠበት፤ የሰው ልጅ ያጣውን ክብር መልሶ ማግኘቱ የተረጋገጠበት ቀን ስለ ኾነ ‹የነጻነት ሐሙስ› ይባላል፡፡ ጌታችን ስለ ሰው ልጅ ነጻነት ሲናገር ‹‹ከእንግዲህ ወዲህ ባሮች አልላችሁም፤ ባርያ ጌታው የሚያደርገውን አያውቅምና፡፡ ወዳጆች ግን ብያችኋለሁ፤›› በማለት ከባርነት የወጣንበትን፤ ልጆች የተባልንበትን ቀን የምናስብበት በመኾኑ ሊቃውንቱ ‹የነጻነት ሐሙስ› አሉት (ዮሐ. ፲፭፥፲፭)፡፡ እያንዳንዱ ክርስቲያንም ከኃጢአት ባርነት ርቆ፣ ከእግዚአብሔር ጋር የሚወዳጀውን መልካም ሥራ በመሥራት ሕይወቱን መምራት ይኖርባታል፡፡ ባሮች ሳይኾን ወዳጆች ተብለን በክርስቶስ ተጠርተናልና፡፡

በዚህ ዕለት እንደ ማክሰኞ ዅሉ ጌታችን በዮሐንስ ወንጌል ፲፬፥፲፮ የሚገኘውን ሰፊ ትምህርት ለደቀ መዛሙርቱ አስተምሯል፡፡ የትምህርቱም ዋና ዋና ክፍሎችም ምሥጢረ ሥላሴን፣ ምሥጢረ ሥጋዌንና ምሥጢረ ትንሣኤ ሙታንን ያካትታሉ፡፡ ጌታችን እነዚህን ትምህርቶች በስፋትና በጥልቀት መማር እንደሚገባ ሲያስረዳ፣ ለደቀ መዛርቱ ምሥጢሩን በተአምራት ሊገልጥላቸው ሲቻለው በሰፊ ማብራርያ እንዲረዱት አድርጓል፡፡ ደቀ መዛሙርቱም ያልገባቸውንም እየጠየቁ ተረድተዋል፡፡ ምእመናንም በቤተ ክርስቲያን ተገኝተን መማርና ያልገባንን ጠይቀን መረዳት እንደሚገባን ከዚህ እንማራለን፡፡ መድኃኒታችን ክርስቶስ ራሱን ለአይሁድ አሳልፎ የሰጠውም በዚሁ ዕለት ከምሽቱ በሦስት ሰዓት ነው (ማቴ. ፳፮፥፵፯-፶፰)፡፡

በጸሎተ ሐሙስ በቤተ ክርስቲያን የሚፈጸም ሥርዓት

በዚህ ዕለት ስግደቱ፣ ጸሎቱ፣ ምንባባቱ እንደ ተለመደው ይከናወናሉ፡፡ መንበሩ (ታቦቱ) ጥቁር ልብስ ይለብሳል፡፡ ጸሎተ ዕጣን ይጸለያል፤ ቤተ ክርስቲያኑም በማዕጠንት ይታጠናል፡፡ ሕጽበተ እግር ይደረጋል፡፡ ቅዳሴ ይቀደሳል፡፡ በየቤቱ ደግሞ ጉልባን ይዘጋጃል፡፡

ሕጽበተ እግር

ከቀኑ በዘጠኝ ሰዓት ዲያቆኑ ሁለት ኵስኵስቶችን ውኃ ሞልቶ ያቀርባል፤ አንዱ ለእግር፣ አንዱ ለእጅ መታጠቢያ፡፡ ‹ጸሎተ አኰቴት› በመባል የሚታወቀው የጸሎት ዓይነት ይጸለያል፡፡ ወንጌል ተነቦ ውኃው በካህኑ (በሊቀ ጳጳሱ) ይባረክና የሕጽበተ እግር ሥርዓት ይከናወናል፡፡ ይኸውም ጌታችን የደቀ መዛሙርቱን እግር በማጠብ ያሳየውን የተግባር ትምህርት ለማሳየት ነው (ዮሐ. ፲፫፥፲፬)፡፡ ከውኃው በተጨማሪ የወይራና የወይን ቅጠልንም ለሥርዓተ ሕጽበቱ ማስፈጸሚያነት እንጠቀምባቸዋለን፡፡ ምሥጢሩም የሚከተለው ነው፤

ወይራ ጸኑዕ ነው፡፡ ወይራ ክርስቶስም ጽኑዕ መከራ መቀበሉን ከማስረዳቱ በተጨማሪ እኛም (እግራችንን የሚያጥቡን አባቶች እና የምንታጠበው ምእመናን) መከራ ለመቀበል ዝግጁ ነን ለማለት ሥርዓተ ሕጽበቱን በወይራ እንፈጽማለን፡፡ የወይኑ ቅጠልም መድኃኒታችን ክርስቶስ በወይን የተመሰለ ደሙን አፍስሶ ለምእመናን የሕይወት መጠጥ አድርጎ መስጠቱን ለማዘከር በወይን ሥርዓተ ሕጽበትን እናከናውናለን (ማቴ. ፳፮፥፳፮)፡፡ በቀኝና በግራ የቆሙ ሊቃውንትም ‹‹ሐዋርያቲሁ ከበበ እግረ አርዳኢሁ ሐጸበ›› እያሉ ይዘምራሉ፡፡ ይህ ሥርዓት ከተጠናቀቀ በኋላ ሥርዓተ ቅዳሴው ተከናውኖ ቅዱስ ሥጋውን ክቡር ደሙን ምእመናን ይቀበላሉ፡፡

 ቅዳሴ

የጸሎተ ሐሙስ ቅዳሴ የሚከናወነው በተመጠነ ድምፅ ሲኾን፣ እንደ ደወል (ቃጭል) የምንጠቀመውም ጸናጽልን ነው፡፡ ልኡካኑ የድምፅ ማጉያ ሳይጠቀሙ በለኆሣሥ (በቀስታ) ይቀድሳሉ፡፡ ምክንያቱም ይሁዳ በምሥጢር ጌታችንን ማስያዙን ለመጠቆም ሲኾን፣ በሌላ በኩል ደግሞ የዘመነ ብሉይ ጸሎት ዋጋው ምድራዊ እንደ ነበር ለማስታወስ ነው፡፡ በመቀጠል ክብር ይእቲ፣ ዕጣነ ሞገር፣ ዝማሬ የተባሉ የድጓ ክፍሎች ተዘምረው አገልግሎቱ ይጠናቀቃል፡፡ ሕዝቡም ያለ ኑዛዜና ቡራኬ ይሰናበታሉ፡፡

ጉልባን

ጉልባን ከባቄላ ክክ፣ ከስንዴ ወይንም ከተፈተገ ገብስ ጋር አንድ ላይ ተቀቅሎ የሚዘጋጅና የጸሎተ ሐሙስ ዕለት የሚበላ ንፍሮ ነው፡፡ በጸሎተ ሐሙስ በቤት ውስጥ ከሚፈጸሙ ተግባራት አንዱ ጉልባን ማዘጋጀት ነው፡፡ ጉልባን እስራኤላውያን ከግብጽ ባርነት ሲወጡ በችኮላ መጓዛቸውን የምናስታውስበት ከእስራኤላውያን የመጣ ትውፊታዊ ሥርዓት ነው፡፡ በአገራችን ኢትዮጵያ አብዛኞቹ የትውፊት ክንዋኔዎች የብሉይ ኪዳን መነሻ ስላላቸው ይህ ሥርዓት ዛሬም በኢትዮጵያውያን ምእመናን ዘንድ ይከበራል፡፡

ጉልባን እስራኤላውያን ከባርነት በወጡ ጊዜ አቡክተው፣ ጋግረው መብላት አለመቻላቸውን ያስታውሰናል፡፡ በወቅቱ ያልቦካውን ሊጥ እየጋገሩ ቂጣ መመገብ፤ ንፍሮ ቀቅለው ስንቅ መያዝ የመንገድ ተግባራቸው ነበርና፡፡ ይህን ታሪክ ለማሰብም በሰሙነ ሕማማት በተለይም በጸሎተ ሐሙስ ቂጣና ጉልባን ይዘጋጃል፡፡ በጸሎተ ሐሙስ የሚዘጋጀው ጉልባንና ቂጣ ጨው በዛ ተደርጎ ይጨመርበታል፡፡ ይኸውም ጨው ውኃ እንደሚያስጠማ ዅሉ፣ ጌታችንም በመከራው ወቅት ውኃ መጠማቱን ለማስታወስ ነው፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ምንጭ፡-

ስምዐ ተዋሕዶ (ልዩ ዕትም ዘሰሙነ ሕማማት)፣ ከሚያዝያ ፩ -፲፭ ቀን ፳፻፬ ዓ.ም፣ ገጽ ፮-፯፣ ፲፫ እና ፳፤ ማኅበረ ቅዱሳን፣ አዲስ አበባ፡፡

ዕለታተ ሰሙነ ሕማማት

በመምህር ቸሬ አበበ

ሚያዝያ ፬ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

የእግዚአብሔር ቸርነት 

ከአባታችን አዳም በደል ወይም ስሕተት በኋላ በሕማማት፣ በደዌያት፣ በመቅሠፍታት፣ ወዘተ. በብዙ መከራ የሰው ልጅ ሊኖርባቸው ግድ የኾነባቸው ዘመናት ጥቂቶች አልነበሩም፡፡ ጥሮ ግሮ ወጥቶ ወርዶ ለፍቶ ማስኖ የዕለት ጉርስ፣ የቀን ልብስ ማግኘት እጅግ አዳጋች ነበር፡፡ ዅልጊዜ የሰው ልጅ ቢያጠፋ ቢበድል ከሕገ እግዚአብሔር ቢወጣ እንኳ የዋህ፣ ታጋሽ፣ ቸር፣ አዛኝ የኾነ አምላክ የጠፋውን ሊፈለግ፣ የተራበውን ሊያጠግብ የታረዘውን ሊያለብስ፣ ፍቅር ያጣውን ፍጹም ፍቅር ሊለግስ፣ ሰላም ለሌለው ፍጹም ሰላምን ሊሰጥ፣ ተስፋ ለሌለው ተስፋን ሊያጐናጽፍ ከሰማይ ወረደ፤ ከቅድስት ድንግል ማርያም ተወለደ፤ በገዳመ ቆሮንቶስ ዐርባ ቀንና ሌሊት ጾመ፡፡ በጾሙም የኃጢአት ሥሮች ወይም ራሶች የተባሉትን ስስትን፣ ትዕቢትንና ፍቅረ ንዋይን ድል አደረገልን፡፡ እኛ እርሱ የጾመውን ጾም እንድናከብር እንድንጾም፤ ዲያብሎስን ድል አድርጐ እኛም ዲያሎስን ድል እንድንነሣው ኃይልና ምሳሌ ኾነን፡፡

ሰሙነ ሕማማት 

ሰሙን ‹ሰመነ – ስምንት አደረገ› ከሚለው የግእዝ ግስ የተገኘ ቃል ሲኾን ትርጕሙም ሳምንት፣ ስምንት ማለት ነው፡፡ ‹ሕማማት› ቃሉ ‹ሐመ – ታመመ› ከሚለው የግእዝ ግስ የተገኘ ሲኾን ትርጕሙም ብዙ ሕማምን ያመላክታል፡፡ ‹ሰሙነ ሕማማት› ስንልም ‹የሕማም ሳምንት› ማለታችን ነው፡፡ ይኸውም ጌታችን አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሰውን ዘር ዅሉ ከዲያብሎስ ባርነት ነጻ ለማውጣት ሲል የተቀበለውን መከራ የምናስብበት ወቅት ነው፡፡ ሰሙነ ሕማማት ከዕለተ ሆሣዕና ሠርክ እስከ ትንሣኤ ሌሊት ያለውን ጊዜ ያጠቃልላል፡፡ ዕለታቱ የዓመተ ኵነኔ ወይም የዓመተ ፍዳ ምሳሌዎች ናቸው፡፡ ክርስቲያኖች የክርስቶስን ውለታ እያሰቡ እጅግ የሚያዝኑበት፤ የሚያለቅሱበት፤ የሚሰግዱበት ቤት ንብረታቸውን ትተው ከሌላው ቀናትና ጊዜያት በተለየ መልኩ በቤተ ክርስቲያን ተሰባስበው እግዚአብሔርን የሚማጸኑበት፤ ጧት ማታ ደጅ የሚጠኑበት፤ ኃጢአታቸውን ለካህን የሚናዘዙበት በዓመት አንድ ጊዜ ብቻ የሚገኝ ልዩ ሳምንት ነው፡፡

በዚህ ሳምንት ብዙ አዝማደ መባልዕት (የምግብ ዓይነቶች) አይበሉም፤ ይልቁን በመራብ፣ በመጠማት፣ በመውጣት፣ በመውረድ፣ በመስገድ፣ በመጸለይ፣ በመጾም በየሰዓቱ የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን ጸዋትወ መከራ በማሰብ ወቅቱን እናሳልፋለን፡፡ በዚህ ሳምንት አብዝቶ ይሰገዳል፡፡ መከራውን፣ ሕማሙን፣ ድካሙን የሚያስታውሱ ቅዱሳት መጻሕፍት በየሰዓቱ ይነበባሉ፡፡ በዚህ ሳምንት መስቀል መሳለም የለም፡፡ ካህናትም ‹‹እግዚአብሔር ይፍታህ›› አይሉም፡፡ ሥርዓተ ፍትሐት አይደረግም፡፡ ይኸውም ይህ ሳምንት ከሞት ወደ ሕይወት የተሸጋገርንበት፤ ከጨለማ ወደ ብርሃን የተጓዝንበት የመሸጋገሪያ ወቅት ምሳሌ በመኾኑ ነው፡፡ በዕለተ ምጽአት መላእክት የሚያሰሙትን የመለከት ድምፅ፤ በዚያች ሰዓት ምእመናን ጥሪውን ሰምተው ከሞት እንደሚነሡ ለማጠየቅ በዚህ ሳምንት ዲያቆኑ ቃጭል እየመታ በየሰዓቱ ምእመናኑን ያሳስባል፡፡

በሰሙነ ሕማማት የሚገኙ ዕለታትና ስያሜአቸው

ዕለተ ሰኑይ (ሰኞ)

ይህ ዕለት አንጾሖተ ቤተ መቅደስ (የቤተ መቅደስ መንጻት) እና መርገመ በለስ የተፈጸመበት ዕለት ነው (ማቴ.፳፩፥፲፰-፳፪፤ ማር. ፲፩፥፲፩፤ ሉቃ. ፲፫፥፲፮)፡፡ ወንጌላዊው ቅዱስ ሉቃስ፡- ‹‹… ለአንድ ሰው በወይኑ አትክልት የተተከለች በለስ ነበረችው፡፡ ፍሬም ሊፈልግባት ወጥቶ ምንም አላገኘም፤›› በማለት በበለስ ስለ ተመሰለው የሰው ልጅ እና በንስሐ ተመልሶ በሕይወት መኖር እንደሚገባው እግዚአብሔር ኢየሱስ ክርስቶስ ማሳሰቡን ያስረዳል፡፡ በለሷ እንደ ጠወለገችና እንደ ተቈረጠች ዅሉ፣ ንስሐ አልገባም አልመለስም የሚሉም የምግባር ፍሬ ባለማፍራታቸው እንደሚቈረጡ፤ እንደዚሁም ወደ እሳት እንደሚጣሉ መጽሐፍ ቅዱስ በግልጽ ይናገራል፡፡ በለስ የተባለች ቤተ እስራኤል፤ ፍሬ የተባለ ደግሞ ሃይማኖትና ምግባር ነው፡፡ ዅላችንም ቤተ እስራኤላውያን ፍሬ ሃይማኖት እና ምግባርን አስተባብረን ይዘን መገኘት ይገባናል፡፡ ፍሬ አልባ እንዳንኾን፣ ጌታ ሲመጣም እንዳናፍር የመጽሐፉን ቃል መፈጸም ይጠበቅብናል፡፡

ዕለተ ሠሉስ (ማክሰኞ)

ይህ ቀን ጌታችን ሰኞ በተናገረውና ባደረገው ላይ አይሁድ ጥያቄ ያቀረቡበት እርሱም መልስ በመስጠት ያስተማረበት ዕለት ነው፡፡ በዚህም ምክንያት የጥያቄ እና የትምህርት ቀን በመባል ይታወቃል፡፡ ጥያቄውም ጌታ ባደረገው አንጽሖተ ቤተ መቅደስ ምክንያት ለጸሐፍትና ፈሪሳውያን ይኸውም ትምህርት ማስተማር፣ ተአምራት ማድረግ፣ ገበያ መፍታትን ‹‹በማን ሥልጣን ታደርጋለህ? ይህንስ ሥልጣን ማን ሰጠህ የሚል ነበር (ማቴ. ፳፩፥፳፫-፳፯)፡፡ ጌታችንም «… እውነት እላችኋለሁ፤ ቀራጮችና ጋለሞቶች ወደ እግዚአብሔር መንግሥት በመግባት ይቀድሙአችኋል፤›› ሲል አስተምሯል (ማቴ. ፳፩፥፳፰)፡፡

ዕለተ ረቡዕ

ይህ ዕለት ደግሞ የአይሁድ ሊቃነ ካህናትና ጸሐፍት ጌታን እንዴት መያዝ እንደሚችሉ ምክር የጀመሩበት ቀን ነው፡፡ በዚህም ምክንያት ዕለቱ ‹የምክር ቀን› በመባል ይጠራል፡፡

ዕለተ ሐሙስ

ጌታችን አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዚህ ዕለት ፍጹም ሰው፤ ፍጹም አምላክ መኾኑን ለመግለጥ እና ለአርአያነት ሲጸልይ በማደሩ ምክንያት ዕለቱ ‹ጸሎተ ሐሙስ› በመባል ይታወቃል፡፡ ትሕትናንና ፍቅርን እንደዚሁም የአገልግሎትን ትርጕም ለማስረዳትና ለማስገንዘብ ጌታችን የደቀ መዛሙርቱን እግር በማጠቡ ዕለቱ ‹ሕጽበተ ሐሙስ› በመባልም ይጠራል፡፡ ጌታችን የደቀ መዛሙርቱን እግር ባጠበ ጊዜም፡- «… ያደረግሁላችሁን ታስተውሉታላችሁን?… እንግዲህ እኔ ጌታና መምህር ስኾን እግራችሁን ካጠብሁ እናንተ ደግሞ እርስ በእርሳችሁ ትተጣጠቡ ዘንድ ይገባችኋል፤››  በማለት የእርሱን አርአያነት መከተል እንደሚገባ አስተምሯል (ዮሐ. ፲፫፥፲፪-፳)፡፡

ዕለተ ሐሙስ ጌታችን ‹‹… ይህ ስለ እናንተ በመስቀል ላይ የሚቈረሰው ሥጋዬ ነው፤ እንካችሁ ብሉ፡፡ ይህ ስለ እናንተ የሚፈስ ደሜ ነው፤ ከእርሱ ጠጡ፤›› በማለት ምሥጢረ ቍርባንን የመሠረተበት የጀመረበት ቀን በመኾኑ ‹የምሥጢር ቀን› ተብሎም ይጠራል (ማቴ. ፳፮፥፳፮-፳፱)፡፡ ይኸውም ምእመናን ሥጋውንና ደሙን ተቀብለን ከእርሱ ጋር አንድነትና ኅብረት እንዲኖረን፤ ጥንተ ጠላት ዲለብሎስንም ፍጹም ድል ነሥተን ሰማያዊት ርስት መንግሥተ ሰማያትን እንድንወርስ ለማስቻል ነው፡፡ አይሁድ ጌታችንን የያዙበት ቀን ስለ ኾነ በዚህ ዕለት በለኆሣሥ (ብዙ የድምፅ ጩኸት ሳይሰማ) የቅዳሴ ሥርዓት ይፈጸማል፡፡ መላው ሕዝበ ክርስቲያን የሕጽበት፣ የምሥጢር፣ የጸሎት ቀን በተባለው በዚህ ዕለት በንስሐ ታጥበው፣ ሥጋ ወደሙ እንዲቀበሉ ቤተ ክርስቲያን በአጽንዖት ታስተምራለች፡፡

ዕለተ ዐርብ

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ «አውቀውስ ቢኾን የክብርን ጌታ ባልሰቀሉት» በማለት እንደ ተናገረው (፩ኛ ቆሮ. ፩፥፲፰) ይህ ዕለት የአይሁድ ካህናት ንጹሕና ጻድቅ የኾነውን ጌታ ያለበደሉና ያለጥፋቱ በሐሰት ወንጅለው የሰቀሉበት፤ ጌታችንም በፈቃዱ በመስቀል የተሰቀለበት ዕለት ነው፡፡ ይህ ዕለት ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የዓለም ዅሉ መድኃኒት ለአዳምና ለልጆቹ ሲል በመልዕልተ መስቀል በቀራንዮ አደባባይ ተሰቅሎ መዋሉን የምናስብበት ታላቅ ቀን ነው (ማቴ. ፳፯፥፴፭-፸፭)፡፡ በዚያን ጊዜ አሳልፎ የሰጠው ይሁዳ እንደ ተፈረደበት አይቶ ተጸጸተ፤ ሠላሳውንም ብር ለካህናት አለቆችና ለሽማግሎች መልሶ ‹‹ንጹሕ ደም አሳልፌ በመስጠቴ በድያለሁ›› አለ፡፡ እነርሱ ግን ‹‹እኛስ ምን አግዶን?  አንተው ተጠንቀቅ፤›› አሉ፡፡ ይሁዳም ብሩን በቤተ መቅደስ ጥሎ ሔደና ታንቆ ሞተ፡፡ የካህናት አለቆችም ብሩን አንሥተው ‹‹የደም ዋጋ ነውና ወደ መባዕ ልንጨምረው አልተፈቀደም፤›› አሉ፡፡ ተማክረውም ለእንግዶች መቃብር የሚኾን የሸክላ ሠሪ መሬት ገዙበት፡፡ ስለዚህ ያ መሬት እስከ ዛሬ ድረስ ‹የደም መሬት› ተባለ (ማቴ. ፳፯፥፫-፱)፡፡

ዕለተ ዓርብ እኛ የሰው ልጆች በዘር ኃጢአት (ቁራኝነት) እንኖርበት የነበረው የጨለማ ሕይወት ያከተመባትና ፍጹም ድኅነት ያገኘንባት ታላቅ ዕለት ናት፡፡ ክርስቲያኖች ዅልጊዜም ዕለተ ዓርብ ሲመጣ የክርስቶስን ሕማሙን፣ ስቅለቱንና ሞቱን የምናስብበት ጊዜ ነው፡፡ በሮማውያን ሕግና ሥርዓት መስቀል የወንጀለኞች መቅጫ ምልክት፤ የሕይወት መቅጫ አርማ ኾኖ ሳለ ለእኛ ግን የዲያብሎስ ድል መንሻ ስላደረገው፤ በስቅለቱና በሞቱም ሕይወትን ስለአገኘን በዚህም ምክንያት ዕለቱ ‹መልካሙ ዓርብ› በመባል ይታወቃል፡፡

ቀዳሚት ሥዑር

ዕለተ ቅዳሜ እግዚአብሔር አምላካችን የሚታዩትንና የማይታዩትን፣ በእግር የሚሔዱትን፣ በክንፍ የሚበሩትን እና በባሕር የሚዋኙትን እንስሳትን፣ በመጨረሻም ሰውን በአርአያውና በአምሳሉ ፈጥሮ ያረፈባት ዕለት ነች፡፡ የመጀመሪያዋ ቅዳሜ ለእግዚአብሔር የዕረፍት ዕለት ናት፡፡ እግዚአብሔርን ፍጥረታትን ፈጥሮ ከፈጸመ በኋላ ስላረፈባት ‹ሰንበት ዐባይ› (ታላቋ ሰንበት) ትባላለች፡፡ ይህቺን ዕለት እስራኤላውያን እንዲያከብሯት ታዟል፡፡ ዕለተ ቀዳሚት (ሰንበት ዐባይ) በዘመነ ሐዲስም የተለየ የደኅነት ሥራ ተከናውኖባታል፡፡ እግዚአብሔር ጥንት ሥነ ፈጥረትን በመፍጠር ዕረፍት እንዳደረገባት ዅሉ፣ የፍጥረት ርእስ የኾነውን አዳምን ለማዳን ሕማምና ሞት የተቀበለው አምላካችን ክርስቶስ በመቃብር አርፎባታል (ማቴ. ፳፯፥፷፩)፡፡

ቀዳሚት ሰንበት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በከርሠ መቃብር አርፎ የዋለባት ዕለት በመኾኗ ‹ቀዳሚት ሥዑር› ትሰኛለች፡፡ ‹ሥዑር› የተባለችበት ምክንያትም በዓመት አንድ ቀን ስለምትጾም (የጾም ቀን በመኾኗ) ነው፡፡ የጌታችን እናት ቅድስት ድንግል ማርያም፣ ወዳጆቹ ቅዱሳን ሐዋርያት ጌታችን ተላልፎ ከተሰጠበት ዕለት ጀምሮ ብርሃነ ትንሣኤውን እስኪያዩ ድረስ እኽል ውኃ በአፋቸው አልዞረም፡፡ ይመኩበትና ተስፋ ያደረጉት የነበረ አምላካቸው በመቃብር ስላረፈ ዕለቷን ሞቱን በማሰብና ትንሣኤውን በመናፈቅ በጾም አክብረዋታል፡፡

እመቤታችንና ቅዱሳን ሐዋርያት በማዘን፣ በመጾምና በመጸለይ ዕለቷን እንዳከበሯት ዅሉ የተዋሕዶ ልጆችም የተቻላቸው ከዓርብ ጀምረው በማክፈል (በመጾም) እኽል ውኃ ሳይቀምሱ ለሁለት ቀናት ያድራሉ፡፡ ያልተቻላቸው ደግሞ ዓርብ ማታ በልተው ቅዳሜን በመጾም ትንሣኤን ያከብራሉ፡፡ በዚህ ዕለት ከሰኞ ከሆሣዕና ማግሥት ጀምረው እስከ ስቅለተ ዓርብ ድረስ በስግደት እና በጾም ያሳለፉ ምእመናን በዕለተ ቅዳሜ በቅጽረ ቤተ ክርስቲያን ይሰበሰባሉ፡፡ የጠዋቱ ጸሎት ሲፈጸምም ካህናቱ ‹‹ገብረ ሰላመ በመስቀሉ፤ በመስቀሉ ሰላምን መሠረተ» እያሉ በቤተ ክርስቲያን ለተሰበሰቡ ምእመናን የምሥራች ቄጠማ ያድላሉ፡፡

ቄጠማው የምሥራች ምልክት ነው፡፡ ቄጠማው የምሥራች ምልክት ተደርጐ የተወሰደው በኖኅ ዘመን ከተፈጸመው ታሪክ ጋር በማቆራኘት ነው፡፡ ቅዱስ መጽሐፍ እንደሚነግረን በጻድቁ ኖኅ ዘመን የነበሩ ሕዝቦች ከሕገ እግዚአብሔር ውጪ ኾነው እጅግ የሚያሳዝን ኃጢአት በሠሩ ጊዜ በንፍር ውኃ ተጥለቅልቀዋል፡፡ በወቅቱ ጻድቁ ኖኅ ወደ መርከብ ይዞአቸው ከገባው እንስሳት መካከል የውኃውን መጉደል ለመረዳት ርግብን በመርከብ መስኮት አሾልኮ ይለቃታል፤ እርሷም ቄጠማ በአፍዋ ይዛ ትመልሳለች፡፡ ኖኅም በዚህ ቄጠማ የውኃውን መድረቅ ተረድቶ ተደስቷል (ዘፍ. ፱፥፩-፳፱)፡፡

ቄጠማ ለጥፋት ውኃ መድረቅ የምሥራች መንገሪያ እንደ ኾነ ዅሉ፣ አሁንም ‹‹በክርስቶስ ሞት ሞተ ነፍስ ከሰው ልጆች ተወገደ፤›› ስትል ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ለልጆቿ ቄጠማ ታድላለች፡፡ ምእመናንም የምሥራች ተምሳሌት የኾነውን ቄጠማ በግንባራቸው ያስሩታል፡፡ የክርስቶስ ተከታዮች ዅሉ ከጨለማ ወደ ብርሃን፤ ከዋዕየ ሲኦል (የሲኦል ቃጠሎ) ወደ ጥንተ ማኅደራቸው ገነት መመለሳቸውን በዚህ አኳኋን እየገለጡ በዓለ ትንሣኤን በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ያከብራሉ፡፡

 ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ሰሙነ ሕማማት (ከሰኞ እስከ ረቡዕ)

በመ/ር ኃይለ ማርያም ላቀው

ሚያዝያ ፫ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

ሰሙነ ሕማማት እግዚአብሔር ለሰው ልጆች ያለው ፍቅር ስለ ተገለጠበት፣ የመሥዋዕትነት ሥራ ስለ የተሠራበት፣ የሰው ልጆች ድኅነት ስለ ተፈጸመበት፣ መድኃኔ ዓለም በመስቀል ተሰቅሎ ለእኛ ቤዛ መኾኑ በስፋት ስለሚነገርበት ‹ቅዱስ ሳምንት› ይባላል፡፡ በተጨማሪም ‹የመጨረሻ ሳምንት› ተብሎ ይጠራል፡፡ ይኸውም ጌታችን አምላችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዚህ ዓለም በመዋዕለ ሥጋዌው ለፈጸማቸው የቤዛነትና የአርአያነት ተግባራት ፍጻሜ በመኾኑ ነው፡፡

በዚህ ልዩ ሳምንት ካህናትና ምእመናን በነግህ፣ በሠልስት፣ በቀትር፣ በተሰዓትና በሠርክ ወደ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በመጓዝ ስለ ጌታችን ኢየስስ ክርስቶስ ሕማማተ መስቀል የሚያዘክረውን ምዕራፍ ከቅዱሳት መጻሕፍት በማንበብና በመጸለይ ሕማሙንና ሞቱን ይዘክራሉ፤ ቅዱስ ያሬድ በመጨረሻው ሳምንት በየዕለቱ በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ላይ የተፈጸመውን ነገረ መስቀል በተመለከተ ያዘጋጀውን መዝሙር ይዘምራሉ፤ አብዝተው ስግደትን ይሰግዳሉ፡፡

ሰሙነ ሕማማትን ከሌሎች የዐቢይ ጾም ሳምንታት ልዩ የሚያደርገው ሥርዓት አለ፡፡ በኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አብያተ ክርስቲያናት ሥርዓትና ደንብ መሠረት በሰሙነ ሕማማት ከጸሎተ ሐሙስ በስተቀር ቅዳሴ አይቀደስም፤ ስብሐተ ነግህ አይደረስም፤ ጸሎተ ፍትሐት አይጸለይም፤ ጸሎተ አስተስርዮም አይደረግም፡፡ ጥምቀተ ክርስትናም አይፈጸምም፡፡ ከላይ የተዘረዘሩት የቤተ ክርስቲያን ሥርዓቶች አስቀድሞ በዕለተ ሆሣዕና ይከናወናሉ፡፡ በተጨማሪም ማንኛውም ክብረ በዓል በዚህ ሳምንት ቢውል ከትንሣኤ በኋላ ይከበራል፡፡ ይህም በኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አብያተ ክርስቲያናት ዘንድ የጸና ኦርቶዶክሳዊ ሥርዓት ነው፡፡

ሕማምና ሞት የማይገባው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የእኛን ሕማምና ሞት ለራሱ በማድረግ በዚህ ሳምንት ለእኛ ቤዛ መኾኑ ይነገራል፡፡ ‹‹ደዌያችንን ተቀበለ፤ ሕማማችንንም ተሸከመ፡፡ ከዓመፀኞችም ጋር ተቈጠረ፡፡ እርሱ ግን ግፍን አላደረገም፤ ተንኮልም በአፉ አልተገኘበትም፤›› ተብሎ እንደ ተጻፈ (ኢሳ. ፶፫፥፬-፲፪)፡፡ ምእመናን ክርስቶስ የተቀበለው የእኛን ሕማም መኾኑን በመዘከር፤ ከማንኛውም የሥጋ ሥራ በመታቀብ ዋዛ ፈዛዛ ባለመነጋገር ሰሙነ ሕማማትን ልናከብር ይገባል፡፡ ብድራትን የማያስቀረው አምላካችን እግዚአብሔር መተላለፋችንና በደላችንን በመደምሰስ የመንግሥቱ ወራሽ አድርጎናልና፡፡

ሰሙነ ሕማማት አስከ አራተኛው ምዕተ ዓመት ድረስ ከዐቢይ ጾም ተለይቶ ለብቻው ይከበር ነበር፡፡ በኋላ ግን በባሕረ ሐሳብ ቀመር መሠረት ጾሙም፣ ሕማማቱም፣ ትንሣኤውም ተከታለው እንዲከበሩ ተደረገ፡፡ ምዕራባውያን ከዐርባ ጾም ውስጥ የመጨረሻውን ሳምንት ሰሙነ ሕማማት ያደርጉታል፡፡ የምሥራቃውያን (ኦርየንታል) ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አብያተ ክርስቲያናት ግን ዐርባውን ጾም ጨርሰን ከኒቆዲሞስ በኋላ ያለውን ተከታዩን አንድ ሳምንት ሰሙነ ሕማማት አድርገን እናከብራለን፡፡ ከእነዚህ የሕማማት ሳምንት ውስጥ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሦስቱ ዕለታት (በሰኞ፣ ማክሰኞ እና ረቡዕ) ያከናወናቸው የድኅነት ሥራዎች የሚከተሉት ናቸው፡፡

ሰኞ

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሰው ኾኖ በዚህ ዓለም ሲመላለስ በሆሣዕና ማግሥት ከቢታንያ ወደ ኢየሩሳሌም ሲገባ ሁለት ነገሮችን አከናውኗል፤ አንደኛ ከቅጠል በስተቀር ፍሬ ያልተገኘባትን ዕፀ በለስ ረግሟል፡፡ ሁለተኛ ወደ ቤተ መቅደስ ገብቶ የሚሸጡትንና የሚለውጡትን አስወጥቷል (ማቴ. ፳፩፥፲፪-፲፯፤ ማር. ፲፩፥፲፯፤ ሉቃ. ፲፱፥፵፭-፵፮)፡፡ በቅዱስ ማቴዎስ አገላለጥ ‹‹በማግሥቱ ተራበ›› የሚል ቃል እንመለከታለን፡፡ ነቢዩ ኢሳይያስ ‹‹እግዚአብሔር ለዘለዓለም አይራብም፤ አይጠማም፤ አይደክምም፤›› ይላል (ኢሳ. ፵፮፥፳፭)፡፡ በቅዱስ ወንጌል በመጀመሪያ ቃል እንደ ነበር፤ ያ ቃል ቀዳማዊ እንደ ኾነ፤ ቃልም በእግዚአብሔር ዘንድ እንደ ነበር፤ ያም ቃል እግዚአብሔር እንደ ኾነ ተጽፏል (ዮሐ. ፩፥፩-፪)፡፡ ጌታችንም በመዋዕለ ትምህርቱ ሲያስተምር፡- ‹‹የእኔስ መብል የላከኝን የአባቴን ፈቃድ አደርግ ዘንድ፤ ሥራውንም እንፈጽም ዘንድ ነው፤›› ሲል ተናግሯል (ዮሐ. ፬፥፴፬)፡፡ ታዲያ ጌታችን ለምን ተራበ?

ሰማያውያን መላእክት እንዳይራቡ አድርጎ የፈጠረ፤ እስራኤልን ገበሬ በማያርስበት፣ ዘር በሌለበት፣ ዝናብ በማይጥልበት ምድረ በዳ የመገበ፤ ድኅረ ሥጋዌ በአምስት አንጀራና በሁለት ዓሣ ከአምስት ሺሕ የሚበልጡ ሰዎችን የመገበ ጌታ ‹‹ተራበ›› ተብሎ ሲነገር እጅግ ይደንቃል፡፡ በእርግጥ ኢየሱስ ክርስቶስ ፍጹም አምላክ ፍጹም ሰው በመኾኑ አልተራበም አንልም፡፡ የጌታችን ረኃብ የድህነት (የማጣት) አይደለም፡፡ የክርስቶስ ረኃቡ የበለስ ፍሬ ሳይኾን የሃይማኖትና የመልካም ሥነ ምግባርን ፍሬ የሻ መኾኑን ለማጠየቅ ‹‹ተራበ›› ተባለ፡፡ ‹‹በለስ ብሂል ቤተ እስራኤል እሙንቱ›› እንዲል፡፡ ጌታችን የፈለገውን ባለማግኘቱ ጉባኤ አይሁድን ረግሟል፡፡ በአይሁድ ጉባኤ የነገሠውን ኃጢአት፤ በበለስ አንጻር መርገሙን ታላቁ ሊቅ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ‹‹በአንጻረ በለስ ረገማት ለኃጢአት፤ በበለስ አንጻር ኃጢአትን ረገማት›› ብሏል፡፡

እስራኤልም በአንድ ወገን የተጠበቀባቸውን ፍሬ ባለማፍራታቸው ተረግመዋል፡፡ ሊቁ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እስራኤል ከፍቅር ይልቅ እርግማን እንዳገኛቸው፤ አሕዛብ ደግሞ የቃሉን ትምህርት ሰምተው የእጁን ተአምራት አይተው ያመኑበትን የእግዚአብሔር የጸጋ ልጁ ለመኾን መብቃታቸውን ሲመሰክር እንዲህ ይላል፤ ‹‹አሕዛብ አስተጋብኡ ጽጌሬዳ በኂሩቱ ወሶኩሰ ተርፈ ኀበ አይሁድ ዘውእቱ ሕፀተ ሃይማኖት፤ አሕዛብ በእግዚአብሔር ቸርነት አበባ ሰበሰቡ፤ በአይሁድ ዘንድ ግን እሾኹ ተረፈ፡፡ ይኸውም የሃይማኖት ጉድለት ነው፤›› ብሎ ተርጕሞታል፡፡ እሾኽ የእርግማን፤ አበባ የእግዚአብሔር ጸጋ ልጅነት ምሳሌ ነው፡፡

የእግዚአብሔር ቤተሰቦች! ዛሬ ጌታችን ወደ መቅደስ ሕይወታችን ቢመጣ ምን ያገኝ ይኾን? ፍሬ ወይስ ቅጠል? የእግዚአብሔር ቃል ‹‹ለንስሐ የሚገባ ፍሬ አድርጉ፤›› ይለናልና እግዚአብሔር ከእኛ የሚፈልገውን የመንፈስ ቅዱስ ፍሬ እናፍራ (ማቴ. ፫፥፰፤ ገላ. ፭፥፳፪)፡፡ ጌታችን በዳግም ልደት ሲመጣ ከሰው ልጅ ሃይማኖት መገኘቱ አጠራጣሪ እንደ ኾነ ተናግሯል፡፡ ‹‹የሰው ልጅ ወደዚህ ዓለም ሲመጣ ሃይማኖት ያገኝ ይኾንን?›› ሕይወታችንን በአምላካዊ ሥልጣኑ የቃኘ አምላክ ለፍርድ በመጣ ጊዜ የእምነት ፍሬ አፍርተን እንዲያገኘንና ዘላለማዊ መንግሥቱን እንዲያወርሰን የጽድቅ ሥራ ለመሥራት እንትጋ፡፡

ማክሰኞ

በማቴዎስ ወንጌል ፳፩፥፳፰፤ ፳፭፥፵፮፤ ማርቆስ ወንጌል ፲፪፥፲፪፤ ፲፫፥፴፯፤ በሉቃስ ወንጌል ፳፥፱፤ ፳፩፥፴፰ የሚገኙ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች ማክሰኞ ዕለት የሚነገሩ ትምህርቶችን ይዘዋል፡፡ በዚህ ዕለት ጌታችን በቤተ መቅደስ ረጅም ትምህርት ስላስተማረ ዕለቱ የትምህርት ቀን ይባላል፡፡ ክርስቲያን የኾነ ዅሉ ከሥጋዊ ነገር ርቆ በዚህ ሰሞን የሃይማኖት ትምህርት ሲማር፣ ሲጠይቅ መሰንበቱ መጽሐፋዊ ሥርዓት ነው፡፡

በዚህ ዕለት ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ ሥልጣኑ ተጠይቋል፡፡ ጠያቂዎቹ የካህናት አለቆችና የሕዝብ አለቆች ሲኾኑ፣ ጥያቄውም፡- ‹‹በማን ሥልጣን እነዚህን ታደርጋለህ? ይህንስ ሥልጣን የሰጠህ ማነው?›› የሚል ነበር፡፡ ይህ ጥያቄ ጌታችን ሰኞ ዕለት ሁለት ነገሮችን ማከናወኑን ተከትሎ የተነሣ ጥያቄ ነው፡፡ ይኸውም ጌታችን ሲያደርጋቸው የነበሩ ተአምራትና ድንቅ ድንቅ ሥራዎች የካህናት አለቆችን ስላስቀኗቸው ጌታችንን ከሮማ መንግሥት ባለ ሥልጣናት ጋር ለማጋጨት የቀየሱት ስልት ነው፡፡ ጌታችን በቤተ መቅደስ የነበሩትን ነጋዴዎችን አባሯል፤ መደባቸውን ገለባብጧል፡፡ ነጋዴን ማባረርና መደብን ማስለቀቅ መንግሥታዊ ሥራ ነው፡፡ ጌታችን ‹‹በራሴ ሥልጣን›› ቢላቸው ፀረ መንግሥት አቋም አለው በማለት ከሮማ መንግሥት ዘንድ ለማሳጣት ነበር ዕቅዳቸው፡፡

ጌታችን ግን የፈሪሳውያንን ጠማማ አሳብ ስለሚያውቅ ‹‹የዮሐንስ ጥምቀት ከየት ነው? ከሰማይ ነው ወይስ ከምድር?›› ሲል ጠይቋቸዋል፡፡ ጌታችን ፈሪሳውያን ላቀረቡለት ጥያቄ ቀጥተኛ ምላሽ አልሰጠም፡፡ ምክንያቱም ጥያቄው ለከሳሾቹ ዓላማ መሳካት አመቺ ኹኔታን ስለሚፈጥር ጥያቄውን በጥያቄ መልሶላቸዋል፡፡ እነርሱም ‹‹ከሰማይ ነው›› ቢሉት ‹‹ለምን አላመናችሁበትም?›› እንዳይላቸው፤ ‹‹ከሰው ነው›› ቢሉት ደግሞ ሕዝቡ ዮሐንስን እንደ አባት ይፈሩት፣ እንደ መምህር ያከብሩት ነበርና ሕዝቡ እንዳይጣሏቸው ስለፈሩ ‹‹ከወዴት እንደ ኾነ አናውቅም›› ብለው መለሱለት፡፡ እርሱም ‹‹እኔም በማን ሥልጣን እነዚህን እንደማደርግ አልነግራችሁም›› አላቸው፡፡ ይህን ጥያቄ መጠየቃቸውም እርሱ የሚያደርጋቸውን ተግባራት ዅሉ በራሱ ሥልጣን እንዲያደርግ አጥተውት አልነበረም፤ ልቡናቸው በክፋትና በጥርጥር ስለተሞላ ነበር እንጂ፡፡

ዛሬም ቢኾን መልካም ሥራን በሠራን ጊዜ ከልዩ ልዩ ወገኖች የሚመጡ ፈተናዎች ለመልካም ሥራችን እንቅፋት ሊኾኑ እንደሚችሉ መገንዘብ አለብን፡፡ ብዙ ወገኖች ‹‹ለቅን አሳባችን ለምን ሰዎች ክፉ ነገር ይመልሱልናል?›› በማለት ሲጠይቁ ይሰማል፡፡ ለቅን አሳባችን ከዓለም ዘንድ ተቃራኒ ነገር እንደሚጠብቀን ለመረዳት ‹‹ዓለም የሚወደው የገዛ ወገኑን ነው›› የሚለውን የጌታችንን ትምህርት ልብ ይሏል፡፡ በዘመናችን አሳልፈው ሊሰጡን የሚፈልጉ ሰዎች ፈታኝ ጥያቄ እንደሚያቀርቡልንም ከወዲሁ ልንገነዘብ ይገባል፡፡

 ረቡዕ

በቅዱስ ማቴዎስና በቅዱስ ማርቆስ አመዘጋገብ መሠረት በዕለተ ረቡዕ የሚከተሉት ሦስት ነገሮች ተፈጽመዋል፤

  • አንደኛ የካህናት አለቆች፣ የሕዝብ ሽማግሌዎችና ጸሐፍት ፈሪሳውያን በጌታችን ላይ  ተማክረዋል፤
  • ሁለተኛ ጌታችን በስምዖን ዘለምጽ ቤት ሳለ አንዲት የተጸጸተች ሴት ሽቱ ቀብታዋለች፡፡
  • ሦስተኛ ከዳተኛው ይሁዳ ጌታችንን አሳልፎ ለመስጠት ከጸሐፍት ፈሪሳውያንና ከካህናት አለቆች ዘንድ ሠላሳ ብር ለመቀበል ተስማምቷል፡፡

የካህናት አለቆችና የሕዝብ ሹማምት በጌታችን ላይ ይሙት በቃ ለመወሰን የሰበሰቡት ሸንጐ ሲኒሃ ድርየም› ይባላል፡፡ በዚህ ሸንጐ ላይ በአብዛኛው የተሰየሙት ሰዱቃውያን ሲኾኑ ሌሎቹ ደግሞ ጸሐፍት ፈሪሳውያን ነበሩ፡፡ ሸንጐው በአጠቃላይ ሰባ ሁለት አባላት የነበሩት ሲኾን የሚመራውም በሊቀ ካህናቱ በቀያፋ ነበር፡፡ በዕለቱ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን እንዴት ይዘው እንደሚገድሉት አይሁድ በዚህ ሸንጎ መክረዋል፡፡ ከዳተኛው ይሁዳም ጸሐፍት ፈሪሳውያንና የካህናት አለቆች በጌታን ላይ የነበራቸውን ጥላቻ ያውቅ ስለነበር ‹‹ምን ልትሰጡኝ ትወዳላችሁ? እኔም አሳልፌ እሰጣችኋለሁ፤›› በማለት ጌታችን አሳልፎ ሊሰጣቸው እንደሚችል ተስማቷል፡፡

ጌታችን ያስተምር በነበረበት ወቅት የአስቆሮቱ ይሁዳ ከምእመናን ለሚገባው ገንዘብ ሰብሳቢ (ዐቃቤ ንዋይ) ነበር፡፡ ከሚሰበሰበው ሙዳየ ምጽዋት ለግል ጥቅሙ እየቀረጠ የማስቀረት የእጅ አመል ነበረበት፡፡ ይሁዳ ፍቅረ ንዋይ እንደሚያጠቃው ድብቅ አመሉ ጎልቶ የወጣው ጌታችን በለምጻሙ በስምዖን ቤት ሳለ አንዲት ሴት ዋጋው ውድ የኾነ ሽቱ በቀባችው ጊዜ ነው፡፡ በዚያች ዕለት ይሁዳ የተቃውሞ ድምፅ ካሰሙት አንዱ ነበር፡፡

‹‹ይህ ሽቱ ተሽጦ ለድሆች ቢሰጥ መልካም ነበር፤›› በማለት ያቀረበው አሳብ ‹‹አዛኝ መሳይ ቅቤ አንጓች›› እንደሚባለው ነበር፡፡ ሽቱ ሲሸጥ የሚያገኘው ጥቅም አለ፤ ሽቶው በጌታችን እግር ሥር ከፈሰሰ ለእርሱ የሚተርፈው የለም፡፡ ይሁዳ ተቆርቋሪ መስሎ ያቀረበው አሳብ ተቀባይነት በማጣቱም ማኩረፊያ ያገኘ መስሎት በቀጥታ ከካህናት አለቆች ዘንድ ሔዶ ጌታንን በሠላሳ ብር ለመሸጥ ተዋዋለ፡፡ ይህ ታሪክም በሦስቱ ወንጌላት ውስጥ በሚከተሉት ምዕራፎች ተመዝግቦ እናገኛዋለን፤ ማቴ. ፳፮፥፫-፲፮፤ ማር. ፲፬፥፩-፲፩፤ ሉቃ. ፳፪፥፩፮፡፡

የአስቆሮቱ ይሁዳ እንደ ሌሎች ሐዋርያት ከጌታችን ተምሯል፡፡ በረከተ ኅብስቱን ተመግቧል፡፡ ልዩ ልዩ ተአምራት በጌታችን እጅ ሲደረጉ ዅሉ ተመልክቷል፡፡ ጌታችንም ከሌሎች ሐዋርያት ሳይለየው እግሩን አጥቦታል፡፡ ከዳተኛው ይሁዳ ግን ለሐዋርያነት የጠራውን፣ ተንበርክኮ እግሩን ያጠበውን ጌታ ለሞት አሳልፎ ሰጥቷል፡፡ ‹‹የሰው ልጅስ ስለ እርሱ እንደ ተጻፈ ይሔዳል፤ ነገር ግን የሰው ልጅ አልፎ ለሚሰጥበት ለዚያ ሰው ወዮለት!›› ተብሎ እንደ ተጻፈ (ማቴ. ፳፮፥፳፬)፡፡ ሌሎች ሐዋርያት ከጌታችን ዘንድ ፍቅሩን ገንዘብ ሲያደርጉ ይሁዳ ግን እርግማንን ነው ያተረፈው፡፡ ‹‹ገንዘብ የኃጢአት ሥር ነው፤›› ተብሎ አንደ ተነገረ የኃጢአት ሥር የተባለው ገንዘብ የክርስቲያኖችን ሕይወት ያዳክማልና ምእመናን እንደ ይሁዳ በገንዘብ ፍቅር እንዳንወድቅ መጠንቀቅ ያስፈልጋል፡፡ ሰው ‹‹ይህን ዓለ ቢያተርፍ ነፍሱን ከጐዳ ምን ይጠቅመዋል?›› ተብሎ የተነገረውን ቃል ልብ ማለት ጠቃሚ ነው፡፡

ክርስቲያን ነን በማለት የክርስትናውን ስም በመያዝ እምነታቸውን፣ የቆሙበትን ዓላማ በመገንዘብ የሚለውጡ ሰዎች ዛሬም እንደ ይሁዳ ጌታችንን እየሸጡት እንደ ኾነ ሊገነዘቡት ይገባል፡፡ ለድሆች መመጽወት ክርስቲያናዊ ግዴታ ነው፡፡ ዳሩ ግን በድሆች ስም የሰውን ገንዘብ ለግል ጥቅም ማዋል እጅግ የከፋ ኃጢአት ነው፡፡ እንደዚህ ዓይነት ሰዎች ለገንዘብ ብለው ድሆችን ለረኃብ ለችግር ባልንጀራቸውን ለመከራ እና ለሞት አሳልፈው ሲሰጡ ምንም አይጸጽታቸውም፡፡ እውነተኛ ክርስቲያኖች ግን ሕይወታችንን ለገንዘብ ፍቅር ሳይኾን ለእምነታችንና ለባልንጀራችን አሳልፈን መስጠት ይኖርብናል፡፡ በፍቅረ ንዋይ ተጠምደን ሰዎችን አሳልፎ በመስጠት ለአይሁዳዊ ሸንጐ ምቹ ኾነን መገኘት እንደሌለብን መገንዘብ አለብን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ምንጭ፡

ስምዐ ተዋሕዶ (ልዩ ዕትም ዘሰሙነ ሕማማት)፣ ከሚያዝያ ፩ -፲፭ ቀን ፳፻፬ ዓ.ም፣ ገጽ ፬-፮፤ ማኅበረ ቅዱሳን፣ አዲስ አበባ፡፡