የዘመነ ጰራቅሊጦስ ምንባባት

ግንቦት ፳፮ ቀን ፳፻፱ .

በዓለ ጰራቅሊጦስ ሀብተ መንፈስ ቅዱስ ለሐዋርያት የተሰጠበት፤ ብዙ ሺሕ ምእመናን የሥላሴን ልጅነት ያኙበት ዕለት በመኾኑ ‹የቤተ ክርስቲያን የልደት ቀን› ተብሎ ይጠራል፡፡ በዓሉ ከዘጠኙ የጌታችን ዐበይት በዓላት አንዱ ሲኾን፣ በያዝነው ዓመትም ግንቦት ፳፯ ቀን ይዘከራል፡፡ መንፈስ ቅዱስ ከወረደበት ሰንበት (ከኀምሳኛው ቀን) ጀምሮ እስከሚቀጥለው ሰንበት ያለው ጊዜም (ስምንቱ ቀናት) ‹ዘመነ ጰራቅሊጦስ› ወይም ‹ሰሙነ ጰራቅሊጦስ› ይባላል፡፡ ይህም መንፈስ ቅዱስ በሐዋርያት ላይ ስለ መውረዱና በምእመናን ላይ ስለ ማደሩ የሚነገርበት ወቅት ነው፡፡ በዚህ ሰሙን በቤተ ክርስቲያን የሚነገረው ቃለ እግዚአብሔር፣ የሚሰጠውም ትምህርት የመንፈስ ቅዱስን በሐዋርያት ላይ መውረድ የሚመለከት ነው፡፡

በበዓለ ጰራቅሊስ ዕለት ‹ይትፌሣሕ› የሚለው የትንሣኤ መዝሙር በቤተ ክርስቲያን ይዘመራል፡፡ በቅዳሴ ጊዜ የሚነበቡ የቅዱሳት መጻሕፍት ክፍሎችም በትንሣኤ ዕለት የተነበቡት ናቸው፡፡ ምንባባቱ ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሙታን ተለይቶ በመነሣቱ፣ በማረጉና መንፈስ ቅዱስን ለሐዋርያት በመላኩ፤ እንደዚሁም ሥጋውን ቈርሶ፣ ደሙን አፍስሶ የሰውን ልጅ ከዘለዓለም ሞት በማዳኑ የሰው ዘር ብቻ ሳይኾን የሰማይ መላእክት፣ የምድር ፍጥረታት ሳይቀሩ ሐሤት እንደሚያደርጉ፤ ምድርም በክርስቶስ ደም በመንጻቷ የጌታችንን ትንሣኤ በደስታ እንደምታከብር የሚያስረዳ መልእክት አላቸው፡፡

ከበዓለ ጰራቅሊጦስ በኋላ ባሉት ሰንበታት (እሑዶች) የሚዘመሩ መዝሙራትም ትንሣኤን፣ ዕርገትን፣ የመንፈስ ቅዱስን መውረድ የሚያስረዱ ሲኾኑ፣ ምሥጢራቸውም ከሙታን ተለይቶ ለተነሣው፣ አዳምና ልጆቹን ከዲያብሎስ ተገዢነት እና ከሲኦል ባርነት ላወጣቸው ለልዑል እግዚአብሔር ምስጋና ማቅረብ እንደሚገባ ያስተምራል፡፡ ከኀምሳኛው ቀን (ከበዓለ ጰራቅሊጦስ) ቀጥሎ በሚመጣው እሑድ (በስምንተኛው ቀን) የሚዘመረው መዝሙር፡- ‹‹ወረደ መንፈስ ቅዱስ ላዕለ ሐዋርያት ከመ ዘእሳት ወተናገሩ በነገረ ኵሉ በሐውርት …›› የሚል ሲኾን፣ ትርጕሙም መንፈስ ቅዱስ በእሳት አምሳል በሐዋርያት ላይ መውረዱንና በእርሱ ኃይል በዓለሙ ዅሉ ቋንቋዎች መናገራቸዉን የሚያስረዳ ነው፡፡

በዚህ ዕለት በቅዳሴ ጊዜ የሚነበቡ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች፡- ኤፌ.፬፥፩-፲፯፤ ፩ኛዮሐ.፪፥፩-፲፰፤ ሐዋ.፪፥፩-፲፰፤ መዝ.፷፯፥፲፰ (ምስባክ)፤ ዮሐ.፲፬፥፩-፳፪ ሲኾኑ፣ የምንባባቱ ፍሬ ሐሳብም የሚከተለው ነው፤

የጳውሎስ መልእክት፡- እያንዳንዳችን መንፈስ ቅዱስ በገለጸልን መጠን የየራሳችን ልዩ ልዩ ጸጋ እንዳለን፤ የዮሐንስ መልእክት፡- የእግዚአብሔርን ፈቃድ የሚፈጽም ለዘለዓለም ሕያው እንደ ኾነ፤ የሐዋርያት ሥራ፡- መንፈስ ቅዱስ በሐዋርያት ላይ እንደ ወረደና በዓለሙ ዅሉ ቋንቋዎች መናገር እንደቻሉ፤ መዝሙረ ዳዊት (ምስባኩ)፡- እግዚአብሔር ለሰው ልጅ ልዩ ልዩ ጸጋን እንደሚሰጥ፤ የዮሐንስ ወንጌል፡- እግዚአብሔር እኛን ልጆቹን እንደ ወላጅ አልባ እንደማይተወን ያስረዳሉ፡፡ ቅዳሴው ቅዳሴ ዲዮስቆሮስ ሲኾን፣ ይህም ምሥጢረ ሥላሴን፣ የጌታችንን ሰው መኾን፣ ሕማሙን፣ ሞቱን፣ ትንሣኤዉን፣ ዕርገቱንና መንፈስ ቅዱስን መላኩን ይናገራል፡፡

ቅድስት በኾነች በጽርሐ ጽዮን በሐዋርያት ላይ የወረደው የእግዚአብሔር አብ ጸጋ፣ የእግዚአብሔር ወልድ ፍቅር፣ የእግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ አንድነት በዅላችን ላይ ይደር፤ እጽፍ ድርብም ይኹን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

በዓለ ጰራቅሊጦስ

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ግንቦት ፳፮ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

‹ጰራቅሊጦስ› የሚለው ቃል ከሦስቱ አካላት አንዱ የኾነው የእግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ መጠሪያ ስም ሲኾን፣ ትርጕሙም በጽርዕ (ግሪክ) ቋንቋ ናዛዚ (የሚናዝዝ)፣ መጽንዒ (የሚያጸና)፣ መስተፍሥሒ (የሚያስደስት) ማለት ነው፡፡ መንፈስ ቅዱስ ለሐዋርያት በወረደበት ዕለት በቤተ ክርስቲያን የሚከበረው ይህ በዓል ‹በዓለ ጰራቅሊጦስ› ወይም ‹በዓለ ጰንጠቆስጤ› በመባል ይታወቃል፡፡ ‹ጰንጠቆስጤ› በግሪክ ቋንቋ በዓለ ኀምሳ፣ የፋሲካ ኀምሳኛ ዕለት፣ በዓለ ሠዊት (የእሸት፣ የመከር በዓል) ማለት ነው (ኪዳነ ወልድ ክፍሌ፣ ገጽ ፱፻፮-፱፻፯)፡፡

ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ካረገ በኋላ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም፣ ዐሥራ ሁለቱ ደቀ መዛሙርት፣ ሰባ ሁለቱ አርድእት፣ አምስት መቶው ባልንጀሮች እና ሠላሳ ስድስቱ ቅዱሳት አንስት በኢሩሳሌም ከተማ በአንድነት ኾነው በጸሎት ይተጉ ነበር፡፡ ጌታችን በሚያርግበት ጊዜ ‹‹እነሆ አባቴ የሰጠውን ተስፋ እኔ እልክላችኋለሁ፤ እናንተ ግን ከላይ ኃይል እስክትለብሱ ድረስ በኢየሩሳሌም ከተማ ቆዩ፤›› ሲል ለሐዋርያቱ በሰጣቸው የተስፋ ቃል መሠረት በዐረገ በዐሥረኛው ቀን መንፈስ ቅዱስን ልኮላቸዋል (ሉቃ. ፳፬፥፵፱)፡፡ ዅሉም በአንድ ቦታ ተሰባስበው ሳሉ በበዓለ ጰራቅሊጦስ ማለዳ እንደ ዐውሎ ነፋስ ያለ ድምፅ ድንገት ከሰማይ ወርዶ የነበሩበትን ቤት ሞላው፡፡ ከዚያም የተከፋፈሉ የእሳት ላንቃዎች በዅሉም ላይ አረፉባቸው፡፡ በዚህ ጊዜ ዅላቸውም መንፈስ ቅዱስ ባደላቸው መጠን በየአገሩ ቋንቋዎች ዅሉ ተናገሩ (ሐዋ.፪፥፩-፬)፡፡

ጌታችን መንፈስ ቅዱስን ለሐዋርያት የላከበት ይህ ዐቢይ በዓል ዐሥራቱን፣ በኵራቱን፣ ቀዳምያቱን ካህናተ ኦሪት ስለሚቀበሉበት በብሉይ ኪዳን በዓለ ሠዊት ተብሎ ይከበር ነበር፡፡ በሐዲስ ኪዳን ደግሞ ቅዱሳን ሐዋርያት መንፈስ ቅዱስን ስለ ተቀበሉበት በበዓለ ሠዊት ምትክ በዓለ ጰራቅሊጦስ ገብቶበታል፡፡ የበዓለ ትንሣኤ መነሻው የአይሁድ የፋሲካ በዓል ማለትም በግብጽ፣ እስራኤል ከሞት የዳኑበት የመታሰቢያ በዓል እንደ ኾነው ዅሉ፣ ለበዓለ ጰራቅሊጦስም መነሻው ይኸው የአይሁድ የፋሲካ በዓል ነው፡፡ የአይሁድ ፋሲካ ከተከበረ ከሰባት ሳምንታት በኋላ በኀምሳኛው ቀን የሩቆቹ ከከተሙበት ወጥተው፣ የቅርቦቹ ከተሰባሰቡበት ተገናኝተው ለበዓሉ ፍጻሜ የሚኾነውን በዓለ ሠዊት (የእሸት በዓል) ያከብሩ ነበር፡፡

ከግብጽ እስከ ከነዓን ምድር የደረሰው የእንስሳት መሥዋዕት ሲጠናቀቅ በኀምሳኛው ቀን ይሰባሰብ የነበረው የአይሁድ ጉባኤም መንፈስ ቅዱስ ከወረደበት ዕለት ጀምሮ ተበትኗል፡፡ መሥዋዕተ ኦሪቱ በአማናዊው መሥዋዕት በኢየሱስ ክርስቶስ ሥጋና ደም እንደ ተለወጠ ዅሉ ጉባኤ አይሁድም በኢየሩሳሌም ከተማ በተሰበሰቡ በቅዱሳን ሐዋርያት ጉባኤ ተለውጧል (ተቀይሯል)፡፡ ይህችውም ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ናት፡፡ ቤተ ክርስቲያናችን ከጉባኤያት ዅሉ ከፍ ከፍ ያለች የመንፈስ ቅዱስ ቤት ናትና፡፡ ‹‹ከዅሉ በላይ በምትኾን፣ ሐዋርያት በሰበሰቧት፣ በአንዲት፣ በቅድስት ቤተ ክርስቲያን እናምናለን፤›› እንዳሉ ሠለስቱ ምእት በጸሎተ ሃይማኖት፡፡

ሐዋርያት በጽርሐ ጽዮን ተሰባስበው ሳሉ መንፈስ ቅዱስ በእሳት አምሳል ወርዶ ሰማያዊ ሀብትን፣ ዕውቀትና ጸጋን አድሏቸዋል፡፡ መንፈስ ቅዱስ ከወረደላቸው በኋላም በአእምሮ ጐልምሰዋል፤ ጥቡዓን (ቈራጦች)፣ ጽኑዓን ኾነዋል፤ ለስብከተ ወንጌል የሚፋጠኑበትንና ለሰማዕትነት የሚዘጋጁበትን ልቡና ታድለዋል፡፡ ቀድሞ ይናገሩት ከነበሩት ቋንቋ በተጨማሪ ፸፩ ቋንቋዎች ተገልጠውላቸው ምሥጢራትን በልዩ ልዩ ቋንቋ መተርጐም ጀምረዋል፡፡ ሐዋርያት በየገአሩ ቋንቋ ሲናገሩ የሰሙ በዚያ የነበሩ ሰዎችም በሐዋርያት ተገረሙ፡፡ አንዳንድ የአይሁድ ወገኖች ግን በሐዋርያት ላይ ያዩት ክሥተት አዲስ ነገር ስለኾነባቸው ‹‹ጉሽ ጠጅ ጠጥተው ሰክረው የኾነ ያልኾነውን ይቀባጥራሉ›› እያሉ ሐዋርያትን ያሟቸው ነበር፡፡

ቅዱስ ጴጥሮስም ይህንን ዐሳባቸውን በመንፈስ ቅዱስ አውቆ ‹‹ሰክረዋል የምትሉ እናንተ እንደምትጠራጠሩት አይደለም፡፡ ጊዜው ማለዳ፣ ሰዓቱም ገና ሦስት ሰዓት ነውና፡፡ ዳሩ ግን በነቢዩ ኢዩኤልከዚህም በኋላ እንዲህ ይኾናል፤ መንፈሴን በሥጋ ለባሽ ዅሉ ላይ አፈሳለሁ፤ ወንዶችና ሴቶች ልጆቻችሁም ትንቢት ይናገራሉ› (ኢዩ.፪፥፳፰) ተብሎ የተነገረው ትንቢት ይፈጸም ዘንድ፣ ይህንን ድንቅ ተአምር ያደረገው እናንተ የሰቀላችሁት ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፤›› በማለት ሰፊ ትምህርተ ወንጌል ሰጥቷቸዋል፡፡

በትምህርቱም ነቢያት ትንቢት የተናገሩለት፣ ምሳሌ የመሰሉለት አምላክ ወልደ አምላክ ኢየሱስ ክርስቶስ ከሙታን ተለይቶ መነሣቱን፣ ማረጉንና ዳግም በክብር በምስጋና መጥቶ በሕያዋንና በሙታን ላይ የሚፈረድ መኾኑን ሐዋርያት እንደሚመሰክሩ በአይሁድ ፊት አሰምቶ ተናገረ፡፡ በቅዱስ ጴጥሮስ ትምህርት የተማረኩ አሕዛብም ‹‹ምን እናድርግ?›› ብለው በጠየቁት ጊዜ ከክፋታቸው ተመልሰው፣ ንስሐ ገብተው በኢየሱስ ክርስቶስ ስም እንዲጠመቁ ነገሯቸዋል፡፡ በዚያችም ሰዓት ሦስት ሺህ ሕዝብ በኢየሱስ ክርስቶስ አምኖ ተጠምቋል (ሐዋ.፪፥፩-፵፩)፡፡

ቅዱሳን ሐዋርያት፡- ‹‹በዚህች ቀን በሦስት ሰዓት ኢየሱስ ክርስቶስ ጰራቅሊጦስን ልኮልናልና በላያችን ኃይልን ሞላ፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ የእግዚአብሔር ልጅ በሕያዋንና በሙታን ይፈርድ ዘንድ ሥልጣን እንዳለው በአዲስ ቋንቋ ተናገርን፤›› በማለት በዕለቱ ያዩትንና የተደረገላቸውን፣ እንደዚሁም የበዓሉን ታላቅነት ከመሰከሩ በኋላ ይህንን በዓል ማክበር እንደሚገባ አዝዘዋል፤ በዚህ ወቅት መጾምና ማዘን ተገቢ አለመኾኑንም ተናግረዋል (ዲድስቅልያ ፴፥፴፰-፴፱፤ ፴፩፥፷፱-፸)፡፡

ከዚህ ላይ ማስተዋል የሚገባን ቁም ነገር ‹መንፈስ ቅዱስ ወረደ› ሲባል፣ በሰዉኛ ቋንቋ መንፈስ ቅዱስ ከከፍታ ወደ ዝቅታ፣ ከሩቅ ወደ ቅርብ መምጣቱን ወይም መምጣቱን ለመናገር አይደለም፡፡ የእግዚአብሔር መንፈስ በሐዋርያት ላይ አድሮ ሰማያዊ ሀብትን፣ ዕውቀትን፣ ጥበብንና ልዩ ልዩ ጸጋን ማደሉን ለማስረዳት ነው እንጂ፡፡ ይኸውም ሥራዉን በሰው ላይ መግለጡን፣ ጸጋዉንም ማብዛቱን ለማመልከት የሚያገለግል ቋንቋ ነው፡፡ ስለዚህ መንፈስ ቅዱስ በሐዋርያት ላይ ወረደ የሚለው ትምህርት መንፈስ ቅዱስን በቦታ፣ በጊዜና በወሰን መገደቡን አያመለክትም፡፡ የእግዚአብሔር መንፈስ በዓለሙ ዅሉ የሞላ ነውና፡፡ በሰው ላይ አድሮ ጥበብን ሲገልጥ ግን ‹ሞላ፤ አደረ፤ ወረደ› ተብሎ ይነገራል፡፡ የመንፈስ ቅዱስ ጸጋ ለጊዜው ለሐዋርያት ቢሰጥም፣ በእነርሱ ላይ ብቻ ሳይገደብ እስከ ዕለተ ምጽአት ድረስ በምእመናን ላይም አድሮ ይኖራልና፡፡

በዓለ ትንሣኤውን በደስታ እንድናሳልፍ ፈቅዶ እስከ ዛሬ ድረስ ስለ ጠበቀን፣ አሁን ደግሞ በጾም፣ በጸሎት ኾነን እርሱን የምናመሰግንበትን ወቅት ስላመጣልን አምላካችን ልዑል እግዚአብሔር ስሙ ለዘለዓለሙ የተመሰገነ ይኹን፡፡

ምንጮች፡

  • መዝገበ ታሪክ፣ ክፍል ፪፤ መ/ር ኅሩይ ኤርምያስ፤ ፲፱፻፺፭ ዓ.ም፤ ገጽ ፹፬-፹፭፡፡
  • መጽሐፈ ስንክሳር፣ ግንቦት ፲፰ ቀን፡፡
  • መጽሐፈ ግጻዌ፡፡
  • ማኅቶተ ዘመን፣ መ/ር በሙሉ አስፋው፤ ፳፻፩ ዓ.ም፤ ገጽ ፻፺፭-፪፻፬፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ዘመነ ዕርገት – ካለፈው የቀጠለ

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ግንቦት ቀን ፳፻፱ .

በቅዳሴ ጊዜ የሚነበቡ ምንባባትም በዕለተ ዕርገት (ሐሙስ) ከተነበቡት ጋር ተቀራራቢነት ያላቸው የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች ናቸው፡፡ ለማስታወስ ያህልም ከጳውሎስ መልእክት ሮሜ ፲፥፩ እስከ ፍጻሜው፤ ከሌሎች መልእክታት ፩ኛ ጴጥሮስ ፫፥፲፭ እስከ ፍጻሜው ድረስ ይነበባሉ፡፡ የሐዋርያት ሥራ፣ ምስባኩና ቅዳሴው ከሐሙስ ዕለቱ (ከዕርገት) ጋር አንድ ዓይነት ሲኾን ወንጌሉም ሐሙስ ጠዋት (በነግህ) የተነበበው ሉቃስ ፳፥፵፭ እስከ ፍጻሜው ድረስ ያለው ኃይለ ቃል ነው፡፡

በዘመነ ዕርገት ከሚቀርቡ ዝማሬያት መካከል ‹‹ዐርገ ሰማያተ በዐምደ ደመና›› የሚለው አንደኛው ሲኾን፣ ይህም ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ከሥጋዋ ሥጋ፣ ከነፍሷ ነፍስ የነሣ (የተዋሐደ)፤ ለእስራኤላውያን በሲና በረኀ መና ያወረደ፤ ሶስናን ከረበናት እጅ ያዳነ፤ ሰንበትን ለሰው ልጆች ዕረፍት የሠራ፤ የክርስትና ሃይማኖትን ያቀና (የመሠረተ)፤ ከሰማይ የወረደው የሕይወት እንጀራ፤ በባሕርዩ ምስጋና የሚገባው ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በደመና ተጭኖ ወደ ሰማይ ማረጉን የሚያስረዳ ሰፊ ምሥጢር አለው፡፡

ሊቁ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ዐርባ ስድስተኛውን የመዝሙረ ዳዊት ክፍል በተረጐመበት አንቀጹ ‹‹‹ድል መንሳት ባለበት የነጋሪት ድምፅ እግዚአብሔር ዐረገ› አለ እንጂመላእክት አሳረጉት› አላለም፡፡ በፊቱ መንገድ የሚመራው አልፈለገም፡፡ በዚያው ጎዳና እርሱ ዐረገ እንጂ፤›› በማለት ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በአምላካዊ ሥልጣኑ ወደ ሰማይ ማረጉን ተናግሯል፡፡ በተመሳሳይ ምሥጢር የጌታችንን ዕርገት ከነቢዩ ኤልያስ ዕርገት ጋር በማነጻጸር ነቢዩ ኤልያስ በመላእክት ርዳታ ወደ ሰማይ መወሰዱን፤ መድኀኒታችን ክርስቶስ ግን የመላእክት ፈጣሪ ነውና በእነርሱ ርዳታ ሳይኾን በገዛ ሥልጣኑ ማረጉን ሊቁ ያስረዳል (፪ኛነገ.፪፥፩-፲፫፤ ሐዋ.፩፥፱-፲፪)፡፡

ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ በተጨማሪም ‹‹ሕማም የሚስማማው ግዙፍ ሥጋን ተዋሕዶ ሳለ ከስቅለቱ አስቀድሞ በባሕር ላይ ከሔደ፣ ዛሬ ነፋስን ከፍሎ ሲያርግ ቢታይ ማንም ማን አይጠራጠር፡፡ ሥጋው አልተለወጠምና፤››  ሲል ጌታችን ከሞቱና ከትንሣኤው አስቀድሞ በውኀ ላይ እንደ ተራመደ ዅሉ፣ ከሙታን ተለይቶ ከተነሣ በኋላም በለበሰው ሥጋ በክብር በምስጋና ወደ ሰማይ ማረጉን አስረድቷል (ሃይማኖተ አበው ዘዮሐንስ አፈወርቅ፤ ክፍል ፲፫፣ ምዕ.፷፯፥፲፪-፲፭)፡፡

መጽሐፈ ስንክሳርም በዓለ ዕርገት የክብር ባለቤት ጌታችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከእኛ በነሣው ሥጋ ከአባቱና ከመንፈስ ቅዱስ ጋራ ወዳለው የአንድነት አኗኗሩ ወደ ሰማይ ያረገበት ዕለት መኾኑን ጠቅሶ፣ ‹‹ያን ጊዜ በኪሩቤል ላይ ተቀምጦ ወጣ፤ በነፋሳትም ክንፎች ላይ ኾኖ ወጣ፤›› (መዝ.፲፯፥፲) የሚለው የዳዊት ትንቢት በዚህች ቀን መፈጸሙን ያትታል፡፡ በተጨማሪም ‹‹ሌሊት በራእይ አየሁ፤ እነሆም እንደ ሰው ልጅ የሚመስል በሰማይ ደመና መጣ፡፡ በዘመናትም ወደ ሸመገለው ደረሰ፡፡ ወደ ፊቱም አቀረቡት፡፡ ወገኖችና አሕዛብ፣ በልዩ ልዩ ቋንቋም የሚናገሩ ኹሉ ይገዙለት ዘንድ ግዛትና ክብር፣ መንግሥትም ተሰጠው፡፡ ግዛቱም የማያልፍ የዘለዓለም ግዛት፤ መንግሥቱም የማይጠፋ ነው፤›› የሚለው የነቢዩ ዳንኤል ትንቢት በጌታችን ዕርገት መፈጸሙን ይናገራል (ዳን.፯፥፲፫-፲፬፤ መጽሐፈ ስንክሳር፣ ግንቦት ፰ ቀን)፡፡

ከላይ እንደ ተመለከትነው በዘመነ ዕርገት በማኅሌት፣ በቅዳሴ፣ በመሥዋዕት ጊዜ በቤተ ክርስቲያን የሚሰጡ ትምህርታት፣ የሚቀርቡ መዝሙራትና የሚነበቡ መጻሕፍት የእግዚአብሔርን ሰው መኾን፣ ተአምራቱን፣ ሕማሙን፣ ሞቱን፣ ነፍሳትን ከሲኦል ማውጣቱን፣ ትንሣኤውን፣ ለሐዋርያትና ለቅዱሳት አንስት መግለጡን፣ በተለይ ደግሞ ዕርገቱን፣ ዳግም ምጽአቱንና ምእመናን በእርሱ አምነው የሚያገኙትን ድኅነት፣ ጸጋና በረከት፣ እንደዚሁም የመንግሥተ ሰማያትን ምሥጢር የሚያስረዳ ይዘት አላቸው፡፡

ከዚሁ ዅሉ ጋርም ምርኮን (የነፍሳትን ወደ ገነት መማረክ) የሚያትቱ ትምህርቶች የሚሰጡትም በዚህ በዘመነ ዕርገት ወቅት ሲኾን፣ ይኸውም በሰይጣን ባርነት ተይዘው ይኖሩ የነበሩ ነፍሳት በኢየሱስ ክርስቶስ አምላካዊ ሥልጣን ነጻ መውጣታቸውን ያመለክታል፡፡ ‹‹ምርኮን ማረከህ፤ ወደ ሰማይም ወጣህ፡፡ ስጦታህንም ለሰዎች ሰጠህ፡፡ ያድሩ ዘንድ ይክዱ ነበርና፤›› እንዳለ ቅዱስ ዳዊት (መዝ.፷፯፥፲፰)፡፡ ይህም ጌታችን ነፍሳትን ከሲኦል ወደ ገነት እንደ መለሰ እና ለምእመናን የሥላሴ ልጅነትን እንደ ሰጠ የሚያስረዳ ሲኾን፣ ‹‹ያድሩ ዘንድ ይክዱ ነበር›› ሲልም በክህደት ይኖሩ የነበሩ ዅሉ ጌታችን በሰጠው ልጅነት ተጠርተው፣ አምነውና በሃይማኖት ጸንተው መኖራቸውን ያጠይቃል፡፡

በአጠቃላይ ዘመነ ዕርገት ወደ ላይ የመውጣት፣ የማረግ፣ ከፍ ከፍ የማለትና የማደግ ወቅት ነው፡፡ ይኸውም በአካል ማረግን (ከፍ ከፍ ማለትን) ወይም ወደ ሰማይ መውጣትን ብቻ ሳይኾን፣ በአስተሳሰብና በምግባር መለወጥን፣ በአእምሮ መጐልመስንም ያመለክታል፡፡ ከዅሉም በላይ መድኀኒታችን ክርስቶስ ወደ ሰማይ እንደ ዐረገ እና ዳግም ለፍርድ ተመልሶ እንደሚመጣ በስፋት የሚነገርበት ወቅት ነው – ዘመነ ዕርገት፡፡ ‹‹እናንተ የገሊላ ሰዎች ሆይ! ወደ ሰማይ እየአያችሁ ስለ ምን ቆማችኋል? ይህ ከእናንተ ወደ ሰማይ ያረገው ኢየሱስ፣ ወደ ሰማይ ሲሔድ እንዳያችሁት እንዲሁ ዳግመኛ ይመጣል፤›› ተብሎ እንደ ተጻፈ (ሐዋ.፩፥፲፩)፡፡ እኛም ሞት የማያሸንፈው አምላክ የኢየሱስ ክርስቶስ ልጆች እንደ መኾናችን በሞት ከመወሰዳችን በፊት (በምድር ሳለን) ለሰማያዊው መንግሥት የሚያበቃ መልካም ሥራ መሥራት ይጠበቅብናል፡፡ እናም ሕሊናችን በጽድቅ ሥራ እንዲያርግ (ከፍ ከፍ እንዲል) ዘወትር በሃይማኖታችን እንጽና፤ በክርስቲያናዊ ምግባር እንበርታ፤ በትሩፋት ሥራ እንትጋ፡፡

በሞቱ ሕይወታችንን ለመለሰልን፤ በትንሣኤው ትንሣኤያችንን፣ በዕርገቱ ክብራችንን ለገለጠልን፤ ዜና ብሥራቱን፣ ፅንሰቱን፣ ልደቱን፣ ዕድገቱን፣ ስደቱን፣ ተአምራቱን፣ ሕማሙን፣ ሞቱንና ትንሣኤውን በሰማንበት ዕዝነ ልቡናችን፣ ባየንበት ዓይነ ሕሊናችን ዕርገቱንም እንድንሰማና እንድናይ ዕድሜ ለንስሐ ሰጥቶ እስከ ዛሬ ድረስ እንደ ለጠበቀን ልዑል እግዚአብሔር ክብር ምስጋና ይደረሰው፡፡ ዳግም ለፍርድ በሚመጣበት ጊዜም ‹‹እናንተ ቡሩካን ወደ እኔ ›› የሚለውን የሕይወት ቃል እንዲያሰማን ቅዱስ ፈቃዱ ይኹንልን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ምንጮች፡

  • መጽሐፍ ቅዱስ፣ የኢትዮጵያ መጽሐፍ ቅዱስ ማኅበር፤ አዲስ አበባ፣ ፳፻ .ም፡፡
  • መዝሙረ ዳዊት ንባቡና ትርጓሜው፣ ተስፋ ገብረ ሥላሴ፤ አዲስ አበባ፣ ፲፱፻፹፪ .ም፡፡
  • ማኅቶተ ዘመን፣ / በሙሉ አስፋው፣ ገጽ ፻፺፩፻፺፬፤ አዲስ አበባ፣ ፳፻፩ .ም፡፡
  • ዝማሬ ወመዋሥዕት፣ ትንሣኤ ማሳተሚያ ድርጅት፤ አዲስ አበባ፣ ፲፱፻፹፱ .ም፡፡

ዘመነ ዕርገት 

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ግንቦት ቀን ፳፻፱ .

‹ዕርገት› በግእዝ ቋንቋ ማረግ፣ ከታች ወደ ላይ መውጣት ማለት ሲኾን የጌታችን ትንሣኤ በተከበረ በዐርባኛው ቀን የሚውለው ዐቢይ በዓልም ‹ዕርገት› ይባላል (ኪዳነ ወልድ ክፍሌ፣ ገጽ ፯፻፷)፡፡ በዓለ ዕርገት ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሙታን ከተነሣ በኋላ ለዐርባ ቀናት በግልጽም በስውርም ለቅዱሳን ሐዋርያትና ለቅዱሳት አንስት መጽሐፈ ኪዳንን፣ ትርጓሜ መጻሕፍትን፣ ምሥጢራትን፣ ሕግጋትንና ቀኖናተ ቤተ ክርስቲያንን ሲያስተምር ቆይቶ ወደ ቀደመ ዙፋኑ ወደ ሰማይ በክብር በምስጋና ማረጉን በደስታ የምንዘክርበት ዐቢይ በዓል ነው፡፡ በዓለ ዕርገት በቤተ ክርስቲያናችን በየዓመቱ በድምቀት ይከበራል፡፡ በዓሉ የሚውልበት ዕለት ሐሙስን ባይለቅም ቀኑ ግን የአጽዋማትና በዓላት ማውጫ ቀመርን ተከትሎ ከፍ እና ዝቅ ይላል፡፡

በዚህ መሠረት የዘንድሮው በዓለ ዕርገት ግንቦት ፲፯ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ይውላል ማለት ነው፡፡ ከጌታችን የዕርገት በዓል ጀምሮ (ከበዓለ ትንሣኤ ዐርባኛው ቀን) እስከ በዓለ ጰራቅሊጦስ ዋዜማ (ዐርባ ዘጠነኛው ቀን) ድረስ ያለው ወቅትም ‹ዘመነ ዕርገት› ተብሎ ይጠራል፡፡ በዘመነ ዕርገት ውስጥ በሚገኘው እሑድ (ሰንበት) ሌሊት ሊቃውንቱ የሚያደርሱት መዝሙርም ‹‹በሰንበት ዐርገ ሐመረ›› የሚል ሲኾን ይኸውም ጌታችን በሰንበት ወደ ታንኳ በመውጣት ባሕርንና ነፋሳትን እንደ ገሠፀ፤ ሐዋርያቱንም ‹‹ጥርጥር ወደ ልቡናችሁ አይግባ፤ አትጠራጠሩ›› እያለ በሃይማኖት ስለ መጽናት እንዳስተማራቸው፤ እንደዚሁም ወንጌልን ይሰብኩ፣ ያስተምሩ ዘንድ በመላው ዓለም እንደሚልካቸው፤ በሰማያዊ መንግሥቱ ይኖሩ ዘንድም ዳግመኛ መጥቶ እንደሚወስዳቸው የሚያስገነዝብ መልእክት አለው (ሉቃ.፰፥፳፪-፳፬፤ ዮሐ.፲፬፥፪፤ ፳፥፳፩)፡፡

በበዓለ ዕርገት ሊቃውንቱ ሌሊት በማኅሌት፣ በዝማሬ እግዚአብሔርን ሲያመሰግኑ ያድራሉ፡፡ ሥርዓተ ማኅሌቱ እንዳበቃ የሚሰበከው የነግህ ምስባክም፡- ‹‹ዘምሩ ለእግዚአብሔር ዘዐርገ ውስተ ሰማይ ሰማይ ዘመንገለ ጽባሕ ናሁ ይሁብ ቃሎ ቃለ ኃይል›› የሚለው የዳዊት መዝሙር ሲኾን፣ ቀጥተኛ ትርጕሙ፡- ‹‹በምሥራቅ በኩል ወደ ሰማየ ሰማያት ለወጣ (ላረገ) ለእግዚአብሔር ዘምሩ፤ የኀይል የኾነውን ቃሉን እነሆ ይሰጣል፤›› ማለት ነው (መዝ.፷፯፥፴፫)፡፡ ምሥጢራዊ ትርጕሙ ደግሞ ‹‹ነፍሳትን ይዞ ከሲኦል ወደ ገነት ለወጣ፤ አንድም በደብረ ዘይት በኩል ላረገ ለእግዚአብሔር ምስጋና አቅርቡ›› የሚል መልእክት አለው፡፡ እንደዚሁም ጌታችን በዐረገ በዐሥረኛው ቀን ‹የኀይል ቃል› የተባለ መንፈስ ቅዱስን ለሐዋርያት እንደ ላከላቸው፤ በተጨማሪም ጌታችን በሕያዋን እና በሙታን (በጻድቃን እና በኃጥአን) ላይ ለመፍረድ ዳግም እንደሚመጣ፤ እኛም ይህንን የጌታችንን የማዳን ሥራ እያደነቅን ለእርሱ ምስጋና፣ ዝማሬ ማቅረብ እንደሚገባን ያስረዳናል – ምስባኩ፡፡

በነግህ (ከቅዳሴ በፊት የሚነበበው) ወንጌል ደግሞ ሉቃስ ፳፬፥፵፭ እስከ መጨረሻው ድረስ ያለው ኃይለ ቃል ነው፡፡ ቃሉም ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሰማየ ሰማያት እንደሚወርድ፣ የሰውን ልጅ ለማዳን ሲል መከራ እንደሚቀበል፣ እንደሚሞት፣ ከሙታን ተለይቶ እንደሚነሣ፣ ወደ ሰማይ እንደሚያርግና ዳግም እንደሚመጣ በነቢያት የተነገረው ትንቢት መፈጸሙን፤ ለዚህም ቅዱሳን ሐዋርያት ምስክሮች መኾናቸውን ማለትም በመላው ዓለም እየዞሩ ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ የማዳን ሥራ እንዲሰብኩና በሰማዕትነት እንዲያልፉ፤ እንደዚሁም ሰማያዊ ሀብትንና ዕውቀትን እስኪያገኙ ድረስ በኢየሩሳሌም እንዲቆዩ መታዘዛቸውን ያስረዳል፡፡ ይህ ምሥጢር ለጊዜው የሐዋርያትን ተልእኮ የሚመለከት ይኹን እንጂ ለፍጻሜው ግን ዅላችንም ቅዱሳት መጻሕፍት የተናገሩትን ቃል አብነት አድርገን የእግዚአብሔርን ሰው መኾንና የማዳኑን ሥራ አምነን፣ ሌሎችንም በማሳመን በሃይማኖታችን ጸንተን መኖር እንደሚገባን፤ እግዚአብሔር አምላካችን ኃይሉን፣ ጸጋውን፣ ረድኤቱን እንዲያሳድርብንም ከቅድስት ቤተ ክርስቲያን መለየት እንደሌለብን የሚያስገነዝብ መልእክት አለው፡፡

በቅዳሴ ጊዜ የሚነበቡ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎችም ከቅዱስ ጳውሎስ መልእክት ዕብራውያን ፩፥፩ እስከ ፍጻሜው ድረስ፤ ከሌሎች መልእክታት ደግሞ ፩ኛ ጴጥሮስ ፫፥፲፰ እስከ ፍጻሜው፤ የሐዋርያት ሥራ ፩፥፩-፲፪ ሲኾኑ፣ ምስባኩም ‹‹ዐርገ እግዚአብሔር በይባቤ ወእግዚእነ በቃለ ቀርን ዘምሩ ለአምላክነ ዘምሩ›› የሚለው ነው፡፡ ትርጕሙም ‹‹በዕልልታና በመለከት ድምፅ ላረገ ለአምላካችን፣ ለጌታችንና ለመድኀኒታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ ምስጋና አቅርቡ›› ማለት ነው (መዝ.፵፮፥፭-፮)፡፡ ወንጌሉ ደግሞ፣ ማርቆስ ፲፮፥፲፬ እስከ ፍጻሜ ድረስ ሲኾን ቃሉም በነግህ ከተነበበው የወንጌል ክፍል ቃል ተመሳሳይነት አለው፡፡ ቅዳሴውም ቅዳሴ ዲዮስቆሮስ ሲኾን ይህ ቅዳሴ ከሦስቱ አካላት አንዱ የኾነውን የእግዚአብሔር ወልድን (የኢየሱስ ክርስቶስን) ዘለዓለማዊነት የሚያስረዳ፤ ሥጋዌዉን፣ ሕማሙን፣ ሞቱን፣ ትንሣኤዉን፣ ዕርገቱንና ዳግም ምጽአቱንም የሚናገር በመኾኑ በዘመነ ትንሣኤ፣ በዘመነ ዕርገትና በበዓለ ኀምሳ ሰሙን ይቀደሳል፡፡

ቅዱስ ዲዮስቆሮስ በቅዳሴዉ መጀመሪያ ላይ ሀልዎተ እግዚአብሔርንና ምሥጢረ ሥላሴን መሠረት በማድረግ ለእግዚአብሔር ምስጋና ካቀረበ በኋላ፣ ቍጥር ፴፩ ላይ ‹‹… ወበ፵ ዕለት አመ የዐርግ ሰማየ አዘዞሙ እንዘ ይብል ጽንሑ ተስፋሁ ለአብ፤ከሙታን ተለይቶ በተነሣ በዐርባኛው ቀን በብርሃን፣ በሥልጣን፣ በይባቤ ወደ ሰማይ በሚያርግበት ጊዜ ‹አብ የሚሰድላችሁ መንፈስ ቅዱስን እስክትቀበሉ ድረስ ከዚህ ቆዩ ብሎ አዘዛቸው›፤›› በማለት ቅዱስ ወንጌልን መሠረት ባደረገ ኃይለ ቃል ጌታችን ወደ ሰማይ ስለ ማረጉና ለሐዋርያት አምላካዊ ትእዛዝ ስለ መስጠቱ ይናገራል (ሉቃ.፳፬፥፵፱)፡፡

ይቆየን

ፍልሰተ ዐፅሙ ለአቡነ ተክለ ሃይማኖት

በዝግጅት ክፍሉ

ግንቦት ፲፩ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

ቅዱሳን ጻድቃን በሕይወተ ሥጋ ሳሉም ኾነ ካረፉ በኋላ (በዐጸደ ሥጋም ኾነ በዐጸደ ነፍስ) በጸሎታቸው ለሚታመኑ፣ በቃል ኪዳናቸው ለሚማጸኑ ምእመናን በመጸለይና ወደ እግዚአብሔር በማማለድ ድኅነተ ሥጋ፣ ድኅነተ ነፍስን የሚያስገኙልን የችግር ጊዜ አማላጆቻችንና አስታራቂዎቻችን ናቸው፡፡ ቅዱሳን በጸሎታቸውና በትምህርታቸው ከከበቡን የነፍስ ጠላቶች፤ ከርኲሳን መናፍስትና ከጨለማው ልጆች፤ ከክፉ ሰዎች ሽንገላና ተንኰል ለመሰወርና ለመጠበቅ ከእግዚአብሔር የተቀበሉት ሥልጣን ምን ጊዜም ሲሠራ ይኖራል፡፡ በጻድቃን መኖር አገር ከጥፋት ትድናለች፡፡

የጻድቃንን ስም ጠርቶ እግዚአብሔርን በመለመን በረከትና ረድኤት ይገኛል፡፡ ስለ ጻድቃን ብሎ እግዚአብሔርም ምሕረቱን ያድላል፡፡ እነርሱን ማሰብና ማክበር፣ ሥራቸውንም መዘከር ክርስቲያናዊ ሕይወታችንን ያጐለምሳል፡፡ ለድኅነተ ሥጋ፣ ለድኅነተ ነፍስ ይረባል፤ ይጠቅማል፡፡ ስለዚህም ነው ቅዱስ ወንጌል ቅዱሳን ጻድቃንን እንድናስባቸው፣ በስማቸውም ለድሆችና ለጦም አዳሮች እንድንመጸውት፣ መታሰቢያቸውን እንድናደርግ የሚመክረን፤ የሚያስተምረን (ማቴ.፲፥፵፩-፵፪)፡፡ ከእነዚህ ቅዱሳን መካከልም ኢትዮጵያዊው ጻድቅ አቡነ ተክለ ሃይማኖት አንደኛው ናቸው፡፡

በየዓመቱ ግንቦት ፲፪ ቀን ቅዱስ ሚካኤል ሊቀ መላእክት፣ ኢትዮጵያዊው ንጉሥ እስክንድር፣ ሊቁ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ፣ ቅዱስ መስቀል፣ ቅዱስ እስጢፋኖስ፣ ቅዱስ ሚናስ፣ የመላልዔል ልጅ ያሬድ እና ጻድቁ አቡነ ተክለ ሃይማኖት በቤተ ክርስቲያናችን ይታሰባሉ፡፡ በዛሬው ዝግጅታችን የጻድቁ አባታችንን የፍልሰተ ዐፅም ታሪክ የስማቸውን ትርጕም በማስቀደም እንደሚከተለው በአጭሩ አቅርበነዋል፤

‹ተክል› ማለት ፍሬያማ ዕንጨት፣ ዛፍ፣ ቅመም፣ ቅጠላ ቅጠል፣ የሚበላ፣ የሚሸተት፣ ገነታዊ ዕፅ፣ እንዲሁም ሕግ ሥርዓት ማለት ነው (ኪዳነ ወልድ ክፍሌ፤ ማቴ.፲፭፥፲፫)፡፡ ‹ሃይማኖት› ማለት ደግሞ በሀልዎተ እግዚአብሔር፣ በእግዚአብሔር አምላክነት፣ በሥላሴ አንድነትና ሦስትነት፣ በቅዱሳን ተራዳኢነት ማመን፤ አምኖም መመስከር ማለት ነው፡፡ ‹ተክለ ሃይማኖት› የሚለው ሐረግም የሃይማኖት ተክል፣ ይኸውም የጽድቅ ፍሬን ያፈራና ከኃጢአት ሐሩር ማምለጫ ዛፍ፤ ምእመናንን በቃለ ወንጌል ያጣፈጠ ቅመም፤ መዓዛ ሕይወቱ የሚማርክ፣ ቢመገቡት ረኃበ ነፍስን የሚያስወግድ ቅጠል፤ የጻድቃን መጠለያ ዕፅ የሚል አለው፡፡ መጽሐፈ ገድላቸውም ‹‹ተክለ ሃይማኖት ማለት የአብ፣ የወልድ፣ የመንፈስ ቅዱስ ተክል ማለት ነው›› በማለት የስማቸውን ትርጕም ያትታል፡፡ ጻድቁ አባታችን ተክለ ሃይማኖት በአሚነ ሥላሴ ጸንተው ሌሎችንም እንዲጸኑና እንዲያምኑ አድርገዋልና፡፡

‹‹… ስምዑ ወለብዉ ፍቁራንየ መጽሐፈ ዜናሁ ለክቡር ወቅዱስ ወለብፁዕ ፍቁረ እግዚአብሔር ዘይትነበብ በዕለተ ፍልሰተ ሥጋሁ አመ ፲ወ፪ ለግንቦት ውእቱ ድሙር ምስለ በዓለ ትንሣኤሁ ለእግዚእነ ኢየሱስ ክርስቶስ ወበዓለ ሚካኤል ሊቀ መላእክት ፍቁሩ ለተክለ ሃይማኖት፤ ወዳጆቼ ሆይ፣ የከበረ፣ የተቀደሰ፣ የተደነቀ፣ የእግዚአብሔር ወዳጅ የሚኾን የአባታችን የተክለ ሃይማኖትን ክብሩን፣ ገናንቱን የሚናገረውን፤ ዐፅሙ በፈለሰበት ግንቦት ፲፪ ቀን የሚነበበውን መጽሐፍ አስተውላችሁ ስሙ፡፡ ይኸውም ከጌታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ የትንሣኤ በዓል እና ከተክለ ሃይማኖት ወዳጅ ከሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል በዓል ጋር የተባበረ ነው …፤›› (ገድለ ተክለ ሃይማኖት ምዕ.፷፪፥፭-፰)፡፡

አቡነ ተክለ ሃይማኖት በ፲፫ኛው መቶ ክፍለ ዘመን መጀመሪያ አካባቢ በአገራችን ኢትዮጵያ ምድር በሰሜን ሸዋ ሀገረ ስብከት ኢቲሳ (ደብረ ጽላልሽ) ከአባታቸው ካህኑ ጸጋ ዘአብ እና ከእናታቸው እግዚእ ኀረያ አብራክ የተገኙ ቅዱስ አባት ናቸው፡፡ አባታችን ሕይወታቸዉን ሙሉ ለእግዚአብሔር በመስጠት፣ እንደ በሬ ተጠምደው፣ እንደ ገበሬ ታጥቀው ይህንን ዓለም ንቀው፣ በጾም በጸሎት ተወስነው፣ በብሕትውና ከመኖራቸው ባሻገር እንደ ቅዱሳን ሐዋርያት ወንጌልን በመላው ኢትዮጵያ እየተዘዋወሩ የሰበኩ፣ በጌታችን በመድኃኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ድውያነ ሥጋን በተአምራት፣ ድውያነ ነፍስን በትምህርት የፈወሱ ሐዋርያ ናቸው፡፡ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችንም ይህንን ውለታቸውን በማሰብና ከእግዚአብሔር ዘንድ የተሰጣቸውን ቅድስና መሠረት አድርጋ በስማቸው ጽላት ቀርፃ ስታከብራቸው ትኖራለች፡፡

አቡነ ተክለ ሃይማኖት በዚህ ዓለም የኖሩበት ዕድሜ ዘጠና ዘጠኝ ዓመት ከዐሥር ወር ከዐሥር ቀን ነው፡፡ በእናት አባታቸው ቤት ፳፪ ዓመት፤ በከተታ ፫ ዓመት፤ በዊፋት ፱ ወር፤ በዳሞት ፲፪ ዓመት፤ በአማራ ፲ ዓመት፤ በሐይቅ ፲ ዓመት፤ በደብረ ዳሞ ፲፪ ዓመት፤ በትግራይ ገዳማት በመዘዋወርና ወደ ኢየሩሳሌም በመመላለስ ፩ ዓመት፤ ዳዳ በሚባል አገር ፩ ወር፤ በአሰቦ ገዳም ፳፱ ዓመት ከ፲ ቀን መቆየታቸውን መጽሐፈ ገድላቸው ይናገራል (ገ.ተ.ሃ ፶፱፥፲፬-፲፭)፡፡

ጻድቁ አባታችን ምድራዊ ሕይወታቸውን በተጋድሎና በሐዋርያዊ አገልግሎት ከፈጸሙ በኋላ ከዚህ ዓለም ውጣ ውረድ የሚያልፉበት ቀን በተቃረበ ጊዜ ጌታችን አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከእናቱ ከቅድስት ድንግል ማርያም፣ ከቅዱሳን መላእክት፣ ከቅዱሳን ነቢያትና ከቅዱሳን ሐዋርያት ጋር ወደ እርሳቸው በመምጣት የሚያርፉበት ዕለት መድረሱን ነግሯቸው፣ የተጋድሏቸውን ጽናት አድንቆላቸው በስማቸው መታሰቢያ ለሚያደርጉ፣ ለነዳያን ለሚመጸዉቱ ቤተ ክርስቲያን ለሚያሠሩ የምሕረት ቃል ኪዳን ሰጥቷቸው በክብር በምስጋና ወደ ሰማይ ዐረገ፡፡

አቡነ ተክለ ሃይማኖትም የዕረፍት ጊዜያቸው መቃረቡን ባወቁ ጊዜም የመንፈስ ልጆቻቸውን ጠርተው ጌታችን የነገራቸውን ዅሉ አስረድተው አባታዊ ምክርና ተግሣፅ ከሰጧቸው በኋላ ነሐሴ ፳፬ ቀን ከዚህ ዓለም ድካም ዐረፉ፡፡ የመንፈስ ልጆቻቸውም ለአንድ ቅዱስ አባትና ካህን በሚገባ ሥርዓት በማኅሌት፣ በዝማሬና በምስጋና ቀበሯቸው፡፡ ጌታችንም ከእመቤታችንና ከቅዱሳን መላእክት ጋር ተገልጾ ታያቸው፤ ነፍሳቸውንም ‹‹የጠራሽ፣ ንጽሕት ነፍስ ሆይ! ወደ እኔ ነዪ›› ብሎ በክብር ተቀበላት፡፡

ወደ ፍልሰተ ዐፅማቸው ታሪክ ስንመለስ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ከዚህ ዓለም ውጣ ውረድ ከተለዩ በ፶፯ኛው ዓመት የካቲት ፲፱ ቀን ለመንፈስ ልጃቸው ለአባ ሕዝቅያስ ብርሃን ለብሰው በሕልም ተገለጡላቸውና ‹‹ወዳጄ ሕዝቅያስ ሆይሰላም ለአንተ ይኹን! ጌታዬበኋለኛው ዘመን ከዚህ ሥፍራ ልጆችህ ሥጋህን ያፈልሳሉያለኝ ዘመን ደርሷልና ሳትዘገይ ልጆቼን ዅሉ ቅጠራቸውና እስከምፈልስበት ቀን ድረስ ግንቦት ፲፪ ቀን ይሰብሰቡ፡፡ እናንተም በምስጋና በጸሎት መንፈሳዊ በዓልን አድርጉ፡፡አባቴ ተክለ ሃይማኖትየሚለኝ ዅሉ በዚህች በፍልሰተ ዐፅሜ ቀን ይምጣ፤ መንፈሳዊ በዓልንም ያድርግ፡፡ እኔና ቅዱስ ሚካኤል ከወዳጄ አባ ፊልጶስ ጋር ስለ እኔ ፍቅር የተሰበሰበውን ሕዝብ ልንባርክ እንመጣለን፤›› ከአሏቸው በኋላ ተሠወሯቸው፡፡

አባ ሕዝቅያስም እንደ ታዘዙት ‹‹የአባታችሁን ዐፅም ከዋሻው ወደ ታላቁ ቤተ ክርስቲያን ታፈልሱ ዘንድ ኑ፤ ተሰብሰቡ›› ብለው የአባታችን ወዳጆች ባሉባቸው አገሮች ዅሉ መልእክት ላኩ፡፡ ምእመናንም ጥሪውን ተቀብለው በዓሉን ለማክበር ከአራቱም አቅጣጫ ተሰበሰቡ፡፡ ዐሥራ ሁለቱ መምህራንም መጡ፤ እነዚህም፡- የወረብ አገሩ አባ አኖሬዎስ፣ የፈጠጋሩ አባ ማትያስ፣ የእርናቱ አባ ዮሴፍ፣ የሞረቱ አባ አኖሬዎስ፣ የመርሐ ቤቴው አባ መርቆሬዎስ፣ የጽላልሹ አባ ታዴዎስ፣ የወገጉ አባ ሳሙኤል፣ የወንጁ አባ ገብረ ክርስቶስ፣ የድንቢው አባ መድኃኒነ እግዚእ፣ የዳሞቱ አባ አድኃኒ፣ የክልአቱ አባ ኢዮስያስ እና የመሐግሉ አባ ቀውስጦስ ናቸው፡፡

እነዚህ መምህራን ከአባ ሕዝቅያስ ጋር በመኾን የአቡነ ተክለ ሃይማኖትን ዐፅም ከዐረፈበት ዋሻ ባወጡት ጊዜ ዐፅማቸው ዕለት የተገነዘ በድን ይመስል ነበር፤ መዓዛውም ሽቱ፣ ሽቱ ይሸት ነበር፡፡ በአባታችን ዐፅም ቀኝና ግራም መስቀል ተተክሎ ነበር፡፡ በዐፅማቸውም ብዙ ድንቅ ተአምራት ተደርገዋል፡፡ ይህንን የአባታችንን ዐፅም አባ ሕዝቅያስና ዐሥራ ሁለቱ መምህራን በሣጥን አክብረው ወደ ቤተ ክርስቲያኑ ወስደው በመንበሩ ፊት ሦስት ጊዜ አዞሩት፡፡

በዚህች ዕለት አስቀድመው የካቲት ፲፱ ቀን ለአባ ሕዝቅያስ በሕልም እንደ ነገሯቸው ብፁዕ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ከቅዱስ ሚካኤልና ከአባ ፊልጶስ ጋር ወደ ቤተ ክርስቲያኑ መጥተው ዐፅማቸው እስኪያረፍ ድረስ ከመንበሩ ተቀምጠው ቆይተው ዐፅማቸው ካረፈ በኋላ የተሰበሰበውን ሕዝብ ባርከው በክብር ወደ ሰማይ ዐረጉ፡፡ መምህራኑና ምእመናኑም በዓሉን በታላቅ ደስታ አክብረው በሰላም ወደየቤታቸው ተመለሱ፡፡ በዘመኑ የአቡነ ተክለ ሃይማኖት ፍልሰተ ዐፅም በዋለበት ዕለት ርክበ ካህናትም አብሮ መከበሩ በዓሉን ልዩ ድምቀት ሰጥቶት እንደ ነበር በመጽሐፈ ገድላቸው ተገልጿል፡፡ ከዚያን ዘመን ጀምሮ እስከ ዛሬ ድረስ በታላቁ ገዳም በደብረ ሊባኖስ ቅዱሳን ፓትርያሪኮች፣ ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳትና በርካታ ምእመናን እየተሰበሰቡ በዓሉን በድምቀት ያከብራሉ (ገ.ተ.ሃ ፷፭፥፩-፳፬)፡፡

የብፁዕ አባታችን ዐፅም በፈለሰበት ዕለት ዐሥራ ሁለቱ መምህራን እና በርካታ ምእመናንን እንደ ተሰበሰቡ ዅሉ እኛንም እግዚአብሔር አምላካችን በኢየሩሳሌም ሰማያዊት ይሰብስበን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ምንጭ፡

  • መጽሐፈ ስንክሳር፣ ግንቦት ፲፪ ቀን፡፡
  • ገድለ ተክለ ሃይማኖት፣ ፲፱፻፹፱ .ም፤ አዲስ አበባ፡፡

ዝክረ ቅዱስ ያሬድ ኢትዮጵያዊ

ቅዱስ ያሬድ

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ግንቦት  ቀን ፳፻፱ .

በየዓመቱ ግንቦት ፲፩ ቀን ከሚታወሱ ቅዱሳን መካከል የእመቤታችን እናት ቅድስት ሐና፣ ቅድስት ታውክልያ፣ ቅዱስ በፍኑትዩስ፣ አባ አሴር፣ ቅዱስ ያሬድ፣ ብፅዕት አርሴማ፣ ቅድስት ኤፎምያ፣ ቅድስት አናሲማ፣ ቅድስት ሶፍያ፣ አባ በኪሞስ፣ አባ አብላዲስ፣ አባ ዮልዮስ እና ስማቸውን ያልጠቀስናቸው ሌሎች በርካታ ቅዱሳንም ተጠቃሾች ናቸው፡፡ በዛሬው ዝግጅታችን ‹የቤተ ክርስቲያን እንዚራ›፣ ‹የኢትዮጵያ ብርሃን› እየተባለ የሚጠራውን የቤተ ክርስቲያናችን ድምቀት፣ የአገራችን ኩራት የኾነውን የጥዑመ ልሳኑ ማኅሌታይ ቅዱስ ያሬድን ታሪክ በአጭሩ ልናስታውሳችሁ ወደድን፤

ቅዱስ ያሬድ ሚያዝያ ፭ ቀን በ፭፻፭ ዓ.ም በአገራችን በኢትዮጵያ በአክሱም ከተማ ከአባቱ ከአብዩድ (ይስሐቅ) እና ከእናቱ ታውክልያ (ክርስቲና) ተወለደ፡፡ ዕድሜው ለትምህርት ሲደርስ ከአጎቱ ከአባ ጌዴዎን ዘንድ ትምህርት ሊማር ቢሔድም ለበርካታ ዓመታት ትምህርት ሊገባው አልቻለም ነበር፡፡ በዚህም የተነሣ መምህሩ ይገርፉት፣ ይገሥፁት ነበር፡፡ እርሱም ከትምህርቱ ክብደት ባለፈ የመምህሩ ተግሣፅ ሲበረታበት ጊዜ ከአባ ጌዴዎን ቤት ወጥቶ በመሸሽ ላይ ሳለ ደክሞት ከአንድ ዛፍ ሥር ተቀመጠ፡፡

ከዛፉ ሥር ተጠልሎ ሳለ አንድ ትል ፍሬውን ለመመገብ ወደ ዛፉ ሊወጣ ሲል መውጣት ስለ ተሳነው በተደጋጋሚ ሲወድቅ ቆይቶ ከብዙ ሙከራ በኋላ ከዛፉ ላይ ሲወጣ፤ ፍሬውንም ሲመገብ ይመለከታል፡፡ ቅዱስ ያሬድ የትሉን ትጋት ከአየ በኋላ እርሱም በተደጋጋሚ ሙከራ ቢያደርግ የከበደው ምሥጢር እንደሚገለጽለት በማመን ወደ መምህሩ ተመልሶ ይቅርታ በመጠየቅ ትምህርቱን እንደ ገና መቀጠል ጀመረ፡፡ እግዚአብሔርን በጸሎት እየተማጸነ ትምህርቱን ሲከታተል ከቆየ በኋላ በአጭር ጊዜ ውስጥ ልቡናው ብሩህ ኾኖለት የብሉይና የሐዲስ ኪዳን መጻሕፍት ትርጓሜን አጠናቆ መዓርገ ዲቁና ተቀበለ፡፡

እግዚአብሔርም የክብር መታሰቢያ ሊያቆምለት ወዷልና ከኤዶም ገነት ሦስት አዕዋፍን ልኮ በሰው አንደበት እንዲያናግሩት አደረጋቸው፡፡ እነርሱም ካናገሩት በኋላ ወደ ኢየሩሳሌም ሰማያዊት አወጡትና በዚያም የሃያ አራቱን ካህናተ ሰማይ (ሱራፌል) ማኅሌት ተማረ፡፡ ወደ ምድርም ተመልሶ በአክሱም ጽዮን በሦስት ሰዓት ገብቶ በታላቅ ቃል፡- ‹‹ሃሌ ሉያ ለአብ ሃሌ ሉያ ለወልድ ሃሌ ሉያ ለመንፈስ ቅዱስ ቀዳሚሃ ለጽዮን ሰማየ ሣረረ ወበዳግም አርአዮ ለሙሴ ዘከመ ይገብር ግብራ ለደብተራ፤ ለአብ ምስጋና ይገባል፤ ለወልድ ምስጋና ይገባል፤ ለመንፈስ ቅዱስ ምስጋና ይገባል፡፡ የጽዮን ደገኛዋ ሰማይን ፈጠረ፡፡ ዳግመኛም እንዴት መሥራት እንዳለበት የድንኳንን አሠራር ለሙሴ አሳየው፤ አስተማረው፤›› እያለ በዜማ እግዚአብሔርን አመሰገነ፡፡ የቅዱስ ያሬድን ድምፅ የሰሙ ዅሉ ጳጳሳቱና ነገሥታቱ ሳይቀሩ ካህናቱም ምእመናኑም ወደ እርሱ ተሰብስበው ሲሰሙት ዋሉ፡፡ ይህንንም ምስጋና ‹አርያም› ብሎ ሰየመው፤ ይኸውም በዜማ ትምህርት ቤት ከቃል ትምህርቶች አንደኛው ኾኖ በቤተ ክርስቲያን በመሰጠት ላይ ይገኛል፡፡

መጽሐፈ ስንክሳር ቅዱስ ያሬድን፡- አምሳሊሆሙ ለሱራፌል፤ የሱራፌል አምሳላቸው› ይለዋል፡፡ ከመላእክት ወገን የኾኑት ሱራፌል እግዚአብሔርን ‹‹ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ›› እያሉ በመንበሩ ፊት ቆመው እንደሚያመሰግኑ ዅሉ ቅዱስ ያሬድም ‹‹ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ›› እያለ በመላእክት ቋንቋ እግዚአብሔርን አመስገኗልና፤ ደግሞም የተማረው ከእነርሱ ነውና የሱራፌል አምሳላቸው› ተባለ፡፡ እርሱም፡- ‹‹ሃሌ ሉያ ዋይ ዜማ ዘሰማዕኩ በሰማይ እመላእክት ግናይ እንዘ ይብሉ ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ እግዚአብሔር መልዐ ሰማያተ ወምድረ ቅድሳተ ስብሓቲከ፤ ምስጋና ለእግዚአብሔር ይኹን! ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ እግዚአብሔር፤ የምስጋናህ ስፋት ሰማይና ምድርን መላ፤›› እያሉ ሲያመሰግኑ ከመላእክት የሰማሁት ምስጋና ምንኛ ድንቅ ነው? በማለት ዜማውን የተማረው ከመላእክት መኾኑን በድርሰቱ መስክሯል (ኢሳ.፮፥፫)፡፡

ከዚያ በኋላ በመንፈስ ቅዱስ ተቃኝቶ ከዓመት እስከ ዓመት ድረስ በየክፍለ ዘመኑ በክረምትና በበጋ፣ በመጸውና በጸደይ፣ በአጽዋማትና በሰንበታት፣ እንዲሁም በመላእክት፣ በጻድቃን፣ በሰማዕታት፣ በደናግል በዓላት የሚደረስ ቃለ እግዚአብሔር በሦስት ዜማዎች ማለትም በግእዝ፣ በዕዝልና በአራራይ ደረሰ፡፡ የሰው ንግግር፣ የአዕዋፍ፣ የእንስሳትና የአራዊት ጩኸት ዅሉ ከእነዚህ ከሦስቱ ዜማዎች እንደማይወጡ መጽሐፈ ስንክሳር ይናገራል፡፡ በዘመኑ የነበረው ንጉሥ ገብረ መስቀል በሊቁ ዜማ ረቂቅነት እና የድምፅ ማማር ከመመሰጡ የተነሣ የቅዱስ ያሬድን እግር በጦር መውጋቱም በመጽሐፈ ስንክሳር እንዲህ ተመዝግቧል፤

በአንዲት ዕለት ቅዱስ ያሬድ ከብሉይና ከሐዲስ፣ እንደዚሁም ከሊቃውንትና ከመነኮሳት የተውጣጣውን መንፈሳዊ ድርሰቱን ከንጉሡ ፊት ቆሞ ሲዘምር ንጉሡ በድምፁ በመማረኩ የተነሣ ልቡናው በተመስጦ ተሠውሮበት (የሚያደርገዉን ባለማወቁ) የቅዱስ ያሬድን እግር በጦር ወጋው፡፡ ከቅዱስ ያሬድ እግር ደምና ውኃ ቢፈስስም ነገር ግን ማኅሌቱን እስኪፈጽም ድረስ ሕመሙ አልተሰማውም ነበር፡፡ ንጉሡም ያደረገዉን ዅሉ ባወቀ ጊዜ ደነገጠ፤ ጦሩንም ከእግሩ ነቅሎ ‹‹ስለ ፈሰሰው ደምህ ዋጋ የምትፈልገዉን ዅሉ ለምነኝ›› እያለ ተማጸነው፡፡ ቅዱስ ያሬድም ‹‹ላትከለክለኝ ማልልኝ›› ብሎ ቃል ካስገባው በኋላ ወደ ገዳም ሔዶ ይመነኵስ ዘንድ እንዲፈቅድለትና እንዲያሰናብተው ለመነው፡፡ ንጉሡም ከመኳንንቱ ጋር እጅግ አዘነ፤ ተከዘ፡፡ ከእርሱ እንዲለይ ባይፈልግም ነገር ግን መሐላዉን ማፍረስ ስለ ከበደው አሰናበተው፡፡

ከዚያም ቅዱስ ያሬድ በአክሱም ጽዮን ቤተ መቅደስ በታቦተ ጽዮን ፊት ቆሞ፡ ‹‹ቅድስት ወብፅዕት ስብሕት ወቡርክት ክብርት ወልዕልት አንቀጸ ብርሃን መዐርገ ሕይወት …፤ፈጽሞ የከበርሽና የተመሰገንሽ፣ ከፍ ከፍም ያልሽ፣ የብርሃን መውጫ የሕይወት ማዕረግ የኾንሽ …›› እያለ አንቀጸ ብርሃን የተሰኘውን የእመቤታችንን ምስጋና እስከ መጨረሻው ድረስ ደረሰ፡፡ ይህንን ጸሎት ሲያደርስም አንድ ክንድ ያህል ከመሬት ከፍ ብሎ ይታይ ነበር፡፡ ከዚህ በኋላ ወደ ሰሜን አገር ሔዶ (ሰሜን ተራሮች አካባቢ) በጾም በጸሎት ተወስኖ ሥጋውን እጅግ እያደከመ ኖሮ ገድሉን በዚያው ፈጸመ፡፡ እግዚአብሔርም ስሙን ለሚጠራ፣ መታሰቢያውን ለሚያደርግ ቃል ኪዳን ሰጠው፤ ከዚያም በሰላም ዐረፈ፡፡

(ምንጭ፡መጽሐፈ ስንክሳር፣ ግንቦት ፲፩ ቀን)፡፡

የቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት በገድለ ቅዱስ ያሬድ ላይ እና በመጽሐፈ ስንክሳር እንደ መዘገቡልን ግንቦት ፲፩ ቀን ቅዱስ ያሬድ ከዚህ ዓለም ውጣ ውረድ ያረፈበት ቀን ነው፤ እዚህ ላይ ግን አከራካሪ ጉዳይ አለ፤ ይኸውም አንደኛው ቅዱስ ያሬድ ሞቶ ተቀብሯል የሚል ሲኾን፣ ሌላኛው ደግሞ ቅዱስ ያሬድ እስከነነፍሱ ተሠወረ እንጂ አልሞተም የሚል ነው፡፡ በእርግጥ ቃሉን በትኩረት ለተመለከው ሰው ዐረፈ ማለት ሞትን ብቻ ሳይኾን እንደነሄኖክ ከዚህ ዓለም ጣጣ እና እንግልት ተለይቶ በሕይወት እያሉ (ሳይሞቱ) ተሠውሮ መኖርንም ያመለክታል፡፡ የቤተ ክርስቲያን መምህራን እንደሚያስተምሩን እነእገሌ ቀበሩት የሚል ቃል ስለማይገኝ ቅዱስ ያሬድ ተሠወረ እንጂ ሞተ ተብሎ አይነገርለትም፡፡ ለዚህም ማስረጃ እርሱ በተሠወረበት ተራራ አካባቢ እና በስሙ በተመሠረተው በደብረ ሐዊ ቅዱስ ያሬድ ገዳም እስከ አሁን ድረስ የከበሮ (የማኅሌት) ድምፅ ይሰማል፤ የዕጣን መዓዛም ይሸታል፡፡ ይህም ቅዱሱ ከሰው ዓይን ተሠውሮ እግዚአብሔርን እያመሰገነ እንደሚገኝ አመላካች ነው፡፡

በመጨረሻም የቅዱስ ያሬድ ድርሰቶች ለቤተ ክርስቲያን ብቻ ሳይኾን ለአገርም ድንቅና ወደር የሌላቸው ሀብቶች መኾናውን ዅላችንም ልብ ልንለው ይገባል፡፡ በመኾኑም የዜማ ድርሰቶቹ (ድጓ፣ ጾመ ድጓ፣ ምዕራፍ፣ ዝማሬ፣ መዋሥዕት) እንደ ሌሎቹ ቅርሶች ዅሉ በዩኔስኮ እንዲመዘገቡ የሚመለከታቸው አካላት ከፍተኛ ርብርብ በያደርጉ መልካም ነው፡፡ በቅዱስ ያሬድ ዜማ የሚደምቁት በዓለ ጥምቀት እና በዓለ መስቀል በዩኔስኮ ሲመዘገቡ ዜማውን ከበዓላቱ ለይቶ ማስቀረት አይገባምና፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ርክበ ካህናት

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ግንቦት ፪ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

‹ርክብ› ወይም ‹ረክብ› የሚለው ቃል ‹ተራከበ፤ ተገናኘ› ከሚለው የግእዝ ግስ የወጣ ሲኾን፣ ትርጕሙም ማግኛ፣ መገኛ፣ መገናኛ ማለት ነው (ኪዳነ ወልድ ክፍሌ ገጽ ፰፻፴፩)፡፡ ‹ክህነት› የሚለው ስያሜም ከጵጵስና ጀምሮ እስከ ዲቁና ድረስ ያሉትን የቤተ ክርስቲያን መዓርጋት የሚያጠቃልል ቃል ሲኾን ካህን (ነጠላ ቍጥር)፣ ካህናት (ብዙ ቍጥር) በአንድ በኩል ቀሳውስትን የሚወክል ኾኖ በሌላ በኩል ደግሞ የጳጳሳት፣ የኤጲስ ቆጶሳት፣ የቀሳውስት፣ የዲያቆናት የጋራ መጠሪያ ነው፡፡ ‹ርክበ ካህናት› የሚለው ሐረግም የካህናት መገኛ፣ መገናኛ፣ ጉባኤ (መሰባሰቢያ)፣ መወያያ፣ ወዘተ የሚል ትርጕም አለው፡፡ በአጭሩ ‹ርክበ ካህናት› ማለት – የአባቶች ካህናት ማለትም የብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት (የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት) ጉባኤ ማለት ነው፡፡

በቅዱስ ዮሐንስ ወንጌል እንደ ተገለጸው ጌታችን አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሞት ከተነሣ በኋላ ለሦስተኛ ጊዜ ተገልጦ ከዐሥራ አንዱ ቅዱሳን ሐዋርያት ጋር ምሳ በልቷል፡፡ ከምሳ በኋላም ጌታችን ቅዱስ ጴጥሮስን ሦስት ጊዜ ጠርቶ ‹‹ትወደኛለህን?›› እያለ ከጠየቀው በኋላ እንደሚወደው ምላሽ መስጠቱን ተከትሎ በቅደም ተከተል ‹‹በጎቼን ጠብቅ፤ ጠቦቶቼን አሰማራ፤ ግልገሎቼን ጠብቅ፤›› በማለት የአለቅነት ሥልጣን ሰጥቶታል፡፡ ይህ ምሥጢር ለጊዜው ጌታችን ሐዋርያትን፣ ሰብዐ አርድእትንና ሠላሳ ስድስቱን ቅዱሳት አንስት በአጠቃላይ መቶ ሃያውን ቤተሰብእ እንዲጠብቅና እንዲከባከብ ቅዱስ ጴጥሮስን ማስጠንቀቁን፤ ለፍጻሜው ግን የቤተ ክርስቲያን አባቶች (ጳጳሳት) መምህራንንና መላው ሕዝበ ክርስቲያንን እንዲጠብቁና እንዲያስተዳድሩ በእግዚአብሔር መሾማቸውን የሚያስረዳ ምሥጢር አለው (ዮሐ.፳፩፥፩-፲፯)፡፡

ይህን የጌታችንን ትእዛዝና የሐዋርያትን ሥልጣነ ክህነት መሠረት በማድረግ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ በዓመት ሁለት ጊዜ ጉባኤ ያደርጋል፤ የመጀመሪያው ጉባኤ ጥቅምት ፲፪ ቀን (የቅዱስ ማቴዎስ በዓል) ሲኾን፣ ሁለተኛው ደግሞ ርክበ ካህናት ነው፡፡ በዓሉ (ርክበ ካህናት) ወሩና የሚውልበት ቀን የበዓላትንና የአጽዋማትን ቀመር ተከትሎ ከፍና ዝቅ ቢልም በየዓመቱ የትንሣኤ በዓል በተከበረ በ፳፭ኛው ቀን በዕለተ ረቡዕ ይውላል፡፡ የአጽዋማትና የበዓላት ቀመር ከመዘጋጀቱ በፊት ማለትም በቅዱስ ድሜጥሮስ አማካኝነት ዐቢይ ጾም ሰኞ፣ ስቅለት ዓርብ፣ ትንሣኤ እሑድ፣ ርክበ ካህናት ረቡዕ፣ ዕርገት ሐሙስ፣ ጰራቅሊጦስ እሑድ እንዲኾን ከመደረጉ በፊት ርክበ ካህናት ግንቦት ፳፩ ቀን ይውል ነበር (መጽሐፈ ግጻዌ፣ ግንቦት ፳፩ ቀን)፡፡

ከዚህ በኋላ በዓለ ትንሣኤ በዋለ በ፳፭ኛው ቀን፣ በበዓለ ኃምሳ እኩሌታ በዕለተ ረቡዕ ርክበ ካህናት እንዲዘከር የቤተ ክርስቲያን አባቶች ወስነዋል፡፡ በያዝነው ዓመት በ፳፻፱ ዓ.ም የትንሣኤ በዓል ከተከበረበት ዕለት (ሚያዝያ ፰ ቀን) ጀምሮ ብንቈጥር ፳፭ኛው ቀን ግንቦት ፪ ቀን ነው፡፡ በመኾኑም የዘንድሮው ርክበ ካህናት ግንቦት ፪ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ይውላል ማለት ነው፡፡ ይህ በዓል (ርክበ ካህናት) ከቅዱሳን ሐዋርያት ጀምሮ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ሲመሩ የቆዩ አባቶቻችን በጋራ በመሰባሰብ ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን የተቀላጠፈ አገልግሎት እንደዚሁም ለምእመናን አንድነትና መንፈሳዊ ዕድገት የሚበጁ መንፈሳውያን መመሪያዎችን የሚያስተላልፉበት ዕለት ነው፡፡ በዚህ ዕለት ቅዱስ ሲኖዶስ በሚያደርገው ጉባኤ የሚተላለፉ መመሪያዎችና የሚጸድቁ ውሳኔዎች ለቤተ ክርስቲያን ዕድገት፣ ለምእመናን አንድነት፣ ለአገር ሰላምና ደኅንነት የሚጠቅሙ ይኾኑ ዘንድ ዅላችንም በጾም በጸሎት እግዚአብሔርን መጠየቅ ይኖርብናል፡፡

አምላካችን ቤተ ክርስቲያናችንንና አባቶቻችንን ይጠብቅልን፤ እኛንም ለአባቶች የሚታዘዝ ልቡና፣ ሓላፊነታችንን የምንወጣበትን ጥበብና ማስተዋልን ያድለን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ትንሣኤ ክርስቶስ በሊቃውንት – ካለፈው የቀጠለ

በመምህር ሳሙኤል ተስፋዬ

ሚያዝያ ፲፱ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

‹‹በእርሱ ሞት ከብረናል፡፡ በመለኮቱ ሞት ሳይኖርበት በሥጋ ሞተ፤ ምንጊዜም ቢኾን እርሱ የሕይወት ልጅ ሕይወት ነው፡፡ ይኸውም ከእግዚአብሔር አብ የተወለደው ልደት ነው፡፡ ወደ ሕይወት ሥጋ ደፍሮ በመጣ ጊዜ ሞት እንዲህ ድል ተነሣ፤ መፍረስ መበስበስም በእርሱ (በክርስቶስ) እንዲህ ጠፋ፤ ሞትም ድል ተነሣ፤›› (ቅዱስ ቄርሎስ፣ ሃይ. አበ. ፸፪፥፲፪)፡፡

‹‹ሕማምን፣ ሞትን ገንዘብ አደረ፡፡ በሥጋው የሞተው የእኛን ባሕርይ በመዋሐዱ ነው፡፡ ከዚህ በኋላ ተዋሕዶውን አስረዳ፡፡ ሞት ሰው የመኾን ሥራ ነውና፡፡ ከሙታን ተለይቶ መነሣትም አምላክ የመኾን ሥራ ነውና፡፡ እነዚህ ሁለት ሥራዎችን (ሞትን እና ትንሣኤን) እናውቃለን፤›› (ዝኒ ከማሁ ፸፪፥፴፭)፡፡

‹‹በሥጋ ሞተ እንዳልን ዳግመኛ በሥጋ ተነሣ እንላለን፤ ስለ ትንሣኤም የእርሱ ገንዘብ እንደ ኾነ፤ ሙስና መቃብርም እንዳላገኘው ይነገራል፡፡ ይህ (መሞት፣ መነሣት) ለመለኮት አይነገርም፡፡ የተነሣው ሥጋው ነው እንጂ፤›› (ዝኒ ከማሁ ፸፱፥፱)፡፡

‹‹የሞትን ሥልጣን አጠፋ፤ ዲያብሎስንና ኃይሉን (ኃጢአትን) ሻረ፡፡ የብረት መዝጊያዎችን ሰበረ (ፍዳ፣ መርገምን አጠፋ)፡፡ ሲኦልን በዘበዘ፤ የጣዖት ቤቶችን አፈረሰ፡፡ የምሕረትን በር ከፈተ፡፡ ይህችውም በደሙ የከበረች ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ናት፡፡ ለዅሉ የዘለዓለም ሕይወት መገኛ የሚኾን ልጅነት የተገኘበት ሥጋውን ደሙን ሰጠን፤›› (ቅዱስ ቴዎዶስዮስ፣ ሃይ. አበ. ፹፫፥፮)፡፡

‹‹ለእኛስ እግዚአብሔር ቃል በባሕርየ መለኮቱ እንደ ታመመ፤ እንደ ሞተ፤ እንደ ተቀበረ ልንናገር አይገባንም፡፡ ከሙታን ተለይቶ በመነሣቱ ሞት የሌለበት እንደ ኾነ፣ መድኃኒታችን በሚኾን በሞቱና በሦስተኛው ቀንም በመነሣቱ ትንሣኤን እንደ ሰጠን እናምናለን፡፡ የሞተ እርሱ ከሙታን ተለይቶ ተነሥቷልና፡፡ ዅሉን የሚችል እርሱ ካልተነሣ፣ የችሎታ ዅሉ ባለቤት እርሱ የሌለ ከኾነ፣ እንኪያስ ትንሣኤም ሐሰት ነዋ! ትንሣኤም ሐሰት ከኾነ ሃይማኖታችን ከንቱ ነው፡፡ እንኪያስ አይሁድንም እንመስላቸዋለን፡፡ ሰው እንደ መኾኑ በሥጋ ባይሞትስ በሞት ላይ ሥልጣን ያለው አምላክ እንደ መኾኑ ሞትን ባላጠፋ ነበር፡፡ የአዳም የዕዳ ደብዳቤም ከእግዚአብሔርና ከሰው መካከል ባልተደመሰሰም ነበር፤›› (ቅዱስ ሳዊሮስ፣ ሃይ. አበ. ፹፬፥፲፰-፳)፡፡

‹‹ፈጣሪያችን ክርስቶስ ለጌትነቱ እንደሚገባ ሥጋ መለወጥ የሌለበት እስኪኾን ድረስ ድንቅ በሚያሰኝ ትንሣኤ ሙስና መቃብርን አጥፍቷልና፤ በሥጋ በተቀበላቸው በሚያድኑ በእነዚህ ሕማማት ከጽኑ ሞት፣ ከዲያብሎስም ሥልጣን ያድነን ዘንድ፤ ወደ ቀደመ ቦታችንም ያገባን ዘንድ፤›› (ቅዱስ ዮሐንስ ዘአንጾኪያ፣ ሃይ. አበ. ፺፥፴፬)፡፡

‹‹ይታመም ዘንድ በተገባው በሥጋው፣ ነውር የሌለበትን ሕማም በፈቃዱ በእውነት ተቀበለ እንጂ በምትሐት እንዳልታመመ እናገራለሁ፡፡ እንደ ሕማሙ ሞትንም በመስቀል ላይ ተቀበለ፡፡ ለአምላክነቱ በሚገባ፣ ድንቅ በሚያሰኝ ትንሣኤውም የጌትነቱን ሥልጣን ገለጠ፡፡ ሥጋውንም የማይሞት አደረገ፡፡ ከኃጢአት በራቀ በንጹሕ ማኅፀን በተዋሐደው ጊዜ ለመለኮት ገንዘብ ስለኾነ በሥራው ዅሉ አይለወጥም፤›› (ቅዱስ ቴዎዶስዮስ፣ ሃይ. አበ. ፺፪፥፲፭)፡፡

‹‹ሕማም የማይስማማው እርሱ በሥጋ ሞትን ታገሠ፤ ብረት ወደ እሳት በገባ ጊዜ ዅለንተናው እሳት እንደኾነ እስኪታሰብ ድረስ በእሳት ዋዕይ እንዲግል፤ በመዶሻ በተመታ ጊዜ በመስፍሕ (መቀጥቀጫ) ላይ እንዲሳብ (እንዲቀጠቀጥ)፤ እሳትም ከብረት ጋር ተዋሕዶ ሳለ ፈጽሞ እርሱ እንዳይመታ፤ ከብረቱም እንዳይለይ፤ ግን የመዶሻ ኃይል ሳያገኘው እንዲመታ፤ ለመዶሻ እንዲሰጥ፤ የሚያድን የጌታ ሕማም እንዲህ እንደ ኾነ ዕወቅ፡፡ በዚህ ትንሽ ምሳሌ፤ በእሳትና በብረት ተዋሕዶ ምልክትነት ፍጹም ተዋሕዶን እንወቅ፤ የእግዚአብሔር ቃል ይህ መከራና ሕማምን የሚቀበል ሥጋን ተዋሕዶ በሞተ ጊዜም ከሦስት ቀን በኋላ አምላክነቱ በተገለጠበት ትንሣኤው ሞትን አጠፋው፡፡ ሥጋው በመቃብር በመቀበሩም በመቃብር ውስጥ የነበረ መፍረስ፣ መበስበስን አጠፋልን፤ ከሥሩም ነቀለው፡፡ ለዚህም ማስረጃ ከቅዱሳን ወገን ብዙ ሰዎች ተነሡ፤›› (ቅዱስ ባስልዮስ፣ ሃይ. አበ. ፺፮፥፶-፶፪)፡፡

‹‹ዳግመኛ እርሱ እንደ ሞተ፤ በሦስተኛውም ቀን እንደ ተነሣ፤ ስለ ተነሣም ሥጋው የማይፈርስ የማይበሰብስ፣ የማይታመም፣ የማይሞት እንደ ኾነ እናምናለን፡፡ ሥጋውም ከእርሱ ጋር አንድ ኾኖ ወደ ሰማይ ዐረገ፤ በአርያም በልዑል ዙፋኑ ተቀመጠ፡፡ ዳግመኛም በሙታንና በሕያዋን ይፈርድ ዘንድ ዅሉ አንድ ኾኖ በሚነሣበት ጊዜ እርሱ በጌትነት ይመጣል፡፡ ለዅሉም እንደ ሥራው ይከፍለዋል፡፡ እኛ በእነዚህ ቃላት ሳናወላውል ጸንተን እንኖራለን፤›› (ቅዱስ ዲዮናስዮስ፣ ሃይ. አበ. ፺፱፥፴፪)፡፡

‹‹በፈቃዱ በሥጋው የእኛን ሕማም ታመመ፤ በእውነት የእኛን ሞት ሞተ፡፡ ይኸውም የነፍስ ከሥጋ መለየት ነው፡፡ በፈቃዱ በተለየ አካሉ ሞትን ገንዘብ አደረገ፡፡ በሦስተኛውም ቀን በሥልጣኑ ከሙታን ተለይቶ ተነሣ፤ በክብር ወደ ሰማይ ዐረገ፤ በአባቱ ዕሪና ተቀመጠ፡፡ በኋለኛይቱ ቀንም በሙታንና በሕያዋን ሊፈርድ ይመጣል፤›› (ቅዱስ ፊላታዎስ፣ ሃይ. አበ. ፻፭፥፲፬)፡፡

‹‹በሞቱ ሞትን ያጠፋው እርሱ ነው፤ በሦስተኛው ቀን በመነሣቱም ሲኦልን በዘበዘ፣ ለዅሉም ትንሣኤን ገለጠ፡፡ ፈጽሞ አልተለወጠም፤ ለዅሉ አምላክነቱን አስረዳ፤ ሙስና መቃብርን ከእኛ አጠፋ፤ በቀደመ ሰው በአባታችን በአዳም ትእዛዝ ማፍረስ ምክንያት ሠልጥኖብን ለነበረ ኃጢአት ከመገዛት አዳነን፤›› (ቅዱስ ዲዮናስዮስ ፻፲፩፥፲፫)፡፡

‹‹እሑድ በመንፈቀ ሌሊት ነፍሱን ከሥጋው አዋሕዶ በመለኮታዊ ኃይል ተነሣ፡፡ እርሱ ራሱ ‹ነፍሴን በፈቃዴ አሳልፌ ልሰጥ፣ ሁለተኛም መልሼ ላዋሕዳት ሥልጣን አለኝ፤ ይህን ትእዛዝ ከአባቴ ተቀበልሁ› እንዳለ፡፡ በነጋም ጊዜ ለማርያም መግደላዊት ታያት፤ እጅ ልትነሣው በወደደች ጊዜም ‹ገና ወደ አባቴ አላረግሁምና አትንኪኝ› አላት፡፡ ስለዚህም ሥጋዊ አካሉ ከዚያን አስቀድሞ በአብ ቀኝ እንዳልተቀመጠ ዐወቅን፤›› (አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ፣ መጽሐፈ ምሥጢር ዘትንሣኤ ፺፭)፡፡

‹‹ዮሴፍ ኒቆዲሞስ ከጲላጦስ ተካሰው፣ ከመስቀል አውርደው፣ በድርብ በፍታ ገንዘው በአዲስ መቃብር ቀበሩት፡፡ በሦስተኛው ቀን መቃብር ክፈቱልኝ መግነዝ ፍቱልኝ ሳይል ከሙታን ተለይቶ ተነሣ፡፡ ደቀ መዛሙርቱ ወዳሉበት በዝግ ቤት ገብቶ በጽርሐ ጽዮን ታያቸው፤›› (ቅዳሴ ዲዮስቆሮስ ፩፥፳፱-፴፩)፡፡

‹‹ሰውን ስለ መውደድህ ይህን ዅሉ አደረግህ፤ ከሙታን ተለይተህ መቃብር ክፈቱልኝ፤ መግነዝ ፍቱልኝ ሳትል ተነሣህ፡፡ ከእግረ መስቀል ሙታንን አስነሣህ፡፡ ነፍሳትን ከሲኦል ማርከህ ለአባትህ አቀረብህ፤›› (ቅዳሴ ያዕቆብ ዘስሩግ፣ ፩፥፳፬)፡፡

‹‹በታወቀች በተረዳች በሦስተኛይቱ ቀን መቃብር ክፈቱልኝ መግነዝ ፍቱልኝ ሳይል ተነሣ፡፡ ደቀ መዛሙርቱ ወዳሉበት በዝግ ቤት ገባ፡፡ የተወጋውን ጎኑን፣ የተቸነከረውን እጁን፣ እግሩን አሳያቸው፡፡ በዓለመ ነፍስ የኾነውን እያስተማራቸው ዐርባ ቀን ኖረ፤›› (ቅዳሴ ዘሠለስቱ ምዕት ፬፥፳፭-፳፯)፡፡

‹‹ሰማያት (ሰማያውያን መላእክት) የደስታ በዓልን ያደርጋሉ፤ ደመናት (ቅዱሳን) የደስታን በዓል ያደርጋሉ፡፡ ምድር (ምድራውያን ሰዎች) በክርስቶስ ደም ታጥባ (ታጥበው) የፋሲካን በዓል ታደርጋለች (ያደርጋሉ)፤ ያከብራሉ (ታከብራለች)፡፡ ዛሬ በሰማያት (በሰማያውያን መላእክት) ዘንድ ታላቅ ደስታ ኾነ፡፡ ምድርም በክርስቶስ ደም ታጥባ የፋሲካን የነጻነት በዓል ታደርጋለች፡፡ የትንሣኤያችን በኩር ክርስቶስ ከሙታን ሰዎች ዅሉ ተለይቶ ቀድሞ ተነሣ፤›› (ቅዱስ ያሬድ፣ ድጓ ዘፋሲካ)፡፡

‹‹ሞትን በሥጋ በቀመሰ ጊዜ መለኮቱ በመቃብር ውስጥ ያለነፍሱ ከበድኑ ጋር ነበር፡፡ በሲኦልም ውስጥ ያለ ሥጋው ከነፍሱ ጋር ህልው ነበር፡፡ በአባቱም ቀኝ ያለ ነፍስና ያለ ሥጋ ህልው ነበር፡፡ በትንሣኤውም ጊዜ ነፍሱን ከሥጋው ጋር አዋሕዶ አስቀድሞ ለአይሁድ ‹ይህን ቤተ መቅደስ አፍርሱት፤ በሦስተኛው ቀን እሠራዋለሁ› ብሎ እንደ ተናገረ፡፡ አይሁድም ‹ይህ ቤተ መቅደስ ተሠርቶ ያለቀው በዐርባ ሰባት ዓመት ነው፤ አንተ ግን በሦስት ቀን እሠራዋለሁ ትላለህ› አሉት፤ ይህንንም የተናገረው ስለ ራሱ ሰውነት ነው፡፡ በተነሣም ጊዜ ደቀ መዛሙርቱ ስለዚህ ነገር እንደ ተናገረ አሰቡ፡፡ በመጽሐፍና ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስም የተናገራቸውን ቃል አመኑ፤ ሁለተኛም ‹ነፍሴን በፈቃዴ አሳልፌ እሰጣለሁ፤ ልለያት መልሼም አዋሕጄ ላስነሣት ሥልጣን አለኝ፤ ይህንንም ትእዛዝ ከአባቴ ተቀበልሁ› ብሏል፡፡ ዳዊትም ‹አቤቱ የመቅደስህን ታቦት ይዘህ ተነሥ› ይላል፡፡ ነቢዩ ‹አቤቱ አንተ የመቅደስህን ታቦት ይዘህ ተነሥ› ለምን አለ? የመቅደሱ ታቦት ከኾነችው ከዳዊት ዘር ከነሣው ሥጋ ጋር በመለኮታዊ ኃይሉ ከሞት እንቅልፍ ከመንቃት በስተቀር የእግዚአብሔር መነሣት ምንድን ነው?›› (አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ መጽ. ምሥጢር ዘትንሣኤ ፸፯-፸፱)፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ትንሣኤ ክርስቶስ በሊቃውንት – የመጀመርያ ክፍል

በመምህር ሳሙኤል ተስፋዬ

ሚያዝያ ፲፱ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

የጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ትንሣኤ የድኅነታችን ብሥራት በመኾኑ ለአምሳ ቀናት ያህል በቤተ ክርስቲያን በቅዳሴው፣ በማኅሌቱ፣ በወንጌሉ ወዘተ. ይዘከራል፡፡ በዚህ ሰሙን ‹‹ክርስቶስ ተንሥአ እሙታን በዐቢይ ኃይል ወሥልጣን …›› እየተባለ ሞት መደምሰሱ፣ ነጻነት መመለሱ ያታወጃል፡፡ በየጊዜያቱና በየዘመናቱ የተነሡ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንም ስለ ክርስቶስ ትንሣኤ ከዚህ ቀጥሎ የተገለጠውን ትምህርትና ምስክርነት ሰጥተዋል፤

‹‹ከሙታን ተለይቶ ተነሥቶ ሲኦልን ረግጦ፣ በሞቱ ሞትን አጠፋው፤ በሦስተኛው ቀንም ከሙታን ተለይቶ ከተነሣ በኋላ ‹አባት ሆይ፤ አመሰግንሃለሁ› ብሎ ሥግው ቃል አመሰገነ፤›› (እልመስጦአግያ ዘሐዋርያት ፭፥፩)፡፡

‹‹እንደ ሞተ እንዲሁ ተነሣ፤ ሙታንንም አስነሣ፡፡ እንደ ተነሣም እንዲሁ ሕያው ነው፤ አዳኝ ነው፡፡ በዚህ ዓለም እንደ ዘበቱበት፣ እንደ ሰደቡት፣ እንዲሁ በሰማይ ያሉ ዅሉ ያከብሩታል፤ ያመሰግኑታል፡፡ ለሥጋ በሚስማማ ሕማም ተሰቀለ፤ በእግዚአብሔርነቱ ኃይል ተነሣ፤ ይኸውም መለኮቱ ነው፡፡ ወደ ሲኦል ወርዶ ነፍሳትን ማረከ፤›› (ቅዱስ ሄሬኔዎስ፣ ሃይ. አበ. ፯፥፳፰-፴፩)፡፡

‹‹እንዲህ ሰው ኾኖም ሰውን ፈጽሞ ያድን ዘንድ ታመመ፤ ሞተ፤ ተቀበረ፡፡ በሦስተኛውም ቀን ከሙታን ተለይቶ ተነሣ፤›› (ሠለስቱ ምዕት፣ ሃይ. አበ. ፲፱፥፳፬)፡፡

‹‹ሞትን ያጠፋው፣ ከሙታን ተለይቶ በመነሣቱ የሞት ሥልጣን የነበረው ዲያብሎስን የሻረው እርሱ ነው፡፡ ሰው የኾነ፣ በሰው ባሕርይ የተገለጠ አምላክ ነው፡፡ እግዚአብሔር ያደረበት ዕሩቅ ብእሲ አይደለም፤ ሰው የኾነ አምላክ ነው እንጂ፡፡ ፈጽሞ ለዘለዓለሙ በእውነት ምስጋና ይገባዋል፤›› (ቅዱስ አትናቴዎስ፣ ሃይ. አበ. ፳፭፥፵)፡፡

‹‹ሥጋው በመቃብር ያሉ ሙታንን አስነሣ፤ ነፍሱም በሲኦል ተግዘው የነበሩ ነፍሳትን ፈታች፡፡ በዚያም ሰዓት የጌታችን ሥጋው በመስቀል ላይ ተሰቅሎ ሳለ መቃብራት ተከፈቱ፤ ገሃነምን የሚጠብቁ አጋንንትም ባዩት ጊዜ ሸሹ፡፡ የመዳብ ደጆች ተሰበሩ (ሊቃነ አጋንንት፣ ሠራዊተ አጋንንት ድል ተነሡ)፡፡ የብረት ቁልፎቿም ተቀጠቀጡ (ፍዳ፣ መርገም ጠፋ)፡፡ ቅድስት ነፍሱ በሲኦል ተግዘው የነበሩ የጻድቃን ነፍሳትን ፈታች፤›› (ዝኒ ከማሁ ፳፮፥፳-፳፩)፡፡

‹‹ሥጋ ከመለኮቱ ሳይለይ በመቃብር አደረ፤ ነፍሱም ከመለኮት ሳትለይ በገሃነም ተግዘው ለነበሩ ነፍሳት ደኅነትን ታበስር ዘንድ፣ ነጻም ታደርጋቸው ዘንድ ወደ ሲኦል ወረደች፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ እንደ ተናገረው ቃል ዐፅም፣ ሥጋ ወደ መኾን ፈጽሞ እንደ ተለወጠ የሚናገሩ የመናፍቃንን የአእምሮአቸውን ጉድለት ፈጽመን በዚህ ዐወቅን፡፡ ይህስ እውነት ከኾነ ሥጋ በመቃብር ባልተቀበረም ነበር፡፡ በሲኦል ላሉ ነፍሳት ነጻነትን ያበስር ዘንድ ወደ ሲኦል በወረደ ነበር እንጂ፡፡ ነገር ግን ከነፍስና ከሥጋ ጋር የተዋሐደ ቃል ነው፡፡ እርሱ የሥጋ ሕይወት በምትኾን በአካለ ነፍስ ወደ ሲኦል ወርዶ ለነፍሳት ነጻነትን ሰበከ፡፡ ሥጋ ግን በበፍታ እየገነዙት በጎልጎታ በዮሴፍ በኒቆዲሞስ ዘንድ ነበረ፤ ቅዱስ ወንጌል እንደ ተናገረ፡፡ አባቶቻችን ሥጋ በባሕርዩ ቃል አይደለም፤ ቃል የነሣውሥጋ ነው እንጂ ብለው አስተማሩን፤ ይህንን ሥጋም ከሙታን ተለይቶ ከተነሣ በኋላ ቶማስ ዳሠሠው፤ በሥጋው ሲቸነከር ቃል ታግሦ የተቀበለውን የችንካሩን እትራትም (ምልክት) በእርሱ አየ፤›› (ዝኒ ከማሁ ፴፥፴፩-፴፮)፡፡

‹‹አሁን እግዚአብሔር ሞተ ሲል ብትሰማ አትፍራ፤ ‹የማይሞተውን ሞተ ሊሉ አይገባም› ከሚሉ፤ ዕውቀት ከሌላቸው፤ ሕማሙን፣ ሞቱን ከሚክዱ መናፍቃን የተነሣ አትደንግጥ፡፡ እኛ ግን በመለኮቱ ሞት እንደ ሌለበት፤ በሥጋ ቢሞትም በመለኮቱ ሥልጣን እንደ ተነሣ እናውቃለን፡፡ ሞት የሌለበት ባይኾንስ ኖሮ በሥጋ በሞተ ጊዜ ሥጋውን ባላስነሣም ነበር፤ ሥጋው እስከ ዓለም ፍጻሜ በመቃብር በኖረ ነበር እንጂ፤›› (ቅዱስ ባስልዮስ፣ ሃይ. አበ. ፴፬፥፲፯-፲፰)፡፡

‹‹ከመስቀሉ ወደ ሲኦል በመውረዱ አዳነን፤ በአባታቸው በአዳም በደል በሲኦል ተግዘው የነበሩ ጻድቃንን ፈታ፤ ከሙታን ተለይቶ አስቀድሞ በተነሣ በእውነተኛ ትንሣኤውም አስነሣን፡፡ የንስሐንም በር ከፈተልን፤›› (ቅዱስ ጎርጎርዮስ ዘኑሲስ፣ ሃይ. አበ. ፴፮፥፴)፡፡

‹‹በአባታችን በአዳም በደል የተዘጋ የገነት ደጅን የከፈተልን፤ ዕፀ ሕይወትን የሚጠብቅ ኪሩብንም ያስወገደው፤ የእሳት ጦርን ከእጁ ያራቀ፤ ወደ ዕፀ ሕይወት ያደረሰን እርሱ ነው፡፡ ፍሬውንም (ሥጋውን፣ ደሙን) ተቀበልን፡፡ አባታችን አዳም ሊደርስበት ወዳልተቻለው፤ በራሱ ስሕተት ተከልክሎበት ወደ ነበረው መዓርግ ደረስን፡፡ ክፉውንና በጎውን ከሚያስታውቅ፤ ወደ ጥፋት ከሚወስድ፤ በአዳምና በልጆቹም ላይ ኃጢአት ከመጣበት ከዕፀ በለስ ፊታችንን መለስን፤›› (ዝኒ ከማሁ ፴፮፥፴፰-፴፱)፡፡

‹‹የሕይወታችን መገኛ የሚኾን የክርስቶስ ሞት የእኛን ሞት ወደ ትንሣኤ እንደ ለወጠ እናምናለን፤ ክርስቶስም ሞትን አጥፍቶ የማታልፍ ትንሣኤን ገለጠ፤ እንደ ተጻፈ፡፡ ከሰው ወገን ማንም ማን ሞትን ያጠፋ ዘንድ፣ ትንሣኤንም ይገልጣት ዘንድ አይችልም፤ ዳዊት ‹በሕያውነት የሚኖር፤ ሞትንም የማያያት ሰው ማነው? ነፍሱን ከሲኦል፤ ሥጋውን ከመቃብር የሚያድን ማን ነው?› ብሎ እንደ ተናገረ፤›› (ቅዱስ አቡሊዲስ፣ ሃይ. አበ. ፵፪፥፮-፯)፡፡

‹‹በመለኮትህ ሕማም፣ ሞት የሌለብህ አንተ ነህ፡፡ በሥጋ መከራ የተቀበልህ አንተ ነህ፡፡ ከአብ ጋር አንድ እንደ መኾንህ ሞት የሌለብህ አንተ ነህ፡፡ ከእኛም ጋር አንድ እንደ መኾንህ በፈቃድህ የሞትህ አንተ ነህ፡፡ በመቃብር ያደርህ አንተ ነህ፡፡ በኪሩቤል ላይ ያለህ አንተ ነህ፡፡ ከሙታን ጋር በመቃብር የነበርህ አንተ ነህ፡፡ በአንተ ሕማምና ሞትም ድኅነት ተሰጠ፤ ከሙታን ጋር የተቆጠርህ አንተ ነህ፤ ለሙታንም ትንሣኤን የምትሰጥ አንተ ነህ፡፡ ሦስት መዓልት፤ ሦስት ሌሊት በመቃብር ያደርህ አንተ ነህ፤ በዘመኑ ዅሉ ከአብ ከመንፈስ ቅዱስ ጋር የምትኖር አንተ ነህ፤ በመለኮት ሕማም ሳይኖርብህ በሥጋ የታመምክ አካላዊ እግዚአብሔር ቃል አንተ ነህ፤›› (ቅዱስ ኤራቅሊስ፣ ሃይ. አበ. ፵፰፥፲፪-፲፫)፡፡

‹‹እኛስ ኃጢአታችንን ለማስተሥረይ በሥጋ እንደ ታመመ፤ እንደ ሞተ፤ ከነፍሱም በተለየ ጊዜ ሥጋውን እንደ ገነዙ፤ ከሙታንም ተለይቶ በእውነት እንደ ተነሣ፤ ከተነሣም በኋላ በእውነት ወደ ሰማይም እንደ ዐረገ እናምናለን፡፡ በኋላም በሚመጣው ዓለም እርሱ በሕያዋንና በሙታን ይፈርድ ዘንድ ይመጣል፡፡ የሰውን ወገኖች ዅሉ በሞቱበት፤ በተቀበሩበት ሥጋ ከሞት ያስነሣቸዋል፡፡ ከትንሣኤውም በኋላ ያለ መለወጥ ዅልጊዜ ይኖራል፡፡ እርሱ በዚህ በሞተበት፤ በተገነዘበት ሥጋ ከሙታን አስቀድሞ እንደ ተነሣ፤›› (ቅዱስ ዮሐንስ ዘኢየሩሳሌም፣ ሃይ. አበ. ፶፪፥፲፩-፲፪)፡፡

‹‹የሥጋን ሕማም ለመለኮት ገንዘብ በአደረገ ጊዜ የእግዚአብሔር አካል በባሕርዩ በግድ ሕማምን አልተቀበለም፤ ሕማም በሚስማማው ባሕርዩ ኃይልን እንጂ፡፡ ሞትም በሥጋ ለእግዚአብሔር ቃል ገንዘብ በኾነ ጊዜ ሞትን አጠፋ፡፡ ከሞትም በኋላ ፈርሶ፣ በስብሶ መቅረትን አጠፋ፤›› (ቅዱስ ቴዎዶጦስ ሃይ. አበ. ፶፫፥፳፯)፡፡

‹‹መለኮት በሥጋ አካል በመቃብር ሳለ የሥጋ ሕይወት በምትኾን በነፍስ አካል ወደ ሲኦል ወረደ፤ እንደዚህ ባለ ተዋሕዶ ከሙታን ተለይቶ ተነሣ፡፡ ከትንሣኤ በኋላ አይያዝም፤ አይዳሰስም፡፡ በዝግ ቤት ገብቷልና፡፡ ነገር ግን ምትሐት እንዳይሉት ቶማስ ዳሠሠው፡፡ የተባለውን ከፈጸመ በኋላ ቶማስ አመነበት፤›› (ቅዱስ ኤጲፋንዮስ፣ ሃይ. አበ. ፶፮፥፴፯-፴፰)፡፡

‹‹ክርስቶስ የሙታን በኵር እንደምን ተባለ? እነሆ በናይን ያለች የደሀይቱን ልጅ አስቀድሞ አስነሣው፤ ዳግመኛም አልዓዛርን በሞተ በአራተኛው ቀን አስነሣው፡፡ ኤልያስም አንድ ምውት አስነሣ፡፡ ደቀ መዝሙሩ ኤልሣዕም ሁለት ሙታንን አስነሣ፤ አንዱን ሳይቀበር፣ ሁለተኛውን ከተቀበረ በኋላ ሥጋውን አስነሣ፡፡ እነዚያ ሙታን ቢነሡ ኋላ እንደ ሞቱ፤ እነርሱ ኋላ አንድ ኾነው የሚነሡበትን ትንሣኤ ዛሬ ተስፋ ያደርጋሉ፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ግን የሙታን ትንሣኤያቸው በኵር ነው፡፡ ‹እንግዲህ ወዲህም ሞት የሌለበትን ትንሣኤ አስቀድሞ የተነሣ እርሱ ነው፤ ዳግመኛም ሞት አያገኘውም› ተብሎ እንደ ተጻፈ፤›› (ቅዱስ ኤጲፋንዮስ፣ ሃይ. አበ. ፶፯፥፫-፮)፡፡

‹‹ቃል ሥጋውን በመቃብር አልተወም፤ በሲኦልም ካለች ከነፍሱ አልተለየም፡፡ ከነፍስ ከሥጋ በአንድነት ነበረ እንጂ፡፡ ለዘለዓለም ክብር ምስጋና ይግባው፤›› (ቅዱስ ጎርጎርዮስ ዘእንዚናዙ ሃይ. አበ. ፷፥፳፱)፡፡

‹‹ጌታ ለደቀ መዛሙርቱ ‹በትንሣኤ ከእናንተ ጋር እስከምመጣበት ቀን ድረስ ከዚያ ወይን ጭማቂ አልጠጣም፤ በሐዲስ ግብር በምነሣበት ጊዜ የምታዩኝ እናንት ምስክሮቼ ናችሁ› ያለውን የማቴዎስን ወንጌል በተረጐመበት አንቀጽ እንዲህ አለ፤ ሐዲስ ያለው ይህ ነገር ምንድን ነው? ይህ ነገር ድንቅ ነው! መዋቲ ሥጋ እንዳለኝ ታያላችሁ፤ ነገር ግን ከትንሣኤ በኋላ የማይሞትነው፤ አይለወጥም፤ ሥጋዊ መብልንም መሻት የለበትም፤ ከትንሣኤ በኋላ ከደቀ መዛሙርቱ ጋር ቢበላም ቢጠጣም መብልን ሽቶ አይደለም፤ እርሱ ከሙታን ተለይቶ እንደ ተነሣ ያምኑ ዘንድ በላ ጠጣ እንጂ፡፡ ይህ ድንቅ ሥራ ነው! ያለ መለወጥ ሰው የኾነ ቃል የተቸነከረበትን ምልክት (እትራት) አላጠፋምና፡፡ በሚሞቱ ሰዎች እጅ እንዲዳሠሥ አድርጎታልና፡፡ አምላክ የኾነ ሥጋ የሚታይበት ጊዜ ነውና አላስፈራም፡፡ እርሱ በዝግ ደጅ ገባ፤ ግዙፉ ረቂቅ እንደ ኾነ ሥራውን አስረዳ፡፡ ነገር ግን በትንሣኤው ያምኑ ዘንድ የተሰቀለው እርሱ እንደሆነ የተነሣውም ሌላ እንዳይደለ ያውቁ ዘንድ ይህን ሠራ፡፡ ስለዚህም ተነሣ፤ በሥጋውም የችንካሩን ምልክት (እትራት) አላጠፋም፤ ዳግመኛም ከትንሣኤው አስቀድሞ ደቀ መዛሙርቱ ጧት ማታ ከእርሱ ጋር ይበሉ እንደ ነበረ ከደቀ መዛሙርቱ ጋር በላ፤ ስለዚህም በአራቱ መዓዝነ ዓለም ትንሣኤውን አስረዱ፡፡ ከትንሣኤውም በኋላ ‹ያየነው ከእርሱም ጋር የበላን የጠጣንም እርሱ ነው› ብለው አስረዱ፤›› (ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ሃይ. አበ. ፷፮፥፯-፲፪)፡፡

ይቆየን

በዓለ ትንሣኤን በትንሣኤ ልቡና እናክብር

በገብረ እግዚአብሔር ኪደ

ሚያዝያ ፲፰ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

 ፋሲካ ማለት መሻገር ማለት ነው፡፡ እግዚአብሔር ወልድ እኛን ከወደቅንበት አንሥቶና ተሸክሞ ከዚኽ ምድር ወደ ሰማያት ተሻግሯልና (ተነሥቶ ዐርጓልና)፡፡ ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስ፡- ‹‹እንግዲኽ ከክርስቶስ ጋር ከተነሣችኁ ክርስቶስ በእግዚአብሔር ቀኝ ተቀምጦ ባለበት በላይ ያለውን ሹበላይ ያለውን አስቡ እንጂ በምድር ያለውን አይደለም፡፡ ሞታችኋልና ሕይወታችኁም በእግዚአብሔር ከክርስቶስ ጋር ተሰውሯልና፡፡ ሕይወታችኁ የኾነ ክርስቶስ በሚገለጥበት ጊዜ እናንተ ደግሞ ከእርሱ ጋር በክብር ትገለጣላችኁ፤›› እንዳለን /ቈላ.፫÷፩-፬/፣ በጥምቀት ውኃ ሞቱን በሚመስል ሞት ስንሞት፣ አሮጌው ሰውነታችን እንደ ግብጻውያን ተቀብሮ ቀርቷል፡፡ አዲሱ ሰውነታችን ግን እስራኤላውያን ባሕሩ ተከፍሎላቸው እንደ ተሻገሩ ተሻግሯል (ተነሥቷል)፡፡

ብልየት ያለበት የቀዳማዊ አዳም ሰውነታችን በግብረ መንፈስ ቅዱስ ተቀብሮ አዲሱ ሰውነታችን ሕይወትን አግኝቶ ተነሥቷል፡፡ መሬታዊው ሰውነታችን ሞቶ ሰማያዊው ሰውነታችንን ለብሰን መንፈሳውያን ኾነን ተነሥተናል፡፡ ወደ ጥንተ ተፈጥሯችን ተመልሰናል፡፡ አኹን ከእኛ የሚጠበቀው ይኽ ተፈጥሯችንን ሳናቆሽሽ መጠበቅ ነው፤ እንደ ተነሣን መዝለቅ፡፡ ይኽን ለማድረግም ተራራ መውጣት፣ ምድርን መቆፈር፣ የእሳት ባሕርን መሻገር አይጠበቅብንም፡፡ ይኽን ጠብቀን እንድንቈይ እግዚአብሔር ከእኛ የሚፈልገው አንድ ነገር ብቻ ነው፤ ፈቃዳችንን፡፡ የሚሠራው እርሱ ራሱ ነውና /ዮሐ.፲፭÷፭/፡፡ መጽንዒ (የሚያጸና) መንፈስ ቅዱስን ያደለንም ስለዚኹ ነው፡፡

የምናመልከውን አምላክ መስለን በሕይወት ሳንሻገር የመሻገርን በዓል (ፋሲካን) የምናከብረው ምን ጥቅም እንዲሰጠን ነው? ከጨለማ ሥራ ወደ ብርሃን ሥራ፣ ከፍቅረ ዓለም ወደ ፍቅረ ክርስቶስ ሳንሻገር ፋሲካን የማክበራችን ትርጕሙ ምንድነው? እኛው ሳንነሣ የመነሣት በዓልን ማክበራችን በፍርድ ላይ ፍርድ በበደል ላይ በደል ከመጨመር ውጪ የሚሰጠን ጥቅም ምንድን ነው? የምንነሣውስ መቼ ነው? በዐይናችን ጉድፍ ብትገባ ስንት ደቂቃ እንታገሣታለን? ታድያ በነፍሳችን ላይ የተጫነውን የኃጢአት ግንድ መቼ ነው የምናስወግደው? መቼ ነው ወደ ላይኛው ቤታችን ቀና የምንለው? ብዙዎቻችን በሕይወታችን ሳንሻገር ነው በዓለ ፋሲካን የምናከብረው፡፡ ክርስቲያን ኾኖ በመብልና በመጠጥ ብቻ ፋሲካን ማክበር ኢ ክርስቲያናዊ ተግባር ነው፡፡

አዲሱን ሰውነታችን ለብሰን ከተነሣን በኋላ እንደ ቀድሞ ምልልስ የምንጓዝ ከኾነ ግን ተመልሰን ወድቀናል፤ አዲሱ ሰውነታችንን አውልቀን አሮጌውን ሰውነታችንን በድጋሜ ለብሰነዋል፡፡ በእኛነታችን ውስጥ ፍቅረ ንዋይ፣ ፍቅረ ሲመት፣ ፍትወት፣ ይኽንንም የመሰሉ ዅሉ ካለ አዲሱ ሰውነታችን ከእኛ ጋር የለም፤ ቢኖርም ታሟል፡፡ በኃጢአት የመቃጠል ስሜት፣ ርኵሰትና ክፉ ምኞት ከእኛ ዘንድ ካለ አሮጌ ሰው ኾነናል፤ ትንሣኤ ልቡናን ገንዘብ አላደረግንም፡፡ ስለዚኽ ከልቡና ሞት እንነሣና ፋሲካን እናክብር፡፡ እስከ አኹን በኃጢአት ውስጥ ካለን ወደ ብርሃን ክርስቶስ እንምጣ (እንሻገርና) የመሻገርን በዓል እናክብር፡፡ ከክፉ ሥራ ወደ ጽድቅ ሥራ እንሻገርና የእውነት ፋሲካን እናክብር፡፡ ከኃይል ወደ ኃይል እንሻገርና ፋሲካን እናክብር፡፡ ከሞት ሥራ ወደ ሕይወት ሥራ እንነሣና የመነሣትን በዓል እናክብር፡፡

እግዚአብሔር የሚወዳችሁ አንድም እግዚአብሔርን የምትወዱት ሆይ! እኛን የሚያሰነካክል ደግሞም የሚጥለን ፈርዖን (ዲያብሎስ) ተሰነካክሎ ወድቋልና ከግብጽ ሕይወታችን እንውጣ፡፡ ተነሥተንም እንሻገር፡፡ ተሻግረንም ሰማያዊውን ፋሲካ እናክብር፡፡ በግብጽ የነበሩት እስራኤላውያን የበጉን ደም በጉበኑና በኹለቱም መቃን ሲቀቡት አጥፊው ከቤታቸው እንዳለፈ አንብበናል /ዘፀ.፲፪÷፲፫/፡፡ ይኸውም በጉ በራሱ ያንን የማድረግ ኃይል ስለ ነበረው አይደለም፤ ደሙ የክርስቶስ ደም አምሳል ስለ ነበር ነው እንጂ፡፡ እኛ ግን የአማናዊውን በግ /ዮሐ.፩፡፳፱/ ደም በልቡናችን፣ በአስተሳሰባችንና በሰውነታችን ዅሉ እንቀባና (እንቀበልና) እንሻገር፡፡

ይኽን ስናደረግ በእባቡና በጊንጡ ይኸውም በዲያብሎስና በሠራዊቱ ላይ ሥልጣን ይኖረናል /ሉቃ.፲÷፲፱/፡፡ የምንበላው በግ ራሱ ሕይወት ስለ ኾነ ሞት በእኛ ላይ አይነግሥም /ዮሐ.፲፬÷፮/፡፡ በዚኽ ዓለም ሳለን ከዚኽ ደስታ ተካፋዮች ከኾንን (የመዠመሪያውን ትንሣኤ ልቡና በንስሐ ከተነሣን) በሚመጣው ዓለምም በክብር ላይ ክብር፣ በሹመት ላይ ሹመት እንቀበላለን (ኹለተኛውን ትንሣኤ እንነሣለን) /ሉቃ.፳፪÷፲፭-፲፮/፡፡ ብንወድቅ እንኳን መልሰን በመነሣት ከባሕርይ አባቱ ከአብ፣ ከባሕርይ ሕይወቱ ከመንፈስ ቅዱስ ጋር ክብር፣ የክብር ክብር፣ ጌትነት የባሕርዩ በሚኾን፤ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ሰጭነት በመንግሥተ ሰማያት ጸጋ ክብር እናገኛለንና የጭንቅ ቀን ሳይመጣ በዓለ ትንሣኤን እናክብር፡፡ ለዚህም ሊቁ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ የመከረንን የሚከተለውን ኃይለ ቃል በተግባር ላይ ብናውለው እንጠቀማለን፤

‹‹በምነግራችኁ ነገር እያበሳጨኋችሁና እያሳመምችሁ እንደ ኾነ ይገባኛል? ግን ምን ላድርግ? እኔም እናንተም በምግባር በሃይማኖት የታነጽን እንኾን ዘንድ ብቻ ሳይኾን ከዚያም እናመልጥ ዘንድ ነው፡፡ ነገር ግን በኃጢአት ከመጨማለቃችን የተነሣ እንዴት አድርጌ ላሳምማችኁ እችላለኁ? ብትሰሙኝና ብትለወጡስ እኔም ማረፍ እንኳን በቻልኩ ነበር፡፡ ስለዚኽ እስካልተለወጣችሁ ድረስ እናንተን መገሠንና መምከሬን አላቆምም፡፡ ስለ ገነመ እሳት ተደጋግሞ ሲነገር የሚበሳጭ ሰው ሊኖር ይችላል፡፡ እኔ ግን ከዚኽ የበለጠ ያማረ የተወደደ አስደሳች ትምህርት የለም እለዋለኁ፡፡ እንዴት ይኽ አስደሳች ትምህርት ነው ትለናለህ? ልትሉኝ ትችላላችሁ፡፡ እኔም ወደዚያ መጣል ከደስታ ዅሉ የራቀ ነውናብዬ እመልስላችኋለሁ፡፡ ስለዚኽ ነፍሳችን ከመታሠሯ በፊት የነቃን የተጋን እንኾን ዘንድ ይኽን ደጋግሜ እነግራችኋለሁ፡፡ ስሐ ይግባ እንጂ ማንም እንደ ተወቀሰ አያስብ፤ በንግግሬም የሚቆጣ አይኑር፡፡ ዅላችንም ወደ ጠባቢቱ መንገድ እንግባ፡፡ እስከ መቼስ በስንፍና አልጋ እንተኛለን? ዛሬ ነገ ማለት አይበቃንም ወይ? ሰማያዊ ቪላችንን ቀና ብለን ብንመለከት እኮ በዚኽ ምድር ይኽንን ለመሥራት ባልደከምን ነበር፡፡ እስቲ ንገሩኝ! ሩጫችንን ስንጨርስ ከሬሳ ሳጥንና ከመግነዝ ጨርቅ ውጪ ይዘነው የምንሔድ ነገር ምን አለ? ታድያ ለምን እንከራከራለን?›› (ሰማዕትነት አያምልጣችሁ እና ሌሎች፣ ገጽ ፻፶፮ – ፻፶፯)፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡