ወርኃ ጥርና የወጣቶች ሕይወት

ዲ/ን ወልደ ቂርቆስ ደሳለኝ

የወጣትነት ምንነትና ፈተናዎቹ

በዚህ ጽሑፍ የወጣትነት ምንነት፣ መገለጫዎች እና ተግዳሮቶቹ ላይ ትኩረት አድርገን እንመለከታለን፡፡ ወጣትነት ፈጣን፣ አካላዊ፣ ስሜታዊና ማኅበራዊ ለውጦች የሚሰተናገዱበት ከልጅነት ወደ ጎልማሳነት፣ ከጥገኝነት ራስን ወደ መቻል መሸጋገሪያ ድልድይ የሆነ የዕድሜ ክልል ነው፡፡ እነዚህን ለውጦች ተክትሎ በወጣቶች ጠባይ (ባሕርይ) ላይ የሚከሠቱ ብዙ ጉዳዮች አሉ፡፡ ከእነዚህም መካከል፡- ከፍተኛ የሆነ የአቻ ግፊት ተጋላጭነት፣ የሥጋዊ ፍትወት ፍላጎትና ግፊት፣ ከመጠን ያለፈ ግትርነትና ግልፍተኝነት፣ የስሜት መለዋወጥ፣ ቀድሞ ለመረዳት፣ አስቸጋሪ የሆኑ አስተሳሰቦች እና አመለካከቶች፣ ወላዋይነትና ውሳኔ ለመወሰን መቸገር፣ ለፍልስፍና ብሎም ለማኅበራዊና ፖለቲካዊ ጉዳዮች ትልቅ ትኩረት መስጠት፣ ራስን ከሌሎች የዕድሜ አቻዎች ጋር ማወዳደርና ማነጻጸር፣ ከቤተሰብ ብሎም ከሌሎች በዙሪያቸዉ ካሉ ታላላቆች ቊጥጥር ተላቆ ነጻ የመውጣት ፍላጎት፣ ራስን የመቻል ከፍተኛ ፍላጎት ወዘተ ናቸው፡፡
ከላይ በተዘረዘሩት ማለትም ወጣትነት በራሱ ከሚያመጣቸው ፈተናዎች ወይም ተግዳሮቶች ምክንያት የዕድሜ ክልሉን ፈታኝ ያደርገዋል፡፡ ለዚህም ነው አበው ወጣትነት ከዐራቱ ባሕርያት መካከል የእሳትነት ባሕርይ የሚያይልበት ነው ብለው የሚያሰተምሩን፡፡ ከዚህ በላቀ ደግሞ የወጣቶች አካባቢያዊና ቤተሰባዊ ተፅዕኖ ችግሮቹን የበለጠ አባብሶ የወጣቶችን ቀጣይ ሕይወት አደጋ ላይ ይጥላል፡፡
ወርኃ ጥር በሀገራችንና በቤተ ክርስቲያናችን
ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ከመፍቀሬ ጥበብ ሰሎሞን “ለሁሉም ጊዜ አለው፤ ከፀሐይ በታችም ለሆነው ነገር ሁሉ ጊዜ አለው፡፡” (መክ.፫፥፩) የሚለውን መሠረት አድርጋ ዘመናትን በተለያዩ አዕዋዳት እና አቅማራት ከፋፍላ ከማስቀመጥና ከማሳወቅ ባለፈ የሀገራችንን የተፈጥሮ ሁኔታ ባገናዘበ መልኩ በየክፍለ ዓመቱ (ወቅቶች) ሊከናወን የሚገባውን ተግባር በመዘርዘር በአበው ሊቃውንት አማካይነት በቃልና በጽሑፍ ትመክራለች፤ ታስተምራለችም፡፡ ምእመናንም ይህንን ድንቅ ትምህርት ተከትለው ለመንፈሳዊ እና ማኅበራዊ ጉዳዮች ማከናወኛ የሚሆኑትን ጊዜያት በወቅት በወቅት ከፍለው ይጠቀሙበታል፡፡
በአብዛኛው የሀገራችን ክፍል በወርኃ ጥር ክብረ በዓላት በደመቀ ሁኔታ የሚከበሩበት (ከበዓለ ልደት ጀምሮ ጥር ፲፩ በዓለ ጥምቀት፣ በበርካታ አድባራትና ገዳማት ዓመታዊ ክብረ በዓላት በተለያዩ ቀናት በአማረና በደመቀ ሁኔታ መከናወኑ)፣ እንዲሁም በርከት ያሉ የማኅበራዊ ጉዳዮች በስፋት የሚከናወኑበት ወራት ነው፡፡
በእነዚህም ምክንያት በወርኃ ጥር ወጣቶች መንፈሳውያን ነን የሚሉትም ሳይቀሩ ለተለያዩ ፈተናዎች ተጋላጭ ይሆናሉ፡፡ ይህ ደግሞ ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስ “አንተ የዕውሮች መሪ በጨለማም ላሉት ብርሃን እንደሆንህ በራስህ የምትተማመን ከሆንህ ሰነፎችን ልባሞች የምታደርግ፣ ሕፃናትን የምታስተምር፣ ጻድቅና የምትከብርበትን የኦሪትን ሕግ የምታውቅ የምትመስል እንግዲህ ሌላውን የምታስተምር ራስህን ለምን አታስተምርም” (ሮሜ፪፥፲፱-፳፩) በማለት እንዳስተማረን አስቀድመን ራሳችንን በፈተና ከመውደቅ ልንጠብቅ ይገባናል፡፡
በዚህ ጽሑፍ መንፈሳውያን ወጣቶች ከሌላው ጊዜ በበለጠ በጥር ወር ከሚከበሩ በዓላት ጋር ተያይዞ ጥንቃቄ ሊያደርጉባቸውና ራሳቸውን በፈተና ተሰናክለው ከመውደቅ ይጠነቀቁ ዘንድ መሠረታዊ ጉዳዮችንና የመፍትሔ ሐሳቦችን ጠቅለል አድርገን እንመለከታለን፡፡
ችግሮቹ
፩. ከሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን ማፈንገጥ
ቤተ ክርስቲያን በውስጧ ለሚከናወን ማንኛውም ተግባር ቅዱስ መጽሐፍን፣ ትምህርተ አበውን እና መንፈሳዊውን ትውፊት አብነት በማድረግ ሕገ ደንብና ሥርዓትን በዝርዝር አስቀምጣለች፡፡ ለዚህም ነው ሊቃውንት ቤተ ክርስቲያንን ስንዱ እመቤት በማለት የሚጠሯት፡፡ ቤተ ክርስቲያንን ምሉዕ እና ስንዱ እመቤት ከሚያሰኟት ሀብቶቿ አንዱና ዋነኛው ደግሞ ስለ በዓላት አከባበር ያስቀመጠችው ዝርዝር ሥርዓት ነው፡፡ ዛሬ ዛሬ ወጣቶች በአፍላ ስሜታዊነት እና በሉላዊነት (ዘመናዊነት) ተጽእኖ ምክንያት በታላላቅ መንፈሳውያን በዓላት ከሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን ብሎም ከሀገር ባሕልና ወግ ያፈነገጡ መጥፎ ድርጊቶች በዓላትን በማሳመርና በማድመቅ ሰበብ ሲያከናውኑ እንታዘባለን፡፡ በዓላት በቤተ ክርስቲያን የራሳቸው ነገረ ሃይማኖታዊ ትርጓሜና ትውፊታዊ ሥርዓት አላቸው፡፡ ነገር ግን ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ ወጣቶች ከበዓላቱ ምንነትና ትርጓሜ ይልቅ በማወቅም ይሁን ባለማወቅ ወደ ስሕተት እየወሰዱና መንፈሳዊና ማኅበራዊ ሕይወታቸውን ፈተና ላይ የሚጥሉ ጉዳዮቸ ላይ ትኩረት ሲያደርጉ እንመለከታለን፡፡
ከእነዚህም መጥፎ ልማዶች መካከል፡- ያልተገባና ከሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን ከዚያም አልፎ ከሀገር ባሕል ያፈነገጡ አለባበሶች፣ የበዓላቱን ሃይማኖታዊና መንፈሳዊ ጥቅም ከመመልከት ይልቅ ምድራዊና ባሕላዊ ጠቀሜታቸው ላይ ብቻ ትኩረት ማድረግ ላይ ያዘነብላሉ፡፡ ለመንፈሳዊ ሱታፌ እና ለሰማያዊ በረከት ከመትጋት ይልቅ በዓይነ ሥጋ ብቻ አይቶ መደሰትን፣ በልቶ፣ ጠጥቶና ጨፍሮ መዝናናትን ዓላማ አድርጎ ወደ ክብረ በዓላቱ መምጣት፣ ሕገ ቤተ ክርስቲያንን የሚከተሉ ምእመናንን ከመንፈሳዊ ተመስጦ ማስወጣት፣ እንዲሁም ራሳቸውን ወደ ሥጋዊ ሐሳብና ዝሙት የሚመሩ ብሎም ለኃጢአት የሚያነሳሱ ዘፈንና ጭፈራዎች መብዛት ዋና ዋናዎቹ ናቸው፡፡
ከዚህ በተጨማሪ ሌላው በወርኃ ጥር በወጣቶች መንፈሳዊ ሕይወት ላይ የምንመለከተዉ ፈታኝ ችግር የአንዳንድ ወጣቶች “የድሮውን ዘመን አስብ፤ የልጅ ልጅንም ዓመታት አስተውል፤ አባትህን ጠይቅ ይነግርህማል፤ ሽማግሌዎችህን ጠይቅ፤ ይተርኩልህማል፡፡” (ዘዳ.፴፪፥፯) እንዲል መጽሐፍ የአበው መምህራንን ምክረ ቃልና ትእዛዝ በማዳመጥ በመንፈሳዊ ብስለትና ቀናዒነት ከማገልገል ይልቅ በስሜት፣ በማን አለብኝነትና በግልፍተኝነት ለማገልገል መነሳት ነው፡፡ ይህም ሕገ ቤተ ክርስቲያንን ወደ ማፍረስና እና እኔ ብቻ ያልኩት ካልሆነ በሚል አኩራፊነት ስሜት ብዙ ወጣቶችን ከቤተ ክርስቲያን እያሸሸ ይገኛል፡፡ ከዚህ ይልቅ “የሰው ወርቅ አያደምቅ” እንዲሉ አበው የሌላውን ከመናፈቅ ለራስ ሀብትና ሥርዓት ትኩረት መስጠት ያስፈልጋል፡፡
፪. ከመጠን ያለፈ ምግብና መጠጥ
ሊቀ ሐዋርያት ቅዱስ ጴጥሮስ በመልእክቱ ደጋግሞ ካነሳችው ምክር አዘል ጉዳዮች አንዱ በመጠን ስለ መኖር ነው፡፡ “ዳሩ ግን የነገር ሁሉ መጨረሻ ቀርቧል፤ እንግዲህ እንደ ባለ አእምሮ አስቡ ትጸልዩም ዘንድ በመጠን ኑሩ” (፩ኛ ጴጥ ፬፥፯፤፰፥፭) እንዲል፡፡ ቤተ ክርስቲያናችን ነገር ሁሉ በአግባቡና በመጠኑ ይሆን ዘንድ ዘወትር ትመክራለች፤ ታስተምራለች፡፡ እርግጥ ነው የሰው ልጅ ለቁመተ ሥጋ ምግብ ይመገብ ዘንድ ግድ ነው፡፡ ነገር ግን መብላት፣ መጠጣት ከመጠን ባለፈ ጊዜ በመጀመሪያ ድኃ ወገናችንን ያስረሳል፤ ከዚያም ከፍ ሲል ራስን ያስረሳል፤ ከሁሉም በላይ ግን በመጠን አለመኖር የእግዚአብሔርን ሀልዎት ያስዘነጋል፡፡ ሕዝበ እስራኤል ከዚያ ሁሉ ውለታና ስጦታ በኋላ የሊቀ ነቢያት ሙሴን ወደ ደብረ ሲና መውጣት ተከትሎ ከፈርኦን የባርነት ቀንበር ያወጣቸውን፣ ባሕር ከፍሎ ያሻገራቸውን አምላክ ረስተው ጣዖት አስቀርጾ ወደ ማምለክ የወሰዳቸው ከመጠን ያለፈ ምግብና መጠጥ መሆኑን መጽሐፍ መዝግቦልናል፡፡ (ዘፀ. ፴፪፥፩-፮)፡፡
በዘመናችን በተለይም በወርኃ ጥር ለክብረ በዓላት፣ ለጋብቻና ለሌሎች ማኅበራዊ ጉዳዮች የሚዘጋጁ ግብዣና ድግሶችን ተከትሎ አንዳንድ ምእመናን በተለይም ወጣቶች በመጠን ኑሩ ያለውን የሐዋርውን ምክረ ቃል በመዘንጋት ራሳቸውን ለዓለም ፈተና አሳልፈዉ ሲሰጡ ይስተዋላል፡፡ እንዲያውም “ዐሥር ጊዜ ካልበሉ፣ ጠጥተውስ ካልሰከሩ የት አለ ዓመት በዓሉ” የሚል ብሂልም ያለማቋረጥ ይጠቀሳል፡፡ ከዚህ ይልቅ “እጅግ ለሰበሰበ አልተረፈውም፣ ጥቂትም ለሰበሰበ አልጎደለበትም፡፡” (ዘፀ፲፮፥፲፯) ተብሎ እንደተጻፈ አብዝተን በልተን ከእግዚአብሔር ጋር ከመጣላት ሁሉንም በመጠን ማድረግ አንዱ የክርስትና መገለጫ ነው፡፡
፫.ለባዕድ ልማዶችና ሱሶች ተጋላጭነት
በወርኃ ጥር ለወጣቶች ፈተና ከሚሆኑ ታላላቅ ጉዳዩች መካከል አንዱና ዋነኛው ደግሞ ለባዕድ ልማዶችና ሱሰኝነት መጋለጥ ነው፡፡ የተለያዩ ጥናቶች እንደሚጠቁሙት ወጣቶች መጤ ልማዶችንና ሱሰኝነትን የሚቀላቀሉት ወይም የሚጀምሩት በማኅበራዊ ጉዳዮች ምክንያት የሚዘጋጁ እንደ ሠርግ ያሉ የበዓላት ግብዣና ድግሶች ላይ ነው፡፡ በአቅራቢያችን ያሉ በሱስ የተጠመዱ ወጣቶችን ወደ አልኮል፣ ጫት፣ ሺሻ ወይም ሐሺሽ መጠቀምን እንዴት እንደገቡ ብንጠይቅ የምናገኘው ምላሽ ይኸው ነው፡፡
በዘመናችን ከማኅበራዊ ሚድያ ማደግና ከቴክኖሎጂ መዘመን ጋር ተያይዞ የዓለም ሀገራት አንድ መሆንና ልማዶች መወራረስ መጀመራቸውን መመልከት ይቻላል፡፡ ለዚህም ከጋብቻና ከወሊድ ጋር በተያያዘ የሚወራረሱ ልማዶች ትልቅ ማሳያ ናቸው፡፡ በሀገራችንም ነባሩ ባሕላዊው፣ መንፈሳዊውና ትውፊታዊው የጋብቻ ሥርዓት (ሠርግ) እየተዘነጋ አልያም እየተበረዘ የጥንት ማንነትና ትርጉሙን እያጣ ይገኛል፡፡ በተለይ ወጣቶች ከመንፈሳዊውና ባሕላዊው ሥርዓት ይልቅ ለምዕራባውያን የሠርግ ሥርዓቶች ትኩረት በመስጠት መንፈሳዊ፣ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ቀውስ ውስጥ ራሳቸውን ሲከቱ ይስተዋላል፡፡ በዚህም ምክንያት ወጣቶች ለጊዜው ነፃነትና ዘመናዊነት የሚመስሉ፤ ነገር ግን ሙሉ ሕይወታቸውን አሰናክለው፣ ንጽሕናቸውንም አጉድፈው ለከባድ ውድቀት ለሚዳርጉ ጎጂ ሱሶችና ልማዶች ተጠጋላጭ ይሆናሉ፡፡
፬.መጠጥ፣ ጭፈራ፣ ስካርና ዝሙት
ከላይ የተጠቀሱት ከሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን ያፈነገጡ ልማዶች ባስከተሉት ተጽዕኖ ምክንያት ብዙ ወጣቶች በወርኃ ጥር በሚደረጉ መርሐ ግብሮች ወደ መጠጥ፣ ጭፈራ ብሎም ለስካርና ዝሙት ኃጢያት ይጋለጣሉ፡፡ በሉላዊነት ተፅዕኖ ምክንያት ሠርግን ከመሰሉ ታላላቅ ግብዣዎች አልኮል አለመጠጣት ጠጥቶም አለመስከርና ራስን አለመሳት፣ ከዚያም ከፍ ሲል ዝሙት አለመፈጸም በወጣቶች ዘንድ ያለመዘመንና የኋላ ቀርነት መገለጫ ተደርገው መወሰድ ጀምረዋል፡፡ በዚህም ምክንያት አንዳንድ ጠንካራ መንፈሳውያን ወጣቶች ሳይቀር ከዕድሜ እኩዮቻቸው ጋር ለመመሳሰል በሚል ሰበብ ሕይወታቸውን ወዳልተገባ አቅጣጫ ሲመሩና ተሰናከለው ሲወድቁ መመልከት የዘወትር ገጠመኛችን ከሆነ ሰነባብቷል፡፡
፭.ግጭትና ጠብ
በሌላ በኩል በወርኃ ጥር በሚከናወኑት ተደጋጋሚ የአደባባይ በዓላትና የሠርግ መርሐ ግብሮች መነሻነት ወጣቶችን የሚፈትነው ተግዳሮት ድንገታዊ ግጭት እና ጠብ ነው፡፡ በተለይም በአሁኑ ወቅት ባለው የሀገራችን የሰላምና የፖለቲካ አለመረጋጋት ወጣቶች በጭፍን ጥላቻ፣ በአፍላ ስሜታዊነትና በተዛባ መረጃ ተገፋፍተው ወደ ጠብ፣ ግርግር እና ግጭት የመግባት ዕድላቸው ከሌላው ጊዜ እጅግ የሰፋ ነው፡፡
ከዚህ ጋር በተያያዘ አንዳድ ወጣቶች ለበዓለ ጥምቀት በሚወጡበት ጊዜ አስበውና ተዘጋጅተው ስለታም ነገሮችንና ባልንጀራቸውን የሚቀጠቅጡበት በትር (ዱላ) ይዘው ሲወጡ ስናይ በእውነቱ ታቦተ ሕጉን አጅበውና አክብረው በረከተ ሥጋ ወነፍስ ለማግኘት ሳይሆን ጦር ሜዳ ወርደው የሀገርን ዳር ድንበር የደፈረ ጠላትን ለማውደም ቆርጦ የተነሣ የጦር ሠራዊት ይመስላሉ፡፡ ይህ የጠብና ግርግር አጫሪነት ልማድ የሚለበሱ ቲሸርቶች ላይ ከሚያስቀምጡት ኃይለ ቃል ይጀምርና በሚጨፈረው የባህል ጭፈራ ዓይነትና የግጥም ይዘት ይቀጥላል፡፡ እነዚህ ጉዳዮች ሲታዩ ቀላል ቢመስሉም በጽሑፋችን መግቢያ ላይ ያነሳናቸውን የወጣትነት መገለጫዎች ጋር አያይዘን ለመረዳት ከሞከርን ከደረቅ ሣር ላይ ቤንዚን አርከፍክፎ እሳት ከመልቀቅ ይልቅ የከፋ ነው፡፡
መፍትሔዎች
ሀ/ ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን በአግባቡ መረዳት
ወጣትነት ከተጠቀምንበት ብዙ ኃይል፣ ትልቅ ተስፋ የአገልግሎት ትጋት ያለበት የዕድሜ ክልል ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያንም ይህንን ለማስገንዘብ “በጉብዝናህ ወራት ፈጣሪህን አስብ” (መክ.፲፪፥፩) እያለች ዘወትር ታስተምራለች፡፡ ብዙ ወጣቶች ይህንኑ የጠቢቡን ምክር በመከተል የወጣትነት ዘመናቸውን ለቤተ ክርስቲያን በመስጠትና በሰ/ት/ቤቶች በጽዋና የጉዞ ማኅበራት በመሰባሰብ ለቤተ ክርስቲያን በጎ ስጦታ ሲያበረክቱ ይስተዋላል፡፡
ነገር ግን በዘመናችን አንዳንድ ወጣቶች በቀናዒነት ተነሣስተው የሚያደርጓቸው ድርጊቶች ከቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ(ዶግማ) እና ሥርዓት (ቀኖና) የሚጣረሱና አንዳንዴም ከጥቀማቸው ጉዳታቸው የሚያይል ይሆናል፡፡ ይህም የሚመጣው በዋነኛነት ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንን በሚገባ ተምሮና መርምሮ ካለማወቅ ነው፡፡ ስለዚህ አገልግሎታችን “ያላዋቂ ሳሚ …” እንደሚሉት ተረት እንዳይሆንብን ጥረታችንም እግዚአብሔርን የሚያስደስት ቤተ ክርስቲያንንም የሚጠቅምና ራስንም የሚያንጽ እንዲሆን አካሄዳችንን ሁሉ በሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን የተቃኘ ማድረግ ይገባናል፡፡ ወጣቶች ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንን በልማድና በወሬ ሳይሆን መጻሕፍትን በማንበብና መምህራንን በመጠየቅ ራሳቸውን ከጥፋት መታደግ ይኖርባቸዋል፡፡
ለ/ ከስሜታዊነት ወጥቶ በመንፈሳዊ ብስለት ማገልገል
ወጣትነት ስሜታዊነትና ችኩልነት የሚጨምርበት እርጋታና ማገናዘብ የማይታይበት ወቅት ነው፡፡ ብዙ የቤተ ክርስቲያን ወጣቶች ለአገልግሎት ወደ ቤተ ክርስቲያን ሲመጡ ከሚገጥማቸው ትልቅ ፈተና አንዱ ስሜትን ተቈጣጥሮ ራስን ገዝቶ ዝቅ ብሎ በትሕትናና በታዛዥነት ማገልገል አለመቻል ነው፡፡ መንፈሳዊ አገልግሎት ውጤታማ የሚሆነው መንፈሳዊ በሆነ አገልጋይ ሲከናወን ነው፡፡ መንፈሳዊ አገልጋይ ደግሞ አርምሞን፣ አስተዋይነትንና ታዛዥነትን ገንዘብ ያደረገ እንጂ በአጋጣሚዎች ሁሉ በስሜት ተገፋፍቶ ወደ ግጭትና ግርግር የሚያመራ አይደለም፡፡ ስለዚህ ወጣቶች በተለይ በዚህ በወርኃ ጥር በሚኖራቸው መንፈሳዊ ሱታፌ ቤተ ክርስቲያንን እንጥቀም:: እኛም ለበረከት እንብቃ ካሉ አገልግሎታቸውን በስሜትና በችኮላ ሳይሆን በመንፈሳዊ ብስለት፣ በትሕትናና በታዛዥነት የተዋጀ ሊያደርጉት ይገባል፡፡
ሐ/ ከመጥፎ የአቻ ግፊት መጠበቅ
የወጣትነት የዕድሜ ክልል የአቻ ግፊት የሚያይልበት፣ ከቤተሰብ የነበረን ቅርበትና ቁርኝት እየላላ ለዕድሜ አቻዎቻችን ያለን ቅርበት የሚጨምርበት ነው፡፡ በዚህ የዕድሜ ክልል ስንሆን ምሥጢሮቻችንና ወሳኝ የምንላቸውን ጉዳዮች ለቤተሰብ ከመንገርና ከማማከር ይልቅ ለዕድሜ ጓደኞቻችን ማጋራት ትልቅ ደስታ ይሰጠናል፡፡ ስለሆነም በዚህ ወቅት ወጣቶች በራሳቸው አስበውና አገናዝበው ከሚወስኗቸው ውሳኔዎች ይልቅ በጓደኞቻቸው ቀጥተኛና ተዘዋዋሪ ግፊት(ጫና) ተገፋፈተው የሚያሳልፏቸው ውሳኔዎች እጅግ ብዙ ናቸው፡፡ በዘመናችን የሀገራችን በርካታ ወጣቶች በዕድሜ እኩያቸው ግፊት ከቤተ ክርስቲያን እየሸሹ፣ ከመንፈሳዊነት እየወጡ ወደ ዝሙትና ሱሰኝነት ሲወሰዱ እንመለከታለን፡፡ በዚህ በወርኃ ጥር ከላይ በዘረዘርናቸው ነገሮች ምክንያት ወጣቶች ከቤተሰብ ተለይተው በጋራ ሆነው የሚዝናኑባቸውና ለኃጢአት የሚጋለጡባቸው አጋጣሚዎች የበዙ ናቸው፡፡
ወጣቶች በቅድሚያ አብረዋቸው የሚውሉ ጓደኞቻቸውን ከመንፈሳዊና ትምህርታዊ ዓላማቸው አንጻር ሊፈትሹና ሊመርጡ ይገባል፡፡ በቅዱስ መጽሐፍ በባልንጀራቸው ምክንያት የተጠቀሙ እንደተገለጹት ሁሉ በመጥፎ ባልንጀራቸው ምክንያት ወደ ክሕደትና ኃጢአት ያመሩ ሰዎች ጉዳይም በስፋት ተጠቅሶ እናገኛለን፡፡ ስለዚህ ወጣቶች ባልንጀራዬ ማነው? ብለው ራሳቸውን መጠየቅ ይገባቸዋል፡፡ በተለያዩ አጋጣሚዎች ጓደኞቻቸውን መምረጥ እንኳን ቢከብዳቸው መጥፎ የአቻ ግፊትን በመከላከል ለፈቃደ እግዚአብሔር እና ለሕይወት ግባቸው ቅድሚያ በመስጠት በንቃትና በቆራጥነት ለመጥፎ ተጽዕኖዎች አይሆንም እምቢ ማለትን ሊለማመዱ ይገባል፡፡
ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት በመዝሙሩ “ምስለ ጻድቅ ትጸድቅ ወምስለ ብእሲ ንጹሕ ንጹሐ ትከውን ወምስለ ጠዋይ ትጠዊ፤ ከጻድቅ ሰው ጋር ጻድቅ ትሆናለህ፤ ከቅን ሰው ጋርም ቅን ትሆናለህ፤ ከንጹሕ ሰው ጋር ንጹሕ ትሆናለህ፤ ከጠማማም ጋር ጠማማ ትሆናለህ፡፡” (መዝ፲፯፥፳፬) በማለት እንዳስረዳን ማንኛውም ሰው ውሎውን ካላስተካከለ አወዳደቁ የከፋ ይሆናልና ጓደኞቻችንን መምረጥ ያስፈልጋል፡፡ በጓደኛ ተጽዕኖ ሕይወታቸው የተበላሸባቸው በርካታ ምሳሌዎችን ከመጽሐፍ ቅዱስ መጥቀስ ይቻላል፡፡ ከነዚህም መካከል አምኖን ከኢዮናዳብ ጋር፣ ሶምሶን ከደሊላ ጋር ያደረጉት ጓደኝነት ሕይወታቸውን እንደጎዳው ተጠቃሽ ነው፡፡
መ/ ምን አለበት ከሚል አስተሳሰብ መጠንቀቅ
ሌላው ወጣቶች በወርኃ ጥር ፈታኝ የሆኑ ተግዳሮቶችን በድል ለመወጣትና ከውድቀት ለመዳን ሊያደርጉት የሚገባ የአስተሳሰብና የአመለካከት ለውጥ ማምጣት ነው፡፡ ብዙ ወጣቶች ወደ ጥፋት ጎዳና የሚመራቸው የውሳኔ አሰጣጥ ክህሎት ማነስ ወይም መዳከም ነው፡፡ ይህ ክህሎት ከአስተዳደጋችን፣ ከትምህርት ግብዓት ብሎም ከንባብ ሕይወታችን ጋር የተያያዘ ነው ፡፡ ከሁሉም በላይ ግን አስተሳሰባችንና አመለካከታችን በዚህ ጉዳይ ላይ ትልቅ አስተዋጽኦ አላቸው፡፡ በድኅረ-ሥልጣኔ ማኅበረሰብ አስተሳሰብ ላይ ጎልተው የሚታዩት ”ምን አለበት” ምን “ችግር አለው” እና “ልሞክረው” ዓይነት አመለካከቶች ውሳኔዎችን ከራሳችን ይልቅ ሌሎች ሰዎች በተጽዕኖ እንዲወስኑ ትልቅ መንገድ ከፋች ናቸው፡፡ እንደዚህ ዓይነት አመለካከቶች የአፍላ ወጣትነት ዕድሜም ላይ ያሉ የቤተ ክርስቲያን ልጆችን ወደ ጥፋትና ውድቀት ሲወስዱ ይስተዋላል፡፡ ስለዚህ ምን አለበት፣ ሞት አለበት ነውና ወጣቶች ራሳቸውን ከዚህ ዓይነት አመለካከት ሊጠብቁ ይገባል፡፡
በአጠቃላይ ወጣቶች በዚህ በወርኃ ጥር ራሳቸውን ለጽድቅና ለመንፈሳዊ በረከት የሚያበቁባቸው አጋጣሚዎች ብዙ ቢሆኑም ፈተናዎችም የሚበዙበት ወቅት ነው፡፡ ስለሆነም በዚህ ወቅት ወጣቶች በመንፈሳዊ ብስለትና በማስተዋል ከተጓዙ የወጣትነት ዘመናቸውን እንደ ዮሴፍና ሰማዕቱ ቅዱስ ጊዮርጊስ ለድል አክሊል ለመንግሥተ ሰማያት የሚያበቃ ማድረግ ይችላሉ፡፡ ነገር ግን በስሜትና በትዕቢት እንዲሁም ባለማስተዋል ከተጓዙ ወጣትነታቸው በሕይወታቸውን ለጉዳት አሳልፎ ይሰጣቸዋል፡፡ ወጣቶች ከእንደዚህ ዓይነት ጥፋት ይድኑ ዘንድም የቤተ ክርስቲያን አባቶች መምህራን የሰ/ት/ቤት አባላትና አመራሮች እንዲሁም ቤተሰብ ድርሻቸውን ሊወጡ ይገባል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ምንጭ ሐመር መጽሔት 26ኛ ዓመት ቁ.9 ጥር 2011 ዓ.ም.

በአፋን ኦሮሞ የተዘጋጁ ሦስት የኮርስ መጻሕፍት ታትመው በሥርጭት ላይ የሚገኙት

 

– Barattootni Yaa’iiwwan Mooraa Afaan Oromoon barattan Baga Gammaddan! Kitaaboleen koorsii sadii Afaan Oromootiin, adeemsa barnoota isa haaraatiin qophaa’anii isiniif dhiyaataniiru! Kanneen kaanis dhiyootti isin harka gahu!

 

በአፋን ኦሮሞ የምትማሩ የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች፡- እንኳን ደስ አላችሁ!

በአዲሱ ሥርዓተ ትምህርት መሠረት በአፋን ኦሮሞ የተዘጋጁ ሦስት የኮርስ መጻሕፍት ታትመው ቀርበውላችኋል! ሌሎቹም መጻሕፍት በቅርቡ ታተመው በእጃችሁ ይገባሉ!!!

የተሰጠህን አደራ ጠብቅ (፩ጢሞ. ፮:፳) (በእንተ ላ ሊበላ)

ብዙአየሁ ጀምበሬ
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ለሀገራችን ያበረከተችው አስተዋጽኦ በብዙ ዐውድ የሚገለጽ እና መጠነ ሰፊ ነው፡፡ ከእነዚህም መካከል በቋንቋ፤ በባሕል፤ በአለባበስ፤በሥነ ጽሑፍ፤ በኪነ ጥበብ፤ በኪነ ሕንፃ እና በቅርጻ ቅርጽ ዘርፍ የተደረጉት አስተዋጽዖዎች ተጠቃሽ ናቸው፡፡ ይህች ስንዱ የሆነች ቤተ ክርስቲያን ተፈጥሮአዊ የሆኑ የዕፀዋት ዝርያዎችን በአግባቡ በመጠበቅ እና በመንከባከብ የሀገር ሕልውናን በማስጠበቅ እና ተፈጥሮ ዑደቱ ሳይዛባ እንዲቀጥል በማድረግም እጅግ የጎላ አገልግሎቷን በማስመዝገብ ላይ ናት፡፡ ዝርያቸው ሊጠፉ የተቃረቡ የዕፀዋት ዓይነቶችን ጠብቃ ያቆየች የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ናት፡፡ በሥነ ጽሑፍ ዘርፍም ቢሆን ሀገራችን የራሷ ፊደል እንዲኖራት እና ለሥልጣኔ ጉልህ አስተዋጽዖ የሚያበረክቱ መጻሕፍት ባለቤት እንድትሆን ረድታለች፡፡

የንባብ ባሕልን ከሥር መሠረቱ በማጎልበት ለከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ምሳሌ ሊሆን የሚችል የአብነት ትምህርት ቤቶችን በማቋቋም አያሌ ምሁራን እንዲፈሩበት ጉልህ ሥራን ሠርታለች፡፡ በዜማውም ዘርፍ የዜማ ሥርዓትን ለዓለም በቀዳሚነት በማስተዋወቅ፣ ሰማያዊ ሥርዓት ያለውን ዜማ በሊቁ ቅዱስ ያሬድ አማካኝነት አበርክታለች፡፡ በኪነ ሕንፃ ዘርፍ ደግሞ በዓለማችን ታሪክ በየትኛውም ክፍላተ አህጉራት የማይገኙ እና ደግመው መሠራት ያልተቻሉ ልዩ ልዩ የኪነ ሕንፃ ጥበቦችን በውስጧ የያዘች፤ ያስተዋወቀች እና ጠብቃ ያቆየች ናት፡፡
ለምሳሌ ያህል የአክሱም ሐውልት፤ የላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት እና የንጉሥ ፋሲለደስን ግንብ መጥቀስ በቂ ነው፡፡ ይህች ቤተ ክርስቲያን እነዚህን ቅርሶች ለሀገራችን እና ለመላው ዓለም ብታበረክትም ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ ለእነዚህ ቅርሶች ተገቢው ጥበቃ እና እንክብካቤ ባለመደረጉ የተነሳ ለከፍተኛ ጉዳት እየተጋለጡ ይገኛሉ፡፡ እንዴት እንደተሠሩ መረዳት እንኳን ግራ እስኪገባን ድረስ አስተውለንና የአሠራር ጥበባቸውን አድንቀን ሳናበቃ በቂ ጥበቃ እና እንክብካቤ ሳይደረግላቸው በመቅረቱ አብዛኞቹ ቅርሶች ለአደጋ እንዲጋለጡ እና ሥጋት ውስጥ እንዲገቡ ሆነዋል፡፡ ይህ ደግሞ የታሪክ ተወቃሽ እንድንሆን ያደርገናል፡፡ ከእነዚህ በአሳሳቢ ሁኔታ ውስጥ ካሉት ቅርሶች መካከል በአሁኑ ሰዓት በከፋና እጅግ በአሳሳቢ በሆነ ሁኔታ ውስጥ የሚገኙት የላልይበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት ናቸው፡፡

የላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት የተፈለፈሉት በ፲፪ኛው መቶ ክፍለ ዘመን በንጉሥ ላላሊበላ አማካኝነት ነው፡፡ ቅዱስ ላሊበላ ታኅሣሥ ፳፱ ቀን በ፲፪ ኛውመቶ ክፍለ ዘመን መግቢያ ከእናቱ ኪርወርና እና ከአባቱ ከዛን ሥዩም በላስታ ሮሐ ቤተ መንግሥት ዋሻ እልፍኝ ውስጥ ተወልዷል፡፡ በተወለደ ጊዜም በንብ ስለተከበበ እናቱ ማር ይበላል “ላል ይበላል” ብላ ስም መጠሪያ ይሆነው ዘንድ አውጥታለታለች፡፡ ማር ከፍተኛ ደረጃ ያለው ተወዳጅ ምግብ ስለሆነ መልካም፤ ስመ ጥር፤ ታላቅ ንጉሥ ይሆናል ስትል ላልይበላ ብላዋለች፡፡

በሌላ መልኩም “ላልይበላ ብሂል ንህብ አእመረ ጸጋሁ ብሂል፣ ላልይበላ ማለት ንብ ጸጋውን (ገዢውን) ዐወቀ” ማለት ነው፡፡ ቅዱስ ላልይበላ የብሉያትን እና የሐዲሳትን የትርጓሜ መጻሕፍት ጠንቅቆ የተማረ ነው፡፡ ውቅር አብያተ ክርስቲያናቱን ከአንድ ወጥ ዓለት በመፈልፈል ያነጸው ንጉሡ ከዐሥራ አንዱ የዛጉዌ ሥርወ መንግሥት ነገሥታት መካከል አንዱ ሲሆን በኢትዮጵያ ለ፵ ዓመታት ያህል ነግሦ እንደነበር የታሪክ መዛግብት ያስረዳሉ፡፡(ምንጭ፡ ገድለ ቅዱስ ላልይበላ ሰኔ 2003 ዓ.ም ገጽ13)፡፡የቅዱስ ላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት በቊጥር ዐሥራ አንድ ሲሆኑ፣እነርሱም፡- ቤተ-ማርያም፤ ቤተ-መድኃኔ ዓለም፤ቤተ-ደናግል፤ ቤተ-መስቀል፤ ቤተ-ደብረሲና፤ቤተ-ጎልጎታ፤ ቤተ-አማኑኤል፤ቤተ-አባሊባኖስ፤ቤተ-መርቆሬዎስ፤  ቤተ-ገብርኤል ወሩፋኤል፤ ቤተ-ጊዮርጊስ የተሰኙ ናቸው፡፡
ቤተ-ደብረሲና በመባል የሚጠራው ፍልፍል ቤተ ክርስቲያን ቤተ-ሚካኤል በመባልም ጭምር ይታወቃል፡፡ ከእነዚህ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት መካከልም በቅድሚያ የታነጸው ቤተ-ማርያም የተሰኘው ሲሆን በወርኃ ታኅሣሥ በ፳፱ኛው ቀን የጌታችን የአምላካችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ የልደት በዓል እና የቅዱስ ላሊበላ የልደት በዓል “ቤዛ ኲሉ” የሚዘመርበት ቤተ መቅደስ ነው፡፡ ከእነዚህ ፍልፍል አብያተ ክርስቲያናት መካከል በመጠን ከሁሉም የሚልቀው እና ግዙፍ የሆነው ቤተ-መድኃኔዓለም ሲሆን በዚሁ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ”አፍሮ አይገባ” በመባል የሚታወቀው የመስቀል ይገኛል፡፡
የላሊበላ አብያተ ክርስቲያናት ሲነሱ በሁላችን አእምሮ የሚታወስና ትዝ የሚለን ከላይ ሲታይ በመስቀል ቅርጽ የታነጸው እና ከሌሎች በተለየ የኪነ ሕንፃ ጥበብ የተወቀረው ቤተ-ጊዮርጊስ ነው፡፡ የላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት ተሠርተው ለመጠናቀቅ ፳፫ ዓመታትን ፈጅተዋል፡፡ ውቅር አብያተ ክርስቲያናቱ በዓለም ላይ በሰው ልጆች ታሪክ ውስጥ ከተገለጡት አስደናቂ የኪነ ሕንፃ ጥበቦች መካከል ወደር እና አቻ የማይገኝላቸው ናቸው፡፡
የአብያተ ክርስቲያናቱ የኪነ ሕንፃ ንድፍ (Design) እና ሥነ ውበት (Aesthetics) በአስደናቂ ሁኔታ ተጣምሮ የተዋሐደበት ልዩ የመንፈሳዊ ምሕንድስና አሻራም የታየበት ነው፡፡እስካሁን ባለው የኪነ ሕንፃ እና የምሕንድስና ታሪክ ውስጥ እንደ ላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት ዓይነት የረቀቀ ጥበብ የታየበት ሥራ በየትኛውም የዓለም ክፍል ላይ እንዳልተሠራ መዛግብት ያስረዳሉ፡፡ ፡፡ የአሠራሩ መንገድ ከታች ከመሠረት ሳይሆን ከላይ ከጣራ መጀመሩ በዋነኛነት ልዩ ያደርገዋል፡፡ ከዓለት መፈልፈላቸው እና በሥራቸው የውኃ ማጠራቀሚያ ቋት መያዛቸውም በራሱ ለየት ያደርጋቸዋል፡፡ ንጉሥ ላሊበላ ይህንን አስደናቂ የኪነ ሕንፃ ሥራ ሲሠራ ከፈጣሪው ከልዑል እግዚአብሔር ባገኘው መንፈሳዊ ጥበብ እንደሆነ የታሪክ ድርሳናት ይገልጣሉ፡፡
እግዚአብሔር አምላክ ለመረጣቸው እና አካሄዳቸውን ከእርሱ ጋር ላደረጉ መልካም ሰዎች ጥበብን ያድላል፤ ለዚህም የባስልኤል እና የኤልያብን ታሪክ ከመጽሐፍ ቅዱስ ማስታወስ ያሻል፡፡ “ለመቅደስም ማገልገያ ሥራ ሁሉ ያደርጉ ዘንድ እንዲያውቁ እግዚአብሔር ጥበብንና ማስተዋልን የሰጣቸው ባስልኤልና ኤልያብ በልባቸው ጥበበኛዎችም ሆኑ፣ እግዚአብሔር እንዳዘዘው ነገር ሁሉ አደረጉ፡፡ ሙሴም ባስልኤልና ኤልያብን እግዚአብሔርም በልቡ ጥበብን ያደረገለትን በልብ ጥበበኛ ሰው ሁሉ ሥራውንም ለመሥራት ይቀርብ ዘንድ ልቡ ያስነሣውን ሁሉ ጠራቸው፡፡ (ዘጸ.፴፮፡፩-፩) እንዲል፡፡
የውቅር አብያተ ክርስቲያናቱ መሠረታዊ የጂኦሜትሪያዊ ልኬት(Geometric proportion) የንድፍ ሥርዓትን የጠበቁ ናቸው፡፡ በሥጋዊ ምርምር ሊደረስባቸው አይችልም፡፡ለዚህም ነው ልዩ የከበረና ዘመን የማይሽረው የኪነ ሕንፃ ቅርስ መሆን የቻለው፡፡ ለዚህም ነው የዓለም ዜጎች ያከበሩት እና በየጊዜው ለመጎብኘት ወደ ሀገራችን የሚመጡት፡፡ ስለ ላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት አስደናቂነት እና ዘመን የማይሽራቸው የታሪክ አካላት እንደሆኑ በተለያዩ የሀገር ውስጥ እና የውጭ ሀገር ምሁራን ዘንድ ጥናት ተደርጓል፤ በግልጽም ተመስክሯል፡፡ ከእነዚህም መካከል ጥቂቶቹን እናንሳ ከ፲፭፻፲፪ ዓ.ም እስከ ፲፭፻፲፰ ዓ.ም ድረስ ወደ ኢትዮጵያ በመምጣት አብያተ ክርስቲያናቱን የጎበኘው የፖርቹጋሉ ተወላጅ ፍራንሲስኮ አልቫሬዝ ስለ ላሊበላ ውቅር አቢያተ ክርስቲያናት ድንቅ ምስክርነት ሰጥቷል፡፡ ይህ ሰው የላሊበላን ውቅር አብያተ ክርስቲያናት የጎበኘ የመጀመሪያው አውሮፓዊ ዜጋ ሲሆን ጎብኝቶ ካጠናቀቀ በኋላም ስለ አብያተ ክርስቲያናቱ አስደናቂነት እጅግ ብዙ ጽፏል፡፡
በጽሑፉ ማጠናቀቂያ ላይም እንዲህ ብሏል “ስለ ላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት ሥራዎች ብዙ ብጽፍም የሚያምነኝ ሰው መኖሩ በጣም ያስጨንቀኛል፤ ያሳስበኛልም እስካሁን ያልኩትም እንኳ ቢሆን ውሸት ነው የሚሉኝ፡፡ ነገር ግን የጻፍኩት በሙሉ እውነት ለመሆኑ በኃያሉ እግዚአብሔር ስም እምላለሁ፡፡ እንዲያውም ከዚህ በላይ ማለት ይቻል ነበር፡፡ ሆኖም ስሜ በቀጣፊነት እንዳይነሳ እሰጋለሁ … ይህን የሚመስል በዓለም እንደማይገኝ እገልጻለሁ፡፡” በማለት ድንቅ ምስክርነቱን በዚያን ዘመን ገልጿል፡፡ (ምንጭ፡ገድለ ቅዱስ ላሊበላ ሰኔ 2003 ዓ.ም ገጽ 15)፡፡
ከዚህም በተጨማሪ አንድርዜይ በርትኒስኪ እና ዮዓና ማንቴል ኒየችኮ የተባሉት የታሪክ ጸሐፍት የኢትዮጵያ ታሪክ በሚለው መጽሐፋቸው ላይ “ንጉሡ በስሙ በሚጠራው በላሊበላ ከተማ እስከ ዛሬም ድረስ ዝናቸው ያልደበዘዘውን ከዓለት ተፈልፍለው የታነጹ አብያተ ክርስቲያናት መሥራቱ ታላቅ የታሪክ ባለውለታ አድርጎታል” በማለት ገልጸውታል፡፡ (ምንጭ፡-የኢትዮጵያ ታሪክ አንድርዜይ በርትኒስኪ እና ዮዓና ማንቴል ኒየችኮ ትርጉም አለማየሁ አበበ ገጽ 32፤2003 ዓ.ም እትም)፡፡
ዓለም የተደነቀባቸው እና በእጅጉ ያወደሳቸው የላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት በ፲፱፸፻፱ ዓ.ም በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የትምህርት፤ የሳይንስ እና የባሕል ድርጅት (UNSCO) አማካኝነት በዓለም ቅርስነት ተመዝግበው ይገኛሉ፡፡ የላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት ለቤተ ክርስቲያን ከሚሰጡት መንፈሳዊ አገልግሎት ባሻገር ለሀገራችን ኢትዮጵያም ባለውለታ ናቸው፡፡ ይህም ሲባል ከተለያዩ የዓለማችን ክፍሎች ቅርሶቹን ለመጎብኘት ከሚመጡ የውጭ ሀገራት ጎብኝዎች አማካኝነት በየዓመቱ ከፍተኛ ገቢ በቱሪዝም ዘርፍ ለመንግሥት እንዲገባ ማስቻሉ ነው፡፡ ከዚህም በላይ ደግሞ የሀገራችን አባቶች ዓለምን የሚያስደንቅ ረቂቅ የኪነ ሕንፃ አሻራ አስቀምጠውልን ማለፋቸው አስተዋይ ትውልዶች ከሆን የእነርሱን ፈለግ በመከተል በሥልጣኔ እድገት ከፍተኛ ማማ ላይ እንደምንቀመጥ አመላካች ነው፡፡

ለሀገር ውለታ የዋሉ እነዚህ ታሪካዊ ቅርሶች ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ ግን ከፍተኛ የሆነ አደጋ ተጋርጦባቸው ይገኛል፡፡ ይኸውም በዕድሜ መግፋት እና ለቅርሶቹ ጥበቃ ተብለው በተሠሩት የብረት ጣሪያዎች(Shade structures) ምክንያት አብያተ ክርስቲያናቱ ላይ በግርግዳቸው በኩል የመሰንጠቅ አደጋ እየተስተዋለባቸው ይገኛል፡፡ ችግሩ በዚሁ ከቀጠለ እና አፋጣኝ እርምጃ መውሰድ ካልተቻለ ጉዳቱ አመዛኝ ሆኖ የቅርሶቹ ሕልውና ጥያቄ ውስጥ ሊገባ ይችላል፡፡ ለእኛ ለዚህ ትውልድ ሰዎች ደግሞ ከአባቶች በአደራ የተላለፉትን ዘመን የማይሽራቸውን ውድ ቅርሶች በአግባቡ ባለመጠበቅ የታሪክ ተወቃሽ ለመሆን እንበቃለን፡፡
ለመሆኑ ንጉሥ ላሊበላ ምን ይለን ይሆን? አባቶቻችንስ እንዴት ይታዘቡን ይሆን? እነዚያን የመሰሉ አይደለም ደግመን ለመሥራት ቀርቶ እንዴትስ እንኳን እንደተሠሩ ተመራምረን መድረስ ያልቻልንባቸውን ድንቅ የታሪክ አሻራዎች ሠርተው አስረክበውን እኛ እንዴት በኃላፊነት መጠበቅ እና በአግባቡ መንከባከብ ያቅተን? በሀገራችን የሚገኙ በኪነ ሕንፃውም በምሕንድስናውም ዘርፍ አንጋፋ ልምድ እና ዕውቀት ያላቸው የቤተ ክርስቲያን ብሎም የሀገሪቱ ምሁራንስ በዚህ ጉዳይ ለምን በአስቸኳይ መፍትሔ መስጠት አልቻሉም?
እንደ ሀገር የቤተ ክርስቲያን የሆኑትን ብቻ ሳይሆን በሀገሪቱ የሚገኙ ማንኛውም ሰው ሰራሽ እና ተፈጥሮአዊ ቅርሶች ላይ አደጋ ሲጋረጥ “የእከሌ ኃላፊነት ነው፣ እኔን አይመለከተኝም” በማለት ራስን ገለልተኛ ከማድረግ ይልቅ በመወያየት እና አግባብነት ያላቸውን ምክክሮች በማድረግ መፍትሔ ማምጣት ግድ ይለናል፡፡ ይህ ካልሆነ ግን “እነርሱም አልሠሩትም፤ እነርሱም አልጠበቁትም” ተብለን የታሪክ ተወቃሽ ሆነን እናልፋለን፡፡
የቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት፤ የሀገሪቱ የባሕል እና ቱሪዝም ኃላፊዎች፤ የኪነ ሕንፃ እና ምሕንድስና ምሁራን፤ በየሥልጣን ተዋረዱ የሚገኙ የመንግሥት ባለድርሻ አካላት ብሎም እያንዳንዱ ምእመን ችግሩ ይመለከተኛል በማለት አስቸኳይ እና ቀጠሮ የማይሰጠው መፍትሔ ማምጣት አስፈላጊ ነው፡፡ ከዚህም በላይ እያንዳንዱ ምእመን ፈጣሪ ሀገራችንን፤ ሕዝቦቿን እና ቅርሶቻችንን እንዲጠብቅልን ዘወትር በጸሎት መጠየቅም ይጠበቅበታል፡፡
ለወደፊቱ ተመሳሳይ ችግር በቅርሶቻችን ላይ እንዳያጋጥም እና ቢያጋጥም እንኳን ተገቢውን መፍትሔ ለመስጠት ያስችለን ዘንድ በኪነ ሕንፃ እና በምሕንድስና ላይ የተሰማሩ የቤተ ክርስቲያን ልጆችን በማስተባበር ሥርዓትን እና ሥነ መዋቅርን የተከተለ የቤተ ክርስቲያን ቴክኒካዊ ክፍል መዘርጋት እና ከባለድርሻ አካላት ጋር አብሮ መስራት ያስፈልጋል፡፡ የሲቪል መሀንዲሶች(Civil and Structural Engineers )፣ የኪነ ሕንፃ እና የከተማ ልማት ባለሙያዎች(Architects Urban planners and Architectural Historians)፤ የኮንስትራክሽን ግንባታ ባለሙያዎች (Construction TechnologyManagement)፤ የመካኒካል መሐንዲሶች(Mechanical Engineers)፤ የአፈር እና የድንጋይ ምርምር ባለሞያዎች(Geologists and Geo Tech Engineers)፤የቅርስን እና አካባቢ ጥበቃ ባለሞያዎች(Culture and Heritage professionals)፤ የሥነ ሰብእ ተመራማሪዎች(Anthropologists)፤ የታሪክ ምሁራን (Historian) እና የቤተ ክርስቲያን አባቶችን ያሰባሰበ ቡድን በማቋቋም ችግሩ የተከሰተበትን ምክንያት በማጥናት እና በምን መልኩ ጥገና እና ዕድሳት ይደረግለት የሚለውን ታሳቢ በማድረግ መፍትሔ ሊሰጠው ይገባል፡፡

ይህ የሞያተኞች ቡድን ወደፊትም ተመሳሳይ ችግር በቤተ ክርስቲያን እና በሀገር ቅርሶች ላይ ሲጋረጥ መፍትሔ ለማምጣት የሚሠራ የቤተ ክርስቲያን የአስተዳድር ወይም የቴክኒክ አካል ተደርጎ ሊመሠረት ያስፈልጋል፡፡ እንዲህ ባለመሥራታችን ተመሳሳይ ችግሮች በተከሰቱ ቊጥር የመፍትሔ ያለህ እያልን መጮህ እና የቅርሶቹን የእንግልት እና የአደጋ ሥጋት ጊዜ ማስፋት እና እስከወዲያኛውም ድረስ ላናገኛቸው እና ላይተኩ ሆነው እንዲጠፉ እናደርጋለን፡፡ ከዚህ በፊት ከኢትዮጵያ በጣሊያን አማካኝነት ተወስዶ የነበረውን የአክሱም ሐውልት ለማስመለስ የተደረገውን ጥረት ለአብነት እንደ ጥሩ ተሞክሮ አድርጎ ማንሳት ያስፈልጋል፡፡ በጊዜው በሁሉም ባለድርሻ አካላት የተደረገውን ዓይነት ርብርብ አሁን ላይም በመድገም ቅርሶቻችንን መታደግ ያስፈልጋል፡፡
በሌሎች ሀገሮች የሚገኙ የሃይማኖት ተቋማት የቅርስ ጥበቃ እና እንክብካቤ የሚያደርጉ ከዲዛይን፤ ምሕንድስና እና ግንባታ ዘርፎች የተወጣጡ አባላትን ያካተቱ የቴክኒክ ክፍሎችን በማዋቀር የቅርስ ጥበቃ እና እድሳት (Conservation and Restoration) እንደ አስፈላጊነቱ ያደርጋሉ፡፡ የእኛም ሀገር የሃይማኖት ተቋማት ከነዚህ ሀገራት አብያተ ክርስቲያናት እና ሌሎች እምነት ተቋማት ተሞክሮ በመውሰድ በቅርሶቻችን ላይ የተጋረጠውን አደጋ መቀነስ ብሎም ማስቀረት ያስፈልጋል፡፡ አባቶቻችን የሠሩልንን እና ያስረከቡንን የታሪክ ቅርሶች በአግባቡ ተቀብለን እና ጠብቀን ለትውልድ ማስተላለፍ እና ቅብብሎሹ እንዲቀጥል ማድረጉ ከእያንዳንዳችን ይጠበቃል፡፡ በቤተ ክርስቲያን የአስተዳድር ሥነ መዋቅርም ቢሆን እንደዚህ ዓይነት ችግሮች ሲከሰቱ ከመንግሥት ባለድርሻ አካላት ጋር በመነጋገር መፍትሔ ማምጣት ጊዜ የሚሰጠው ጉዳይ መሆን የለበትም፡፡

               ወስብሐት ለእግዚአብሔር
ምንጭ፤ሐመር መጽሔት 26ኛ ዓመት ቁ7 ኀዳር2011 ዓ.ም

ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ የተሰጠ መግለጫ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ በዓመት ሁለት ጊዜያት እንዲሆን በፍትሕ መንፈሳዊ አንቀጽ 5 ቁጥር 164 በተደነገገው መሠረት ምልዓተ ጉባኤው የመክፈቻው ሥርዓተ ጸሎት ከተፈጸመበት ከጥቅምት 11 ቀን 2011 ዓ.ም ጀምሮ እስከ ጥቅምት 21 ቀን 2011 ዓ.ም ድረስ የተለመደውን ዓመታዊ መደበኛ ስብሰባ ሲያካሒድ ሰንብቶ ማህበራዊና መንፈሳዊ ለቤተ ክርስቲያናችንና ለሀገራችን የሚበጁ ውሳኔዎችን አሳልፎአል ፡፡
በዚሁ መሠረት፤
1. ለቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ በቀረበው አጀንዳ ተራ ቁጥር አንድ ላይ በተገለፀው የጉባኤ መክፈቻ ንግግር የተመዘገበው ፍሬ ሐሳብ የበጀት ዓመቱ መመሪያ ሆኖ ያገልግል ዘንድ ምልዓተ ጉባኤው ተቀብሎታል፤
2. የብፁዓን አባቶች የሥራ ምደባና ዝውውር በማስፈለጉ ቅዱስ ሲኖዶስ ያለውን ሁኔታ ከመረመረ በኋላ ዝውውሩን አከናውኗል፤ አዲስ የሥራ ምደባም ተካሒዷል ፡፡
3. በሀገራችን ኢትዮጵያ በአንዳንድ ክልሎችና ዞኖች ተከስቶ የነበረው ሕልፈተ ሕይወት፣ የአብያተ ክርስቲያናት መቃጠልና የንብረት መውደም የዜጎች መፈናቀል ይገታ ዘንድ በመደጋገም የተላለፈው ጥያቄ በኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዲሞክራሲያዊ ሪፑብሊክ መንግሥት በኩል ተቀባይነትን ያገኘ ቢሆንም፤ አሁንም በሀገሪቱ አንዳንድ ችግሮች እንዳሉ እየተሰማ ነው ፡፡
ስለዚህ ከየአቅጣጫው እየተሰማ ላለው ችግር አስቸኳይ መፍትሔ ተፈልጎ እንዲገታ ካልተደረገ እየሰፋና እያደገ ሊሔድ ስለሚችል መንግሥት ከአቅም በላይ እየሆነ ለሚታየው ችግር አጽንዖት ሰጥቶ አስፈላጊውን ሕጋዊ መፍትሔ እንዲገኝ በማድረግ ተገቢውን እንዲፈጸም የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ በድጋሚ ያሳስባል ፡፡
4. የዘንድሮውን የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ልዩ ታሪካዊ ጉባኤ ከሚያደርጉት መካከል፣ የብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ ዐራተኛ ፓትርያርክ፣ አብረዋቸው ከነበሩት አባቶች ጋር ወደ እናት ሀገራቸው ኢትዮጵያ የመመለሳቸው ጉዳይ አንዱ እንደሆነ አያጠያይቅም፤
5. ለኢትዮጵያ ምእመናን ከኤርትራ ምእመናን፤ ለኤርትራ ቤተ ክርስቲያን ከኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን፣ ለኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያንም የኤርትራ ቤተ ክርስቲያን የመፈቃቀርና የአንድነት እንዲሁም የበለጠ የክፉ ቀን ደራሽ ይኖራል ተብሎ አይገመትም ፡፡
ስለዚህ በሁሉም መንፈሳዊና ማኅበራዊ አገልግሎት ዘርፍ ተቀራርቦ እየሠሩ መረዳዳት ይቻል ዘንድ ከወዲሁ ሁኔታዎችን የሚያመቻች የጋራ ኮሚቴ እንዲቋቋም ምልዓተ ጉባኤው ተስማምቷል ፡፡
6. በቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ የጸደቀው ሠላሳ ሰባተኛው የመንበረ ፓትርያርክ አጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ የጋራ መግለጫ በአፈጻጸም ዙሪያ የሚከሰት ችግር ካጋጠመው በቋሚ ሲኖዶስ እየተመረመረ ለውጤት ይበቃ ዘንድ ቅዱስ ሲኖዶስ ተስማምቶ መመሪያ አስተላልፏል፤
7. በአሁኑ ጊዜ በሀገራችን ኢትዮጵያ በአንዳንድ አካባቢዎች እየታየ ያለው የሰላም እጦት ችግር በቀላሉ የሚገታ ሆኖ ካልተገኘ ወደፊት አስቸጋሪ ሁኔታዎች ሊከሰቱ ይችላሉ የሚል ሥጋት አለ፤
ስለዚህ እንደ ቤተ ክርስቲያናችን ቀኖናዊ ሥርዓት የወንጌል ስምሪት ተዘጋጅቶ ከመቼውም ጊዜ በበለጠ ትምህርተ ወንጌል ተጠናክሮ እንዲሰጥ ሆኖ ከዚህም ጋር ከኅዳር 1 እስከ ኅዳር 7 ቀን 2011 ዓ.ም. ድረስ በመላው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አብያተ ክርስቲያናት ጸሎተ ምሕላ እንዲደረግ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ መመሪያውን አስተላልፎአል፤
8. በተቀረፀው አጀንዳ መሠረት አቤቱታ የቀረበባቸውን አህጉረ ስብከቶች በተመለከተ መርምሮና አጣርቶ መፍትሔን የሰጠ ሲሆን በአንጻሩ ከቅን አስተዳደር የሚጠበቅ ድርሻ ስለሆነ አስተዳደራዊ ችግር ያጋጠማቸው አህጉረ ስብከት ተመርምረው ውጤታቸው ተፋጥኖ ይቀርብ ዘንድ ቅዱስ ሲኖዶስ መመሪያን ሰጥቷል ፡፡
9. በበጀትና ሒሳብ መምሪያ በኩል የቀረበው የዘመኑ ገቢና ወጭ ሒሳብ ሪፖርት ከተሰማ በኋላ ገቢው በትክክል እንዲመዘገብ ሆኖ፤ የወጭው አርእስት ተጠብቆ በበጀት ዓመቱ እንዲሠራበት ቅዱስ ሲኖዶስ መመሪያን ሰጥቷል፡፡
10. በጥንታዊት ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያናችን በመንፈሳዊውም ሆነ በማህበራዊው ረገድ ከፍተኛ ሥራ መሠራቱን ቅዱስ ሲኖዶስ ገምግሟል፡፡ በቀጣይም የቤተ ክርስቲያኒቱን ተልዕኮ ለማስፋት በቤተ ክርስቲያኒቱ ከላይ እስከታች የሚተገበር የቤተ ክርስቲያን ሁለንተናዊ ችግርና መሪ እቅድ ተዘጋጅቶ የቀረበ በመሆኑ ለዚሁ ተግባር በተከፈተው ጽ/ቤት ሥራው እንዲቀጥል፣
በውጭ አገር ለምትገኘውም ቤተ ክርስቲያናችን የየአገሮቹን ሕገ መንግሥት ባገናዘበ መልኩ ቃለ ዓዋዲ እንዲዘጋጅና ሁሉም አብያተ ክርስቲያናት በመዋቅራዊ አስተዳደር እንዲመራ ተወስኖአል፡፡
11. አሁን በቤተ ክርስቲያናችን ቅዱስ ሲኖዶስ መካከል የተፈጠረው አንድነት ለቀጣይ መንፈሳዊና ማህበራዊ ሥራችን መቃናት በር ከፋች በመሆኑ ከአሁን በኋላ በአገር ውስጥም ሆነ በውጭው ዓለም ያለችው ቤተ ክርስቲያን በአንዲት ቀኖናዊት ቤተ ክርስቲያን በማዕከል እንድትመራ ወስኗል፡፡
12. ከሐምሌ ወር በዋሽንግተን ዱሲ የሁለቱ ሲኖዶስ ልዑካን የስምምነቱን ሠነድ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ተቀበሎ በማጽደቅ በሠነድነት እንዲቀመጥ ወስኗል፡፡
13. በቅድስት ሀገር ኢየሩሳሌም በዴር ሡልጣን ገዳማችን ይዞታ ላይ እየታየ ያለው ችግር ከጊዜ ወደጊዜ እየጨመረ ከመሔዱ የተነሣ ችግሩ ይፈታ ዘንድ ቅዱስ ሲኖዶስ በጽሑፍም ሆነ በቃል ለሚመለከተው ሁሉ በአካል ቀርቦ ከማመልከት የተገታበት ጊዜ እንደሌለ ይታወቃል፤
ታሪካዊ እውነትን ለመሻር በማይገባ ሁኔታ የኮፕቲክ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን በሌላት ርስትና መብት የዴርሡልጣን ገዳማችን ባለቤትነታችንን ለማሳጣት ብዙ የፈጠራ ወሬዎችን በመንዛት የተሰማሩት ግብጻውያን ኮፕቲኮች ሊያውቁት የሚገባ ትልቁ ጉዳይ በማን ርስት ማን ያዝዛል? ኢትዮጵያውያን ለዘመናት ሕይወታቸውን ሳይቀር መስዋዕት በማድረግ ሃይማኖታቸውንና ጥንታዊ ታሪካቸውን ጠብቀው ለእኛ አስረክበውናል፤ እኛም ጠብቀን ለትውልዱ የማስረከብ ኃላፊነታችንን እንወጣለን፡፡
የግብጽ ኮፕቲክ ኦርቶዶክስ በይዞታችን ላይ አግባብነት የሌለው ሥራን የማደናቀፍና በታሪክም ሆነ በማንኛውም የሠነድ መረጃ የሌለው የባለቤትነት ጥያቄ በማንሳት እየተፈጠረ ያለውን አላስፈላጊ ሁከትና ብጥብጥ ማቆም አለባቸው፤ ዴርሡልጣን ትናትም ዛሬም ነገም የኢትዮጵያ ገዳም ነው፡፡
ዳሩ ግን መፍትሔውን ከማስገኘት ይልቅ እየደረሰ ያለው ተፅዕኖ እየሰፋና እየከበደ መጥቶ በአሁኑ ወቅት ገዳሙን በሚጠብቁና በሚቆጣጠሩ መነኮሳት ላይ በኮፕቲክ ቤተ ክርስቲያን አማካኝነት ያልተጠበቀ ከፍተኛ ችግር እየደረሰ ስለሆነ የችግሩን አስገዳጅነት አስመልክቶ የኢትዮጵያ መንግሥት የጉዳዩ ባለቤት እንደመሆኑ አስፈላጊውን መፍትሔ እንዲያስገኝልን እንጠይቃለን፡፡
14. የቦታቸው ታላቅነትና የታሪካቸው ስፋት ዓለም አቀፍ ዕውቅናን ባስገኘላቸው በርእሰ አድባራት ወገዳማት አክሱም ጽዮን ቤተ ክርስቲያን እየተገነባ ላለው ሙዝየምና፣ የመሰነጣጠቅ አደጋ ለሚታይበት ለቅዱስ ላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት ለጥገናና ለግንባታ አገልግሎት የሚውል ገንዘብ ተፈቅዶዋል፤
በዚሁ መሠረት፤
1. ለርእሰ አድባራት ወገዳማት አክሱም ጽዮን ቤተ ክርስቲያን ቤተ መጻሕፍት ወመዘክር ሥራ ማከናወኛ ብር 20,000,000.00 /ሃያ ሚሊዮን ብር/
2. ለቅዱስ ላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት ማስጠገኛ፤
– ብር 20,000,000.00 /ሃያ ሚሊዮን ብር/ ከመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት ወጭ ሆኖ እንዲሰጥ ተወስኗል፤
15. አንዳንድ ግለሰዎች በግልና በቡድን በመደራጀት የቤተ ክርስቲያኗ መብትና ቀኖና እየተጋፉ መሆናቸውን ከቀረበው ሪፖርት ጉባኤው ተገንዝቧል፡፡
ስለዚህ መንግሥት በዚህ ተግባር ላይ የተሠማሩትን የሕግ ከለላ እንዲያደርግ እንጠይቃለን፡፡
ቅዱስ ሲኖዶስ ከዚህ በላይ በተጠቀሱትና በሌሎችም ዓበይት ጉዳዮች ላይ ለ11 ቀናት ያህል በአገር አቀፍና በዓለም አቀፍ ጉዳዮች በስፋትና በጥልቀት ሲወያይ ሰንብቶ ስብሰባውን በጸሎት አጠናቋል
ወስብሐት ለእግዚአብሔር አሜን
አባ ማትያስ ቀዳማዊ
ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ
ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት
አዲስ አበባ፣ ኢትዮጵያ
ጥቅምት 21 ቀን 2011 ዓ.ም.

“መከራ ልትቀበሉ እንጂ በስሙ ልታምኑ ብቻ አልተጠራችሁም” (ፊል. ፩፥፳፱)

 

ዘመናችን መረጃ በፍጥነት የሚለዋወጥበት፣ ስላሙ ሲደፈርስ ደቂቃ የማይፈጅበት እየሆነ መጥቷል፡፡ ሰዎች ሞትን ለመሸሽ የማያደርጉት ጥረት የለም፡፡ ኃያላን ሰማይ ጠቀስ ፎቆች፣ የኤሌክትሪክ አጥር፣ የድኅንነት ካሜራ እያዘጋጁ ወንጀልንና ወንጀለኞችን ለመቆጣጠር ቢሞክሩም አልተሳካላቸውም፡፡ መንገዳቸው ሥጋዊ ፍላጎትን የተከተለ በመሆኑ መፍትሔ ማሰገኘት አልቻለም፡፡ ችግሩ የሚፈታው ሁልጊዜ ችግርን ወደ ሌላ በመጠቆም አለመሆኑን መረዳት ይገባል፡፡

ምዕራባውያን የአዳጊ ሀገሮችን ቅርስና መዋዕለ ንዋይ እየዘረፉ ወደ ሀገራቸው ሲወሰዱ ኖረዋል፡፡ አሁን ደግሞ እነሱው ባሳዩዋቸው መንገድ ሌሎች ሀብታሞች የሰበሰቡትን እንዳይበሉት እያደረጉዋቸው ነው፡፡ በዚህ ሁሉ ሒደት ከምኑም የሌሉበት ክርስቲያኖች ለአደጋ እየተጋለጡ፣ የሚደርስላቸው አጥተው እግዚአብሔርን እየተማጠኑ ነው፡፡ ለዚህ አብነት የሚሆኑን የሶሪያ ክርስቲያኖች ናቸው፡፡ የተሸፈነው ሁሉ የእልክ መወጫና የጦር መለማመጃ የሚያደርገው ክርስቲያኖችን ነው፡፡ መስቀል የጨበጡ ካህናትን ገድሎ የሚገኝ ደስታ፣ ምእመናንን የሚያረጋጋና ለሀገር ሰላም የሚጸልይን ጳጳስ አስሮ የሚገኝ ሰላም እንዴት ያለ ሰላም ሊሆን እንደሚችል መገመት ያዳግታል፡፡

በመካከላችን የተፈጠረውን ልዩነት ተወያይተን እንፍታው፣ ከጦርነት ጥፋት እንጂ ልማት አናገኝም የሚሉት ወገኖች እየቀነሱ መጥተዋል፡፡ ሀገር በወንበዴዎች ጠፍታ እንደምታድር በሰላማውያን ደግሞ ተሠርታ ታድራለች፡፡ ሰላማውያን ከሆንን ለእኛ የሚያስፈልገን ለሌሎችም እንደሚያስፈልጋቸው ስለምናምን ያለውን ተካፍለን እንጠቀማለን፣ ከሌለ ደግሞ በጋራ ሠርተን የምናገኝበትን ዘዴ እንቀይሳለን፡፡ በዓለማችን እየተሠራ ያለው ግን የሌላውን ነጥቆ የራስ ማድረግ ነው፡፡ የድሀ ሀገሮችን ቅርስ፣ ንዋያተ ቅድሳት እየዘረፉ ወስደው የራሳቸው የሚመስልበትን ሕግ አውጥተው ይኖራሉ፡፡ የታሪኩ ባለቤቶች የራሳቸውን ንዋያተ ቅድሳት ከፍለው ይመለከታሉ፡፡ ይህም የዓለም ሕግጋት የተንሸዋረረና ላለው የሚያደላ መሆኑን ያስገነዝባል፡፡ ትክክለኛ መፍትሔ ለማምጣት ከተፈለገ ፍትሕ ያለ አድሎ ለሁሉም መስጠትና በኢኮኖሚ የዳበሩት ሀገሮች ድሆችን እናውቅላችኋለን፣ እኛ ያልናችሁን ብቻ ፈጽሙ የሚለው አሠራር መታረም አለበት፡፡

እምነት ያላቸው ሰዎች ግን እንኳን የሌላውን ሊነጥቁ የራሳቸውንም አሳልፈው ይሰጣሉ፡፡ መመሪያቸውም “እምነትስ ተስፋ ስለምናደርገው ነገር የምታስረግጥ፣ የማናየውንም ነገር የምታስረዳ ናት፡፡ በዚህም ለሸማግሌዎች ተመሰከረላቸው፡፡ ዓለም በእግዚአብሔር ቃል እንደተፈጠረ፣ የሚታየውም ነገር ከማይታየው እንደሆነ በእምነት እናውቃለን” (ዕብ. ፲፩፥፲፫) የሚለው ቃል ነው፡፡ ተስፋቸው ለዘለዓለማዊው ዓለም በመሆኑም በምድር ሰላማውያን ሆነው ይኖራሉ፡፡ የማይታየውን ተስፋ ስለሚያደርጉም እንደሚታረድ በግ እየተጎተቱ ወደ ሞት ሲወሰዱ በደስታ ይቀበሉታል፡፡ ሞትንም የሚንቁት ከመከራ፣ ከውጣውረድ፣ ከስቃይ የሚያርፉበትና ዳግም ሞት ወደሌለበት የሚሸጋገሩበት በመሆኑ ነው፡፡

ክርስቲያኖች በዚህ ምድር ሲኖሩ ደስታና ኀዘን፣ ማግኘትና ማጣት ቢፈራረቅባቸውም ታግለው ለማሸነፍ፣ እግዚአብሔርን ጠይቀውም መፍትሔ ለማምጣ ይሞክራሉ፡፡ የሚደርስባቸውን ፈተና በጸጋ የሚቀበሉትም በተስፋ ኗሪዎች ሀገራቸው በሰማይ መሆኑን በደንብ የተረዱ በመሆናቸው ነው፡፡ ኃይል እያላቸው የሚሸሹት፣ ማድረግ እየቻሉ አቅም የሌላቸው የሚመስሉት ዘለዓለማዊው ድኅነት በመሞት እንጂ በመግደል የሚገኝ ባለመሆኑ በመስጠት እንጂ በመቀማት ባለመገኘቱ ነው፡፡ የነገሥታት ወገኖች የነበሩት ሰማዕቱ ቅዱስ አቦሊ፣ አባቱ ዮስጦስና እናቱ ታውክልያ ዙፋኑ ለእነሱ እንደሚገባ እያወቁ ስለዘለዓለማዊው ጊዜያውን ናቁት፡፡ የሮማ ሕዝብ ከዲዮቅልጥያኖስ እነሱ እንደሚሻሉት፣ በጉልበት ሳይሆን በእምነት እንደሚመሩት እነሱም፣ ዲዮቅልጥያስም፣ ሕዝቡም ያውቃሉ፡፡ ያደረጉት ግን ለክርስትና ፍቅር ብለው ሥልጣናቸውን መተውና ሰማዕትነትን መቀበል ነው፡፡ አቅም የላቸውም እንዳይባሉ ብቻቸውን ተዋግተው የጠላት ሠራዊት መመለስ እንደሚችሉ አሳይተዋል፡፡ ክርስትናቸው ግን ከዚያ እንዲያልፉ አላደረጋቸውም፡፡ በዚህም ገዳያቸው ዲዮቅልጥያኖስ በክፉ እነሱ ግን በመልካም ሲታወሱ እንዲኖሩ የሚያደርጋቸውን ሥራ ሠርተው ዐልፈዋል፡፡ ሁልጊዜ አስቡን፣ ከአምላካችሁ አስታርቁን እየተባሉ ይለመናሉ፡፡

ክርስቲያኖች እምነት እንጂ ፍርሃት መገለጫቸው አይደለም፡፡ ጦር መሣሪያ የታጠቁት ባዶዋቸውን የቆሙትን ክርስቲያኖች የሚፈሯቸው እምነት ያላቸው ሰዎች እግዚአብሔር አብሯቸው ስለአለ ምን ያህል እንደሚያስፈሩ ማሳያ ነው፡፡ መፍራት የነበረበት ባዶ እጁን ያለና ሞት የተፈረደበት እንጂ ንጹሐንን ወደ ሞት በመውሰድ የሚገድል አይደለም፡፡ በክርስቲያኖች የሚፈጸመው ግን የተገላቢጦሽ ነው፡፡ ንጉሡ እለእስክንድሮስ በፍርሃት እንዲርድ ያደረገው የሦስት ዓመቱ ሰማዕቱ ቂርቆስ ነው፡፡ የእምነት ሰዎችን አላውያን ነገሥታት ብቻ ሳይሆኑ አጋንንትም ይፈሯቸዋል፡፡

እምነታቸውን ጋሻ በማድረጋቸው ለራሳቸው ብቻ ሳይሆን በአጸደ ሥጋ ለምንኖር ሁሉ ኃይላችን፣ ብርታታችን፣ ትውክልታችን፣ ጋሻ መከታችን መሆናቸውን ሐዋርያው “እነሱ በእምነት ተጋደሉ፤ ነገሥታትን ድል ነሡ፤ ጽድቅን አደረጉ፣ ተስፋቸውን አገኙ፣ የአናብስትን አፍ ዘጉ፡፡ የእሳትን ኃይል አጠፉ፤ ከሰይፉ ስለት አመለጡ፤ ከድካማቸው በረቱ፣ በጦርነት ኃይለኞች ሆኑ፤ የባዕድ ጭፍሮችንም አባረሩ፡፡ ሴቶችም እንደ ትንሣኤ ቀን፣ ተነሥተውላቸው ሙታኖቻቸውን ተቀበሉ፤ ተፈርዶባቸው የሞቱም አሉ፤… የገረፉዋቸው፣ የዘበቱባቸውና ያሰሩዋቸው ወደ ወኅኒ ያስገቧቸው አሉ፡፡ በመጋዝ የሰነጠቋቸው፣ በድንጋይ የወገሯቸው፣ በሰይፍም ስለት የገደሏቸው አሉ፤ ማቅ፣ ምንጣና የፍየል ሌጦ ለብሰው ዞሩ፤ ተጨነቁ፣ ተቸገሩ፣ መከራ ተቀበሉ፣ ተራቡ፣ ተጠሙም፡፡ ዓለም የማይገባቸው እነዚህ ናቸው፤ ዱር ለዱርና ተራራ ለተራራ፣ ዋሻ ለዋሻና ፍርኩታ ለፍርኩታም ዞሩ (ዕብ. ፲፩፥፴፫-፴፰) በማለት ገለጠው፡፡ የእስራኤል ኃያላን የሃይማኖት ሰዎች ሕዝበ እግዚአብሔርን ለመጠበቅ ያደረጉትን ተጋድሎ በመዘርዘር ወደ ሐዲስ ኪዳን ሰማዕታት የሚሸጋገረው የሐዋርያው ትምህርት ለደከሙት ብርታት የሚሆን ነው፡፡

ሐዋርያው አስቀድሞ እምነታቸውን ነገረን፡፡ በመቀጠልም እምነታቸውን ለመጠበቅ የፈጸሙትን ተጋድሎ አስረዳን፡፡ አስከትሎም በዚህ ዓለም በፈጸሙት ተጋድሎ በእምነት እንደተመሰከረላቸው፣ የተስፋ ቃል እንደተገባላቸው አበሰረን፡፡ ሐዋርያው የእነዚህን አበው ተጋድሎ የተረከልን በእምነት እንድንጸና፣ በቤተ ክርስቲያንና በምእመናን ፈተና ዛሬ አለመጀመሩን ተገንዝበን እንድንረዳው ነው፡፡ ወታደር ጀብድ የፈጸሙ ጀግኖችን ተጋድሎ እየተረከ የወታደሮችን ስሜት እንደሚቀሰቅስና ፍርሃታቸውን እንደሚያርቅላቸው ሁሉ ክርስቲያኖችም በእምነት የጸኑትን፣ ይህን ዓለም ታግለው ያሸንፉትን መንፈሳዊ ተጋድሎ በመተረክ አርአያ እንድናደርጋቸው እናንተን ያጸና እኛንም ያጽናን እንድንላቸው ነው፡፡ በሃይማኖት ጽኑ፣ የሚያልፈውን በማያልፈው ለመተካት የሚደርስባችሁን ታገሱ፣ በእምነት ጽኑ፣ ጎልምሱም የሚለው ትምህርት ለክርስቲያኖች ስንቅ ነው፡፡ ፍርሃትን አርቆ በእምነት ለመጽናት የሚያበቃ ነው፡፡

በተስፋ የሚጠብቁት ስለበለጠባቸው በዚህ ዓለም የሚደርስባቸውን መከራ መታገሥ እንዳለባቸው ሐዋርያው “እኔስ ከዚህ ዓለም ልለይ በክርስቶስም ዘንድ ልኖር እወዳለሁ፡፡ ይልቁንም ለእኔ ይህ ይሻለኛልና፤ ይበልጥብኛል፡፡ ደግሞም ስለ እናንተ በሕይወተ ሥጋ ብኖር ይሻላል፡፡ ይህንም ዐውቄ ለማደጋችሁና ለሃይማኖትም ለምታገኙት ደስታ እንደምኖር አምናለሁ” (ፊል. ፩፥፳፫-፳፭) በማለት ገልጦታል፡፡ በዚህ ቃል ሐዋርያው የራሱን ፍላጎት ገለጠ፡፡ ለምእመናንና ለቤተ ክርስቲያን የሚያስፈልገውንም አሳወቀ፡፡ የሃይማኖት ሰዎች እንደነሱ ፈቃድ ብቻ ሳይሆን እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ መኖር እንደሚገባ አስገነዘበ፡፡ ይህም ክርስቲያኖች ሌላውን ለመጥቀም ከእግዚአብሔር ጋር ለመኖር ቢናፍቁ እንኳ ሊያዘገዩት እንደሚችሉ ያስረዳል፡፡

ቤተ ክርስቲያን ትገፋለች፡፡ ወድቃ ግን አታውቅም፡፡ የሚገርመው አላውያን ቤተ ክርስቲያንን ለመግፋት የዘረጉት እጃቸው እምነትን ገንዘብ አድርጎ መመለሱን እያየን መሆኑ ነው፡፡ የቤተ ክርስቲያን ጉዞ እንዲህ ነው፡፡ አንዱ ሲቆረጥ ከሥሩ በሺሕ የሚቆጠሩ እያበቀለ ክርስትና እንድታብብ አድርጓል፡፡ የሦስተኛው መቶ ክፍለ ዘመን የዘመነ ሰማዕታት ክርስቲያኖች ብቻ ሳይሆኑ በሀገራችንም ሰማዕትነት አያምልጥህ እያሉ በአንድ ቀን ስምንት ሺሕ ገበሬ ምእመናን ሰማዕታትን ተቀብለዋል፡፡ ይህም በታሪክ እንዲዘከሩ፣ በቤተ ክርስቲያን እንዲታሰቡ አድርጓቸው ይኖራል፡፡

በየዘመኑ ዲያብሎስ በቤተ ክርስቲያን ላይ ፈተና ያስነሣል፡፡ አይታለፍም የተባለው ታልፎ፣ አይሆንም የተባለው ተፈጽሞ እየታየ ነው፡፡ ለዚህም ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ “ዲያብሎስ ዝናሩን አራገፈ፤ ቀስቱን ጨረሰ፤ ቤተ ክርስቲያንን ግን አልጎዳትም፡፡ ቤተ ክርስቲያን ሁልጊዜ ትዋጋለች፤ ተሸንፋ ግን አታውቅም” በማለት መናገሩ ምስክር ነው፡፡ ዲያብሎስ እንደማያሸንፉት እያወቀ፣ ክርስቲያኖችም በጸሎት ኃይል እንደሚያደክሙ እየተረዳ ቤተ ክርስቲያንን ይዋጋል፡፡ ዲያብሎስ የሚያተርፈው ቢኖር ቤተ ክርስቲያንን ለመዋጋት ያሰለፋቸው ጀሌዎቹ በክፋታቸው ከጸኑለት አብረውት ገሃነመ እሳት እንዲወርዱ ማድረግ ነው፡፡ ከዚያ ውጭ የአባቶቻችንና እናቶቻችን ቅድስና እንዲገለጥ ያደርጋል እንጂ ያሰበው ተሳክቶለት፣ ምኞቱ ሞልቶለት አያውቅም፡፡

ክርስቲያኖች ክርስትናን የተቀበሉት፣ የሥላሴ ልጅነትን ያገኙት ለማመን ብቻ ሳይሆን መከራም ለመቀበል መሆኑን ሐዋርያው “የእነሱ ጥፋት የእናንተም ሕይወት ይታወቅ ዘንድ የሚቃወሙትን ሰዎች በማናቸውም አያስደንግጧችሁ፡፡ ይህንም ጸጋ እግዚአብሔር ሰጥቷችኋል፤ ነገር ግን ስለ እርሱ መከራ ልትቀበሉም ነው እንጂ ልታምኑበት ብቻ አይደለም፡፡ እንዲሁም እኔን እንዳያችሁኝ የእኔንም ነገር እንደሰማችሁ ምን ጊዜም ተጋደሉ” (ፊል. ፩፥፳፰-፴) በማለት ገልጦልናል፡፡ ይህን የምንለው ክርስቲያኖች በዚህ ዓለም ሲኖር መሠረታዊ ፍላጎታቸውን ለማሟላት ምንም አያስፈልጋቸውም ለማለት አይደለም፡፡ ከሁሉ የሚቀድመው በእምነት ጸንቶ፣ ነቅቶና ተዘጋጅቶ መኖር እንደሚያስፈልግ ለመግለጥ እንጂ፡፡ እምነት ያላቸውና ትውክልታቸውን በእግዚአብሔር ላይ ያደረጉ ደግሞ በዚህ ዓለም እንዴት እንደሚኖሩ ያውቁነታል፡፡ ራሳቸው ዘመኑን ዋጅተው ነው እኛንም ዘመኑን ዋጁ የሚሉን፡፡

የክርስትና ማእበል በሆነችው ኢትዮጵያ የዘር፣ የሃይማኖት፣ የቋንቋ፣ የባህል ልዩነት ሳይገድበን ተንቀሳቅሰን ይመቸናል በምንለው አካባቢ ወልደን፣ ከብደን፣ ወጥተን፣ ወርደን፣ ነግደን አትርፈን እንኖራለን፡፡ ማን ነህ፣ ከየት መጣህ፣ ሃይማኖትህ ምንድን ነው የሚል ወገን በሀገራችን አይታሰብም ነበር፡፡ ዓለምን ከምናስደንቅበት ነገር አንዱ በሌሎች ዓለማት በበጎ የማይታዩት ክርስትናና እስልምና በኢትዮጵያ የአንድ ሳንቲም ሁለት ገጽታ ሆነው መኖራቸው ነው፡፡ በብዙዎች አካባቢዎች ክርስቲያኖች ቤተ ክርስቲያን መሥሪያ ሲያጡ ከመሬታቸው ቆርሰው፣ ከኪሳቸው ገንዘብ አውጥተው፣ የሰበካ ጉባኤ አባል ሆነው አብያተ ክርስቲያናትን ያሠሩ ብዙ ሙስሊም ወገኖቻችን ነበሩ፤ አሁንም አሉ፡፡ የቤተ ክርስቲያን ዕቃ ቤት ጠባቂ የሆኑና ቤተ ክርስቲያንን በጥበቃነት የሚያገለግሉ ሙስሊም ወገኖቻችን መኖራቸው የሚገልጠው በሃይማኖት ልዩ ብንሆን በማኅበራዊ ሕይወት፣ በባህል ለምን እንለያለን ብለው ነው፡፡ የዚህ ዓይነት ታሪኮችን በሐመር መጽሔት፣ በስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ፣ በማኅበረ ቅዱሳን ቴሌቪዥን ስርጭት ስናስተላልፍ መቆየታችን ይታወቃል፡፡ ይህንን የምንገልጠው ለፕሮፓጋንዳ ሳይሆን በትክክል የተፈጸመ መሆኑን ለመግለጥ ነው፡፡ የገረመንም እንዲህ በሚደረግባት ሀገር ቤተ ክርስቲያንና ክርስቲያኖች የጥፋት ዓላማ እየሆኑ በመምጣቸው ነው፡፡

ሰሞኑን በሶማሌ ክልል ክርስቲያኖችን ብቻና ቤተ ክርስቲያንን መርጠው ጥፋት ሲታወጅባቸው የእስልምና ጉዳዮችም፣ ካቶሊክ ቤተ ክርስቲያንም ድርጊቱን እንደሚያወግዙት የገለጡት የአንዱ በሰላም ማደር ለራስ ሰላምም ስለሚጠቅም ነው፡፡ በሌላ በኩልም እንዲህ ያለ ጥፋት በሀገራችን ያልተለመደ መሆኑን ስለሚያውቁ ነው፡፡ ልዩ ልዩ ወገኖች የሰጡት መግለጫ እንዲያውም ቤተ ክርስቲያኗ ከሰጠችው የጠነከረ ነው፡፡ አሜሪካና ኢትዮጵያ ይኖሩ የነበሩ አባቶች ይቅር ተባብለው ዕርቁንም በሚሊኒየም አዳራሽ ባበሠሩበት ወቅት የእስልምና፣ የካቶሊክ፣ የወንጌላውያን ኅብረትና የቃለ ሕይወት ተወካዮች ያደረጉት ንግግር ይህ ድምፅ ከቤተ ክርስቲያን ነው ከሌላ የሚያሰኝ ነበር፡፡ ይህ ደስታ ሳይፈጸም በክርስቲያኖችና በቤተ ክርስቲያን ላይ ጭፍጨፋና ቃጠሎ ተተካ፡፡ ሕግና ሥርዓት ባለበት ሀገር እንዲህ ማድረግ ተገቢ አለመሆኑን የምንገልጠው ከቤተ ክርስቲያን ይልቅ በተሳለ ሰይፍ ላይ ለቆሙት በማዘን ነው፡፡ አስቀድመን እንደተናገርነው ቤተ ክርስቲያንን ብዙዎች ለመግፋት ሞክረው ነበር አልቻሉም እንጂ፡፡ ዐርፍተ ዘመን ገትቷቸው፣ ተአምር ተደርጎ ተመልሰው አምላኬ ሆይ ሳላውቅ ባጠፋሁት አትቅሰፈኝ ሲሉ ኖረዋል፡፡ አንመለስም ያሉትም አሟሟታቸው ምን ይመስል እንደነበር የቤተ ክርስቲያንን ታሪክ ማንበብ በዲዮቅልጥያኖስ፣ የዮልዮስቂሳርና በሌሎችም የደረሰውን ማሰብ ይገባል፡፡

የሊቀ ሰማዕታት ቅዱስ ጊዮርጊስን ቤተ ክርስቲያን ለማፍረስ ሞክሮ የነበረው ዲዮቅልጥዮስ የደረሰበትን መከራ ገድሉንና ስንክሳር መጽሐፉን ማንበብ ይገባል፡፡ በቅድስት አርሴማና በተከታዮቿ ላይ በቃላት ተነግሮ የማያልቅ መከራ አድርሶ የነበረው የአርማንያው ንጉሥ ድርጣድስ አእምሮው ተነሥቶት ለሰባት ዓመታት እንደ በራሃ እሪያ ሣር ሲበላ ኖሮ በገባሬ ተአምራት ቅዱስ ጎርጎርዮስ ዘአርማንያ ጸሎት እንደዳነ፣ ታላቁ ባስልዮስ ዘቂሳርያንና ጎርጎርዮስ ዘእንዚናዙን ከዋሉበት አላሳድር፣ ካደሩበት አላውል ብሎ የነበረው በአቴንስ የፍልስፍና ትምህርት ቤት የትምህርት ቤት ጓደኛቸው የነበረው ዩልዮስቄሳር መጨረሻቸው አላማረም፡፡ እነሱ ስለ ጓደኝነት፣ ስለ ክርስቶስ ፍቅር ጭምር ብለው ቢታገሱት አልሰማም በማለቱና ከጦርነት ሲመለስ እነሱንም ለመግደል ቤተ ክርስቲያናቸውንም ለማቃጠል ዝቶ ጠላቶቹን ለመውጋት ሲሔድ ቅዱስ ባስልዮስ ክርስቲያኖችን ካሳደደ ከሔደበት በሰላም እንደማይመለስ ነገረው፡፡ ንጉሡ ድንኳን ውስጥ በተኛበት የቅዱስ መርቆርዮስ ሥዕል በጦር ወጋው፡፡ ከአልጋው ሳይነሣ ቀረ፡፡ አጃቢዎቹ ወዳለበት ቢገቡ በደም ተንክሮ ስላገኙት ደንግጠው ተበተኑ፡፡

በክርስቲያኖች ደም እጃቸውን የታጠቡ ወገኖች የደረሰባቸውን ለማወቅ መጻሕፍትን ማንበብ ሊቃውንትን መጠየቅ ይገባል፡፡ እነዚህ ሁሉ ግፈኞች “መልካሙን ሥራችሁን አይተው በሰማያት ያለውን አባታችሁን እንዲያከብሩ ብርሃናችሁ እንዲሁ በሰው ፊት ይብራ” (ማቴ. ፭፥፲፮) ለተባለላቸው ከስቃይ ወደ ረፍት መሸጋገሪያ ናቸው፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ የእነሱን ደካማ ጎን የክርስቲያኖችን ጥብዓት የሚገልጥ ነው፡፡ ክርስቲያኖች “ክርስትና ሊኖሩት እንጂ ሊያወሩት ብቻ እንደማይገባ፣ ወንጌል በተግባር ሲገለጥ እንጂ እንደ ርዕዮተ ዓለም በቃላት ብቻ በንግግር ማሳመር እንደማይሰበክ ሕያው ምስክር ናቸው፡፡ ጌታችንና አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አዳምን ከመንጸፈዳይን ለማውጣት መከራ ተቀብሏል፤ ሞትንም ድል አድርጎ ተነሥቷል፡፡ ትንሣኤውን በሚመስል ተንሣኤ ተነሥተን ከክርስቶስ ጋር እንኖር ዘንድ ሞቱን በሚመስል ሞት መተባበር እንዳለብን ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ አስተምሮናል፡፡ የኑሮዋቸውን ፍሬ እየተመለከታችሁ በእምነት ምሰሏቸው የተባልናቸው ዋኖቻችን ጌታችንና አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን በሁሉ መስለውታል፡፡ እኛም እነሱን እንድንከተልና እንድመስላቸው አርአያነታቸውን መከተል ይገባናል፡፡”

ለእግዚአብሔር ሕዝብ ብሎ መከራ የመቀበልን አርአያነት ከሊቀ ነቢያት ሙሴ እንድንማር ሐዋርያው “ሙሴ ለጊዜው በኃጢአት ከሚገኝ ደስታ ይልቅ ከእግዚአብሔር ሕዝብ ጋር መከራ መቀበልን መረጠ፤ ብድራቱን ትኩር ብሎ ተመልክቷልና፡፡… የማይታየውን እንደሚታየው አድርጎ ጸንቶአልና” (ዕብ. ፲፩፥፳፭-፳፯) በማለት አስተምሮናል፡፡ ይህ ሁሉ የሚያስገነዝበው የክርቲያኖች በመከራ የማይገበሩ መሆን ነው፡፡

እንደ ሀገር የምንበለጽገውና ሰላማችን እውን የሚሆነው በሰላም ተከባብረን ስንኖር ነው፡፡ ሰላም ከሌለ ያለንን መጠቀም፣ የጎረስነውን መዋጥ አንችልም፡፡ ሌት ዕንቅልፍ ቀን ረፍት አናገኝም፡፡ ዛሬ በክርስቲያኖችና በቤተ ክርስቲያን ላይ የተጀመረው ጥፋት መልኩን ለውጦ ብዙዎችን እንዳይበላና መጨረሻችንን ዳር ቆመው አይተው መሬታችንን ለመውረር ለሚጎመጁት ጠላቶቻችን መንገድ ጠራጊ እንዳንሆን መጠንቀቅ ይገባናል፡፡ ጥፋት ቢከሠት እንኳ ጥፋትን በጥፋት መመለስ ኪሳራ እንጂ ትርፍ የለውም፡፡ የተጠቃሉት አብያተ ክርስቲያናትና የሞቱና የተሰደዱ ክርስቲያኖች እስከ አሁን በክልሉ መንግሥት መልካም ፈቃድና በሕዝቡ አብሮ የመኖር ባህል በቦታው  ብዙ ዓመታት ኖረዋል፡፡ መቀጠል የሚኖርበት እንደ እስከአሁኑ በፍቅር መኖር ነው፡፡ የሚስተካከል ካለ ማስተካከል፣ ጎደሎ ካለ መሙላት፣ የሚያስቸግር ካለ ማስተካከል እንጂ ሰላማውያንን ማወክ ውጤቱ ምን ሊሆን እንደሚችል እንኳን አእምሮ ያለው ሕፃናትም ያውቁታል፡፡ መንግሥት አልባ ለመሆን ካልፈለግንና ሀገራችን ውስጥ ቀምቶ የሚበላ እንዲኖር ካልፈለግን በቀር፡፡ ወደፊት አብረን እንድንኖር የሚያደርጉንን እየተመካከርን መሥራት፣ የሚያስቸግሩ ካሉ ማስተካከል ይገባል፡፡ እምነትን ሽፋን አድርጎ ሕዝብን ከሕዝብ የሚያለያይ ካለ ቢቻል መክሮ ማስተካከል አልመለስም ካለ ለሚመለከተው የመንግሥት አካል እያሳወቅን ሰላማችንን ጠብቀን መኖር ይጠበቅብናል፡፡

የተሰደዱት እንዲመለሱ፣ የተቃጠሉት አብያተ ክርስቲያናት እንዲሠሩ፣ የሟች ወገኖች እንዲደገፉ ማድረግ ይገባል፡፡ ችግሩን ወደ ሌላ መጠቆም አይጠቅምም፡፡ የሚጠቅመው መፍትሔ ማበጀትና ፍቅርንና አብሮ መኖርን የሚያጸና ተግባር መፈጸም ነው፡፡ ዐይን ስለ ዐይን የሚለው ሕግ ቀኝህን በመታህ ግራውን አዙርለት በሚለው ቢተካም ለሀገር ደኅንነት ሲባል ጥፋተኞች የሚታረሙበትን፣ ዳግም ለጥፋት እንዳይሰለፉ የሚሆኑበትን ሥራ መሥራት ከመንግሥት፣ ከቤተ ክርስቲያን፣ ከፍትሕ አካላትና ከሚመለከታቸው ሁሉ ይጠበቃል፡፡ በዚህ ወቅት በቤተ ክርስቲያንና በክርስቲያኖች ላይ የደረሰው “መከራ ልትቀበሉ እንጂ በስሙ ልታምኑ ብቻ አልተጠራችሁም” በማለት ሐዋርያው የተናገረውን እንዳንረሳው ለማድረግ እንደሆነስ ማን ያውቃል፡፡ ማን ያውቃል ነገ ከነገወዲያ ከተቃጠሉት ዐሥር አብያተ ክርስቲያናት ሁለትና ሦስት ዕጥፍ በአጭር ጊዜ ውስጥ የሚያንፁ ክርስቲያኖችን እግዚአብሔር ሊያሥነሣም እንደሚችል ማመን ያስፈልጋል፡፡

  ምንጭ  ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ ከነሐሴ16-ጳጉሜ5ቀን 2010ዓ.ም

“ሰላምን ሻት ተከተላትም”(መዝ.፴፫፥፲፬)

በመ/ር ኃይለ ሚካኤል ብርሃኑ
ሰላም ማለት ጸጥታ፣ ዕረፍት፣ እርጋታ፣ እርካታ ማለት ሲሆን የእርስ በእርስ ስምምነት በአንድነት አብሮ መኖር መቻልና የዕረፍት ስሜት እንደሆነ የመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት ያስረዳል፡፡ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት “ሰላምን ሻት ተከተላትም” ብሎ ከመናገሩ አስቀድሞ የመጽሐፉን ክፍል ወደ ኋላ መለስ ብለን የተነሳንበትን ኃይለ ቃል ሙሉ አሳቡን ለመረዳት ስንመለከተው እንዲህ የሚል ቃል እናገኛለን፡፡ “ልጆቼ ኑ ስሙኝ እግዚአብሔርን መፍራት አስተምራችሁ ዘንድ፤ ሕይወትን የሚፈቅድ ሰው ማን ነው? በጎ ዘመንንም ለማየት የሚወድድ ማን ነው? አንደበትህን ከክፉ ከልክል ከንፈሮችህም ሸንገላን እንዳይናገሩ ከክፉ ሽሽ መልካንም አድርግ ሰላምን ሻት ተከተላትም” ይላል፡፡
ልበ አምላክ ቅዱስ ዳዊት ሰላምን የምንሻበትን ምክንያት በዚሁ በተመለከትነው ኃይለ ቃል ላይ ገልጦታል፡፡ እንደ አባትነቱ እግዚአብሔር ልጆቹ ለምንሆን ለእኛ ሊያስተምረን የፈቀደለትንና እርሱ በሕይወቱ ገንዘብ አድርጎት በእግዚአብሔር እንደ ልቤ ተብሎ የተመረጠበትን ጥበብ ለእኛም ሲያካፍለን “እግዚአብሔርን መፍራት አስተምራችኋለሁአለ፡፡ምክንያቱም እግዚአብሔርን መፍራት ከሁሉ ይልቅ ቀዳሚ ነውና፡፡ ለዚህም ነው አባትና ልጅ ተባብረው(ተቀባብለው) የጥበብ መጀመሪያ እግዚአብሔርን መፍራት እንደሆነ የነገሩን(መዝ. 111፥10፣ምሳ.1፥7፣9፥10)፡፡
ከሁሉ አስቀድሞ በሕይወታችን እግዚአብሔርን መፍራት ትርጉም ላለው ሕይወት አስፈላጊ ነው፡፡ ሰላምን የምንሻበት መንገድ እሱ ነውና፡፡ ቅዱስ ዳዊት እግዚአብሔርን መፍራት ሕይወትን የሚያስገኝና በጎ ዘመንን ለማየት የምንችልበት የጥበብ (የዕውቀት) ሁሉ መሠረት ነው፡፡ ይህንንም ከገለጸ በኋላ “ሕይወትን የሚፈቅድ ሰው ማን ነው? በጎ ዘመንንም ለማየት የሚወድድ ማን ነው? ብሏል፡፡ ከላይ እንዳየነው ሕይወትን ለማግኘት የሚሻ በጎ ዘመንንም ለማየት የሚፈልግ ጥበብን (ማስተዋልን) ገንዘብ ያደረገ ሰው ነው፡፡ በመሆኑም ሕይወትን ለማግኘትና በጎ ዘመንን ለማየት የሚሻ ሰው ምን ማድረግ እንዳለበት ስንመለከትም ቅዱስ ዳዊት እንደነገረን ቀጥለን በዝርዝር እንመለከታቸዋለን፡፡
      ፩ኛ አንደበትን ከክፉ መከልከል
የሰው ልጅ በልቡ ያሰበውን በአንደበቱ ይናገራል፡፡ በልብ የታሰበውን መልካምም ይሁን ክፉ የሚያውቀው እግዚአብሔር ብቻ ሲሆን ነገር ግን የታሰበው ነገር በውጫዊ ሰውነት ላይ በሚታዩ ምልክቶች (ገጽን በማየት) መታወቅ የሚችልበት አጋጣሚ ከተፈጠረ ወይም በአንደበት ቢነገርና በሥራ ቢተገበር ሰዎች ይረዱት ይሆናል፡፡
ይሁንና አንደበትን ከክፉ ካልከለከሉት ሰዎችን የሚጎዳና የማይሽር ጠባሳ ጥሎ የማለፍ በዚያም ሰበብ ተናጋሪውን ሳይቀር ሁለተኛውን አካል በቁጣ በመጋበዝ ለሞት የማብቃት ዕድል አለው፡፡ ለዚህም ነው ቅዱስ ያዕቆብ በመልእክቱ “ምላስ እሳት ናት እነሆ ትንሽ ምላስ በሰውነታችን ውስጥ ዐመፅ የተመላበት ዓለም ናት ሥጋችንን ትበላዋለች ውስጣዊ ሰውነታችንንም ትጠብሰዋለች ከገሃነምም ይልቅ ታቃጥላለች” ይላል፡፡
ስለዚህ ሕይወትን የሚፈቅድና በጎ ዘመንን ለማየት የሚፈልግ ሰው አንደበቱን ከክፉ ነገር መከልከልና መጠበቅ ያስፈልጋል፡፡ ተናግሮ ሰውን ላለማስቀየምና ላለማስከፋት መጠንቀቅ አለበት፡፡ ሌላውንም ሰው ወደ ጥፋት ላለመምራት ማስተዋል ተገቢ ነው፡፡ አንደበት ኃያል ነውና ጦር ከፈታው ወሬ የፈታው ይበልጣል የሚል አባባል እንዳለ እናስታውሳለን፡፡
አንደበትን ከክፉ ካልከለከልነው ስድብንና ሐሜትን እናበዛለን፡፡ ይህ ደግሞ ከሕይወት ጎዳና የሚያወጣ ክፉ ተግባር ነው፡፡ በጓደኛ መካከል፣ በባልና ሚስት መካከል፣ በአንድ ሀገርና በሌላው ሀገር መካከል፣በጎሳና በጎሳ መካከል ፣ በጎረቤትና በጎረቤት መካከል ሐሜትና መነቃቀፍ፣ ስድብና ጥላቻ ካለ በጎ ዘመንን ማየት አይቻልም፡፡ ነገር ግን ሕይወትንም ሆነ በጎ ዘመንን ለማየት አንደበትን ከክፉ መከልከልና በጎ ነገርን ማውራት አስፈላጊ ነው፡፡
                                                           ፪ኛ. ከክፉ መሸሽ
ከክፉ መሸሽ ማለት ክፉን ከማድረግ መቆጠብና ክፉ ከሚያደርጉት ጋር በክፋታቸው አለመተባበር ነው፡፡ የእግዚአብሔር ሰው ሁል ጊዜም ቢሆን ከክፉዎች ጋር ኅብረት የለውም አባታችን ያዕቆብ ልጆቹን በሚመርቅበት ጊዜ ክፉ ሥራ ከሠሩ ከልጆቹ የክፋት ሥራ ጋር እንደማይተባበርና ከክፋት ጋር ኅብረት እንደሌለው ገልጧል፡፡ “ስምዖንና ሌዊ ወንድማማቾች ናቸው፡፡ በጭቅጭቃቸውና በጦራቸው ዐመጽን ፈጸሟት በምክራቸው ሰውነቴ አትገናኛቸው አሳቤም በአመጻቸው አትተባበርም በቊጣቸው ሰውን ገድለዋልና በገዛ ፈቃዳቸውም የሀገርን ሥር ቆርጠዋልና ቁጣቸው ርጉም ይሁን ጽኑ ነገርና ኩርፋታቸውም ብርቱ ነበርና በያዕቆብ እከፋፍላቸዋለሁ በእስራኤልም እበታትናቸዋለሁ” (ዘፍ.49፥5)
ያዕቆብ ምንም እንኳ በሥጋ የወለዳቸው ልጆቹ ቢሆንም በፈጸሙት ክፉ ሥራ ግን እንደማይተባበር ከክፉ ሥራቸው የራቀና ከክፋት የተለየ መልካም አሳብ እንዳለው ገልጧል፡፡ ዛሬም ቢሆን የሰው ልጆች ክፋትና በደል እየበዛ ባለበት ሰዓት የእግዚአብሔር ልጆች ከክፋት፣ ከተንኮል፣ ከውሸት፣ ከሌብነት፣ ከቅሚያ፣ ከዝርፊያ፣ ከጭካኔ፣ ከሴሰኝነት፣ ከዘማዊነት፣ ከዘረኝነት በአጠቃላይ ለራስም ለሀገርም ከማይበጁ እኩይ ምግባራትና ከሚፈጽሟቸው ሰዎች ጋር መተባበር የለብንም፡፡ ቅዱስ ዳዊት እንደነገረን ሕይወትን ለማግኘት የምንሻና በጎ ዘመን ለማየት የምንፈልግ ሁሉ ከክፉዎች ጉባኤ መለየትና አለመተባበር ያስፈልጋል፡፡
                                                     ፫ኛ. መልካም ማድረግ
ሕይወትን ለማግኘትና በጎንም ዘመን ለማየት የሚሻ ሰው ሁሉ መልካምን ሁሉ ሊያደርግ ያስፈልገዋል፡፡ ከክፉ መሸሻችንና ከከፉዎች ጋር አለመተባበራችን መልካም ሥራ ለመሥራት መሆን አለበት እንጂ ከሥራ ርቀን እንዲሁ እንድንኖር አይደለም፡፡ያለ በጎ ሥራ መኖር ስንፍና ነውና፡፡
እግዚአብሔር የሰውን ውድቀቱንና መጥፋቱን የማይሻ አምላክ ስለ ሆነ በማወቅም ይሁን ባለማወቅ በክፉ ሥራ ተጠምዶ የነበረ ሁሉ ሊመለስና በሕይወት ሊኖር ይገባዋል፡፡ በቀደመው ስሕተቱ ወንድሙን ያሳዘነ፣ሰው የገደለ፣አካል ያጎደለ፣ ግፍን የፈጸመ፣የድሃውን ገንዘብ በተለያየ ሰበብ የዘረፈ፣ጉቦ የተቀበለ፣በነዚህና መሰል እኩይ ሥራዎች ሀገሩን የጎዳ፣ እግዚአብሔርን የበደለ ሁሉ ከልብ በመጸጸት በልቅሶና በዋይታ ወደ እገዚአብሔር መመለስ ያስፈልገዋል፡፡ ለዚህም አምላካችን ልዑል እግዚአብሔር በነቢዩ ሕዝቅኤል ላይ አድሮ ኃጢአተኛው ከኃጢአቱ ተመልሶ በሕይወት መኖር እንዳለበት አስገንዝቦናል፡፡
“እኔ ሕያው ነኝና ኃጢአተኛው ከመንገዱ ተመልሶ በሕይወት ይኖር ዘንድ እንጂ ኃጢአተኛው (በደለኛው) ይሞት ዘንድ አልፈቅድም ይላል ጌታ እግዚአብሔር፡፡የእስራኤል ቤት ሆይ ተመለሱ ከከፉ መንገዳችሁ ተመለሱ ስለምንስ ትሞታላችሁ? (ሕዝ.33፥11) እንዲል፡፡
እግዚአብሔር በነቢዩ ላይ አድሮ እንደ ነገረን በደለኛ ሰው በበደሉ ቀጥሎ መጥፋት የለበትም፡፡መመለስና በሕይወት መኖር ያስፈልገዋል እንጂ፡፡ እሱም እንደ በደሉ ዓይነት የቅርታ ጠይቆ፣ ንስሓ ገብቶ፣ የበደለውን ክሶ፣ የሰረቀውን መልሶ፣ የሰበረውን ጠግኖ፣ ያጎደለውን መልቶ በፍጹም መጸጸት ሊመለስና መልካም በመሥራት ሌት ተቀን ከሚተጉት ጋራ በመልካም ሥራ ሊተባበር ያስፈልገዋል፡፡
ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ እንዳስተማረን “ስለዚህ ሐሰትን ተውአት ሁላችሁም ከመንገዳችሁ ጋር እውነትን ተነጋገሩ እኛ አንድ አካል ነንና አትቆጡ አትበድሉም ፀሐይ ሳይጠልቅም ቊጣችሁን አብርዱ ለሰይጣንም መንገድን አትስጡት የሚሰርቅም እንግዲህ አይስረቅ ነገር ግን ድሃውን ይረዳ ዘንድ በእጆቹ መልካም እየሠራ ይድከም” (ኤፌ. 4፥25) ይላል፡፡
                                                                           ሰላምን መሻት 
ሰላም ለሁሉ ነገር አስፈላጊና ሁሉን ለማድረግ የምንችልበት የመልካም ነገር ሁሉ በር ነው፡፡ ሰላምን መፈለግ ሕይወትን ለማግኘትና በጎ ዘመንንም ለማየት ያስችላል፡፡ በአይነቱ ሰላምን በሁለት መልኩ እናየዋለን፡፡ እሱም የውስጥ ሰላምና የውጭ ሰላም ወይም ውስጣዊ ሰላምና ውጫዊ ሰላም ብለን እንመድበዋለን፡፡
የሰው ልጅ ለመኖር ውስጣዊ ሰላምም ሆነ ውጫዊ ሰላም ያስፈልጉታል፡፡ ውስጣዊ ሰላም የምንለው አንድ ሰው ከፍርሐት፣ ከጭንቀት፣ ከመረበሽ፣ ከሥጋትና ወዘተ ነጻ ሆኖ መኖር ሲችል ውስጣዊ ሰላም አለው ይባላል፡፡ ይህም የውስጥን ሰላም ከሚያደፈርሱ፣ አእምሮን ከሚረብሹ፣ ልብን ከሚያቆስሉ፣ የጸጸት እሮሮን ከሚያስከትሉ ነገሮች ስንርቅና ለአእምሮ የሚመች ሥራ ስንሠራ ውስጣችን ሰላም ይሆናል፡፡ውጫዊ ሰላም የምንለው ደግሞ፡- ከቤተሰብ፣ ከጓደኛ፣ ከጎረቤት፣ ከሀገራት ጋር ተስማምተንና ተግባብተን ተቻችለንና ተረዳድተን በፍቅር ተሳስረን መኖር ነው፡፡ በመሆኑም ሰላም ከጥል፣ ከመለያየት፣ ከመጠላላት፣ ከመገፋፋት፣ ከመነቃቀፍ ተቆጥበን የጠብንና የጦርነትን ወሬ ባለመስማትና በስምምነት ተግባብቶ በመኖር የሚገለጥ ነው፡፡ ስለዚህ ሰላም ለሁሉ እንደሚያስፈልገው ካወቅን የሰላም መገኛ ማን እንደሆነና ሰላም ከየት እንደሚገኝ ማወቅ ደግሞ አስፈላጊ ነው፡፡

                                                                         የሰላም መገኛ
ሰላም የሚገኘው የሰላም ባለቤት ከሆነው ከልዑል እግዚአብሔር ነው፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ እንደገለጠው እውነተኛ ሰላም ከእግዚአብሔር ይገኛል፡፡ እርሱ የሰላም አምላክ ነውና (ሮሜ. 15፥33)፡፡ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሰላም አለቃ ተብሏል፡፡ “ሕፃን ተወዶልናልና ወንድ ልጅም ተሰጥቶናልና አለቅነትም በጫንቃው ላይ ይሆናል ስሙም ድንቅ መካር፣ ኃያል አምላክ፣ የዘለዓለም አባት፣ የሰላም አለቃ ተብሎ ይጠራል” (ኢሳ. 9፥6) እንዲል፡፡
ዓለም ለአምስት ሺሕ አምስት መቶ ዘመን ያህል ሰላሙን አጥቶ በመቅበዝበዝ ይኖር የነበረ ሲሆን በጌታችን በመድኃኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ሰው መሆን፣ መሞትና መነሣት እውነተኛውን ሰላም አግኝቷል፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በእርሱ ሞት ምክንያት ፍርሐት ጸንቶባቸው ለነበሩት ደቀ መዛሙርት “ሰላምን እተውላችኋለሁ ሰላሜንም እሰጣችኋለሁ እኔ የምሰጣችሁ ዓለም እንደሚሰጠው አይደለም ልባችሁ አይደንግጥ አትፍሩም (ዮሐ.14፥27) በማለት ፍርሐትን፣ ስጋትን፣ ጭንቀትን፣ ሁከትን፣ መረበሽን የሚያርቀውን (የሚያስወግደውን) እውነተኛውን ሰላም አደለን፡፡
ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት እንዳለው ሕይወትን ለማግኘትና በጎ ዘመንን ለማየት የምንሻ ሁሉ ሰላምን መሻት ያስፈልጋል፡፡ ደግሞም ሰላምን መሻት ብቻ ሳይሆን መከተል ተገቢ ነው፡፡ ምክንያቱም መሻት ብቻውን ዋጋ ሊኖረው ስለማይችል፡፡ መሻታችን ወደ ማግኘት የሚደርሰው የምንሻውን ነገር ለማግኘት ወደ መገኛው መጓዝና መቅረብ ሲቻል ነው፡፡ ለዚህም ነው ሰላምን ሻት ካለ በኋላ ተከታላትም በማለት በሰላም መንገድ መጓዝ፣ የሰላም ወሬ ማውራት፣ ለሰላም የሚስማማ ሥራ መሥራት የራሳችን ሰላም መጠበቅና የሌላውንም ሰላም አለማደፍረስ ማለት እንደሆነ የነገረን፡፡በሀገራችን ኢትዮጵያ በአሁኑ ሰዓት እየተሰማ ያለው የሰላም ዜና፣እየዘነበ ያለው ሰላም ፣እየተጠረገ ያለው የሰላም መንገድ ለዚሁ ማሳያ ነው፡፡ በአንድም ይሁን በሌላ ምክንያት ተራርቀው የነበሩ ሁለት አካላት የሚያለያያቸውን የጥላቻ ድንበር አፍርሰው የሚያገናኛቸውን የፍቅር ድልድይ መመሥረት አንዱ የሰላም መንገድ የሰላም መገለጫ ነው፡፡
ወደ ቤተ ክርስቲያን አባቶችም ስንመጣ ቀደም ሲል በነበሩት ዓመታት ተለያይቶ የነበረው ቅዱስ ሲኖዶስ ልዩነቱን እንደ ውበት ቆጥሮ ወደ መቀራረብና ወደ አንድነት ጉባኤ ለመምጣት የዘረጋው የሰላም መድረክ አንዱ የሰላም መገለጫ ነው፡፡ስለዚህ እንደ ግል ከራስ ጋር ተስማምቶ፣እንደ ሀገር በሀገር ውስጥ ካሉት ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ጋር ተግባብቶ መኖር የሚያስችሉትን የፍቅር መረቦች መዘርጋት የሰላም መንገድ፣ ሰላምን መሻትና መከተል ነው፡፡
የእግዚአብሔር ሰላም ለሁላችን ይሁንልን፡፡ አሜን
ምንጭ፤ሐመር መጽሔት 26ኛ ዓመት ቁጥር 3 ሐምሌ 2010ዓ.ም

  የ፳፻፲፩ ዓ.ም የአጽዋማት ባሕረ ሐሳባዊ ቀመር

በዲ/ን ታደለ ሲሳይ

በዘመናት ሁሉ የነበረው ያለውና የሚኖረው፣ ሁሉን የፈጠረ በሁሉም ያለ እግዚአብሔር ብቻ ነው፡፡ ለእርሱ በዚህን ጊዜ መኖር ጀመረ፣ በዚህን ጊዜ መኖር ያቆማል የማይባልለት የህልውናው መጀመሪያም ሆነ መጨረሻ የሌለው ዘለዓለማዊ ነው፡ “ተራሮች ሳይወለዱ ምድርም ዓለምም ሳይሠሩ ከዘላለም እስከ ዘለዓለም ድረስ አንተ ነህ”፡፡ “ኢየሱስም እውነት እውነት እላችኋለሁ አብርሃም ሳይወለድ እኔ አለሁ አላቸው፡፡”፣ ብሏል፡፡ በተጨማሪም፣ “ኢየሱስ ክርስቶስ ትናንትናና ዛሬ እስከ ዘለዓለም የሚኖር እርሱ ነውና” እንዲል /መዝ.89÷2፣ዮሐ. 8÷56-69 ዕብ.13÷8/፡፡

የሰው ልጅ ሐሳቡ፣ ንግግሩና ተግባሩ የሚከናወነው በጊዜ ነው፡፡ የጊዜያትና የዘመናት ቁጥርም ከሰው ልጅ ሕይወት ጋር የተቆራኘ ነው፡፡ የጊዜያትና የዘመናት ቁጥርም ከሰው ልጅ ሕይወት ጋር የተቆራኘ ነው፡፡ ዘመን ማለት በኅሊና ሲመረመር የጊዜና የዕድሜን መጠንና ልክ የሚወስን መሆኑን መጽሐፈአቡሻኸር ያስረዳል፡፡  ይህ ዘመን የሚባለው የጊዜ ዕድሜ በስያሜው አጠራር መሠረት ኃላፊ፣ የአሁንና የትንቢት/የወደፊት/  ጊዜ ተብሎ በሦስት ክፍላተ ጊዜ ይመደባል፡፡ «ወፉካሬሁሰ ለዘመን በውስተ ልብ አርአያ ወሰን ውእቱ ለጊዜ ዕድሜ ወዝንቱሰ ጊዜ ዕድሜ ዘስሙ ዘመን ይትከፈል እመንገለ ስሙ ኅበ ሠለስቱ ክፍል ኀበ ዘኅለፈ ዘመነ ወኀበ ዘይመጽእ ወኀበ ዘሀሎሂ እንዲል[1]፡፡

ከጥንተ ፍጥረት እስከ ዳግም ምጽአት ድረስ ያለው ዘመን ሁሉ በእነዚህ ሦስት ጊዜያት ሲሠፈርና ሲቆጠር ይኖራል፡፡ ያለፈውንና የሚመጣውን ዘመን ቆጥሮና ሠፍሮ መረዳትና ማስረዳት  እንደሚገባ ሲገልጽ ደግሞ፣  “ተሰአሉ  ዘቀደሙ መዋዕለ ዘኮነ እምቅድሜክሙ እምአመ ፈጠሮሙ እግዚአብሔር ለእጓለ እመሕያው ዲበ ምድር እም አጽናፈ ሰማይ እስከ አጽናፈ ሰማይ ለእመ ኮነ ዝንቱ ነገር፤ እግዚአብሔር  ሰውን በምድር ላይ ከፈጠረው ጀምሮ ከሰማይ ዳር እስከ ዳርቻዋ ድረስ ከቶ እንዲህ ያለ ታላቅ ነገር ወይም እንደ እርሱ ያለ ተሰምቶ እንደሆነ ከአንተ በፊት የነበረውን የቀድሞው ዘመን ጠይቅ”  ተብሎ ተጽፏል /ዘዳ.4÷32 ፡፡

ልበ አምላክ ዳዊትም ያለፈውን ዘመን በማስታወስ “የድሮውን ዘመን አሰብሁ፤ የዘለዓለሙን ዓመታት አሰብሁ፤ አጠነጠንሁም” በማለት ተናግሯል /መዝ.76÷51/፡፡

ዳግመኛም ይህ ዓመታትን ቆጥሮ ዘመኑን ያወቀው ልበ አምላክ ዳዊት ሲጸልይ፣ “ንግረኒ ውኅዶን ለመዋዕልየ፤ የዘመኔን አነስተኛነት ንገረኝ” ብሏል/መዝ.101÷23፡፡ ክቡር ዳዊት የዘመኑን ቁጥር ሲያሰላ እየቀነሰ እንደሚሔድ ገብቶታል፡፡ ይህ ግን ከኃጢአቱ የተነሣ አይደለም፡፡ ይልቁንም ስለ እርሱ የተጻፈው ምሥክርነት “ዳዊትም በራሱ ዘመን የእግዚአብሔርን አሳብ ከገሰገሰ በኋላ አንቀላፋ”  ይላል/ሐዋ.13÷37/፡፡ ይህ ደግሞ ዘመንን ታረዝማለች፡፡ እንዲል /ምሳ.10÷27/

በመሆኑም ኦርቶዶክሳውያን አባቶቻችንን ሥርዓት ጠብቀን፣ ሕገ እግዚአብሔርን አክብረን፣ እግዚአብሔር ሠፍሮ የሰጠንን ዘመን እርሱ በገለጸልን አቆጣጠር እየተጠቀምን በየዓመቱ አጽዋማትን እንጾማለን፣ በዓላትን እናከብራለን፡፡ በመሆኑም እንደእስካሁኑ ሁሉ ዛሬም የ2011 ዓ.ም አጽዋማትንና በዓላትን እንደሚከተለው እናወጣለን፡፡

                                                                  መባጃ ሐመር
ለአጽዋማትና በዓላት ማውጫ ወሳኝ የሆነው ነጥብ መባጃ ሐመር ነው፡፡ መባጃ ሐመር መባጊያ ሐመር እየተባለም ይጠራል፡፡ መባጊያ ሐመር ሲሆን የበጋ መመላለሻ የሚል ትርጉም ይሰጣል፡፡ በሌላ በኩል መባጃ በራሱ ማቆያ፣ ማክረሚያ ተብሎ ይተረጎማል፡፡

ሐመር መርከብ፣ መጓጓዣ የሚለውን ትርጉም ያስገኛል፡፡ መባጃ ሐመር የመጥቅዕና የዕለታት ተውሳክ ድምር ሆኖ አጽዋማትና በዓላት የሚውሉበትን ቀን ያመለክታል፡፡ በሐመር የተመሰለውም አጽዋማትና በዓላት ወደ ላይና ወደታች የሚመላለሱበት ሥርዓት /መርከብ/ ስለሆነ ነው፡፡

በአጠቃላይ መባጃ ሐመር ማለት የአጽዋማትንና የበዓላትን መዋያ ወይም መግቢያ ቀን ለማወቅ የሚያገለግል ልዩ ቁጥር ማለት ነው፡፡ [2]

ከሰባቱ አጽዋማት መካከል አራቱ በመባጃ ሐመር መሠረት በየዓመቱ እየተቀያየሩ ወይም ቀመር እየተሠራላቸው የሚወጡ ሲሆን፣ ሦስቱ ግን ያለ መባጃ ሐመር በየዓመቱ በተመሳሳይ ወቅት ይባጃሉ፡፡

በመባጃ ሐመር የሚባጁት አራት አጽዋማት ዐቢይ ጾም፣ ጾመ ድኅነት፣ ጾመ ነነዌና ጾመ ሐዋርያት ሲሆኑ፣ ያለ ማባጃ ሐመር በየዓመቱ ቋሚ ጊዜ ይዘው የሚብቱት ሦስቱ አጽዋማት ደግሞ ጾመ ነቢያት፣ ጾመ ገሃድና ጾመ ማርያም /ፍልሰታ/ ናቸው፡፡

ከላይ በተመለከትነው መሠረት መባጃ ሐመር የአጽዋማትና የበዓላት ማስገኛ ልዩ ቁጥር ነው ካልን ቁጥሩ እንዴት እንደሚገኝ ማወቅ ያስፈልገናል፡፡ መባጃ ሐመርን ለማግኘት መጥቅዕንና በዓለ መጥቅዕ የዋለበትን ዕለት ተውሳክ እንደምራለን፡፡ ይቆየን

ተውሳክ
ተውሳክ ማለት ለአንድ ጾም ወይም ለአንድ ዕለት የተሰጠ ልዩ ቁጥር (ኮድ) ማለት ነው፡፡ በዚህ ቁጥር መሠረትም አጽዋማትንና በዓላትን ማውጣት ይቻላል፡፡

ተውሳክ ማለት ጭማሪ፣ ተጨማሪ ማለት ሲሆን ለበዓላትና ለአጽዋማት ማውጫ ያገለግላል፡፡[3] እንዲል፡፡

መጥቅዕ ማለት ነጋሪት ወይም ደወል ማለት ነው፡፡ ነጋሪት ሲመታ፣ ደወል ሲደወል ሕዝብ ይሰበሰባል፤ መልእክትም ይተላለፋል፡፡ በዓላትና አጽዋማትም በመጥቅዕ ይሰበሰባሉ፤ መዋያቸውንም በዚህ ማወቅ ይቻላል፡፡ በዚህም መሠረት መጥቅዕ ከዕለታት ተውሳክ ጋር ተደምሮ መባጃ ሐመርን ያስገኛል፡፡

      መባጃ ሐመር = መጥቅዕ + በዓለ መጥቅዕ የዋለበት ዕለት ተውሳክ

መጥቅዕ= ያለፈው ዓመት መጥቅዕ + ጥንተ መጥቅዕ (ጥንተ መጥቅዕ በየዓመቱ የማይቀያየር ቁጥር ሲሆን ይኸውም 19 ነው፡፡)

መጥቅዕን በዚህ መንገድ ማግኘት ከቻልን፣ በዓለ መጥቅዕ እንዴት እንደሚገኝ አሁን እንመለከታለን፡፡

‹‹መጥቅዕ ሲበዛ ከመስከረም ንዛ፤ መጥቅዕ ሲያንስ ጥቅምትን ዳስ››

ይህ ታላቅ መልእክት ያለው የአባቶቻችን አባባል ሲሆን ለበዓለ መጥቅዕ ማውጫ የሚያገለግል ንግግራዊ ፎርሙላ ወይም ቀመር ነው፡፡ መጥቅዕ ሲበዛ ከመስከረም ንዛ ማለት በዓለ መጥቅዕን በጥቅምት አውል ማለት ሲሆን፣ መጥቅዕ ሲያንስ ጥቅምትን ዳስ ማለቱ መጥቅዕ ባነሰ ጊዜ በዓለ መጥቅዕን በጥቅምት አውለው ማለት ነው፡፡

መጥቅዕ በዛ የሚባለው ከዐሥራ አራት በላይ ሲሆን ነው፤ አነሰ የሚባለው ደግሞ ከዐሥራ አራት በታች ሲሆን ነው፡፡ በዚህም መሠረት መጥቅዕ ከዐሥራ አራት በላይ ከሆነ በዓለ መጥቅዕ በመስከረም ይውላል፤ መጥቅዕ ከዐሥራ አራት በታች ከሆነ ደግሞ በዓለ መጥቅዕ በጥቅምት ይውላል፡፡ ይህ ሁል ጊዜም ቢሆን የሚያገለግል ሕግ ነው፡፡ ለዚህም ነው አበው ‹‹መጥቅዕ ሲበዛ ከመስከረምንዛ፤ መጥቅዕ ሲያንስ ጥቅምትን ዳስ›› ያሉት፡፡

ለምሳሌ የ2011ን መባጃ ሐመር እንፈልግ፡፡

መባጃ ሐመርን ከመፈለጋችን በፊት ግን መጥቅዕን ማወቅ የግድ ነው፡፡ መጥቅዕን ለማወቅ ደግሞ የወንበርን ዓመታዊ ስሌት ማግኘት ያስፈልጋል፡፡ በመሆኑም፤

ወንበር = ቅልክ+ድልክ – 1

19

=5500+2011 -1

19

=395 ቀሪ 6-1

ወንበር =5

የ2011 ወንበር 5 ነው ማለት ነው፡፡

ከዚህ በመነሣት መጥቅዕን ለማግኘት፤

መጥቅዕ= ወንበር (ጥንተ መጥቅዕ)

= 5(19)

30

= 3 ቀሪ 5

መጥቅዕ = 5

መባጃ ሐመር = መጥቅዕ + በዓለ መጥቅዕ የዋለበት ዕለት ተውሳክ

መጥቅዕ = 5

በዓለ መጥቅዕን ለማግኘት፤ መጥቅዕ ከዐሥራ አራት በታች ስለሆነ ጥቅምት ላይ በዓለ መጥቅዕ ይውላል፡፡ ስለዚህ ጥቅምት 5 ሰኞ በዓለ መጥቅዕ ሲሆን፤ ይህ በዓለ መጥቅዕ የዋለበት ዕለት ሰኞ ተውሳኩ 6 ነው ማለት ነው፡፡

ስለዚህ፤

መባጃ ሐመር = መጥቅዕ + በዓለ መጥቅዕ የዋበት ዕለት ተውሳክ

መጥቅዕ = 5

በዓለ መጥቅዕ የዋለበት ዕለት = ሰኞ

የሰኞ ተውሳክ = 6

መባጃ ሐመር = 5 + 6 = 11

ስለዚህ የ2011 ዓ.ም መባጃ ሐመር 11 ስለሆነ በዚህ መሠረት የ2011ን በዓላትና አጽዋማት ማውጣት ይቻላል፡፡

የመባጃ ሐመር ዋነኛ አገልግሎት ከአጽዋማት ተውሳክ ጋር እየተደመረ በዓላትንና አጽዋማትን ማስገኘት ነው፡፡ ስለዚህ የአጽዋማትንና የበዓላትን ተውሳክ ማወቅ ይጠበቅብናል፡፡በመሆኑም መባጃ  ሐመሩንና የበዓላትና የአጽዋማትን ተውሳክ በመጠቀም የ2011ን የበዓላትና የአጽዋማትን መግቢያ እናገኛለን፡፡

ጾመ ነነዌ
ጾመ ነነዌ የራሱ የሆነ ተውሳክ የለውም፡፡ የሚወጣውም ያለ ተውሳክ በመባጃ ሐመር ብቻ ነው፡፡

ሀ. በዓለ መጥቅዕ በመስከረም በሚውልበት ጊዜ ጾመ ነነዌ በጥር ይውላል፡፡

ለ. በዓለ መጥቅዕ በጥቅምት በሚሆንበት ጊዜ ጾመ ነነዌ በየካቲት ይውላል፡፡

ሐ. መጥቅዕ ከ፲፬(14) በላይ ሆኖ ከዕለት ተውሳክ ጋር ስንደምረው ከ፴(30) ከበለጠ ጾመ ነነዌ በየካቲት ይውላል፡፡

ከላይ የተዘረዘሩት አራት ነጥቦች መቼም ቢሆን የማይለወጡ ቋሚ ሕጎች ናቸው፡፡ በመሆኑም እነዚህን አራቱን በቃል አጥንቶ መያዝ ያስፈልጋል፡፡

ምሳሌ፡- ከላይ የተመለከትነውን የ2011 ዓ.ምን ጾመ ነነዌ እናውጣ፡፡

መጥቅዕ 5 ሲሆን በዓለ መጥቅዕ ጥቅምት ሰኞ ነው፡፡ መባጃ ሐመሩ ደግሞ 11 ነው፡፡ ከላይ በ‹‹ለ››እንደተመለከትነው በዓለ መጥቅዕ በጥቅምት በሚሆንበት ጊዜ ጾመ ነነዌ በየካቲት ይውላል ብለናል፡፡ በተጨማሪም ጾመ ነነዌ ተውሳክ ስለሌላት በመባጃ ሐመርብቻ ነው የምትወጣ ብለናል፡፡ ስለዚህ መባጃ ሐመሩ 11 ስለሆነ የካቲት 11 ቀን ጾመ ነነዌ ትገባለች ማለት ነው፡፡

ዐቢይ ጾም
የዐቢይ ጾምን ተውሳክ ለማግኘት ከጾመ ነነዌ ማግስት ጀምሮ እስከ ዐቢይ ጾም ያሉትን ቀናት መቁጠር ነው፡፡ እኒህም ቀናት ፲፬(14) ናቸው፡፡ በመሆኑም የዐቢይ ጾም ተውሳክ ፲፬(14) ነው ማለት ነው፡፡

ለምሳሌ በ2011 ዓ.ም ዐቢይ ጾም የገባው፤

የዐቢይ ጾም መግቢያ = የ2011 ዓ.ም መባጃ ሐመር + የዐቢይ ጾም ተውሳክ

መባጃ ሐመር = 11

የዐቢይ ጾም ተውሳክ = ፲፬(14)

የዐቢይ ጾም መግቢያ = 11 + 14 = 25

የካቲት 25 የዐቢይ ጾም መግቢያ ነው ማለት ነው፡፡

ደብረ ዘይት
ከጾመ ነነዌ ማግስት እስከ ዐቢይ ጾም ያሉትን ቀናት ቆጥረን የዐቢይ ጾም ተውሳክ ፲፬(14) ነው ብለናል፡፡ የደብረ ዘይትን ተውሳክ ለማግኘትም በተመሳሳይ መልኩ ከጾመ ነነዌ ማግስት እስከ ደብረ ዘይት ያሉትን ቀናት ስንቆጥር ፵፩(41) ቀናትን እናገኛለን፡፡ ለ፴(30) ሲካፈል ቀሪ (፲፩)11ን እናገኛለን፡፡ ስለዚህ የደብረ ዘይት ተውሳክ ፲፩(11) ነው ማለት ነው፡፡

ደብረ ዘይት = የ2011 ዓ.ም መባጃ ሐመር + የደብረ ዘይት ተውሳክ

= 11 + 11

= 22

ከየካቲት ቀጥሎ ያለው ወር መጋቢት ስለሆነ መጋቢት 22 ደብረዘይት ነው ማለት ነው፡፡

ሆሣዕና
ከጾመ ነነዌ ማግስት እስከ ሆሣዕና ያሉት ቀናት ፷፪(62) ናቸው፡፡ እንደተለመደው ለ፴(30) ስናካፍለው ፪(2) ቀሪ እናገኛለን፡፡ በመሆኑም የሆሣዕና ተውሳክ (፪)2 ነው ማለት ነው፡፡

በ2011 ዓ.ም፤

ሆሣዕና መግቢያ = የ2011 ዓ.ም መባጃ ሐመር + የሆሣዕና ተውሳክ

= 11 + 2

= 13

ሚያዝያ 13 በዓለ ሆሣዕና ነበር ማለት ነው፡፡

ስቅለት
ከጾመ ነነዌ ማግስት እስከ ስቅለት ያሉት ቀናት ሥልሳ ሰባት ናቸው፡፡ ለሠላሳ ስናካፍለው ቀሪ ፯(7)ን እናገኛለን፡፡ በመሆኑም የስቅለት ተውሳክ ፯/7/ ነው ማለት ነው፡፡

በ2011 ዓ.ም፤

ስቅለት = የ2011 ዓ.ም መባጃ ሐመር + የስቅለት ተውሳክ

= 11 + 7

= 18

ሚያዝያ 18 ስቅለት ነው ማለት ነው፡፡

ትንሣኤ
ከጾመ ነነዌ ማግስት እስከ ትንሣኤ ያሉት ቀናት ሥልሳ ዘጠኝ ናቸው፡፡ ለሠላሳ ስናካፍለው ቀሪ ፱(9) እናገኛለን፡፡ በመሆኑም የትንሣኤ ተውሳክ ፱ (9) ነው ማለት ነው፡፡

በ2011 ዓ.ም፤

ትንሣኤ = የ2011 ዓ.ም መባጃ ሐመር + የትንሣኤ ተውሳክ

= 11 + 9

= 20

ሚያዝያ 20 ትንሣኤ ነው ማለት ነው፡፡

ርክበ ካህናት
ከጾመ ነነዌ ማግስት እስከ ርክበ ካህናት ያሉት ቀናት ፺፫(93) ናቸው፡፡ ለሠላሳ ስናካፍለውቀሪ ፫(3)ን እናገኛለን፡፡ በመሆኑም የርክበ ካህናት ተውሳክ ፫(3) ነው ማለት ነው፡፡

በ2011 ዓ.ም፤

ርክበ ካህናት = የ2011 መባጃ ሐመር + የርክበ ካህናት ተውሳክ

= 11 + 3

= 14

ግንቦት 14 ርክበ ካህናት ነው ማለት ነው፡፡

ዕርገት
ከጾመ ነነዌ ማግስት እስከ በዓለ ዕርገት ያሉት ቀናት ፻፰(108) ናቸው፡፡ ፻፰(108)ን ለ፴(30) ስናካ ፍለው ፫(3) ጊዜ ደርሶ ፲፰(18) ይቀራል፡፡ በመሆኑም የዕርገት ተውሳክ ፲፰(18) ነው ማለት ነው፡፡

በ2011 ዓ.ም፤

ዕርገት = የ2011 ዓ.ም መባጃ ሐመር + የስቅለት ተውሳክ

= 11 + 18

= 29

ግንቦት 29 ዕርገት ነው ማለት ነው፡፡

ጰራቅሊጦስ
ከጾመ ነነዌ ማግስት እስከ ጰራቅሊጦስ ያሉት ቀናት ፻፲፰(118)ናቸው፡፡ ፻፲፰(118)ን ለ፴(30) ስናካፍለው ፫(3) ቀሪ ፳፰(28) ይሆናል፡፡

፳፰(28) የጰራቅሊጦስ ተውሳክ ይሆናል፡፡

በ2011 ዓ.ም፤

ጰራቅሊጦስ = የ2011 ዓ.ም መባጃ ሐመር + የጰራቅሊጦስ ተውሳክ

= 11 + 28

= 39

ለ፴(30) ሲካፈል 9 ቀሪ ይሆናል፡፡ ጰራቅሊጦስ ሰኔ 9 ነው ማለት ነው፡፡

ጾመ ሐዋርያት
ከጾመ ነነዌ ማግስት እስከ ጾመ ሐዋርያት ያሉት ቀናት ፻፲፱(119) ናቸው፡፡ ፻፲፱ (119)ን ለ፴(30) ስናካፍለው ፫(3) ጊዜ ደርሶ ፳፱ (29) ይቀራል፡፡

፳፱(29) የጾመ ሐዋርያት ተውሳክ ነው ማለት ነው፡፡

በ2011 ዓ.ም፤

ጾመ ሐዋርያት = የ2011 ዓ.ም መባጃ ሐመር + የጾመ ሐዋርያት ተውሳክ

= 11 + 29

= 40

40 ለ30 ሲካፈል 1 ቀሪ 10 ይሆናል፡፡

ስለዚህ ሰኔ 10 የጾመ ሐዋርያት መግቢያ ነው ማለት ነው፡፡

ጾመ ድኅነት
ከጾመ ነነዌ ማግስት እስከ ጾመ ድኅነት ያሉት ቀናት ፻፳፩(121) ናቸው፡፡ ፻፳፩(121) ለ፴(30) ሲካፈል ፬(4) ጊዜ ደርሶ ፩(1) ይቀራል፡፡ የጾመ ድኅነት ተውሳክ ፩(1) ነው ማለት ነው፡፡

በ2011 ዓ.ም፤

ጾመ ድኅነት = የ2011 ዓ.ም መባጃ ሐመር + የጾመ ድኀነት ተውሳክ

= 11 + 1

= 12

ሰኔ 12 የጾመ ድኅነት መግቢያ ዕለት ነው ማለት ነው፡፡

በአጠቃላይ የአጽዋማቱ ተውሳክ እንደሚከተለው ነው፡፡

አጽዋማት       ተውሳክ           የመዋያ ዕለት

ጾመ ነነዌ        = አልቦ (0)         የካቲት 11

ዐቢይ ጾም        = ፲፬(14)           የካቲት 26

ደብረ ዘይት       = ፲፩(11)          መጋቢት 22

ሆሣዕና          = ፪(2)             ሚያዝያ 13

ስቅለት           = ፯(7)             ሚያዝያ 18

ትንሣኤ          = ፱(9)             ሚያዝያ 20

ርክበ ካህናት      = ፫(3)             ግንቦት 14

ዕርገት           = ፲፰(18)          ግንቦት 29

ጰራቅሊጦስ       = ፳፰(28)          ሰኔ 9

ጾመ ሐዋርያት    = ፳፱(29)          ሰኔ 10

ጾመ ድኅነት       = ፩(1)            ሰኔ 12

ኢየዐርግና ኢይወርድ
እነዚህ አጽዋማት ምንም እንኳን በየዓመቱ የየራሳቸው ቀመራዊ ማውጫ ቢኖራቸውም ገደብ ግን አላቸው፡፡ ገደባቸውም በግእዝ ኢይወርድና ኢየዐርግ ሲባል፣ ኢይወርድ የታችኛው እርከን፣ ኢየዐርግ ደግሞ የላይኛው እርከን ነው፡፡ በአማርኛው ገደብ ልንለው እንችላለን፡፡ በዚህም መሠረት የአጽዋማት ገደብ የሚከተለውን ይመስላል፡፡

አጽዋማትና በዓላት          ኢይወርድ    ኢየዐርግ

ጾመ ነነዌ             ጥር 17             የካቲት 21

ዐቢይ ጾም           የካቲት 1             መጋቢት 5

ደብረ ዘይት          የካቲት 28            ሚያዝያ 2

ሆሣዕና             መጋቢት 19           ሚያዝያ 23

ስቅለት          መጋቢት 24           ሚያዝያ 28

ትንሣኤ            መጋቢት 26           ሚያዝያ 30

ርክበ ካህናት        ሚያዝያ 20             ግንቦት 24

ዕርገት             ግንቦት 5                ሠኔ 9

ጰራቅሊጦስ         ግንቦት 15               ሠኔ 19

ጾመ ሐዋርያት      ግንቦት 16               ሠኔ 20

ጾመ ድኅነት        ግንቦት 18               ሠኔ 22

ቋሚ የመግቢያ ጊዜ ያላቸው አጽዋማት
                               ጾመ ነቢያት
ጾመ ነቢያት በአራቱም ዘመናት ምን ጊዜም ኅዳር ዐሥራ አምስት እንዲጾም ተወስኗል፡፡

                                   ጾመ ገሀ  ድ
ጾመ ገሀድ የትክ ጾም ነው፡፡ ይህ ጾም ዓርብንና ሮብን የሚያሽር በዓል በዓርብና በሮብ ሲውል በትኩ በዋዜማው የሚጾም ጾም ነው፡፡ ለምሳሌ ጥምቀት ዓርብ ቢውል ሐሙስ ጾመ ገሀድ ይሆናል፡፡ ነገር ግን አበው ለጾም ማድላት አለብን በማለት ጾመ ገሀድ ምንጊዜም ጥምቀት በጾም ቀን ዋለም አልዋለም በዋዜማው እንዲጾም ወስነዋል፡፡

                                   ጾመ ፍልሰታ 
ሐዋርያት የእመቤታችንን ትንሣኤ ለማየት ይበቁ ዘንድ ሱባኤ ገብተው የጾሙት ጾም ሲሆን ምንጊዜም ነሐሴ አንድ ቀን ገብቶ ከሁለት ሱባኤ በኋላ የእመቤታችን ዕርገት ይፈጸማል፡፡

[1]  አቡሻኸር አንቀጽ 1 ገጽ 17 (የብራና ጽሑፍ)

[2] ዲ/ን ታደለ ሲሳይ ባሕረ ሐሳብ በቀላል አቀራረብ ገጽ 71

[3]  ዝኒ ከማሁ ገጽ 66

ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በኢትዮጵያ ሶማሌ ክልል በተፈጠረው ችግር የተሰጠ መግለጫ

Betekihenet megelecha

ሐምሌ 23 ቀን 2010 ዓ.ም የተካሄደው የቅዱስ ሲኖዶስ አስቸኳይ ምልዓተ ጉባኤ በአባቶች ላይ በተለያየ ወቅት ያስተላለፈውን ቃለ ውግዘቱን አንስቷል

ሐምሌ 23 ቀን 2010 ዓ.ም የተካሄደው የቅዱስ ሲኖዶስ አስቸኳይ ምልዓተ ጉባኤ በአባቶች ላይ በተለያየ ወቅት ያስተላለፈውን ቃለ ውግዘቱን አንስቷል፡፡ሙሉ ውሳኔው እንደሚከተለው ነው

የአባቶች ዕርቀ ሰላም መፍጠር፤ ለቤተ ክርስቲያንሐዋርያዊ አገልግሎትና ለሀገራዊ መግባባት ወሳኝ ሚና አለው!

 

በዮሐንስ አፈወርቅ

ቅድስት ቤተ ክርስቲያን መሠረቷኗ ጉልላቷ ክርስቶስ በመሆኑ የሰላም ደጅ ናት፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ለተሰሎንቄ በጻፈው መልእክቱ “የሰላምም ጌታ ራሱ በሁሉ መንገድ ዘወትር ሰላምን ይስጣችሁ፡፡ ጌታ ከሁላችሁ ጋር ይሁን፡፡” (2ኛ ተሰሎ 3፡16) እንዳለ በክርስቶስ ሰላም እየተጠበቀች አንድነቷ ላይ የሚያጋጥሟትን ፈተናዎች ሁሉ እየተቋቋመች አገልግሎቷን በማስፋፋት ምእመናንን ትጠብቃለች፡፡ አባቶችም ከቤተ ክርስቲያን የተቀበሉትን አደራ ተግተው በመጠበቅ መንጋውን በክርስቶስ ሰላም ማጽናት ይኖርባቸዋል፡፡ የቤተ ክርስቲያን አባቶች ቤተ ክርስቲያንን ይጠብቁ ዘንድ ለመንጋውና ለራሳቸውም መጠበቅ ጥንቃቄ ያደርጉ ዘንድ የእግዚአብሔር ቃል ያስተምረናል፡፡ «በገዛ ደሙ የዋጃትን የእግዚአብሔርን ቤተ ክርስቲያን ትጠብቁአት ዘንድ፣ መንፈስ ቅዱስ እናንተን ጳጳሳት አድርጐ ለሾመባት ለመንጋው ሁሉና ለራሳችሁ ተጠንቀቁ» ሐዋ 20፡28
በመሆኑም የቤተ ክርስቲያን ጭንቀቷ ለጊዜያዊውና ለሚያልፈው ሳይሆን ለዘላለሙ፣ ለምድራዊው ሳይሆን ለሰማያዊው ሕይወት በመሆኑ፣ ዓለሙ ከሚከፋፈልበት የዘር፣ የጐሳ፣ የቋንቋና የርዕዮተ ዓለም አመለካከት ልዩነቶች የራቀች መሆን ይጠበቅባታል፡፡ የመንፈስ ልጆቿን ከአብራከ መንፈስ ቅዱስ ከማኅፀነ ዮርዳኖስ ወልዳ ከማይጠፋ ዘር በክርስቶስ ሥጋና ደም አንድ አድርጋ የምትመራ ለአንድና ለማያልፍ የእግዚአብሔር መንግሥት የምትሠራ ነፍሳትንም ለዚህ ክብር የምታዘጋጅ ናት፡፡ ቤተ ክርስቲያን ጉልላቷ አንድ በመሆኑ፣ ልጆቿ ሁሉ በእግዚአብሔር ቅዱስ መንፈስ የአንድ አካል ብልቶች እንዲሆኑ ትሠራለች፡፡ ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን አንድነት እንቅፋት የሚሆኑ ነገሮች ሁሉ፣ ትእዛዛተ እግዚአብሔርን የሚፃረሩ በመሆናቸው፤ ለጥላቻዎችና መለያየቶች መንስኤ የሆኑ ነገሮችን አጥርቶ ማየትና መፍትሔ ለመስጠት መሄድ ሕገ እግዚአብሔርን መፈጸም ነው፡፡
ጥላቻዎችና መለያየቶች ሰላመ ቤተክርስቲያንንና ሕዝበ እግዚአብሔርን የሚያውኩ በመሆናቸው፣ በእነዚህ አትራፊ የሚሆነው፣ ጥንተ ጠላታችን ዲያብሎስ ብቻ እንጂ፤ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንና ተከታዮቿ የሆኑት ሕዝበ እግዚአብሔር አይደሉም፡፡ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ዓለሙ የሚለያይባቸውን ነገሮች የምታወግዝ እንጂ፣ አካሏን ለሚለያይና ፍቅርን ለሚያደበዝዙ ክፍተቶች አሳልፋ መተው የለባትም፡፡ እንኳን የራስን አካል ቀርቶ ቃሉ ጠላትንም መውደድ እንዲገባን ያስተምረናል፤ “እኔ ግን እላችኋለሁ በሰማያት ላለ አባታችሁ ልጆች ትሆኑ ዘንድ ጠላቶቻችሁን ውደዱ የሚረግሙአችሁን መርቁ ለሚጠሏችሁም መልካም አድርጉ ይላልና—“ (ማቴ 5፡44-45) ክርስቲያኖች ሁሉ እውነተኛ ጨው ሆነን ዓለሙን ማጣፈጥ ሲገባን ይህን ቸል ብለን መንጋውን ለዓለሙ ክፉ ሐሳብ፤ መለያየትና ለዘረኝነት መራራ ፍሬ አሳልፈን እንዳንሰጥ መጠንቀቅ ይገባናል፡፡
ቅዱሳን ሐዋርያት ለዓለሙ ጨው ሆነው የወንጌልን ፋና ያበሩት፣ በአንድ ልብ ሆነው በጸሎትና በጾም በመትጋታቸው የመንፈስ ፀጋን በመጎናጸፋቸው ነው እንጂ፤ እርስ በርሳቸው በመለያየት አይይደለም፡፡ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን፡- በአጥቢያዎች፣ በወረዳና በአህጉረ ስብከት የተደራጀች ስትሆን፤ እነዚህ መዋቅሮቿ፣ ጉልላቷና መሠረቷ የሆነውን የጌታችንና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስን ትእዛዛት፣ መርሓቸው አድርገው የሚሄዱ እንጂ «ከእርሱም የተነሣ አካል ሁሉ እያንዳንዱ ክፍል በልክ እንደሚሠራ፣ በተሰጠለት በጅማት ሁሉ እየተጋጠመና እያተያያዘ፣ ራሱን በፍቅር ለማነፅ አካሉን ያሳድጋል» ኤፌ 4፡16 ተብሎ የተጻፈውን በመቃረን፣ በየራሣቸው የሚመሩ፣ የማይነጋገሩና የማይተጋገዙ፣ አንዱ ለሌላኛው ግብኣት የማይሆኑ ብልቶች ሆነው በየግላቸው የሚጓዙ አይደሉም፡፡
ከቅድስት ቤተ ክርስቲያን አንድነት የሚያርቁ ምክንያቶችና ክስተቶች፣ የክርስቶስ አካል በሆነችው የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሉዓላዊነት ላይ ተፅዕኖ የሚፈጥሩ ስለሆኑ፤ እነዚህን ምክንያቶችና ሁኔታዎች እያንዳንዳችን ትኩረት ሰጥተን መመርመርና ማየት ይገባናል፡፡ በመሆኑም ፈራጅ በመሆን ብቻ ወይም አጋጣሚውን ለየግል ፍላጐታችን መጠቀሚያ በማድረግ፡- መለያየትንና ጥላቻን የምናበረታታና የምናሣድግ፣ በአጠቃላይም ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን የማይጠቅሙ ነገሮች እድል እንዲያገኙና ተደብቀው እንዲያድጉ፣ በቸልተኝነት ቀዳዳ የምንፈጥር እንዳንሆን መጠንቀቅ ይገባናል፡፡
ዓለሙ በራሱ ፍልስፍናና ምድራዊ ጥበብ፣ ሕግጋተ እግዚአብሔርን ባለመጠበቅ፣ የቅድስት ቤተክርስቲያንን ህልውና ለራሱ በሚመቸውና በሚጠቅመው መንገድ እንዲሆንለት ይሠራል፡፡ ጥበብ ምድራዊን መርሑ አድርጐ የሚሄድ ሰው ወይም አካል፡- የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ሉዓላዊነት ዕውቅና ሰጥቶ ከመጠበቅ ይልቅ፣ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ለእርሱ ተገዢና ዓላማ ማስፈጸሚያ እንድትሆንለት ይሻል፡፡ በዚህ ጊዜም የቅድስት ቤተክርስቲያን አባቶች በጥበብ ምድራዊ አመለካከት የሚገጥማቸውን ፈተና በጸሎት ተግተው፣ እየተመካከሩ ድል ያደርጉታል እንጂ፣ ፈተናው ከራሳቸው አልፎ የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን አንድነት፣ ህልውናና አገልግሎት እንዲገዳደር ዕድልና ቀዳዳ የሚፈጥሩለት አይሆኑም፡፡
የቤተ ክርስቲያንን አድነት ለማስጠበቅ አባቶች፡- ፈቃድ፣ አቅጣጫ፣ ኃይልና ጥበብ የሚጠይቁት፣ የቅድስት ቤተ ክርስቲያን መሪ ከሆነው ከመንፈስ ቅዱስ እስከሆነ ድረስ፤ የዓለሙን ፍላጐትና ሐሳብ የሚከተል፣ በእርሱም ተጠልፎ የሚወድቅ አይደለም፡፡ የቅድስት ቤተ ክርስቲያን አባቶች ሕይወትና ሥራ ሙሉ ለሙሉ የእግዚአብሔርን ክብርና የቤተክርስቲያንን ደኅንነት ቅድሚያ ሰጥቶ ለማረጋገጥ የቆመና ቁርጠኝነት ያለው ሲሆን፤ የዓለሙ ፍላጐት፣ ተፅዕኖ ሊያሳርፍበት አይገባም፡፡
የቅድስት ቤተ ክርስቲያን አንድነት፡- በጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መሠረትነት ላይ የታነፀ፣ መንገዱም፡- ግልፅ፣ አንድና የቀና እንጂ፤ ለግል አመለካከትና ፍላጐት ተገዢ የሚይሆን፤ በፈለግን ጊዜ የምንሄድበት? ባልፈለግን ጊዜ ደግሞ መዝጋትም ሆነ መገደብ የምንችለው አይደለም፡፡ ይህ ደግሞ «ማንም እራሱን አያታል፤ ከእናንተ ማንም በዚች ዓለም ጥበበኛ የሆነ ቢመስለው፣ ጥበበኛ ይሆን ዘንድ ሞኝ ይሁን» 1ቆ 3፡18 ተብሎ እንደተጻፈው የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ህልውና የሚፈታተኑ ነገሮችና ሐሳቦች በሚፈጠሩበት ጊዜ፣ በመግባባትና በመተማመን ለመፍታት መሄድ ይገባል እንጂ፣ በራሳችን ጥበብ ጌታችን በሥጋና በደሙ ለመሠረታት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን አንድነትና ሰላም መጠናከር አስተዋጽኦ ለማያደርጉ ሁኔታዎች አሳልፈን የምንሰጥ እንዳንሆን መጠንቀቅ ይገባናል፡፡
አባቶች የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ሰላም፣ ሉዓላዊነትና አንድነት ጠንክረው የሚያስከብሩ በሚሆኑበት ጊዜ፣ ምእመናን ለፈተና ባለመጋለጥ ጸንተው በአጸዷ ውስጥ ለመኖር ያግዛቸዋል፡፡ በዓለሙ ያሉ ሰዎችም፣ ለአባቶች ክብር እንዲሰጡ ያደርጋቸዋል፡፡ አባቶች ሲናገሩ ተደማጭነትን፣ ሲመክሩ ደግሞ ተሰሚነትን ከሕዝቡ ሁሉ እንዲያገኙ ይረዳቸዋል፡፡ «የራሷ ሲያርባት የሰው ታማስል» የሚለው አባባል ሳይጠቀስባቸው፣ ከራሳቸው በመትረፍ፣ በሀገሪቱ ችግሮች አፈታት ላይ ከፍ ያለ ቦታና ተፈላጊነት ያላቸው እንዲሆኑ ያደርጋቸዋል፤ ክብርና ሞገስም ያስገኝላቸዋል፡፡ ብዙዎችን በፍቅር መሸምገል የሚገባው እርሱ ለሽምግልና አስቸጋሪ ሊሆን አይገባም፡፡ ክርስትና በተግባር የሚታይ ሕይወት ነውና፡፡
ቤተ ክርስቲያን አንዲት ሆና እያለች «የውጪ እና የሀገር ውስጡ ሲኖዶስ» በሚል ሐዋርያዊ አገልግሎቷና የምእመናን አስተዳደሯ እርስ በርሳቸው በማይመካከሩና አንዱ ለሌላኛው ዕውቅና በማይሰጣጡ አካላት ለመምራት ሲኬድ የቆየ መሆኑ የታወቀ ነው፡፡ ይህ ደግሞ በቤተ ክርስቲያን አገልግሎትና በምእመናን ሕይወት ላይ ከፍተኛ ችግር ፈጥሮ ቆይቷል፡፡ በመሆኑም እያንዳንዳችን ለችግሩ መፈጠር በቀጥታ ምክንያት ላንሆን ብንችል እንኳ፤ ከክስተቱ በኋላ ከትእዛዛተ እግዚአብሔርና ከሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን አንጻር ተመልክተን ለተፈጠረው ችግር መፍትሔ ለመስጠት በሚገባው መጠን ያህል ያልሄድን፤ ለቅድስት ቤተክርስቲያን አንድነት ቅድሚያ ባለመስጠት በቸልተኝነት ሁኔታው እየተባባሰ እንዲሄድ ያደረግን፤ ወይም ችግሩን መንፈሳዊ ከሆኑ አቅጣጫዎች ይልቅ፣ ዓለማዊና ግላዊ ከሆኑ ነገሮች አንፃር ስንመለከተው የቆየን ከሆነ፤ ለተፈጠረው ችግር የሚመለከተን ሁሉ ከሚጠበቅብን አንፃር፣ ባለድርሻዎች ናችሁ ብንባል፤ ቢያንሰን እንጂ የሚበዛብን አይሆንም፡፡
በቤተ ክርስቲያን አስተዳደር መለያየት ምክንያት በውጭ ያሉ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አድባራት፡- በሀገር ውስጥ ባለው ሲኖዶስ የሚመሩ፣ በውጭ ሀገር የተቋቋመውን ሲኖዶስ እንደግፋለን በሚሉና ከሁለቱም ሳይሆኑ ገለልተኛ ነን በሚሉ ሦስት ቡድኖች ተከፋፍለው የሚገኙ ሆነዋል፡፡ የዚህ ሁሉ ክፍፍል መንስኤው፣ የተፈጠረውን ችግር በወቅቱ ሃይማኖታዊ በሆነ መንገድ ፈቶ መሄድ ባለመቻሉ፣ ማለትም የአንድነት አለመኖር ውጤቱ ምን ሊሆን እንደሚችል ግልጽና የታወቀ ነውና፣ በመንፈሳዊነት ማሸነፍና መሸናነፍ ባለመቻሉ፣ ዓለማዊ የሆኑ ፍላጐቶችና ተፅዕኖዎች አይለውና ተሰሚነት አግኝተው በመቆየታቸው ነው፡፡ አሁንም ይህ መከፋፈል ካልተገታ፣ አሁን ካለው እያደገ በመሄድ፣ ብዙ ውስብስብና አስፈላጊ ያልሆኑ ሁኔታዎችን ሊፈጥር ይችላል፡፡
የቅድስት ቤተ ክርስቲያን አባቶችና ምእመናን ዘመኑን የዋጁ ካልሆኑ፣ የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ጉዳዮች፣ ዓለማዊ የሆኑ ፍላጐቶችና ተፅዕኖዎች ምን ጊዜም መፈታተናቸው የማይቀር ነው፡፡ በዚህ ጊዜም፡- ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሰላም፣ አንድነትና ህልውና ጠቃሚ የሆኑ ነገሮችን እየወሰድንና እየተባበርን የቅድስት ቤተክርስቲያን አንድነት የተጠናከረ፣ አገልግሎቷ የሰመረ፣ ምእመኖቿ በመንፈስ ቅዱስ መሪነትና በማንኛውም አቅም የተሰናሰሉና የጠነከሩ፣ ተስፋ መንግሥተ ሰማያት ያላቸው እንዲሆኑ፣ ዕንቅፋቶችን ሁሉ ማስወገድ እንደየድርሻችን የሁላችንም ተግባር ነው፡፡ ይህንን መፈጸም አባቶችና ምእመናን ከራሳቸው በማለፍ ለሀገሪቱ ዕድገትና ሰላም ድርሻቸው የላቀ እንዲሆን፤ ባጠቃላይም የሀገርን ችግር በመፍታቱ በኩል የሚኖራቸው ተፈላጊነትና ድርሻ ከፍ ያለ ደረጃ እንዲኖረው ያደርጋል፡፡
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በውጪ ሀገር ካሉ የቅድስት ቤተ ክርስቲያን አባቶች ጋር መግባባት እንዲኖር በተለያዩ ጊዜያት የዕርቀ ሰላም ልዑካንን በመላክ፣ በውጭ ሀገር ያሉ አባቶችም ለድርድር ፈቃደኛ በመሆን፣ ውይይቶች እየተጀመሩ እልባት ላይ ሳይደረስ፣ እንዲሁ ይቀሩ የነበረ መሆኑ ይታወቃል፡፡ በቅርቡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ በጥቅምት 2ዐ1ዐ ዓ.ም. ባደረገው መደበኛ ጉባኤው፣ አጀንዳ ቀርጾ ካስተላለፋቸው ውሳኔዎች መካከል፡- በውጭ ሀገር ካሉ የቅድስት ቤተ ክርስቲያን አባቶች ጋር ተጀምሮ የነበረው የዕርቀ ሰላም ድርድር ቀጥሎ መፍትሔ እንዲያገኝ የሚለው አንዱ ነው፡፡ ነገሩ ሁለት ዐሥርት ዓመታትን ያሳለፈ ስለሆነ፣ እንደ ጉዳዩ አሳሳቢነት በፍጥነት እየተሄደበት ነበር ባይባልም፣ ውሳኔውን ተግባራዊ ለማድረግ በቋሚ ሲኖዶሱ አስፈላጊው ዝግጅት ሲደረግበት ከቆየ በኋላ፣ በአሁኑ ሰዓት ለሕዝበ ክርስቲያኑና ለሚመለከታቸው አካላት ግልጽ ተደርጐ፣ በሁለቱም ወገን ተወያይ የሆኑ አባቶች እና የዕርቀ ሰላም ኮሚቴው ለዝግጅቱ ደፋ ቀና በማለት ላይ ይገኛሉ፡፡
የምንስማማውና ዕርቅ የምናደርገው፡- ያስቀየምንና የተቀየምን፣ የበደልንና የተበደልን፣ ይቅር ልንልና ልንባባል ነው፡፡ በአባቶች መካከል ለተፈጠረው አለመግባባት ዕርቀ ሰላም የምናደርገው በሐዋርያት ሥራ 2ዐ፡28 እንደተገለጸው፣ ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለአባቶች የሰጠው የኖላዊነት ተግባር በአግባቡ ይፈጸም ዘንድ ነው፡፡ በዚህም፡- ምእመናን ወደ ለመለመው መስክ ሊመራቸው የሚገባ ጠባቂ በማጣት ለነጣቂ ተኩላ ሳይጋለጡ፤ በአንድ በረት ውስጥ ተጠብቀው፣ የመንግሥተ ሰማያት ወራሾች ይሆኑ ዘንድ ለማስቻል፣ ዕንቅፋት የሚሆኑ ነገሮችን ጊዜና ፋታ ሳይሰጡ ማስወገድና ማስተካከል የትጉህ እረኛ ተግባር ነው፡፡
ከዚህ አኳያም፡- የቅድስት ቤተ ክርስቲያን አባቶች የዓለሙን ክብርና ጥቅም ንቀው የሚተጉ ናቸውና፤ በድርድራቸው ላይ የሚያስቀድሙት የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ፍላጐትና ህልውና ስለሆነ፤ መግባባት የማይችሉባቸው ነጥቦች ይኖራሉ ተብሎ አይጠበቅም፡፡ አባቶች ተለያይተው በመቆየታቸው አንዳቸው በሌላኛው ላይ የሚያነሷቸው ነጥቦች ሊኖሩ ቢችሉ እንኳ፣ ለቤተ ክርስቲያን ዕድገትና ህልውና ተፃራሪና ድብቅ የሆነ ነገር በመካከላቸው የሌለ እስከሆነ ድረስ፣ ይቅር ለመባባል በግንባር ቀደምትነት መቀመጥ ከሚገባቸው የጋራ መርሖዎች (የማስማሚያ ነጥቦች) በተጨማሪ፡- በቀጣይ መስተካከልና መታረም ያለባቸውን ቀሪ ዋና ዋና ነገሮች ርእሰ ጉዳይ አስቀድሞ ለይቶ በጥቅሉ በመያዝ፣ ከይቅር መባባሉ በኋላ በአደራዳሪዎች አማካኝነት በዝርዝር በመነጋገር እየፈቱ ለመሄድ፣ ከወዲሁ ሥርዓት ማበጀት አጋዥነት ያለው ነው፡፡ ርእሰ ጉዳያቸው በቅድሚያ ተመዝግቦ በቀጣይነት ለሚነሡ ነጥቦች ሁሉ፣ የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሕግና ሥርዓት፣ ገዢነትና መሪነት ያለው በመሆኑ፤የዕርቀ ሰላሙ ሂደት የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ያልሆነ፣ የግልም ሆነ የቡድን ፍላጐት፣ አቋምና አካሔድ ጥላ ሊያጠላበት የሚችል አይደለም፡፡ዋናው ነገርም ዕርቀ ሰላሙን አጽንቶ ለመሄድ፣ በልዩነቱ ጊዜ ውስጥ የተፈጠሩ መታረም፣መታየትና የጋራ መደረግ ያለባቸውን ሁኔታዎችና አሠራሮች፣ከሁሉም ወገን ሰብስቦ፣በአደራዳሪ ሽማግሌዎች አማካኝነት ቅቡልነት ያለው አቅጣጫ እንዲያዝባቸው ማድረግ ነው፡፡
ስለ ዕርቀ ሰላሙ አስፈላጊነት፣ የአፈጻጸም ቅደም ተከተል፣ ስለ ምእመናንና የካህናት ድርሻ፣ በደንብ ታስቦበት በተዘጋጀ ሁኔታ፣ በየጊዜው በተለያዩ የመገናኛ ዘዴዎች ሂደቱ ስለሚገኝበት ደረጃ መግለጫዎችንና መረጃዎችን መስጠት፣ የዕርቀ ሰላም ኮሚቴው ተግባር ለውጤቱም አጋዥነት ያለው ነው፡፡ ከዚህ በተጨማሪም በሁለቱም ወገን ለመነጋገርና በመሃል ላይ ሆኖ ለማነጋገር የምንቀርብ አባቶችና የሀገር ሽማግሌዎችም፣ ከዚህ በፊት ተጀምረው የነበሩ ውይይቶች ውጤት ያላመጡት ለምንድን ነው? በሁለቱም ወገኖች አቀራረብ ላይ የነበረው ጠንካራና ደካማ ጐን ምን ነበር? አሁን በቀጣይ ለሚደረገው ምክክር፣ ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን አንድነት መጠናከር ሲባል በእኔ/በእኛ በኩል፣ ተስተካክሎ መቅረብ የሚገባው አቋም ምንድን ነው? ብሎ በተለያዩ የአማራጭ አቅጣጫዎች አስቀድሞ በግልና በቡድን ደረጃ ማየት፣ መዘጋጀትና መሥራት አስፈላጊ ነው፡፡
ሰላመ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን፣ ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለእኛ ሲል ትልቅ ዋጋ የከፈለበት ሀብተ ክርስትናችን ስለሆነ፣ የምናጸናው አባቶችና ምእመናን ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን ህልውና በእውነት በመትጋት በአንድነት ሆነን እንደየድርሻችን አገልግሎቷን ስንፈጽም ነውና፤ ዕርቀ ሰላሙ ጊዜ የሚሰጠው አይደለም፡፡ በተለይም መለያየትን መግቢያ ቀዳዳው በማድረግ ጠላት ዲያብሎስ የራሱን ተልዕኮ ለመፈጸምና ለማስፈጸም ወደ ኋላ አይልምና፤ ዕርቀ ሰላሙን ዳር ለማድረስ ባለፉት ዓመታት ውጤታማ መሆን ባይቻልም፤ ከሚመጣው 2ዐ11 ዓ.ም. መቅደም መቻል ብልህነት ነው፡፡ ስለሆነም ኅብረታችን የቤተ ክርስቲያንን ተልእኮ ከሚያፋጥኑ ጋር እንጂ፤ በውስጧ ሆነው ከሚቦረቡሯት የተሐድሶ መናፍቃን ጋር አይደለምና፤ በሀገር ውስጥም ሆነ በውጪ፣ የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን አስተዳደር፣ ሐዋርያዊ አገልግሎቷን፣ አንድነቷንና ዐቅሟን ለማጠናከር የሚረዱ ነገሮችን ለመፈጸም፣ ኃይለ እግዚአብሔርን አጋዥ አድርጐ መንቀሳቀስ ዘመኑን መዋጀት ነው፡፡
የቅድስት ቤተ ክርስቲያን አንድነትና ዐቅም እንዲጠናከር በተቻለው መጠን እየሠራ ያለው ማኅበረ ቅዱሳንም፣ በአባቶች መካከል ተፈጥሮ መፍትሔ ሳይሰጠው የቆየው መለያየት፣ ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን አይጠቅምም በማለት አቋሙን ሲገልጽ ቆይቷል፡፡ ለምሳሌም በሐመር መጽሔት ላይ ብቻ ካስተላለፋቸው መልእክቶች መካከል፣ ይህን ጉዳይ በተመለከተ ከወጡት ላይ የተወሰኑትን ብንመለከት፡- በ1999 ዓ.ም. ሐመር 15ኛ ዓመት ቁጥር 1 የጥርና የካቲት ዕትም ላይ፣ ከቅርብ ዓመታት በፊት በ2ዐዐ5 ዓ.ም. ላይ ደግሞ በሐመር 2ዐኛ ዓመት ቁጥር 5 መስከረም ወር ዕትም ላይ «ለቤተ ክርስቲያናችን አንድነት፣ ዕርቅና ሰላም መሠረት ናቸው» በሚል ርእስ እንዲሁም በሐመር 2ዐኛ ዓመት ቁጥር 6 የጥቅምት ወር ዕትም ላይ፡- ወቅቱ ፓትርያርክ አቡነ ጳውሎስ ከዚህ ዓለም በሞት በመለየታቸው ምክንያት በምትካቸው ሌላ ፓትርያርክ ለመሾም ጥረት እየተደረገበት የነበረ ጊዜ በመሆኑ «ከሁሉም ነገር በፊት ዕርቀ ሰላም፣ ማሠራቱ የተረጋገጠለት ሕገ ቤተክርስቲያንና የምርጫ መመሪያ ያስፈልጋል» በማለት መልእክት አስተላልፏል፡፡ አሁንም ቢሆን ማኅበሩ ዕርቀ ሰላሙ የተሳካ እንዲሆን ጽኑ የሆነ ፍላጐት ያለው ስለሆነ፤ የሚችለውን ድጋፍ ለማድረግና በአባቶች የሚታዘዘውን በዐቅሙ ለመፈጸም ዝግጁ መሆኑን ይገልጻል፡፡
በአጠቃላይም፡-
1. የዕርቀ ሰላሙ ድርድር የሚጀመረው በጸሎትና በአባቶች ቡራኬ በመሆኑ፤ ሕዝበ ክርስቲያኑም መለያየቱ ዓመታትን በመውሰዱ ላይ እያዘነ ስለሆነ፤ የሚታረቁና የሚያስተራርቁ ብፁዓን ናቸው ተብሎ በተጻፈው መሠረት እኛ ፈቃደኞችና ቁርጠኞች እስከሆን ድረስ፣ ፈቃደ እግዚአብሔር የማይለየን ስለሆነ፣ ዕርቀ ሰላሙ ይሳካል ብሎ በሙሉ ልብ መጀመር፡፡
2. ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ለሀገሪቱ ሰላምና አንድነት ብዙ እንዳላበረከተች ሁሉ፤ አጀንዳ ሁኖ የሚገኘውን ይህን የራሷን ጉዳይ ሳትፈታ መቆየቷ፣ የሰላም ባለቤት የሆነውን እግዚአብሔር የማያስደስት፣ ያላትን ክብርና ዝና ዝቅ የሚያደርገው ስለሆነ፤ በሀገራችን ውስጥ ሲንፀባረቅ ለቆየው የመለያየት መንፈስ፣ እኛም በየፊናችን አስተዋጽኦ አላደረግንም ወይ? ብሎ ራስ ራስን መጠየቅ፡፡

3. ዕርቀ ሰላሙ፣ በውጭ ሀገርና በሀገር ውስጥ ባለው ሕዝበ ክርስቲያን በጉጉት የሚጠበቅ ቢሆንም፤ ከዚህ በፊትም ከ2 ጊዜ በላይ የተደረጉ ጥረቶች ውጤታቸው እና ችግራቸው ምን እንደሆነ ሳይታወቅ እንዲሁ የቀረ ነው፤ በመሆኑም በፊታችን ሐምሌ 2010 ዓ.ም ባለው ድርድር፣ ዕርቀ ሰላም ላይ፣ መድረስ አለመቻል ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለእኛ ዕርቅና ሰላም የከፈለልንን ዋጋ እንደቀላል ማየት ነው ብሎ በማመን፣ ዕርቀ ሰላሙ ሳይቋጭ ከተያዘው የድርድር ጊዜ (ሐምሌ 2010 ዓ.ም) ማለፍ የለበትም ብሎ መነሣት፡፡
4. ዕርቀ ሰላሙ፡- ሙሉ ለሙሉ የቤተ ክርስቲያን ጉዳይ በመሆኑ፣ ከቅድስት ቤተክርስቲያን ጥቅም አንፃር የሚታይና የሚመዘን እንጂ፣ በጉዳዩ ዙሪያ ካሉ፣ የግል ፍላጐቶች፣ አመለካከቶችና አቋሞች አንፃር እንዲመራ የሚተው አለመሆኑን ማመንና መቀበል፡፡ “ጊዜ ገቢር ለእግዚአብሔር” እንዲል በዚህ ወቅት ሁሉም ሰው ለጉዳዩ ትኩረት ሰጥቶ መነሣቱ እውነትም የይቅርታና የሰላም መምጫ ጊዜው ደርሶ ነው ብሎ በቅንነት መነሣት ይገባል፡፡
5. በአባቶች መካከል ለድርድር የሚቀርቡ ሐሳቦች እና ድርድሩ የሚመራበት መንገድና ስልት፣ ለቅድስት ቤተክርስቲያን ጠቃሚ የሆነ ነገር ማስገኘት የሚችል መሆኑን ማረጋገጥ ስለሚገባ፤ የተሻለውን እየተስማሙ መምረጥና መያዝ፣ ጥሩ መነሻ የሌለውን ሐሳብ ከዚህ ወገን ከዚያ ወገን የመጣ ነው ሳይባል፣ ከላይ በተራ ቁጥር 4 ከተገለጸው አኳያ ገንቢ የሆኑ ሐሳቦችና አቅጣጫዎች እየቀረቡበት፣ ግትር ሳይሆኑ፣ በሁሉም የባለቤትነት ስሜት እንዲዳብር፣ ነፃ ሆኖ መቀበልና ማንሸራሸር፡፡
6. በሁለቱም ወገን ተደራዳሪ የሚሆኑ አባቶች፣ በድርድሩ ላይ የሚነሱ ሐሳቦችና የማስማሚያ ነጥቦች ቅቡልነት ያላቸው መሆኑን በማረጋገጥ ይሁንታ የሚሰጡት፤ ከላይ በተራ ቁጥር 4 ላይ ከተገለጸው ዓላማ አንጻር እንጂ፣ ሲንፀባረቅ ከቆየና ቀደም ብሎ ከተያዘ አቋም አኳያ ጽንፍ በመያዝ እንዳይሆን ራስን መፈተሽ፡፡
7. ውጭ ሀገርም ሆነ ሀገር ውስጥ ያለው ሕዝበ ክርስቲያን ዕርቀ ሰላሙን በጉጉት የሚጠብቀው ስለሆነ፤ መስማማት ያልተቻለባቸውን ነጥቦች አደራዳሪዎች ለይተውና ቀርፀው በማቅረብ ላለመስማማት የተያዙትን አቋሞች ያንፀባረቋቸው ወገኖች፣ የገለጿቸውና የእነሱ መሆናቸውን በቅድሚያ እንዲያረጋግጡ በማድረግ፣ እነዚህን ነገሮች (ልዩነቶች) በሚዲያ ምእመኑ እንዲያውቃቸው በማድረግ ምእመናን ልዩነቱ እንዲፈታ የድርሻቸውን እንዲወጡ ማድረግ፡፡

8. ስምምነት ሂደት በመሆኑ፤ ድርድርና ብዙ ጊዜ በማይወስዱ ዋና ዋና በሆኑ ጉዳዮች ላይ ዕርቀ ሰላም ለመፍጠር የሚያስችሉ ግንባር ቀደም የሆኑ ነጥቦችን ለይቶ መስማማት፡፡ ከዚህ በመቀጠልም በአደራዳሪዎች አማካኝነት በቀጣይ ሊታዩ የሚገባቸውን ርእሰ ጉዳዮች ዝርዝርና የሚታዩበትን ሁኔታ አቅጣጫ ማስቀመጥ፡፡
9. በማንኛውም ደረጃ የሚገኙ የቅድስት ቤተ ክርስቲያን አባቶችና ምእመናን፤ ለዕርቀ ሰላሙ መሳካት እግዚአብሔርን በጸሎት እየጠየቁ፣ አስፈላጊውን ዕገዛና ድጋፍ ማድረግ፡፡ አደራዳሪዎችና ሚዲያዎችም ለሕዝበ ክርስቲያኑ መድረስና መታወቅ ያለበትን መረጃ አስፈላጊነቱን በማየት ሳይዛባ በወቅቱ ተደራሽ እንዲሆን ማድረግ፡፡ አጋዥና ወሳኝነት ያለው ስለሆነ«አባቶች ዕርቀ ሰላምን በመፍጠር፤ ለቤተ ክርስቲያን ሐዋርያዊ አገልግሎትና ለሀገራዊ መግባባት ወሳኝ ሚና ሊጫወቱ ይገባል!» በማለት ማኅበሩ መልእክቱን ያስተላልፋል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ምንጭ፤ሐመር  መጽሔት 26ኛ ዓመት ቁጥር 2 ሰኔ 2010 ዓ.ም