የጋብቻ ሕይወት እና የሩካቤ ሥርዓት – ክፍል ፱
ባልና ሚስት በፅንስ፣ በአራስነትና በወር አበባ ወቅት፤ እንደዚሁም በበዓላትና በአጽዋማት ቀን ሩካቤ ሥጋ ማድረግ እንደማይገባቸው ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ታስተምራለች፡፡ ከዚህ በተረፈ ግን ሰይጣን የሚፈትንበትን ክፍተት እንዳያገኝ ባልና ሚስት ሊለያዩ አይገባም፡፡ “ለጸሎት ትተጉ ዘንድ ተስማምታችሁ ለጊዜው ካልኾነ በቀር እርስ በርሳችሁ አትከላከሉ፤ ራሳችሁን ስለ አለመግዛት ሰይጣን እንዳይፈታተናችሁ ደግሞ አብራችሁ ኹኑ፤” እንዳለ ቅዱስ ጳውሎስ (፩ኛ ቆሮ. ፯፥፭)፡፡ ይህ የሐዋርያው ትምህርት “ሰውነታችሁን ንጹሕ አድርጋችሁ በምትጾሙበት፣ በምትጸልዩበት ጊዜ ነው እንጂ ሥራችሁን ከፈጸማችሁ በኋላ ግን ወደ ፈቃዳችሁ ተመለሱ፡፡ የምትሹትን ስላጣችሁ ሰይጣን ድል እንዳይነሳችሁ” ተብሎ በፍትሐ ነገሥትም ተጠቅሷል (አን. ፲፭፣ ቍ. ፳፬)፡፡ ይህም ባልና ሚስት፣ የጾም፣ የጸሎት፣ የበዓል ወቅት ካልኾነ በቀር ሳይለያዩ ፈቃዳቸዉን መፈጸም እንደሚገባቸው ያስገነዝባል፡፡