ከ7500 በላይ አልባሳት ተሰበሰበ

በፈትለወርቅ ደስታ
«ሁለት ልብሶች ያሉት…..» በሚል መሪ ቃል የተጀመረው የአልባሳት ማሰባሰቢያ መርሐ ግብር የቀጠለ ሲሆን የመጀመሪያውን ቀን ጨምሮ እስከ እሁድ ጥር 29 ቀን 2003 ዓ.ም ድረስ ባሉት ቀናት ከ7500 በላይ አልባሳት፣ ከ10 በላይ ጣቃ የተለያዩ ብትን ጨርቆችና ለመነኮሳት የሚሆኑ አልባሳት እንደተሰበሰበ ታውቋል፡፡

በዚህ መርሐ ግብር አልባሳቱ ከአዲስ አበባ፣ ከአዲስ ዓለምና ከኳታር እንደተሰበሰቡ ለማወቅ ተችሏል፡፡ በአልባሳት መደገፍ ያልቻሉ በርካታ ምዕመናንም መርሐ ግብሩን በገንዘብ በመደገፍ ተሳትፎ እያደረጉ ነው፡፡

አንዳንድ ምዕመናን ይዘውት ከመጡት አልባሳት በተጨማሪ ደርበው የመጡትን ጃኬትና ሸሚዝ እስከመስጠት ደርሰዋል፡፡ «ዓላማው በጣም ደስ ብሎኛል በረከትና ረድኤት አገኝበታለሁ ብዬ ነው የማደርገው፤ እኛ ለእኛ እንበቃ ነበር ነገር ግን ሁላችንም አነሳሽና መሪ እንፈለጋለን» በማለት ስሙን መግለጽ ያልፈለገ ወጣት ገልጾልናል፡፡

 

ከአገር ውስጥና ከአገር ውጭ ያሉ ምዕመናን መርሐ ግብሩ የሚከናወንባቸው ቀናት አጭር በመሆኑ መሳተፍ አለመቻላቸውን በስልክና በኢሜይል በመግለጻቸው እስከ የካቲት 6 ቀን 2003 ዓ.ም እንደተራዘመ አስተባባሪ ክፍሉ አሳውቋል፡፡

በእስከ አሁኑ መርሐ ግብር ከ800 በላይ የሆኑ ምዕመናን ተሣትፈዋል፡፡ መርሐ ግብሩ ዘወትር ከጠዋት 2፡30 እስከ ምሽቱ 2፡30 ድረስ ይካሄዳል፡፡