የኀዘን መግለጫ

img_0005

ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ የቅዱስ ሲኖዶስ ርእሰ መንበር እና ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት

መጋቢት ፮ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም  

የተወደዳችሁ የድረ ገጻችን ተከታታዮች! መጋቢት ፪ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም በአዲስ አበባ ከተማ በኮልፌ ቀራንዮ ክፍለ ከተማ ልዩ ስሙ ‹‹ቆሼ›› እየተባለ በሚጠራው ሥፍራ በድንገተኛ አደጋ ከዚህ ዓለም በሞት ለተለዩ ወገኖቻችን፣ ዛሬ መጋቢት ፮ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የተሰጠውን የሐዘን መግለጫ እንደሚከተለው አቅርበነዋል፤

በአዲስ አበባ ከተማ መጋቢት ፪ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ምሽት በወገኖቻችን ላይ የደረሰውን የሞት አደጋ አስመልክቶ ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የተሰጠ የዘን መግለጫ፡፡

መጋቢት ፪ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ከምሽቱ ፪ ሰዓት ሲኾን በኮልፌ ቀራንዮ ክፍለ ከተማ ልዩ ስሙ ‹‹ቆሼ›› እየተባለ በሚጠራው ስፍራ በሚኖሩ ወገኖቻችን ላይ ድንገተኛ የሞት አደጋ ደርሷል፡፡ በደረሰውም አሳዛኝ አደጋ ከፍተኛ ዘን ተሰምቶናል፡፡

በመኾኑም እግዚአብሔር አምላካችን በደረሰው ኅልፈተ ሕይወት ለተጎዱ ወገኖች ቤተሰቦች መጽናናትን፣ ብርታትን እንዲሰጥልን፤ የሟቾችንም ነፍሳት በመንግሥቱ እንዲቀበልልን በመጸለይ የተሰማንን ዘን እየገለጽን፣ ለእነዚሁ በድንገተኛ አደጋ ለተለዩ ወገኖቻችን ከመጋቢት ፯ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ጀምሮ ለሰባት ቀናት በመላ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አብያተ ክርስቲያናትና ገዳማት ጸሎተ ፍትሐት እንዲደረግላቸው፤ እንዲሁም ቤታቸው በመፍረሱ ምክንያት በመጠለያ ለሚገኙ ወገኖቻችን ከቤተ ክርስቲያችን ብር 200,000.00 (ሁለት መቶ ሺሕ) ርዳታ እንዲሰጥ ቋሚ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡

በክርስቶስ ሰላም

(ክብ ማኅተምና የብፁዕ አቡነ ገሪማ ፊርማ አለው)

አባ ገሪማ ሊቀ ጳጳስ ዶክተር

የብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ ልዩ ጽሕፈት ቤት፣

የውጭ ግንኙነት የበላይ ሓላፊ