የሆሣዕና ምንባብ12(ሉቃ.19÷28-ፍጻ.)

 ይህንም ተናግሮ ወደ ፊት ሄደ፤ ወደ ኢየሩሳሌምም ወጣ፡፡ ደብረ ዘይት ወደ ሚባል ተራራ አጠገብ ወዳሉት ወደ ቤተ ፋጌና ወደ ቢታንያ በቀረበ ጊዜ÷ ከደቀ መዛሙርቱ ሁለቱን ላከ፡፡ እንዲህም አላቸው÷ “በፊታችሁ ወደ አለችው መንደር ሂዱ፤ገብታችሁም ሰው ያልተቀመጠበት የታሰረ ውርንጫ ታገኛላችሁ፤ ፈትታችሁም አምጡልኝ፡፡ ለምን ትፈቱታላችሁ? የሚላችሁ ቢኖር ጌታው ይሻዋል በሉ፡፡” የተላኩትም ሄደው እንደ አላቸው አገኙ፡፡ ውርንጫውንም ሲፈቱ ባለቤቶቹ “ውርንጫውን ለምን ትፈቱታላችሁ?” አሉአቸው፡፡ እነርሱም “ጌታው ይሻዋል” አሉ፡፡ ይዘውም ወደ ጌታችን ኢየሱስ ወሰዱት፤ በውርንጫው ላይም ልብሳቸውን ጭነው ጌታችን ኢየሱስን በዚያ ላይ አስቀመጡት፡፡ ሲሄዱም በመንገድ ልብሳቸውን አነጠፉ፡፡ ወደ ደብረ ዘይት ዐቀበት መውረጃም በደረሱ ጊዜ÷ ደቀ መዛሙርቱ በሙሉ ስለ አዩት ኀይል ሁሉ ደስ ይላቸውና እግዚአበሔርን በታላቅ ቃል ያመሰግኑት ዘንድ ጀመሩ፡፡ እንዲህ እያሉ÷ “በእግዚአብሔር ስም የሚመጣ ቡሩክ ነው፤ የእስራኤል ንጉሥ ቡሩክ ነው፤ ሰላም በምድር÷ በአርያምም ክብር ይሁን፡፡” ከፈሪሳውያንም በሕዝቡ መካከል÷ “መምህር ሆይ÷ ደቀ መዛሙርትህን ገሥጻቸው” ያሉት ነበሩ፡፡ እርሱም መልሶ እንዲህ አላቸው÷ “እነዚህ ዝም ቢሉ እኒህ ድንጋዮች ይጮሀሉ፡፡”

በደረሰ ጊዜም ከተማዪቱን አይቶ አለቀሰላት፡፡ እንዲህም አላት÷ “አንቺስ ብታውቂ ሰላምሽ ዛሬ ነበረ፤ ከእንግዲህ ወዲህ ግን ከዐይኖችሽ ተሰወረ፡፡ ጠላቶችሽ አንቺን የሚከቡበት ቀን ይመጣል፤ ይከትሙብሻል፤ ያስጨንቁሻልም፤ በአራቱ ማዕዘንም ከብበው ይይዙሻል፡፡ አንቺን ይጥሉሻል፤ ልጆችሽንም ከአንቺ ጋር ይጠሉአቸዋል፤ ድንጋይንም በደንጋይ ላይ አይተዉልሽም፤ የይቅረታሽን ዘመን አላወቅሽምና፡፡”

ወደ ቤተ መቅደስም ገብቶ በዚያ የሚሸጡትንና የሚገዙትን ሁሉ አስወጣ፤ የለዋጮችንም መደርደሪያ÷ የርግብ ሻጮችንም ወንበር ገለበጠ፡፡ “ቤቴ የጸሎት ቤት ይባላል የሚል ጽሑፍ አለ፤ እናንተ ግን የሌቦችና የቀማኞች ዋሻ አደረጋችሁት” አላቸው፡፡ ዘወትርም በመቅደስ ያስተምር ነበር፤ የካህናት አለቆች÷ ጻፎችና የሕዝብ ታላላቆችም ሊገድሉት ይሹ ነበር፡፡ ነገር ግን የሚያደርጉትን አጡ ሕዝቡ ሁሉ ትምህርቱን በመስማት ይመሰጡ ነበርና፡፡