የሆሣዕና ምንባብ10(ማቴ.21÷1-18)

ጌታችን ኢየሱስ ወደ ኢየሩሳሌም ቀርቦ÷ ወደ ደብረ ዘይት ወደ ቤተ ፋጌ በደረሰ ጊዜ ከደቀ መዛሙርቱ ሁለቱን ላከ፡፡ እንዲህም አላቸው፤ “በፊታችሁ ወደ አለችው መንደር ሂዱ፤ ያንጊዜም የታሰረች አህያ ከውርንጫዋ ጋር ታገኛላችሁ፤ ፍቱና አምጡልኝ፡፡ ምን ታደርጋላችሁ? የሚላችሁ ቢኖርም ጌታቸው ይሻቸዋል በሉ÷ ያንጊዜ ይሰዱአችኋል፡፡” ይህም ሁሉ የሆነው በነቢይ እንዲህተብሎ የተነገረው ይፈጸም ዘንድ ነው፡፡ “ለጽዮን ልጅ፡- እነሆ÷ የዋህ ንጉሥሽ በአህያይቱና በአህያይቱ ውርንጭላ ላይ ተቀምጦ ወደ አንቺ ይመጣል በሉአት”፡፡ ደቀ መዛሙርቱም ሄደው ጌታችን ኢየሱስ እንደ አዘዛቸው አደረጉ፡፡ አህያይቱንና ውርንጫዋንም አመጡለት፤ ልብሳቸውንም በላያቸው ጫኑ፤ ጌታችን ኢየሱስም በእነርሱ ላይ ተቀመጠ፡፡ ብዙ ሕዝብም ልብሳቸውን በመንገድ ላይ አነጠፉ፤ ሌሎችም ከዛፎች ጫፍ ጫፉን እየቈረጡ በመንገድ ላይ ያነጥፉ ነበር፡፡ በፊቱ የሚሄዱትና የሚከተሉት ሕዝብም÷ “ሆሣዕና ለዳዊት ልጅ፤ በእግዚአብሔር ስም የሚመጣ ቡሩክ ነው፤ ሆሣዕና በአርያም” እያሉ ይጮሁ ነበር፡፡ ጌታችን ኢየሱስም ወደ ኢየሩሳሌም በገባ ጊዜ÷ “ከተማዪቱ ይህ ማነው?” እያለች ታወከች፡፡ ሕዝቡም÷ “ይህ ከገሊላ ናዝሬት የመጣው ነቢዩ ኢየሱስ ነው” አሉ፡፡

ጌታችን ኢየሱስም ወደ ቤተ መቅደስ ገብቶ በቤተ መቅደስ የሚሸጡትንና የሚገዙትን ሁሉ አባረረ፤ የገንዘብ ለዋጮችንም መደርደሪያ÷ የርግብ ሻጮችንም ወንበር ገለበጠ፡፡ “ቤቴ የጸሎት ቤት ይባላይ ተብሎ ተጽፎአል፤ እናንተ ግን የሌባና የቀማኛ ዋሻ አደረጋችሁት” አላቸው፡፡ በቤተ መቅደስም ዕውሮችና አንካሶች ወደ እርሱ መጡ፤ አዳናቸውም፡፡ ያን ጊዜም የካህናት አለቆችና ጻፎች ያደረገውን ተአምራት÷ ልጆችንም በቤተ መቅደስ÷ “ሆሣዕና ለዳዊት ልጅ” እያሉ ሲጮሁ ባዩ ጊዜ ደስ አላላቸውም፡፡ እነርሱም÷ “እነዚህ የሚሉትን አትሰማምን?” አሉት፤ ጌታችን ኢየሱስም÷ “አዎን÷ እሰማለሁ÷ ከልጆችና ከሕፃናት አንደበት ምስጋናን አዘጋጀህ የሚለውን ቃል ከቶ ያነበባችሁበት ጊዜ የለምን?” አላቸው፡፡ ትቶአቸውም ከከተማው ወደ ቢታንያ ሄደ፤ በዚያም አደረ፡፡