ጽላተ ሕጉ ወደ ቤተ ክርስቲያን ተመለሰ

ኅዳር ፲፱ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

በይብረሁ ይጥና

st-mic

ከግራ ወደ ቀኝ፡- ቅዱስ ሚካኤል፣ መንበረ ልዑል ቅዱስ ማርቆስ ደብር እና አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ

በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የጥናትና ምርምር ተቋም ሙዚየም ውስጥ የተገኘው የቅዱስ ሚካኤል ጽላት ወደ ቤተ ክርስቲያን ተመለሰ፡፡

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ጠቅላይ ቤተ ክህነት የቅርስ ጥበቃ፣ ቤተ መጻሕፍት ወመዘክር መምሪያ ሓላፊ መጋቤ ሰላም ቀሲስ ሰሎሞን ቶልቻ እንዳስታወቁት፤ ጽላቱ ወደ ፊት ለብቻው ቤተ ክርስቲያን እስኪታነጽለት ድረስ ኅዳር ፲ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም በመንበረ ልዑል ቅዱስ ማርቆስ ቤተ ክርስቲያን በአደራ መልክ እንዲቀመጥ ተደርጓል፡፡

‹‹ጽላቱ መቼ፣ እንዴትና በማን አማካይነት ወደ ዩኒቨርስቲው ሊገባ ቻለ?›› ለሚለው ጥያቄአችን መጋቤ ሰላም ቀሲስ ሰሎሞን ምላሽ ሲሰጡም ‹‹ከየትና እንዴት እንደገባ የሚገልጥ ማስረጃ ባይገኝም ሰኔ ፲፪ ቀን ፲፱፻፶፫ ዓ.ም ሚስተር እስቲፈን ሮቶ በተባለ ግለሰብ ወደ ዩኒቨርስቲው እንደገባ ከዩኒቨርስቲው ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፤›› ብለዋል፡፡ አያይዘውም ጽላቱ በዐፄ ኃይለ ሥላሴና በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ባስልዮስ ዘመን የነበረ መኾኑ ከጽላቱ ላይ ተጽፎ እንደሚገኝ አስረድተዋል፡፡

እንደ መጋቤ ሰላም ቀሲስ ሰሎሞን ማብራሪያ ለጽላቱ መገኘትና ወደ መንበሩ መመለስ መነሻ የኾነው አቶ በለጠ ዘነበ የተባሉ የ፹ ዓመት አረጋዊ የተመለከቱት ራእይና ያደረጉት ጥረት ነው፡፡ እኒህ አባት ‹‹የቅዱስ ሚካኤል ጽላት በዩኒቨርሲቲው ሙዚየም ውስጥ ተቀብሮ ይገኛልና መውጣት አለበት›› በማለት በተደጋጋሚ መምሪያውን ሲያሳስቡ እንደነበረ ያስታወሱት መጋቤ ሰላም ቀሲስ ሰሎሞን በልዩ ልዩ ጊዜያት ከጠቅላይ ቤተ ክህነት ለዩኒቨርሲቲው የተጻፉ ደብዳቤዎችን መሠረት በማድረግ ጽላቱ ወደ ቤተ ክርስቲያን እንዲመለስ መደረጉን አስታውቀዋል፡፡

በመጨረሻም የቅዱስ ሚካኤል ጽላት ለቤተ ክርስቲያናችን እንዲመለስ ጥረት ላደረጉትና ለተባበሩት ለአቶ በለጠ ዘነበ፣ ለአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲና ለመንግሥት አካላት በሙሉ መጋቤ ሰላም ቀሲስ ሰሎሞን ቶልቻ በቤተ ክርስቲያን ስም ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡