ጰራቅሊጦስ(ለሕፃናት)

ሰኔ 07 2003 ዓ.

አዜብ ገብሩ

እንደምን ሰነበታችሁ ልጆች? ደህና ናችሁ? እንኳን ለበዓለ ጰራቅሊጦስ በሰላም  አደረሳችሁ፡፡

ከትንሣኤ በኋላ ያለው ሃምሳኛው ቀን ጰራቅሊጦስ ይባላል፡፡ ይህ ዕለት ጌታ ለሐዋርያት መንፈስ ቅዱስን ያወረደበት ዕለት ነው፡፡ ልጆች ጌታ ከሞት ከተነሣ በኋላ አስራ ሁለቱ ሐዋርያት በቅዱስ ማርቆስ እናት ቤት ከሰባሁለቱ አርድዕት አና ከሰላሳ ስድስቱ ቅዱሳን አንስት ጋር በመሆን ይጸልዩ ነበር፡፡ ጌታም በተለያየ ጊዜ እየተገለጸ ያስተምራቸው ነበር፡፡ አጽናኝ የሆነውን ቅዱስ መንፈስም እንደሚልክላቸው ይነግራቸው ነበር፡፡


ታዲያ ልጆች ሐዋርያት በዚያ ተሰብስበው እየጸለዩ ሳለ ድንገት እንደሚነጥቅ ዓውሎ ንፋስ ከሰማይ ድምጽ መጣ፡፡ መንፈስ ቅዱስም  በእሳት አምሳል በሐዋርያት ላይ ሞላባቸው፡፡ ከዚያም ሐዋርያት በተለያየ ቋንቋ መናገር ጀመሩ፡፡ በዚያ ተሰብስበው የነበሩ ሰዎችም ሐዋርያት በተለያየ ቋንቋ ሲናገሩ ሰምተው በጣም ተደነቁ፡፡ ሐዋርያትም ለተሰበሰቡት ሰዎች በየራሳቸው ቋንቋ አስተማሯቸው፡፡ ሰዎቹም በክርስቶስ አምነው ክርስቲያን ሆኑ፡፡
ልጆች ይህን ለሐዋርያት የወረደውን መንፈስ እኛም ጥምቀትን ስንጠመቅና ቅዱስ የሆነውን ሜሮን ስንቀባ እንቀበለዋለን፡፡ ይህ ቅዱስ የሆነው መንፈስም ከእኛ ጋር ሆኖ ከክፉ ነገር ሁሉ ይጠብቀናል፡፡ ኃጢአት እንዳንሠራም ይጠብቀናል፡፡ እንቢ ብለን ኃጢአትን ብንሠራ ሰው ብንሳደብ፣ ለታላላቆቻችን ባንታዘዝ፣ ውሸት ብንናገር፣ የጓደኛችንን ዕቃ ብንሰርቅ፣…/ ይህ ቅዱስ የሆነው መንፈስ ከእኛ ይሸሻል፡፡ ስለዚሀ ልጆች ሁል ጊዜ መልካም የሆነ ነገር ብቻ መሥራት አለብን ማለት ነው፡፡ ይህን የመሰለ ስጦታ የሰጠንን እግዚአብሔርንም ልናመሰግነውና ልናከብረው ይገባል፡፡

 

ወስብሐት ለእግዚአብሔር