Zimare_Mewasit.JPG

የዝማሬ መዋሥዕት አድራሾች ተመረቁ

በደረጀ ትዕዛዙ
 
Zimare_Mewasit.JPG
 
በዙር አባ አቡነ አረጋዊ ገዳም የዝማሬ መዋሥዕት ትምህርታቸውን ተከታትለው ተመረቁት ደቀ መዛሙርት ከአቡነ እንድርያስ ጋር

በደቡብ ጎንደር ሀገረ ስብከት በላይ ጋይንት ወረዳ ሳሊ በተባለው ቀበሌ የሚገኘው የጽርሐ አርያም ዙር አባ አቡነ አረጋዊ ገዳም ዝማሬ መዋሥዕት ትምህርት ቤት ዐሥራ ሰባት የዝማሬ መዋሥዕት አድራሾችን አስመረቀ፡፡

የአብነት ትምህርት ቤቱ ጥር 30 ቀን 2002 ዓ.ም አድራሾችን ባስመረቀበት ወቅት ብፁዕ አቡነ እንድ ርያስ የሀገረ ስብከቱ ሊቀጳጳስ ለተመራቂዎች ባስተላለፉት መልእክት፤ «በብዙ ጥረት እና ድካም፤ በረጅም ጊዜ ያካበታችሁትን ዕውቀት በተለያዩ ጊዜያትና ቦታዎች ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን እንድታውሉት አደራ እላለሁ» ብለዋል፡፡

ምሩቃኑ ተግተው ቤተክርስቲያንን በማገልገል ሌሎችንም ተተኪ ደቀመዛሙርት ማፍራት እንዳለባቸው ያሳሰቡት ብፁዕነታቸው፤ ሀገረ ስብከታቸው ለዚህ ቅዱስ ተግባር ስኬታማነት የበኩሉን የሓላፊነት ድርሻ ለመወጣት ዝግጁ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡

በምረቃ ሥነ ሥርዓቱ ላይ የተመራቂ ቤተሰቦች፣ ካህናት፣ ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች የተገኙ ሲሆን፤ ዝማሬ፣ ቅኔ መወድስ የአማርኛ እና የግእዝ ቅኔ ግጥሞች በተመራቂዎች መቅረቡን ከደብረ ታቦር ማእከል የደረሰን መረጃ ያመለክታል፡፡ «አድራሽ» ማለት በቤተ ክርስቲያን የአብነት ት/ቤቶች ለመምህርነት የሚያበቃቸውን ሙያ ተምረው ያጠናቀቁ ደቀመዛሙርት ማለት ነው፡፡