የዐቢይ ጾም ሳምንታት (ለሕፃናት) – የመጨረሻ ክፍል

፰. ሆሣዕና

በልደት አስፋው

መጋቢት ፴ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

ልጆች ደኅና ሰነበታችሁ? እግዚአብሔር ይመስገን! ባለፈው ዝግጅት ሰለ ሰባተኛው የዐቢይ ጾም ሳምንት (ስለ ኒቆዲሞስ) ተምራችሁ ነበር፡፡ መልካም ልጆች! በዛሬው ዝግጅታችን ደግሞ ስለ ስምንተኛውና የመጨረሻው የዐቢይ ጾም ሳምንት ማለትም ስለ ሆሣዕና አጭር ትምህርት እንደሚከተለው ይዘንላችሁ ቀርበናል፤

ስምንተኛው የዐቢይ ጾም ሳምንት ‹ሆሣዕና› ይባላል፡፡ ትርጕሙም ‹መድኃኒት፣ አሁን አድን› ማለት ነው፡፡ ሆሣዕና ጌታችን አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በአህያ ጀርባ ተቀምጦ በክብር፣ በምስጋና ወደ ኢየሩሳሌም የገባበት ዕለት ነው፡፡

በዚህ ዕለት ሕፃናትና አረጋውያን በአንድነት ኾነው፣ የዘንባባ ቅጠል ይዘው፡- ‹‹ለዳዊት ልጅ በሰማይ መድኒት መባል ይገባዋል፤ በእግዚአብሔር ስም የመጣ የዳዊት ልጅ ዳዊት አምላክ ኢየሱስ ክርስቶስ ቡሩክ ነው!›› እያሉ በአንድነት ጌታችንን አመስግነዋል፡፡

ስለዚህም ሆሣዕና በየዓመቱ በቤተ ክርስቲያናችን በመንፈሳዊ ሥርዓት ይከበራል፡፡ እኛ ክርስቲያኖችም ለመታሰቢያ ይኾን ዘንድ በራሳችን ላይ የዘንባባ ቅጠል በመስቀል ምልክት እናስራለን፡፡

ልጆች! የዐቢይ ጾም ሳምንታትን ስያሜና ታሪክ በሚመለከት በተከታታይ ክፍል ያቀረብንላችሁን ትምህርት በዚሁ ፈጸምን፡፡ በሉ ደኅና ኹኑ ልጆች! ለበዓለ ትንሣኤው በሰላም ያድርሰን፡፡ ሰላመ እግዚአብሔር ከዅላችን ጋር ይኹን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡