የካናዳ ማእከል ፲፪ኛ ጠቅላላ ጉባኤ ተካሔደ

ሐምሌ ፩ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በካናዳ ማእከል

0002

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን የካናዳ ማእከል ፲፪ኛ ጠቅላላ ጉባኤ ከሰኔ ፳፭-፳፯ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም በሀገረ ካናዳ አልበርታ ግዛት በካልጋሪ ከተማ ተካሔደ፡፡

በካናዳ ልዩ ልዩ ግዛቶች የሚገኙ የማኅበሩ አባላት የተሳተፉበት ጉባኤው በካልጋሪ ሐመረ ኖኅ ኪዳነ ምሕረት አገልጋይ ካህናትና ዲያቆናት በጸሎተ ወንጌል ከተከፈተ በኋላ፣ የካናዳ ሀገረ ስብከትና የማኅበሩ መልእክቶች ቀርበዋል፡፡

 

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የካናዳ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ማትያስ በመልእክታቸው የማኅበረ ቅዱሳን ካናዳ ማእከል አባላት በሀገረ ስብከተቻውና በካናዳ በሚገኙ ፲፱ አብያተ ክርስቲያናት የሚሰጡትን ሰፊ አገልግሎት ዘርዝረው፤ “በየአጥቢያችሁ ከሚገኙ ካህናትና ምእመናን ጋር በመተባበር ለቤተ ክርስቲያን ዕድገት፤ ለስብከተ ወንጌል መጠናከርና ለሰንበት ት/ቤት አገልግሎት መፋጠን ለሕፃናት ትምህርት ልዩ ትኩረት በመስጠት አገልግሎታችሁን የበለጠ እንድታጠናክሩ” ሲሉ አባላቱን አሳስበዋል፡፡

ጉባኤው ስለ ቤተ ክርስቲያን ወቅታዊ ኹኔታና የማኅበሩ እንቅስቃሴ፤ ስለ ቅዱሳት መካናትና አብነት ት/ቤቶች ነባራዊ ኹኔታና ስለሚያስፈልጋቸው ድጋፍ፤ የአባላትና የምእመናንን ተሳትፎ ስለ ማሳደግና በሌሎችም አጀንዳዎች ላይ ሰፊ ውይይት አድርጎ ጠቃሚ ውሳኔዎችን አስተላልፏል፡፡

በተጨማሪም የማእከሉ የ፳፻፰ ዓ.ም የአገልግሎት እንቅስቃሴ ሪፖርትና የ፳፻፱ ዓም የአገልግሎት ዕቅድ ቀርቦ ሰፊ ውይይት ተደርጎበታል፡፡ የ፳፻፱ ዓም የአገልግሎት ዕቅዱም በምልዓተ ጉባኤው ሙሉ ድምፅ ጸድቋል፡፡

በመጨረሻም አባላቱ በያሉበት ኾነው አገልግሎታቸውን ለማጠናከር ቃል ከገቡ፤ ፲፫ኛው የማእከሉ ጠቅላላ ጉባኤም ኦታዋ ላይ እንዲካሔድ ከተወሰነ በኋላ ጠቅላላ ጉባኤው በጸሎት ተፈጽሟል፡፡