የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በዝርወት

ሐምሌ 3 ቀን 2005 ዓ.ም

በዲ/ን ዶ/ር መርሻ አለኸኝ

የዚህ ጽሑፍ ዓላማ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በዝርወት /ከኢትዮጵያ ውጭ/ ያደረገችውን ረጅም ሐዋርያዊ ጉዞ በአጭሩ በመዳሰስ፤ ጉዞዋ ዛሬ የደረሰበትን ምዕራፍ መቃኘት ነው፡፡ የዛሬው ከታየ ዘንድ ግን ጽሑፉ በመጠኑም ቢሆን ጥናታዊ መልክ ይኖረው ዘንድ ዛሬ ቤተ ክርስቲያኗ በውጭው ዓለም ለምትሰጠው አገልግሎት እንቅፋት ናቸው ተብለው ሊጠቀሱ ከሚችሉ ችግሮች ዋና ዋና የሚባሉትን በማቅረብ የይሁንታ አሳብ ይሰነዝራል፡፡

ኢትዮጵያ እንደ ሀገር እምነትን በተመለከተ የግንኙነት መስመሯን ወደ ውጭ መዘርጋት የጀመረችው ቅድመ ክርስትና ከ1000 ዓ.ዓ. ገደማ ጀምሮ ነው፡፡ በቃልም በመጣፍም የቆየን የሀገራችን ወፍራም የእምነት ታሪክ እንደሚነግረን ንግሥተ ሳባ በሕገ ልቡና እግዚአብሔርን ሲያመልክ የነበረ ሕዝቧን በመወከል ወደ ኢየሩሳሌም ተጉዛ ከንጉሡ ከሰሎሞን ጋር በመወያየት እግዚአብሔር ለእሱና ለሕዝቡ የገለጠውን ሕገ ኦሪት ይዛ ወደ አገሯ ተመልሳለች፡፡ ሕዝቧንም በዚሁ የኦሪት ሕግና እምነት እንዲመራ አድርጋለች፡፡ እሷ የጀመረችው ግንኙነትም በኋላ የመንፈሳዊ ጥበብ ፍለጋ ጉዞዋ ሌላ ውጤት በሆነው ልጇ ቀዳማዊ ምንልክና እሱ ባመጣቸው ሌዋውያን ካህናት አማካይነት ተጠናክሮ ቀጥሏል፡፡

ከክርስትና በፊት የነበረውን ድዮስጶራዊ እንቅስቃሴና ግንኙነት በዚሁ እንተወውና የክርስቶስ መወለድና ታላቅ የማዳን ሥራ ለዓለም ከታወጀበት ወዲህ ያለውን ታሪክ እንመልከት፡፡ መግቢያ ይሆነን ዘንድ የዝርወት እንቅስቃሴዋን የምናይላት የኢ.ኦ.ተ.ቤ. እንዴት እንደ ተመሠረተች በሌላ አገላለጥ ክርስትና ወደ ሀገራችን እንዴትና መቼ እንደገባ በአጭሩ እንመልከት፡፡ እኛ ኢትዮጵያውያን ከክርስትና ጋር የተዋወቅንበትን ጊዜ አስመልክቶ ከላይ እንደተጠቀሰው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በአበው ያስቆጠረው ሱባኤ ሞልቶ፣ በነቢያት ያስነገረው ትንቢት እውነት ሆኖ በቤተልሔም በተወለደ ጊዜ ይህንን ታላቅ ዜና በጥበብ ተረድተው፣ በኮከብ እየተመሩ ቤተልሔም ደርሰው በመስገድ ለንጉሠ ሰማይ ወምድርነቱ ወርቅ፣ ለክህነቱ ዕጣን፣ አዳምን ለማዳን በመስቀል ላይ ስለሚቀበለው ሕማምና ሞት ከርቤ እጅ መንሻ አቅርበው ወደ ሀገራቸው ከሔዱት ነገሥታት አንዱ ኢትዮጵያዊ ነው የሚል ታሪክ አለ፡፡

በክርስቶስ የባሕርይ አምላክነት አምኖ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስስም ተጠምቆ ክርስትናን በመያዝ ወደ ሀገራችን የገባው የኢትዮጵያ ንግሥት ሕንደኬ በጅሮንድ /የገንዘብ ሹም/ የነበረው ኢትዮጵያዊው ጃንደረባ ነው፡፡ እንደኦሪቱ ሥርዐት ማንኛውም የብሉይ ኪዳንን እምነት የተቀበለ ወንድ የሆነ ሁሉ በዓመት የሚያከብራቸው በዓላት ነበሩ፡፡ እነዚህም በዓላት በዓለ ናዕት /የቂጣ በዓል/፣ በዓለ ሰዊት /የእሸት በዓል/፣ በዓለ መጸለት /የዳስ በዓል/ ይባሉ ነበር፡፡ በዚህም መሠረት በርካታ ኢትዮጵያውያን የእምነታቸው ሥርዐት በሚያዝዘው መሠረት ከበዓለ ፋሲካ ሰባት ሱባኤ በኋላ የሚከበረውን በዓለ ሰዊትን ወደ ኢየሩሳሌም መንፈሳዊ ጉዞ በማድረግ ያከብሩ ነበር፡፡ /ሶፎ. 3፥10/፡፡ ቅዱስ መጽሐፍ መዝግቦት በምናገኘው ታሪክ መሠረት ሐዋርያት በጌታ ልደት የተበሰረችውን ወንጌል ያለፍርሐትና ያለመሰቀቅ ዓለምን ዞረው ያስተምሩ ዘንድ አጽናኝ የሆነውን መንፈስ ቅዱስን የላከላቸው በ34 ዓ.ም በዓለ ሰዊት በተከበረበት ዕለት ነበር፡፡ /ሐዋ. 3፥10/ በዚህም መሠረት ሐዋርያት መንፈስ ቅዱስን ተቀብለው በየሀገሩ ቋንቋ ሲናገሩና እግዚአብሔርን ሲያመሰግኑ በመደነቅ ከሰሙት ምእመናን መካከል ኢትዮጵያውያንም ይገኙበት እንደነበረ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ በዓለ ሐምሳን አስመልክቶ በሰጠው ስብከቱ መስክሯል፡፡ /ድርሳን ዘቅዱስ ዮሐንስ አፈ ወርቅ ዘበዓለ ሃምሳ/፡፡

በዚሁ በዓል ተሳትፎ የቅዱሳት መጻሕፍትን ምሥጢር እየመረመረ ወደ ሀገሩ በመመለስ ላይ የነበረው ኢትዮጵያዊው ጃንደረባ ከወንጌላዊው ፊል ጶስ ጋር ተገናኘ፡፡ ፊልጶስም ያነበው የነበ ረውን የትንቢት መጽሐፍ ለክርስቶስ እንደተነገረ አምልቶ አስፍቶ ተረጎመ ለት፡፡ ጃንደረባውም በትምህርቱ አመነ፡፡ ተጠመቀ፡፡ በዚህ ዓይነት ክርስትናን ይዞ ወደ ኢትዮጵያ ገባ፡፡ እሱም በተራው ይኸንኑ የክርስቶስን የባሕርይ አምላክነት ዜና ለሕዝቡ አሰማ፡፡ /ሐዋ. 8፥26-40/ አውሳብዮስ ዘቂሳርያ የቤተ ክርስቲያን ታሪክ 2ኛ መጽሐፍ ቀ. 1/፡፡ በዚህ ዓይነት እንደ ሕገ ኦሪቱ ሁሉ በቤተ መንግሥቱ በኩል አድርጎ ወደ ኢትዮጵያ የገባው ክርስትና በዐራተ ኛው መ.ክ.ዘ. ተቋማዊ መልክ ይዞ በሀገር ውስጥና በውጭው ዓለም ኢትዮ ጵያዊ ጉዞውን ጀምሯል፡፡

ከላይ ከቀረበው ታሪክ የምንረ ዳው ሀገራችን ኢትዮጵያ አስቀድሞ ከሕገ ኦሪት ኋላም ከሕገ ወንጌል ጋር የተዋወቀችው በዘረጋችው የውጭ ግንኙነት አማካይነት እንደሆነ ነው፡፡

I. የአገልግሎት ጉዞ ከትላንት እስከ ዛሬ
ቤተ ክርስቲያኗ እንደ መንፈሳዊ ተቋም ከተመሠረተችበት ጊዜ ጀምሮ እስከ አሁን ድረስ በዝርወት ያደረገችውን እንቅስቃሴ እንደሚከተለው በወፍ በረር በክፍል በክፍል እናየዋለን፡፡

1. በመካከለኛው ምሥራቅ   
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በውጭው ዓለም ካላት ሐዋርያዊ ጉዞ ታሪክ ሰፋ ያለውንና ቀዳሚውን ምዕራፍ የሚወስደው በመካከለኛው ምሥራቅ የጻፈችውና ያጻፈችው ነው፡፡ ይህም ሊሆን የቻለው ኢትዮጵያ ከአካባቢው ሀገራት ጋራ ካላት መልክአ ምድራዊ መቀራረብ እንዲሁም የባሕልና የእምነት መዛመድ የተነሣ ነው ማለት ይቻላል፡፡ ቤተ ክርስቲያኗ በዚህ አካባቢ ያደረገችው እንቅስቃሴና አስቀምጣ ያለፈችው የታሪክ አሻራ በወግ አልተጠናም፡፡ የሆነው ሆኖ የሚታወቀውን እንቅስቃሴዋን በሀገራቱ በመከፋፈል ለማየት እንሞክር፡፡

1.1 በኢየሩሳሌም
ኢትዮጵያ እምነትን በሚመለከት ከኢየሩሳሌም ጋር ያላት ግንኙነት ከንግሥተ ሳባ ዘመነ መንግሥት ጀምሮ እንደሚሔድ ተመልክተናል፡፡ ከዚያ ጊዜ ጀምሮ ሀገራችን ከእስራኤል ጋር ባላት ቅርርብ መሠረት በተለያዩ ጊዜ ያት ልዩ ልዩ ገዳማትን በማቋቋም ስታገለግልና ስትገለገል ቆይታለች፡፡ በአሁኑ ጊዜ ቤተ ክርስቲያኗ በኢየሩሳሌም የራሷ ሀገረ ስብከት ያላት ሲሆን በሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ የበላይ ጠባቂነት የሚተዳደሩ ሰባት ቅዱሳት መካናት አሏት፡፡

1.2 በግብፅ
ቤተ ክርስቲያኗ ከምሥረታዋ ጀምሮ ከአምስቱ አኃት አብያተ ክርስቲያናት አንዷ ከሆነችው የግብፅ ቤተ ክርስቲያን ጋር የጠበቀ ግንኙነት ነበራት፡፡ ለ1600 ዓመታት ያህል ግብፃውያን ሊቃነ ጳጳሳት ወደ ሀገራችን በመምጣት ቤተ ክርስቲያኗን መርተዋል፡፡ የዚያኑ ያህል የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ምእመናንና አባቶችም ወደ ግብፅ እየሔዱ ሐዋርያዊ አገልግሎት ሰጥተዋል፡፡ ከሐዋርያዊ አገልግሎቷ መካከል ለግብፃውያኑ ስለእምነት ነፍስን አሳልፎ መስጠት /ሰማዕትነት/ ተጠቃሽ ነው፡፡ አባ ሙሴ ጸሊም ወደ ግብፅ በመሔድ ልዩ ልዩ ተጋድሎ ሲፈጽም ቆይቶ መነኮሳትን ለማጥፋትና ገዳማቸውን ለማቃጠል አረማዊ ሠራዊት በመጣ ጊዜ ከግብፃውያኑ ቀድሞ ሰማዕትነት ተቀብሏል፡፡ ይህ አባት ሰማዕትነትን እንዲቀበሉ ያጸናቸው ታላቅ ኢትዮጵያዊ ሐዋርያ እንደሆነ ቅዱሳት መጻሕፍት ምስክርነታቸውን ይሰጣሉ፡፡ የዚህ ሐዋርያ ተግባር ተሰዐቱ ቅዱሳንን ወደ ኢትዮጵያ እንደሳበ በስፋት ተመዝግቦ የሚገኝ ታሪክ ነው፡፡

በ11ኛው መ.ክ.ዘ. በአስቄጥስ በረሃ በሚገኘው ዮሐንስ ሐፂር ገዳም ውስጥ የኢትዮጵያውያን መነኮሳት እንደነበሩ፤ በ1330 በ1330 አቡነ ብንያም 2ኛ የተባሉት የግብፅ ፓትርያርክ የዮሐንስ ሐፂርን ገዳም በጎበኙ ጊዜ ኢትዮጵያውያንና ግብፃውያን መነኮሳት በዝማሬ እንደ ተቀበሏቸው፣ ጻድቁ አቡነ ተክለ ሃይማኖት በገዳመ አስቄጥስ ጉብኝታቸው ወቅት በገዳመ ዮሐንስ ሐፂር ቆይታ ማድረጋቸው፣ የኢትዮጵያዊው ጻድቅ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ሥዕል በ1517 ዓ.ም በአቡነ መቃርዮስ ገዳም ለጎብኝዎች ማረፊያ በተሠራው ቤተ ክርስቲያን ግድግዳ ላይ ተሰቅሎ መገኘቱ፤ እንዲሁም በግብፅ ውስጥ ዴር አል ሱርያን ተብሎ በሚታወቀው በሶርያውያን ገዳም ኢትዮጵያውያን መነኮሳት ይኖሩ እንደ ነበርና አንድ ትልቅ ቤተ መጻሕፍት እንዳቋቋሙ መዛግብት ያስረዳሉ፡፡ በደቡብ ግብፅ በሚገኘው የቁስቋም ገዳም ከ14ኛው እስከ 17ኛው መ.ክ.ዘ. ድረስ ኢትዮጵያውያን የራሳቸው ገዳም ነበራቸው፡፡ በዚህ ዘመን የተጋድሎን ሕይወት ለግብፃውያኑ ካስተማሩት ኢትዮጵያ ውያን አበው መካከል አቡነ አብደል ጣሉት አል ሐበሽና አቡነ አብደል መሢሕ /ገብረ ክርስቶስ/ በመባል የሚታወቁት ሁለት አበው ተጠቃሽ ናቸው፡፡

በአሁኑ ወቅት ከ1985 ዓ.ም ጀምሮ ብዙ ኢትዮጵያውያን ወደ ግብፅ በስደት በመግባታቸው በግብፅ የአባስያ ሰንበት ት/ቤት አቋቁመው አገልግሎት በመስጠት ላይ ይገኛል፡፡

1.3 በሀገረ ናግራን
በዛሬዋ የመን ደቡብ ዓረቢያ ይገኝ የነበረ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ሀገረ ስብከት ሲሆን በዚህ ቦታ ቤተ ክርስቲያን ለ300 ዓመታት አገልግላለች፡፡ በዚህ አካባቢ ጻድቁ ዐፄ ካሌብ በአይሁድና አረማውያን እንግልት የደረሰባቸውን ክርስቲያኖች በማዳን ታላቅ ተጋድሎ ከመሥራታቸውም ባሻገር አብያተ ክርስቲያናትን አሳንፀው ቤተ ክርስቲያኗ የተገፉትን በመጠበቅ የተበተኑትን በመሰብሰብ በኩል ሰፊ አገልግሎት እንድትሰጥ አድርገው ተመልሰዋል፡፡  

1.4 በሶርያ
በዚህ አካባቢ ቤተ ክርስቲያናችን የሰጠችው ሰፊ አገልግሎት በወግ ስላልተጠና ሰፊ ሐተታ ማቅረብ ባይቻልም ዛሬም ድረስ ሙሴ አል ሐበሻ በመባል የሚታወቀው ገዳምና የዐፄ ገብረ መስቀል ልጅ አባ ሙሴ እንደ መሠረተው የሚነገረው ገዳም መገኘቱ ቤተ ክርስቲያናችን በአካባቢው ያላትን ታሪካዊነትና ጥንታዊነት ይመሰክራል፡፡  

1.5 አርመን
ኢትዮጵያዊው ጻድቅ አቡነ ኤዎስ ጣቴዎስ፣ አባ ባኪሞስ፣ አባ መርቆ ሬዎስና አባ ገብረ ኢየሱስ የተባሉ ደቀ መዛሙርታቸውን አስከትለው ግብፅ ወርደው የግብፁን ፓትርያርክ አቡነ ብንያምን አነጋግረው ወደ ኢየሩሳሌም ከሔዱ በኋላ በአርመን በተለይም ዛሬ ቱርኮች በያዟት ሲሲሊያ በተባለች ቦታ ለ14 ዓመታት ሐዋርያዊ አገልግሎት ሰጥተዋል፡፡   

1.6.  በአሁኑ ጊዜ በመካከለኛው ምሥራቅ
ቤተ ክርስቲያናችን ጥንት ቀይ ባሕርን ተሻግራ በመካከለኛው ምሥራቅ የሰጠችውን አገልግሎት በዚህ ዓይነት ካየን ዘንድ በአሁኑ ወቅት በየመን፣ በሰንዓ፣ በዓረብ ኢምሬቶች፣ በሊባኖስ አብያተ ክርስቲያናት መንፈሳዊ አገልግሎት ለመስጠት ተቋቁመዋል፡፡ በዓረብ ኢምሬቶች ውስጥ በሻርጂያ፣ ዱባይ፣ አቡዳቢ እና አል ዓይን ከተሞች አገልግሎት የሚሰጥ ሲሆን ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን ለመሥራት እንቅስቃሴው ተጀምሯል፡፡  

 

  • ምንጭ፡- ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ 20ኛ ዓመት ቁጥር 19 ከሰኔ 1-15 ቀን 2005 ዓ.ም.