የአሜሪካ ማእከል ልዩ ዐውደ ጥናት ሊያካሒድ ነው

ሐምሌ ፮ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በአሜሪካ ማእከል

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን የአሜሪካ ማእከል *የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አስተዋጽኦ* በሚል ርእስ በፕሪንስተን ከሚገኘው /The Institute for Advanced Semitic Studies and Afroasiatic Studies/ በመባል ከሚታወቀው የሴሜቲክና የአፍሮ እስያ ከፍተኛ ምርምርና ጥናት ተቋም ጋር በመተባበር ሐምሌ ፳፬ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ልዩ ዐውደ ጥናት ያካሒዳል።

ዐውደ ጥናቱ በዋናነት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በተለያየ ዘርፍ ለኢትዮጵያና ለዓለም ያበረከተችውን አስተዋጽኦ በጥልቀት እንደሚዳስስና ቤተ ክርስቲያኗ ይህንን አስተዋጽኦና ሚናዋን በዘመናችን እንዴት ማስቀጠል እንዳለባት እንደሚመክር አዘጋጆቹ አስታውቀዋል።

ይህ ዐውደ ጥናት በታዋቂው የአሜሪካ ዩኒቨርሲቲ ውስጥ መደረጉ የቅድስት ቤተ ክርስቲያናችንን አስተዋጽኦ ለዓለም ለማስተዋወቅ መልካም አጋጣሚ እንደሚፈጥርም ተጠቁሟል፡፡

በዐውደ ጥናቱ የፕሪንስተን ዩኒቨርሲቲ ፕሮፌሰር የኾኑት ኤፍሬም ይስሐቅ *የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን* በሚል ርእስ ያሳተሙት መጽሐፍ ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ስለሚኖረው ፋይዳና በመጽሐፉ ጠቅላላ ይዘት ላይ ሰፊ ውይይት ይደረጋል፡፡

በአሜሪካ አህጉረ ስብከት ሊቃነ ጳጳሳት መልካም ፈቃድ በሚዘጋጀው በዚህ ልዩ ዐውደ ጥናት ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ ካህናት፣ ምሁራን፣ የአሜሪካ ግዛቶችና የአካባቢው ምእመናን፣ እንደዚሁም የውጪ ሀገር ዜጎችና ተጋባዥ እንግዶች እንደሚሳተፉበት ከጥናቱ አዘጋጆች ለመረዳት ተችሏል።