St_Anthony_Icon_3.jpg

የበረሃዉ መልአክ ቅዱስ እንጦንስ

በተ/ሥላሴ ጸጋ ኪሮስ
 
St_Anthony_Icon_3.jpgእንደተለመደው የኦሪት ዘፍጥረትን ትርጓሜ መሠረት ያደረገውን ተከታታይ ትምህርት ለመማር በማኅበረ ቅዱሳን ሕንጻ ውስጥ ካሉት አዳራሾች በአንዱ ተሰብስበናል፡፡  ትምህርቱ ከመጀመሩ በፊት በወረቀት ለሚጠየቁት ጥያቄዎች የሚሰጡት መልሶች ሁላችንም ስለሚያጓጓን በመጠባበቅ ተቀምጠናል። ከመምህራችን የቀረበው የዕለቱ ጥያቄ ግን ሌላ ነበር። «ዛሬ ቀኑ ስንት ነው?» የሚል፡፡ ጥር 22 በማለት መለስን፡፡ «ዛሬ የዕለቱ መታሰቢያነት ለማን ነው?» ቀጥሎ ጠየቀን፡፡ መቼም ቅዱስ ዑራኤል መሆኑን አያጣውም፣ ግን ለምን ጠየቀን? በአእምሮዬ የሚመላለስ ጥያቄ ነበር፡፡ ለነገሩ ዕለቱ የተለየ ነገር ቢኖረው ነው እንጂ አይጠይቀንም ነበር፡፡ ይሄን እያሰብኩኝ ዝምታ በሰፈነበት፥ አንድ ልጅ እጁን አነሳና «የመልአኩ የቅዱስ ዑራኤል በዓል ነው» በማለት መለሰ፡፡ መምህራችንም ጥሩ ነው በማለት ተናገረና  «ሌላስ?» አለ በተረጋጋ አንደበት፡፡ ከዚህ በላይ እንኳን የማውቀው ነገር የለም አልኩኝ ለራሴ፡፡
 
ለማንኛውም በዚህ ዕለት ታላቁ አባት ርእሰ መነኮሳት ቅዱስ እንጦንስ ያረፈበት ዕለት ነው፡፡ ጽሌውም (የጽላት ነጥላ ቁጥር) በዋና ከተማችን አዲስ አበባ በምትገኘው መንበረ ፓትርያርክ ቅድስተ ቅዱሳን ማርያም ገዳም ይገኛል፡፡ በርግጥ በራሱ ስም የተሰሩ ገዳማትም አሉ። ይህ የአዲስ አበባዉ ግን የእመቤታችን ጽሌ ከመምጣቱ በፊት  በቅዱስ እንጦንስ ስም ይጠራ እንደ ነበር ሁሉ ተነገረን። ይሄንን ስንቶቻችን እናውቅ ይሆን? የእኔ ጥያቄ ነበር። ለምን ለሌሎች አላካፍለውም? ሌላ ጥያቄ፤ እነሆ። (ሥዕል፦ቅዱስ እንጦንስ፥  ከታች በግራ በኩል ቅዱስ እንጦንስና የዋህ ጳውሊ ሲገናኙ )

ቅዱስ እንጦንስ በ25ዐ ዓ.ም ቅማን/Qimn El-Arouse/ በሚባል በማዕከላዊ ግብጽ ነው የተወለደው፡፡ ከዕለታት አንድ ቀን በቤተክርስቲያን ሳለ ወንጌል ሲነበብ ጌታችን ለባለፀጋው ጎልማሳ የነገረውን «ፍፁም ልትሆን ብትወድ ያለህን ሁሉ ሸጠህ ለድኾች  ሰጥተህ ተከተለኝ» የሚለውን የእግዚአብሔርን ጥሪ ስለሰማ ወላጆቹ ከታናሽ እህቱ ጋር ትተውለት የሞቱትን ሰፊና በመስኖ የሚለማ መሬት ቶሎ ሽጦ ለድሆች ከሰጠ በኋላ እህቱን ለደናግል ማኅበር አደራ ሰጥቶ የብሕትውና ኑሮውን ጀምሯል፡፡

ቅዱስ እንጦንስ በብዙ ተጋድሎና ፈተና በመካከለኛው የግብጽ በረሃ ውስጥ ብቻውን የኖረ ከዚያም ብዙ ተከታዮችን ያፈራ፣ የምንኩስና ሕይወትም ጀማሪ የሆነ አባት ነው፡፡

ቅዱስ እንጦንስ፣ የቅዱስ አትናቴዎስ ሐዋርያዊ ወዳጁም ነበር፡፡ ርእሰ ባህታውያን የዋህ ጳውሊንም ከፍኖ የቀበረው ቅዱስ አትናቴዎስ በሰጠው ካባ ሲሆን በመልሱም ለቅዱስ አትናቴዎስ የቅዱስ ጳውሊን ለራሱ ከዘንባባ የሠራውን እንደታታ ቅርጫት የመሰለውን ዐፅፍ ልብስ ሰጥቶታል፡፡ ቅዱስ አትናቴዎስም በበዓለ ትንሣኤና በበዓለ ሃምሣ በውስጥ ይለብሳት ነበር፡፡

ቅዱስ እንጦንስና ዘመነ ሰማዕታት

በክርስቲያኖች ላይ መከራና ሞት በዓላውናን ነገሠታትና መኳንንት በታዘዘ ጊዜ ብዙ ክርስቲያኖች ስለ ክርስቶስ ፍቅር እንደበግ እየተነዱ ወደሞት ይሔዱ ነበር፡፡ በዚህ ጊዜ ቅዱስ እንጦንስ ከበአቱ ወጥቶ ወደ እስክንድርያ ሔደ÷ ተጠርተንም እንደሁ በእሽቅድምድም ለመሳተፍ አለበለዚያ ተሽቀዳዳሚዎችን ለመጎብኘት እንሒድ በማለት እንጦንዮስ ሰማዕትነትን ለመቀበል ከፍተኛ ጉጉት ነበረው፡፡ ነገር ግን እርሱን የብሕትውናና የምንኩስና ሕይወት አስተማሪ ይሆን ዘንድ ስለ ብዙዎች ጥቅም ጠበቀው፡፡ ሰማዕታት ለፍርድ ሲጠሩ አጅቦ ይሸኛቸዋል÷ እስኪገደሉም ድረስ አይለያቸውም፡፡ ዳኛው ድፍረቱንና የተከታዮቹን ብዛት ጽኑ መንፈሳቸውንም ባየ ጊዜ ማንም መነኩሴ ወደ ፍርድ ቤት አካባቢና በከተማው ውስጥ እንዳይታይ አዘዘ፡፡
እንጦንስ ግን ሰማዕታትን አጅቦ ከፍርድ ቤት ፊት ለፊት ዳኛው ሊያየው በሚችል ስፍራ ተገኘ። ሁሉም በመገኘቱ ሲደነቁ ኃላፊው በትሩን ይዞ ወደ እርሱ መጣ፥ እርሱ ግን የክርስቲያኖችን ጽኑ መንፈስ ያሳይ ዘንድ ምንም ሳይፈራ ቆመ።
 
    ምንጭ፡ ያረጋል አበጋዝ (ዲ/ን) ና አሉላ ጥላሁን ፣ 1997። ነገረ ቅዱሳን 3። ማኅበረ ቅዱሳን፣ አ.አ።