የሩቅ ምሥራቅ ግንኙነት ጣቢያ በህንድ ሀገር ፭ተኛ ዙር ሐዊረ ሕይወት አደረገ

         ሕይወት ሳልለው

 

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን፣ በሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ  የማኅበረ ቅዱሳን የሩቅ ምሥራቅ ግንኙነት ጣብያ በህንድ ሀገር የሚኖሩ አባላቱንና ምእመናንን በማስተባበር ከጥር ፲፭ እስከ ጥር ፳፩ ቀን  ፳፻፲፩ ዓ/ም ወደ ኬሬላ ፭ተኛውን ዙር የሐዊረ ሕይወት ጉዞ አካሄደ፡፡

በአባ ጂኦ ዮሴፍ መሪነት ፺፱ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃይማኖት ተከታዮች መንፈሳዊ ጉዞ አድርገዋል፡፡ በህንድ ኬሬላ ግዛት ኮታይም ከተማ ወስጥ በሚገኙ ቅዱስ ጊዮርጊስና የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ቤተ ክርስቲያን  ማርታ ማርያም ኦርቶዶክስ ሴርያን ቤተ ክርስቲያን፣ የመነኮሳት ገዳም፣ ማር ባስልዮስ ገዳም እንዲሁም የኦርቶዶክስ ቲኦሎጂካል (ነገር መለኮት) ሴሚናሪ እና የማር ባስልዮስ ክርስቲያን የኢንጅነሪንግና ቴክኖሎጅ ኮሌጅንም በዋነኛነት ጎብኝተዋል፡፡

ኮትያም ወደሚገኘው ኦርቶዶክስ መንፈሳዊ ኮሌጅ በተደረገው ጉዞ ላይ ለምእመናኑ፤ “የቤተ ክርስቲያን ምሥጢራት” በሚል ርእስ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያንን ከህንድ ቤተ ክርስቲያን ጋር ያነጻጸረ ትምህርት በዶ/ር ረጂ ማቲው ተሰጥቷል :: በዚሁ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ በተማሪዎች የበገና መዝሙርና በህንዳውያን ዘማሪዎች በህንድ ቋንቋ የተዘጋጀ መዝሙር በጋራ ቀርቧል፡፡ በጉዞው ላይ የነበሩት አባ ኦ ቶማስም “የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን በባህልና በበርካታ ንዋያተ ቅድሳት የታጀበች ናት” ሲሉ አድነቀዋል፡፡  በሐዋርያው ቅዱስ ቶማስ የተመሠረተችው ዘቫላካራ ማርታ ማርያም ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን በቀድሞው የኢትዮጵያ ፓትርያርክ አቡነ ጳውሎስ እንደተጎበኘ አባ ጂኦ ለምእመናኑ አስታውቀዋል፡፡፡፡

ከማእከሉ በአውቶብስ ሦስት ሰዓት፤ በጀልባ አንድ ሰዓት ተኩል የሚፈጀው እና በደሴት ወደተከበበው የቅዱስ ቶማስ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ጉዞም ያደረጉ ሲሆን ቤተ ክርስቲያኗ በቁጥር ትንሽ አባላት እና ጥቂት አገልጋይ እንዳሏትም አስገንዝቧቸዋል፤ ከዚህ ባሻገር በቅዱስ ቶማስ የተመሠረተችው የቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን ውስጥ በወቅቱ ሲጠቀሙበት የነበሩት ባህላዊ ቅርሶችና ንዋየ ቅድሳትን ጎብኝተዋል፡፡ የጉዞው ተሳታፊዎችም “ከቦታው በረከትን አግተኝናል” ሲሉም የምስክርነታቸውን ቀል ሰጥተዋል፡፡

በከበሮ፣ በጸናጽል፣ በመቋሚያና በበገና ህብር የቀረበው ያሬዳዊ ዝማሬ መርሐ ግብር ላይ ሰፊ ማብራሪያ የሰጠው መ/ር ሳምሶን ስለመሳሪያዎቹ ለህንድ አባቶችና ለምእመናን ገለጻ አድርጓል፡፡ ስለአጠቃላይ መርሐግብሩ ከተሳታፊዎች ሐሳብ ተሰብስቦ፣ የአጋጠማቸው ችግሮች ላይ ውይይት በማድርግና የመፍተሔ አቅጣጫ በመስጠት፣ ፭ተኛው ዙር ሐዊረ ሕይወት  በሰላም ተጠናቋል፡፡