ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ እና ነቢዩ ኤልያስ

 ቅዱስ ዮሐንስ በበርካታ መንገዶች ከነቢዩ ኤልያስ ጋር ተያይዟል፡፡ነቢዩ ሚልክያስ ስለ ቅዱስ ዮሐንስ መምጣትና መንገድ ጠራጊነት ሲናገር እንዲህ ብሎ ነበር፡፡

«እነሆ ታላቁና የሚያስፈራው የእግዚአብሔር ቀን ሳይመጣ ቴስቢያዊውን ኤልያስን እልክላችኋለሁ … እርሱም የአባቶችን ልብ ወደ ልጆች፣ የልጆችንም ልብ ወደ አባቶች ይመልሳል፡፡» /ሚል.4÷5-6/

መልአኩ ቅዱስ ገብርኤልም የቅዱስ ዮሐንስን መወለድ ለአባቱ ለዘካርያስ በቤተ መቅደስ ሲያበሥረው እንዲህ ብሎ ነበር፡፡

«… እርሱም የአባቶችን ልብ ወደ ልጆች የከሐድያንንም ሐሳብ ወደ ጻድቃን ዕውቀት ይመልስ ዘንድ ሕዝብንም ለእግዚአብሔር የተዘጋጀ ያደርግ ዘንድ በኤልያስ መንፈስና ኃይል በፊቱ ይሄዳል» /ሉቃ.1÷17/

በዚህም ምክንያት ሕዝቡ ከመሲህ መምጣት በፊት የኤልያስን መምጣት ይጠብቁ ነበር፡፡ ለምሳሌ ጌታችንን ደቀመዛሙርቱ «ጻፎች ኤልያስ አስቀድሞ ይመጣ ዘንድ አለው ለምን ይላሉ?» ብለው ጠይቀውት ነበር፡፡ /ማቴ.17÷10፣ ማር.9÷11/

ጌታችንም ኤልያስ ይመጣል ተብሎ የተነገረው ስለ መጥምቁ ዮሐንስ መሆኑን እንዳስረዳቸው እነርሱም እንደተረዱ ቅዱስ ማቴዎስ ይነግረናል /ማቴ.17÷11-13/

«ጌታችን ኢየሱስም መልሶ እንዲህ አለችው «አዎን፤ ኤልያስ አስቀድሞ ይመጣል፤ ሁሉንም ያቀናል፡፡ ነገር ግን እላችኋለሁ፡፡ ኤልያስ ፈጽሞ መጥቷል፤ የወደዱትንም አደረጉበት እንጂ አላወቁትም …» ከዚህም በኋላ ደቀመዛሙርቱ ስለ መጥምቁ ዮሐንስ እንደነገራቸው አወቁ፡፡»

ከአንድ ታላቅ እና ታዋቂ ሰው በኋላ የሚነሱ ደጋግ ሰዎችን በእዚያ በታላቁ ሰው ስም መጥራት በትንቢቶች ውስጥ የተለመደ ነው፡፡ ለምሳሌ ቅዱስ ዳዊት እሥራኤላውያን የሚወዱትና ትልቅ ቦታ የሚሰጡት ንጉሣቸው ነው፡፡ ቅዱስ ዳዊት ካለፈ በኋላ እግዚአብሔር ደጋግ ነገሥታትን እንደሚያስነሳላቸው ለእሥራኤል ተስፋ ሲሰጥ ዳዊትን አስነሳላችኋለሁ ይላቸው ነበር፡፡

«ባርያዬም ዳዊት በላያቸው ላይ ንጉሥ ይሆናል፤ ለሁሉም አንድ እረኛ ይሆንላቸዋል» /ሕዝ.37÷24/

«ለእግዚአብሔርም ለማስነሣላቸው ለንጉሣቸው ለዳዊትም ይገዛሉ» /ኤር.3ዐ ÷9/፡

አሁንም የተደረገው ይኸው ነው፡፡ አይሁድ ኤልያስን በጣም ይወዱትና ያከብሩት ነበር፡፡ አሁንም ድረስ ያሉ አይሁዳውያን የፋሲካን በዓል በሚያከብሩበት ዕለት ለማዕድ ሲቀመጡ «ለኤልያስ» ብለው አንድ ቦታ ይተዋሉ፤ የወይን ጠጅ የተሞላ ብርጭቆም ያስቀምጣሉ፡፡ የቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ መምጣት «ኤልያስ ይመጣል» ተብሎ የተነገረው ለዚህ ነው፡፡ «እንደ ኤልያስ ያለ የኤልያስን ዓይነት ሥራ የሚሠራ ነቢይ ይወጣል» ማለት ነው፡፡ ቅዱስ ገብርኤልም ለካህኑ ለዘካርያስ የተናገረው ይህንኑ የሚያመለክት ነው፡፡ «…በኤልያስ መንፈስና ኃይል በፊቱ ይሄዳል…»

በእርግጥም ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅን እና ነቢዩ ኤልያስን ብዙ የሚያመሳስሉአቸው ነገሮች አሉ፡፡

–    አለባበሳቸው፡- የነቢዩ ኤልያስ አለባበስ በሁለተኛው መጽሐፈ ነገሥት እንዲህ ተብሎ ተገልጿል፡፡ «እነርሱም ሰውየው ጠጉራም ነው፡፡ በወገቡም ጠፍር ታጥቆ ነበር አሉት፡፡ እርሱም ቴስብያዊው ኤልያስ ነው አለ» /2ኛነገ.1÷8/

–    ትምህርታቸው፦ የሁለቱም ነቢያት ትምህርት ትኩረት የእስራኤል ሕዝብ ኃጢ አታቸውን ትተው ወደ እግዚአብሔር እንዲመለሱ ማድረግ ሲሆን፤ የሁለቱም ተግሳጽ የተሞላበት ነበር፡፡ ለምሳሌ ነቢዩ ኤልያስ «የእግዚአብሔር ከሆናችሁ የእግዚአብሔር ብቻ ሁኑ፤ የበአል /የጣኦት/ ከሆናችሁ የበአል /የጣኦት/ ብቻ ሁኑ» እያለ ጠንካራ ንግግሮች ይናገር ነበር፡፡

–    ነገሥታትን መገሰጻቸው፡- ነቢዩ ኤልያስ ንጉሡን አክአብንና ንግሥቲቱ ኤልዛቤልን ናቡቴን ርስቱን ቀምተው በግፍ በማስገደላቸው ገስጿቸዋል፡፡

ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ይህንን አስመልክቶ ባስተማረው ትምህርት «በእርግጥም የቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ ትህርምት እጅግ የሚያስደንቅ ነበር፤ አይሁድንም በእርሱ ውስጥ ነቢዩ ኤልያሰን እንዲያዩ አድርጓቸዋል» ብሏል፡፡

የቅዱስ ዮሐንስ ክብር እና መዓርጋት

ቅዱስ ዮሐንስ ክብሩ በጣም ከፍ ያለ ነው፡፡ የክብሩ ምስክሮችም ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እና መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ናቸው፡፡

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንዲህ ሲል የመጥምቁን ክብር ተናግሯል፡፡

«ምን ልታዩ ወደ ምድረ በዳ ወጥታችኋል? ከነፋስ የተነሣ የሚወዛወዛውን ሸንበቆ ነው? ወይስ ምን ልታዩ መጥታችኋል ቀጭን ልብስ የለበሰ ሰውን ነውን? እነሆ ቀጭን ልብስ የሚለብሱማ በነገሥታት ቤት አሉ? ምን ልታዩ መጥታችኋል ነቢይ ነውን? አዎን እርሱ ከነቢያት እጅግ ይበልጣል፤ እነሆ በፊትህ መንገድህን የሚጠርግ መልእክተኛዬን እልካለሁ ተብሎ ስለ እርሱ የተጻፈለት ይህ ነውና፡፡ እውነት እውነት እላችኋለሁ ሴቶች ከወለዷቸው ወገን ከመጥምቁ ዮሐንስ የሚበልጥ አልተነሣም» /ማቴ.11÷7-11/

መልአኩ ቅዱስ ገብርኤልም እንዲህ ሲል ክብሩን ተናግሮለታል፡- «እርሱ በእግዚአብሔር ፊት ታላቅ ይሆናል» /ሉቃ.1÷15/

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ሺኖዳ «የቅዱስ ዮሐንስ ክብር እና ከፍ ከፍ ማለት ምንጮች ሁለት ናቸው፡፡» ይላሉ፡፡

1. በመንፈስ ቅዱስ የተሞላ ስለሆነ

ከመጥምቁ ዮሐንስ በፊት የእግዚአብሔር መንፈስ ወደ ብዙ ሰዎች መምጣቱ ተጽፏል፡፡ ለምሳሌ ያህልም

–  ሳሙኤል ሳኦልን ቀብቶ ባነገሠው ጊዜ «የእግዚአብሔር መንፈስ በእርሱ ላይ ወረደ» ተብሏል /1ኛሳሙ.10÷10/፡፡

–  ሳሙኤል ዳዊትን በንግሥና በቀባው ጊዜ «የእግዚአብሔር መንፈስ ከዚያ ቀን ጀምሮ በዳዊት ላይ መጣ» ተብሏል 1ኛ ሳሙ.16÷13፡፡

–  «የእግዚአብሔር መንፈስ ከሶምሶን ጋር ይሄድ ነበር» ተብሎም ተጽፏል /መሳ.13÷24/፡፡

ይሁን እንጂ የእግዚአብሔር መንፈስ «ሞልቶታል» የተባለ ግን ማንም አልነበረም፡፡ መጥምቁ ዮሐንስ ግን በመንፈስ ቅዱስ የተሞላ ነበር፡፡ የከበረ እና ታላቅ በመሆኑ አንዱ ምክንያት ይህ ነው፡፡

በመንፈስ ቅዱስ የተሞላው ግን መቼ ነበር? በመንፈስ ቅዱስ የተሞላው ገና በማኅፀን ሳለ እናቱ ኤልሳቤጥ የእመቤታችንን የሰላምታ ድምፅ በሰማችበት ቅፅበት ነው፡፡

«ኤልሳቤጥም የማርያምን ሰላምታ በሰማች ጊዜ፤ ፅንሱ በማኅፀኗ ዘለለ፤ በኤልሳቤጥም መንፈስ ቅዱስ መላባት» /ሉቃ.1÷14/

መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል «ከእናቱ ማኅፀን ጀምሮ መንፈስ ቅዱስ ይመላበታል» ብሎ የተናገረው በዚህን ጊዜ ተፈጽሟል፡፡

2. ተጋድሎው

የመንፈስ ቅዱስ ስጦታ በእኛ ሕይወት ፍሬ ሊያፈራ የሚችለው እኛ በድርጊታችንና በተጋድሎአችን ስንጠብቀው፣ ስንንከባከበውና ስንሠራበት ነው፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ ይህንን በሚገባ አድርጓል፡፡

ቅዱስ ዮሐንስ ያደገው በበረሃ ውስጥ፣ በብሕትውና /በብቸኝነት/፣ የግመል ጠጉር እየለበሰ፣ አንበጣ እና የበረሃ ማር ብቻ እየተመገበ ነው፡፡ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ሺኖዳ እንዲህ ብለዋል «እርሱ በበረሃው ውስጥ ጸሎትና ተመስጦን፣ ድፍረትን እና ፍርሃት አልባነትን፣ ጥንካሬን እና እምነትን ተምሯል፡፡ እግዚአብሔር እመቤታችንን አምላክን ፀንሣ ለመውለድ በቤተ መቅደስ እንዳዘጋጃት እርሱን ደግሞ ለመንገድ ጠራጊነት ተልእኮው በበረሃ አዘጋጅቶታል፤ እኛም የእነዚህ ነገሮች ባለቤት ለመሆን የብቸኝነትና የትህርምት ጊዜ የምናሳለፍበት የየራሳችን በረሃ ያስፈልገናል፡፡»

የቅዱስ ዮሐንስ መዓርጋት

ቅዱስ ዮሐንስ በርካታ መዓርጋት አሉት፤ የተወሰኑትን ቀጥለን እንመለከታለን፤

–  መጥምቅ /መጥምቀ መለኮት/፡- ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን በማጥመቁ

–  ነቢይ ከእኔ በፊት የነበረውና ከእኔ የሚበልጠው ይመጣል ብሎ ትንቢት በመናገሩ

–  ካህን ሕዝቡን በማጥመቁ

–  ወንጌላዊ ያስተማረው ትምህርት እንደነቢያቱ ይመጣል ይወለዳል ብቻ ሳይሆን መጥቷል፣ ተወልዷል፣ እነሆ በመካከላችሁ ቆሟል የሚል ለመሆኑ፤ እንደ ነቢያቱ ለቅጣት ምርኮን፣ ለስጦታ /ደስታ/ ምድረ ከነዓንን ሳይሆን ለቅጣት የዘለዓለም ሕይወትን፤ ለስጦታ መንግሥተ ሰማያትንና ገሃነመ እሳትን ማስተማሩ፤ የሥነ ምግባር ትምህርቱም እንደ ወንጌል ትሩፋትን የሚሰብክ በመሆኑ

–  ርእሰ ዓውደ ዓመት ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ በብሉይ ኪዳን እና በሐዲስ ኪዳን መሸጋገሪያ ላይ የነበረ ነቢይ በመሆኑ የዓመቱ መጀመሪያና የዘመን መለወጫ በዓል በሆነው መስከረም አንድ ቀን የእርሱ መታሰቢያ እንዲደረግበት፣ በዓሉም «ቅዱስ ዮሐንስ» ተብሎ እንዲጠራ አባቶቻችን ወስነዋል፡፡ ቅዱስ ያሬድም በድጓው «ውስተ ርእሰ ዓውደ ዓመት ተጽሕፈ ተዝካርከ፤ ባርከኒ እንሣእ በረከተከ»፤ «መታሰቢያህ በርእሰ ዓውደ ዓመት ተጻፈ፤ በረከትህን አገኝ /እውሰድ/ ዘንድ «ባርከኝ» ብሎ ምሥጋናና ጸሎት ደርሷል፡፡

ከዚሁ ጋር በተያያዘ መልክአ ዮሐንስ ደግሞ «ርእሰ ዓውደ ዓመት ዮሐንስ ወላዴ መጥቅዕ ወአበቅቴ» ይለዋል /ሠላም ለሥዕርተ ርእስከ/፡፡ «የመጥቅዕ እና የአበቅቴ ወላጅ፣ አስገኚ» ማለት ነው፡፡ ይህም ስም የተሰጠው የዓመቱ ክብረ በዓላት የሚውሉባቸው ቀናትና ዕለታትን ለማስላት የሚጠቅሙት መጥቅዕ እና አበቅቴ የሚባሉት ቁጥሮች በዚሁ በመስከረም አንድ ቀን ስለሚወጡ /ስለሚስሉ/ ነው፡፡

–  ሰማእት /ምስክር/፡- ስለጌታችን አምላክነትና መድኃኒትነት እንዲሁም ስለ እውነት ስለመሰከረ፤ በመጨረሻም በአላውያን ነገሠታት እጅ ስለ ተገደለ፡፡

ከእነዚህ ሁሉ ስሞች የሚበልጠው ግን መጥምቅ /መጥምቀ መለኮት/ የሚለው ነው፡፡ ምክንያቱም ቅዱስ ዮሐንስ ካደረጋቸውና ከሆናቸው ነገሮች ሁሉ የሚበልጠው አምላክን ማጥመቁ ነው፡፡ ጌታችንም ስለ እርሱ ክብር በተነገረ ጊዜ «እውነት እላችኋለሁ፤ ሴቶች ከወለዱአቸው ወገን ከመጥምቁ ዮሐንስ የሚበልጥ አልተነሣም…» በማለት ይህንን ስያሜ አጽድቆለታል፡፡

ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ ለእኛ

ቅዱስ ዮሐንስ በዘመኑ የነበሩ ሰዎችን ገሥጾና አስተምሮ ወደ እግዚአብሔር አቅርቧቸዋል፡፡ እኛስ በዚህ ዘመን ያለን ሰዎች ከእርሱ ምን እንጠቀማለን? ሁለት ነገሮችን መጥቀስ ይቻላል፡፡

1. ያስተምረናል፡፡
2. ያማልደናል፡፡

1. ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ ያስተምረናል

ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ በቃሉ /በስብከቱ/፣ በሕይወቱ እና በአገልግሎቱ ዛሬ ድረስ ያስተምረናል፡፡

ሀ. በስብከቱ /በቃሉ/ ያስተምረናል

አንድ ሰው የድኅነትን ጸጋ /ስጦታ/ ከእግዚአብሔር ዘንድ ለመቀበል ሦስት ነገሮች ያስፈልጉታል፡፡ እነዚህም እምነት፣ ምሥጢራትን መካፈል እና ምግባር ናቸው፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ በእነዚህ በሦስቱም ዙሪያ ትምህርቶችን ያስተምረናል፡፡

እምነት፡- ቅዱስ ዮሐንስ «አብ ወልድን ይወዳል፤ ሁሉንም ነገር፤ በእጁ ሰጥቶታል፡፡ በወልድ የሚያምን ሁሉ የዘለዓለም ሕይወት አለው፤ በወልድ የማያምን ግን የእግዚአብሔር ቁጣ በእርሱ ላይ ይሆናል እንጂ ሕይወትን አያይም» እያለ ምሥጢረ ሥላሴን ምሥጢረ ሥጋዌን ያስተምረናል፤ ካላመንም የዘለዓለም ሕይወት እንደሌለን ይነግረናል፡፡

ምስጢራትን መካፈል፡- ቅዱስ ዮሐንስ «መንግሥተ ሰማያት ቀርባለችና ንስሐ ግቡ፡፡»፣ «ከእኔ በኋላ የሚመጣው በመንፈስ ቅዱስ እና በእሳት ያጠምቃችኋል»፣ «የዓለምን ኃጢአት የሚያስወግድ የእግዚአብሔር በግ እነሆ» እያለ ምሥጢራትን /ምስጢረ ጥምቀት፣ ምስጢረ ንስሐን እና ምስጢረ ቁርባንን/ እንድንካፈል ያስተምረናል፡፡

ምግባር፡- «እናንት የእፉኝት ልጆች ለመሆኑ ከሚመጣው ቁጣ እንድታመልጡ ማን መከራችሁ፤ ለንስሐ የሚገባ ፍሬ አፍሩ፤ … እነሆ ምሳር የዛፎችን ሥር ሊቆርጥ ተዘጋጅቷል፤ መልካም ፍሬ የማያፈራ ዛፍ ሁሉ ይቆረጣል፤ ወደ እሳትም ይጣላል፡፡» እያለ ምግባር እንድንሠራ ያስተምረናል፤ ያስጠነቅቀናል።

ለ/ በሕይወቱ ያስተምረናል

ከቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ በሕይወቱ እግዚአብሔርን ያስደሰተ፤ «ከሴቶች ከተወለዱ የሚያህለው የለም» የተባለለት ስለሆነ አርአያ ልናደርገው፤ ለዚህ ክብር ያበቃውን ነገር ልንመረምርና በመንገዱ ልንከተለው ይገባናል፡፡ ከሕይወቱ ብዙ ልንማራቸው የሚገቡ ነገሮች ቢኖሩም ጥቂቶቹን ለጊዜው እንመልከት፡-

ትሁት ነው፡- ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ ጌታ «ከሴቶች ከተወለዱት ወገን የሚያህለው የለም» እያለ ቢያመሰግነውም እርሱ ግን ያሉትን መልካምና ታላላቅ ነገሮች በሙሉ ችላ ብሎ «እኔ የጫማውን ማሰሪያ ልፈታ የማይገባኝ ነኝ» ይል ነበር፡፡ በዚህም ምክንያት ቅዱስ ያሬድ «ዘወጠነዝ ትርሢተ ክብር ትሕትና ወፍቅር ትሕትና ወፍቅር ርእዮ እበዩ ለዮሐንስ…» እያለ የቅዱስ ዮሐንስ የክብሩ ጌጥ፣ የታላቅነቱ ምንጭ ትሕትናው እና እግዚአብሔርን ማክበሩ መሆኑን ይገልጻል፡፡ እመቤታችን በጸሎቷ «ትሁታንን ግን ከፍ ከፍ አደረጋቸው» /ሉቃ.1÷52/ እንዳለችው እርሱ ትሁት ሲሆን እግዚአብሔር ከሁሉ በላይ አከበረው፡፡ የቅዱስ ዮሐንስ ትሕትና ግን ምንጩ ምንድን ነው?

ትሕትና ማለት ምንም ነገር የሌለው መሆን ማለት አይደለም፡፡ እግዚአብሔር በባሕርይው ትሁት ነው፡፡ ጌታ «ከእኔ ተማሩ፣ እኔ ትሁት ነኝ» ይላል፡፡ የእግዚአብሔር ትሕትና ምንጩ ክቡር፣ ባዕለ ጸጋ መሆኑ ነው፡፡ የቅዱስ ዮሐንስ ትሕትና ምንጭም ይኸው ነው፤ በእምነትና በምግባር ያጌጠ ባለ ብዙ ፍሬ ባለ ጸጋ መሆኑ ማንም ትሕትናን የሚፈልጋት ቢኖርም ማድረግ ያለበት ይህንኑ ነው፤ ባለብዙ ምግባር፤ ባለ ትልቅ እምነት መሆኑ፤ ያን ጊዜ ትሕትናው አብሮ ይመጣል፡፡

ሁለተኛው የቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ ትሕትና ምንጭ የእግዚአብሔርን ማንነትና ባሕርይ በሚገባ ማወቁ፤ የራሱን ማንነቱንና አቅሙንም መረዳቱ ነው፡፡ እኛም ትሕትናን ገንዘብ ልናደርግ ብንወድ የእግዚአብሔርን ማንነት፣ ባሕርይ፣ እና ክብር የተቻለንን ያህል ለማወቅ መጣር፤ ራሳችንንም ዘወትር መመርመር፣ ድካማችንን መረዳትና ይህንንም ደግመን ደጋግመን ለራሳችን መንገር አለብን፡፡

ጸጋውን ተጠቅሞ ፍሬ አፍርቷል፡ – ቅዱስ ዮሐንስ በእናቱ ማኅፀን ሳለ መንፈስ ቅዱስ መልቶበት ነበር፡፡ እርሱም ይህንን ጸጋውን አትርፎበታል፤ሕዝቡም ካህናቱም አመጸኞች በነበሩበት በዚያ አስከፊ ዘመን /ሐዋ.5÷3ዐ-39/ ጻድቅ ሆኖ ተገኝቷል፤ ለራሱ ብቻ ሳይሆን ለሌሎችም በረከት ሆኖ ነበር፡፡ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ሺኖዳ እንዳሉት ለዚህ የበቃው «የበረሃ እና የተራሮች ልጅ» በመሆኑና በብህትውና /በብቸኝነትና/ እና በትህርምት በመኖሩ ነው፡፡

እያንዳንዳችን ከጥምቀታችን ቀጥሎ በሚፈጸምልን ምሥጢረ ሜሮን አማካኝነት መንፈስ ቅዱስ ያድርብናል፡፡ ይህንን ተጠቅመን ሥራ ለመሥራት እኛም እንደ መጥምቁ የራሳችን በረሃ ያስፈልገናል፤ በትህርምትና ራስን በመግዛት መኖር አለብን፡፡

ይህንን ማድረግ የሚገባቸውና የሚችሉት በገዳም ያሉ ሰዎች ብቻ አይደሉም፡፡ በዓለም የምንኖር ሰዎችም ብቻችንን የምንሆንበትና በጸሎት፣ በተመስጦ፣ ቅዱሳት መጻሕፍትን በማንበብ፣ ራሳችንን በመመርመር የምናሳልፈው ጊዜ በመመደብ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ በወጣትነት ዘመኑ እንዳደረገው መኖሪያ ቤቶቻችንን ገዳማት ማድረግ እንችላለን፡፡ ሁኔታዎችን እያመቻቸን ወደተለያዩ ገዳማት እየሄድን ጊዜ ማሳለፍም ጠቃሚ ነው፡፡

ከዚህም በተጨማሪ ምግባችንን፣ መጠጣችንን እና ልብሳችንን በልክ እያደረግን መጥምቁን ባለ ብዙ ፍሬ በሆነበት ጎዳናው ልንከተለው ያገባናል፡፡

በአግልግሎቱ ያስተምረናል፡ -ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ሺኖዳ ከቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ አገልግሎት ልንማራቸው የሚገቡ በርካታ ቁም ነገሮች አሉ በማለት የሚከተሉትን ይዘረዝራሉ፡፡

ቅድስ ዮሐንስ ያገለገለው ለአጭር /ከስድስት ወራት ብዙ ላልበለጠ/ ጊዜ ብቻ ቢሆንም በርካታ ሥራዎችን ሠርቶ አልፏል፡፡ እኛም አገልግሎታችንን ልንመዝነው የሚገባን በርዝመቱ ሳይሆን በጥልቀቱ፣ በውጤታማነቱ፣ በሚያፈራው ፍሬ እና በሚያመጣው ለውጥ ነው፡፡

ቅዱስ ዮሐንስ ሲያገለግል ዓላማው ሰዎችን ከእግዚአብሔር ጋር ማገናኘት እንጂ ሰዎችን በእርሱ ዙሪያ መሰብሰብና መክበር አልነበረም፡፡ ቅዱስ ማቴዎስ በወንጌሉ እንደሚነግረን «ከኢየሩሳሌም፣ ከመላው ይሁዳ፣ በዮርዳኖስ ዙሪያ ባለው ነገር ሁሉ ሰዎች ወደ እርሱ ይጎርፉ ነበር፡፡» /ማቴ.3÷5-6/ እርሱ ግን «እኔ በውኃ ለንስሐ አጠምቃችኋለሁ፤ ከእኔ በኋላ የሚመጣው ግን በመንፈስ ቅዱስና በእሳት ያጠምቃችኋል፡፡» እያለ ሰዎቹ እርሱን እንዲከተሉ ሳይሆን የጌታችንን መምጣት ተስፋ እንዲያደርጉ የሚያደርግ ትምህርት ያስተምራቸው ነበር፡፡ በዚህም ምክንያት የቅዱስ ዮሐንስ ደቀመዛሙርት በኋላ ወደ ቤተ ክርስቲያን ገብተዋል፡፡

የመጀመሪያዎቹ ጌታችንን የተከተሉት ደቀመዛሙርት የዮሐንስ ደቀመዛሙርት ነበሩ፡፡ ስለዚህ በዚህ ዘመን መታጀብ /በሕዝብ መከበብ/ ለሚያስደስተን የእግዚአብሔርን ሳይሆን የእኛን ተከታዮች እንደ ፈሪሳውያን ለምንፈልግ አገልጋዮች ትልቅ ተግሳጽ ነው፡፡

«በማግስቱ ዮሐንስ ከሁለቱ ደቀመዛሙርቱ ጋር እንደገና በእዚያው ቦታ /ጌታችን በተጠመቀበት/ ቦታ ነበር፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም በዚያ ሲያልፍ አይቶ «እነሆ የእግዚአብሔር በግ» አለ ሁለቱ ደቀመዛሙርትም ይህን ሲናገር ሰምተው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ተከተሉት» /ዮሐ.1÷35-37/

የሐዋርያት ሥራ መጽሐፍም በርካታ የዮሐንስ ደቀመዛሙርት የነበሩና የእርሱን ጥምቀት የተጠመቁ ሰዎች በቀላሉ ወደ ክርስቲያኖች ማኅበር እንደተቀላቀሉ ይነግረናል፡፡ /ሐዋ.18÷24-19፣ 6፣ 13÷24/

ራሱም ይህንን አቋሙን እንዲህ በማለት ልብ በሚነኩ ቃላት እንዳጋለጠው ወንጌላዊው ዮሐንስ በወንጌሉ መዝግቦታል፡፡

ሰዎች ወደ ቅዱስ ዮሐንስ መጥተው «መምህር፣ በዮርዳኖስ ከአንተ ጋር የነበረው፣ ስለ እርሱም የመሰከርክለት … ሰው ሁሉ ወደ እርሱ እየሄዳ ነው» ባሉት ጊዜ እንዲህ ሲል መለሰ «ከላይ ካልተሰጠው በቀር ማንም አንዳች ሊቀበል አይችልም፡፡ «እኔ ክርስቶስ አይደለሁም፤ ነገር ግን ከእርሱ በፊት ተልኬአለሁ» እንዳልሁ እናንተ ራሳችሁ ትመሰክራላችሁ፡፡ ሙሽራይቱ የሙሽራው ነች፡፡ ድምፁን ለመስማት በአጠገቡ የሚቆመው ሚዜ ግን የሙሽራውን ድምፅ ሲሰማ እጅግ ደስ ይለዋል፤ ያ ደስታ የእኔ ነው፤ እርሱም አሁን ተፈጽሟል፡፡ እርሱ ሊልቅ፤ እኔ ግን ላንስ ይገባል፡፡»

እውነት ነው፡፡ ሙሽራይቱ ቤተ ክርስቲያን የሙሽራው የክርስቶስ ነች፡፡ አገልጋዮች ሚዜ ናቸው፡፡ ሥራቸውም ሙሸራይቱን ወደ ሚዜው ማቅረብ ነው፡፡

ቅዱስ ዮሐንስ ሲያገለግል በድፍረት ነው፡፡ እርሱ በነበረበት ወቅት ሔሮድስ አንቲጳስ የወንድሙን ሚስት አግብቶ የሚገሥጸው ጠፍቶ ነበር፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ ግን በበረሃው ሳለ ደፋር፣ ለሰው ፊት የማያደላ፣ መሆንን ተምሮ ነበርና ገብቶ ገሠፀው፡፡

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ሺኖዳ እንዲህ ይላሉ «ከአገልግሎቱ ሊያዘገየው ወይም ሊያስተጓጉለው የሚችል ቢሆንም እንኳን ተገቢውን ነገር ከማድረግ ወደ ኋላ አላለም፡፡ አስተሳሰቡም እንዲህ ነው «እግዚአብሔር እንዳገለግል ፈቃድ ከሆነ አገለግላለሁ፤ ካልሆነም የእርሱ ፈቃዱ ይሁን፡፡ ዋናው ነገር እውነትን መመስከር ነው» ቅዱስ ዮሐንስ ስለእውነት ራሱን አሳልፎ ቢሰጥም ከሞተ በኋላም ቢሆን የትምህርቱ ድምፅ ሄሮድስን ሲወቅሰው ኑሯል፡፡»

እውነት ነው፡፡ በመጀመሪያ ደረጃ ከሞተ በኋላም ቢሆን ራሱ አስራ አምስት ዓመት ዙራ አስተምራለች፡፡ ሔሮድስም ከሞት ተነሥቶ የሚመጣ እስኪመስለው ድረስ ይፈራው እንደበር ቅዱስ ማቴዎስ በወንጌሉ ጽፏል «በዚያን ጊዜ የአራተኛው ክፍል ገዢ የነበረው ሄሮድስ /አንቲጳስ/ ስለ ኢየሱስ ዝና ሰማ፤ ባለሟሎቹንም እንዲህ ከሆነ መጥምቁ ዮሐንስ ከሞት ተነሥቶ መጥቶአል ማለት ነው፤ ይህ ሁሉ ድንቅ ተዓምራት በእርሱ የሚደረገውም ለዚህ ነው» አላቸው፡፡ /ማቴ.14÷1-2/፡፡
ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ ያማልደናል

ቅዱስ ዮሐንስ ዛሬ እኛን እግዚአብሔር ለወዳጆቹ በሰጠው ቃል ኪዳን መሠረት በጸሎቱ ከእግዚአብሔር ያማልደናል፡፡

ቤተ ክርስቲያንም ዘወትር «ሰአል ለነ ዮሐንስ» «ዮሐንስ ሆይ ለምንልን»፤ ትለዋለች፤ «በአንተ ዮሐንስ መጥምቅ መሐረነ» «ስለ ዮሐንስ ስትል ማረን» እያለችም ትጸልያለች፡፡ እኛም ገድሉንና፣ መልኩን በመጸለይ፣ መታሰቢያው በሚደረግበት ጊዜም በስሙ ዝክር በመዘከር፣ ቸርነት በማድረግ በረከትን ለማግኘት ልንተጋ ይገባናል፡፡

«ማንም ከእነዚህ ከታናናሾቹ ለአንዱ ቀዝቃዛ ውኃ ብቻ በደቀመዛሙርቶቼ ስም ቢያጠጣ፤ እውነት እላችኋለሁ ዋጋው አይጠፋበትም» /ማቴ.10÷42/

«የቅዱስ ዮሐንስ ጸሎቱና በረከቱ ይደርብን! አማላጅነቱ ይደረግልን»

ወስብሐት ለእግዚአብሔር