christmas 1

የሕፃኑ የኢየሱስ ልደት /ለሕፃናት/

ታኅሣሥ 26 ቀን 2005 ዓ.ም.

ከወልደ ኢየሱስ /ቤካ ፋንታ/

  • “እነሆ ድንግል ትፀንሳለች ልጅም ትወልዳለች ስሙንም አማኑኤል ትለዋለች” ማቴ.1፥23

 

ልጆችዬ እንደምን ሰነበታችሁ? ዛሬ ስለ ታላቁ ሕፃን ልደት የምነግራችሁ ነገር አለና በማስተዋል ተከታተሉኝ እሺ፡፡ ጎበዞች!

christmas 1

የዛሬ ሁለት ሺ ዓመት ገደማ ነው፡፡ በኢየሩሳሌም ሀገር ንጉሡ ሄሮድስ ሕዝቡን ሁሉ ቤተልሄም ወደምትባል ከተማ ጠራቸው፡፡ እመቤታችንም በዚያ ጊዜ የአሥራ አምስት/15/ ዓመት ልጅ ሆኖ በሚጠብቃት በአረጋዊው /በሽማግሌው/ ዮሴፍ ቤት ትኖር ነበር፡፡ እመቤታችን ድንግል ማርያም ሕፃኑን ኢየሱስ ክርስቶስን ፀንሳ ልትወልድ ደርሳ ሳለ ወደ ቤተልሄም ከተማ ከአረጋዊው ጠባቂዋ ዮሴፍና ከቅድስት ሰሎሜ ጋር ሄደች፡፡

 

በዚያ ሲደርሱ ምን ሆነ መሰላችሁ? እናታችን ማርያም ቅድስት ሰሎሜና አረጋዊው ዮሴፍ ማደሪያ ፈልገው በየቤቱ እየሄዱ “የእግዚአብሔር እንግዶች ነን ማደሪያ ስጡን፣ እባካችሁ አሳድሩን…” ብለው ቢጠይቋቸው ሁሉም “ቦታ የለንም፣ አናሳድርም፣ አናስገባም ሂዱ፡፡” እያሉ መለሷቸው፡፡ በጣም መሽቶ ስለነበረ ጨለማው ያስፈራ ነበረ፣ ብርዱ ደግሞ በጣም ከባድ ነበረ፡፡ ማደሪያ አጥተው የት እንሂድ እያሉ ሲያስቡ በድንገት አረጋዊ ዮሴፍ “ኑ ተከተሉኝ” ብሎ በመንደሩ ውስጥ ወዳለ አንድ የከብቶች ማደሪያ ቤት ወሰዳቸው፡፡

 

ከከብቶቹ ቤት ሲደርሱ በዚያ አህዮች፣ በሬዎች፣ በጎች፣…. ብዙ እንስሳት ተኝተው አገኙዋቸው፡፡ የበረቱ ሽታ በጣም ያስቸግር ነበረ፡፡ ነገር ግን ማደሪያ ስላልነበረ በዚያ ሊያድሩ ተስማሙ፡፡

 

ወደ በረቱ ሲገቡ እንስሶቹ ከተኙበት ተነሥተው በደስታ እየዘለሉ ተቀበሏቸው፡፡ በዚያም እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ሕፃኑን ኢየሱስ ክርስቶስን ወለደችው፡፡ ይህም ታላቅ ሕፃን የሁላችንም አምላክ ነው፡፡ ወዲያውኑ የከብቶቹ ቤት በታላቅ ብርሃን ተሞላ፡፡ ቅዱሳን መላእክት ተገለጡ፤ በእመቤታችንም ፊት ሆነው በደስታ ከበሮ እየመቱ፣ እያጨበጨቡ መዘመር ጀመሩ፡፡ መዝሙሩም እንዲህ የሚል ነበር፡-

 

“ለእግዚአብሔር ክብርና ምስጋና በሰማያት ይሁን፣ በምድርም ሰላም ለሰውም በጎ ፈቃድ”


ልጆችዬ አሁን አንድ ጥያቄ ልጠይቃችሁ ነው፡፡ ተዘጋጃችሁ? መልካም፡-

  • የገናን በዓል እንዴት ነው የምታከብሩት? ለሕፃኑ ለኢየሱስ ክርስቶስ የልደት መዝሙር እየዘመርን ነው አላችሁኝ? ጎበዞች! የገናን በዓል ከወላጆቻችሁ ጋር በቤተ ክርስቲያን ተገኝታችሁ እንደ ቅዱሳን መላእክት በደስታ መዝሙር በመዘመር አክብሩት እሺ፡፡

መልካም የገና በዓል ይሁንላችሁ፡፡