የሐይቅ ቅዱስ ዮሐንስ ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን ሥራ እንዲጠናቀቅ የድጋፍ ጥሪ ቀረበ

በደረጀ ትዕዛዙ

በደቡብ ወሎ ሀገረ ስብከት ሐይቅ ከተማ የሚገኘው የደብረ ናግራን ቅዱስ ዮሐንስ ፍቅረ እግዚእ ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን ግንባታን ለማስፈጸም የምእመናን ድጋፍ ተጠየቀ፡፡

በ1879 ዓ.ም እንደተሠራ የሚነገርለት ይኸው ቤተ ክርስቲያን ለበርካታ ዘመናት እድሳት ባለማግኘቱ አዲስ ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን እንዲሠራ በሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ አትናቴዎስ ፈቃድ ከሰባት ዓመት በፊት ኮሚቴ ተዋቅሮ እንቅስቃሴ ሲደረግ ቆይቷል፡፡

ኮሚቴው ምእመናንን በማስተባበር፣ የተለያዩ የገቢ ማስገኛ ዘዴዎችን በመጠቀምና ጉባኤያትን በማዘጋጀት ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን በማሠራት የተሻለ ደረጃ ላይ እንዳደረሰው የቤተ ክርስቲያኑ አስተዳዳሪ አባ ወልደ ትንሣኤ አሳምነው ተናግረዋል፡፡

የሕንፃ አሠሪ ኮሚቴው ገንዘብ ያዥ አቶ ካሳሁን መብራቱ በበኩላቸው፤ ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን ለማነፅ ምእመናን ያደረጉት ትብብር የሚያበረታታ ቢሆንም ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ በመጣው የግንባታ ዕቃ መወደድ የተነሣ የሕንፃ ቤተ ክርስቲያኑን ግንባታ ሙሉ በሙሉ ማጠናቀቅ አልተቻለም፡፡

ስለዚህ የቆርቆሮ፣ የበርና የመስኮት የመሳሰሉት ቀሪ ሥራዎችን በማጠናቀቅ ቤተ ክርስቲያኑ  ለምእመናን አገልግሎት እንዲሰጥ ለማድረግ ድጋፍ መጠየቅ አስፈልጓል ያሉት አቶ ካሳሁን፤ ለዚህም ምእመናን የተቻላቸው ትብብር እንዲያደርጉ ተማጽነዋል፡፡