ዘመነ ጽጌ

በዶክተር ታደለ ገድሌ

ጥቅምት ፳፬ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሥርዓተ አምልኮ መሠረት ከመስከረም ፳፮ እስከ ኅዳር ፭ ቀን ያለው ወቅት ‹ዘመነ ጽጌ፤ ወርኀ ጽጌ› ተብሎ ይጠራል፡፡ በግእዝ ቋንቋ ‹ጸገየ› ማለት ‹አበበ፤ አፈራ፤ በውበት ተንቆጠቆጠ፤ በደም ግባት አጌጠ፤ የፍሬ ምልክት አሣየ› እንደ ማለት ነው፡፡ ከዚሁ ግስ ላይ ‹ጽጌያት› ብሎ ስም ማውጣት ሲቻል አበባማ፣ ውበታማ፣ አበባ የያዘና የተሸከመ ለማለት ደግሞ ‹ጽጉይ› ይላል፡፡ በተለይም ዘመነ ጽጌ (ወርኀ ጽጌ) የምትከበረው በሀገራችን ከወቅቶች ሁሉ በጣም በሚወደደው የመፀው ወቅት ነው፡፡ በዚህ ምድር በልምላሜና በውበት በምትንቆጠቆጥበት ወቅት በየሳምንቱ እሑድ ከመንፈቀ ሌሊት ጀምሮ ማኅሌተ ጽጌ የሚቆሙትና ሰዓታት የሚያደርሱት ካህናት እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን በአበባ፣ በትርንጎ፣ በሮማን፣ በእንጆሪ … እየመሰሉ ለፈጣሪ መዝሙርና ምስጋና ያቀርባሉ፡፡

በዘመነ ጽጌ ‹‹ጊዜ ገሚድ በጽሐ ቃለ ማዕነቅ ተሰምዓ በምድርነ፤ ተመየጢ ተመየጢ ወንርዓይ ብኪ ሰላመ፤ እንዘ ተሐቅፊዮ ለሕፃንኪ፤ ክበበ ጌራ ወርቅ ጽሩይ በዕንቈ ባሕርይ ዘየኀቱ፤ አክሊለ ጽጌ ማርያም፤ ንዒ ርግብየ ወንዒ ሠናይትየ፤ እንተ ሐዋርያት ይሴብሑኪ መላእክት ይትለአኩኪ፤ ንዒ እምሊባኖስ ሥነ ሕይወት፤ ቡራኬሁ ለሴም፤ ተናግዶቱ ለአብርሃም መዓዛሁ ለይስሐቅ ወሰዋስዊሁ ለያዕቆብ ወናዛዚቱ ለዮሴፍ …›› ይህን የመሳሰሉ ኃይለ ቃላትን እያነሡ ሊቃውንቱና ምእመናኑ እግዚአብሔርንና እመቤታችንን ያመሰግናሉ፡፡

ይህም ማለት ‹‹… በአበባው ወቅት መሆን የሚገባው ነገር ሁሉ ደረሰ፡፡ የአዕዋፍ ውዳሴ ቃልም በምድራችን ተሰማ፡፡ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ሆይ! በአንቺ ሰላምን ማየት እንችል ዘንድ መመለስን ተመለሺ፡፡ ልጅሽን እንዳቀፍሽ፤ ክበቡ ያማረ ወርቅ እንደ ተጎናጸፍሽ የአበባ አክሊል ማርያም ርግቤ፣ ደጌ ሆይ! ነይ፡፡ ሐዋርያት የሚያመሰግኑሽ፤ መላእክት የሚላላኩሽ፤ የሕይወት መሠረት ከሊባኖስ ነይ፡፡ የሴም በረከቱ፤ የአብርሃም መስተንግዶው፤ የይስሐቅ ሽቶው፤ የያዕቆብ መሰላሉ፤ የዮሴፍ አጽናኙ …›› በሚሉና በሌሎችም የዜማ ስልቶች ካህናትና ዲያቆናት፤ ደባትር (ደብተሮች) በቅኔ ማኅሌት ውስጥ ጧፍ እያበሩና እየዘመሩ፤ ከበሮ እየመቱ፤ ጸናጽል እያንሹዋሹ፤ በመቋሚያ አየሩን እየቀዘፉና መሬቱን እየረገጡ፤ እየወረቡ ሌሊቱን ሙሉ ለእግዚአብሔር ምስጋና ያቀርባሉ፡፡

ሰዓታት የሚያደርሱ ካህናትም፡- ‹‹ትመስሊ ምሥራቀ፤ ወትወልዲ መብረቀ፤ ወታገምሪ ረቂቀ፡፡ ትመስሊ ፊደለ፤ ወትወልዲ ወንጌለ፤ ወታገምሪ ነበልባለ፡፡ ትመስሊ ጽጌ ረዳ፤ ወትወልዲ እንግዳ፤ ወታድኅኒ እሞተ ፍዳ … ሐረገ ወይን ሐረገ ወይን ዐፀደ ወይን አንቲ ማርያም›› ማለት፡- ‹‹በምሥራቀ ፀሐይ የምትመሰየሚው፤ እንደ መብረቅ ኃያል የሆነውን ጌታን የወለድሽ፤ ረቂቅ ምሥጢርን የምትችዪ፤ እንደ ፊደል ባለ ብዙ ዘር (ሆሄያት) የሆንሽ፤ ወንጌልን የወለድሽ፤ ነበልባለ እሳትን (ክርስቶስን) የተሸከምሽ፤ በጽጌ ረዳ አምሳል የምትመሰየሚው ቅድስት ማርያም ሆይ! የዓለሙን እንግዳ ፈጣሪን የወለድሽ፤ ከፍዳ ሞት የምታድኚ፤ የወይን ሐረግ የወይን ዐፀድ (ተክል) አንቺ ነሽ …›› እያሉ ያመሰግናሉ፡፡

‹‹እምግብጽ ጸዋዕክዎ ለወልድየ ለክብረ ቅዱሳን፤ ለቅዱሳን ክብር ልጄን ከግብጽ ጠራሁት›› በማለት ነቢዩ ሆሴዕ በምዕራፍ ፲፩ ቍጥር ፩ እና ፪ ላይ አስቀድሞ እንደ ተናገረው ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በልጅነቱ ወደ ምድረ ግብጽ (ምስር) የተሰደደው የነቢያት ትንቢት ይፈጽም ዘንድ ነው፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ሕፃናትን በመፍጀት ከሚታወቀው ከአረመኔው ንጉሥ ከሄሮድስ ለማምለጥ ነው፡፡ አምላካችን ክርስቶስ ያለጊዜው (ዕለተ ዓርብ) ደሙ አይፈስምና፡፡ ስለዚህም ‹‹ሕፃኑንና እናቱን ይዘህ ወደ ምድረ ግብጽ ሽሽ፤ ሄሮድስ ሕፃኑን ለመግደል ይፈልጋልና›› ብሎ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ለዮሴፍ በነገረው ቃል መሠረት ሕፃኑንና እናቱን ይዞ በሌሊት ወደ ግብጽ ምድር ተሰደደ፡፡ ይህንን ስደት አስመልክቶ ሰቆቃወ ድንግል የሚባለውን ቃለ እግዚአብሔር ካህናቱ በሚያሳዝን ዜማ ያደርሳሉ፤ ያቀርባሉ፡፡

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በይሁዳ ግዛት በቤተልሔም በንጉሥ ሄሮድስ ዘመን በተወለደ ጊዜ በሄሮድስ ላይ ቅንዓት አድሮበት ነበር፡፡ ‹‹ከአንተ የሚበልጥና የሚልቅ ንጉሥ በቤተልሔም ይወለዳል›› የሚል ትንቢት ይሰማ ነበር፡፡ ‹‹ወአንቲነ ቤተ ልሔም ምድረ ኤፍራታ ኢትቴሐቲ እምነገሥተ ይሁዳ እስመ እምኔኪ ይወፅዕ ንጉሥ፤ አንቺ የኤፍራታ ምድር ቤተልሔም ሆይ! ብዙ ነገሥታት ከነገሡባት ከይሁዳ አታንሺም፤ የዓለም ንጉሥ የሚሆን ከአንቺ ይወጣልና›› የሚለው የነቢያት ትንቢት ሄሮድስን አስጨነቀው፡፡ በዚህ ላይ ደግሞ ሰብአ ሰገል (የጥበብ ሰዎች) ‹‹የተወለደው የአይሁድ ንጉሥ የት አለ? የምሥራቅ ኮከብ እየመራን መጥተናል፡፡ እንሰግድለት ዘንድ አመላክቱን›› ብለው ወደ ኢየሩሳሌም ብዙ መብዓ ይዘው መምጣታቸውን ሄሮድስ ሲሰማ ዓይኑ ፈጠጠ፤ ሰውነቱም ደነገጠ፡፡ ስለዚህም ጌታችንን ሊገድለው ወደደ፡፡

ለሥልጣን ስሱ የነበረው ሄሮድስ ‹‹ከእኔ በላይ ሌላ ምን ንጉሥ አለ?›› ብሎ ተቆጣና የካህናትን አለቆችና የሕዝቡን ጻፎች (ፈሪሳውያንን) አስጠርቶ በመሰብሰብ ‹‹ክርስቶስ የተወለደው የት ነው?›› ብሎ አፈጠጠባቸው፡፡ በኋላም አንደበቱን አለሰለሰና ‹‹እውነት ከሆነ እኔም እሰግድለት ዘንድ ፈልጉልኝ›› አለ ብልጡ ንጉሥ፡፡ ካህናቱም ከልቡ መስሏቸው ‹‹‹አንቺ ቤተልሔም የይሁዳ ምድር ከይሁዳ ገዢዎች ከቶ አታንሽም፤ ሕዝቤን እስራኤልን የሚጠብቅ መስፍን ከአንቺ ይወጣልና› ተብሎ በተጻፈው መሠረት ጌታችን የተወለደው በይሁዳ በቤተልሔም ነው፡፡ ሰብአ ሰገልም አምኃ (እጅ መንሻ) ለማቅረብ የሚሔዱት ወደዚያው ነው›› ብለው እቅጩን ነገሩት፡፡ ሄሮድስም መንገደኞቹን ሰብአ ሰገልን ጠራና ‹‹ወገኖቼ አደራችሁን ለተወለደው ልጅ መብዓ አድርሳችሁ በእኔ በኩል ተመለሱ፡፡ እኔ ደግሞ ሒጄ እሰግድለት ዘንድ ሁኔታውን ትነግሩኛላችሁ›› ብሎ አሰናበታቸው፡፡

እነርሱም ‹‹ኧረ ግድ የለም ንጉሥ ሆይ!›› ብለው የምሥራቁ ኮከብ እየመራቸው፤ ሕፃኑ ባለበት ቦታ ላይ ደርሰው፤ ወደ ቤትም ገብተው፤ ወድቀው ለሕፃኑ ሰገዱለት፡፡ ሳጥኖቻቸውንም ከፍተው እጅ መንሻ ወርቅና ዕጣን፣ ከርቤም አቀረቡለት፡፡ ሲመለሱ በሌላ መንገድ እንዲሔዱ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል በሕልም ነግሯቸው ነበርና በሌላ መንገድ ወደ ሀገራቸው ተጓዙ፡፡ ሄሮድስ ይህን በመሰማ ጊዜም የበለጠ ቅንዓት አደረበትና ሕፃኑን ለመግደል ይበልጥ ተነሣሣ፡፡ በሐሳብ የተጨነቀው ንጉሥ ጉዳዩን ለመጠንቁል (ለጠንቋይ) አማከረ፡፡ ጠንቋይ መቼም እበላና እወደድ ባይ ነውና ‹‹‹እስከ ሁለትና ሦስት ዓመት ዕድሜ ለአላቸው ወንድ ሕፃናት ቀለብ ልሠፍርላቸው አስቤአለሁና ተሰብሰቡ› ብለው አዋጅ ያስነግሩ፡፡ ሕፃናቱን ሲሰበሰቡልዎም ያን ጊዜ ሁሉንም ይግደሏቸው፡፡ ከዚያ ውስጥ የእርስዎ የወደፊት ጠላት አብሮ ይሞታል›› ብሎ መከረው፡፡ በዚህ መሠረት በመቶ ሺሕ የሚቆጠሩ ሕፃናትን ሄሮድስ አስፈጅቷል፡፡ ‹‹ድምፅ በራማ ተሰማ፤ ለቅሶና ብዙ ዋይታ፡፡ ራሔል ስለ ልጆቿ አለቀሰች፡፡ መጽናናትም አልወደደችም፤ የሉምና›› የሚለው ትንቢትም ተፈጸመ፡፡

ከሦስት ዓመት ከመንፈቅ የግብጽ ስደት በኋላ ሊቃውንቱ፡- ‹‹ተመየጢ ማርያም ሀገረኪ ናዝሬተ፣ በላዕሌኪ አልቦ ዘያበጽሕ ሁከተ፣ ወኢትጎንድዪ በግብጽ ከመ ዘአልብኪ ቤተ፣ ዘየኀሥሦ ለወልድኪ ይእዜሰ ሞተ፣ በከመ ነገሮ መልአክ ለዮሴፍ ብሥራተ›› እያሉ ከስደት መመለሷን ያበሥራሉ፡፡ ትርጉሙም፡- ‹‹ማርያም ሆይ! ወደ ሀገርሽ ወደ ናዝሬት ተመለሺ፡፡ በአንቺ ላይ ሁከት የሚያመጣ ማንም የለም፡፡ ቤት እንደሌለሽ ሁሉ በግብጽ አትቆይ፡፡ ለዮሴፍ በሕልሙ መልአክ እንደ ነገረው የሕፃኑን ነፍስ የፈለገው (ጠላት ሄሮድስ) ሞቷልና›› ማለት ነው፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ምእመናን በዐርባው ቀን (በዘመነ ጽጌ) ወቅት የማርያምን የሽሽትና የመመለስ (የሚጠት) ታሪክ እያነሡ ውዳሴ የሚያቀርቡትና ማኅሌት የሚቆሙት በዚሁ ምክንያት ነው፡፡ በዚህ ወቅት ለእመቤታችን ክብር ሲባል የፈቃድ ጾም የሚጾሙ ምዕመናንና ምዕመናትም ብዙዎች ናቸው፡፡

መምህር ክፍሌ ወልደ ጻድቅ ‹የጽጌ ዚቅ› በሚለው፣ ዓመተ ምሕረት በሌለውና በእጅ ጽሑፍ ተዘጋጅቶ በታተመው መጽሐፋቸው ከገጽ 1 – 75 እንደ ገለጹት ከበዓለ ጽጌ ጋር የጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ፤ የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም፤ የቅዱን መላእክት፤ የቅዱሳም ጻድቃን እና የቅዱሳን ሰማዕታት በዓላት አብረው ይከበራሉ፡፡ ለአብነትም የሥላሴ፤ የአማኑኤል፤ የዐርባዕቱ እንስሳ፤ የሩፋኤል፤ የኪዳነ ምሕረት፤ የመጥምቀ መለኮት ዮሐንስ (ፅንሰቱ)፤ የእስጢፋኖስ፤ የወንጌላውያኑ ማቴዎስና የማርቆስ፤ የዘብዴዎስ ልጆች የያዕቆብና የዮሐንስ፤ የቶማስ ዘህንደኬ፤ የሐና፤ የአቡነ አረጋዊ፤ የቂርቆስ፤ የአባ ኤዎስጣቴዎስ፤ የአብርሃም፣ የይስሐቅና የያዕቆብ፤ የአብርሃ አጽብሐ ነገሥትና የሌሎችም ቅዱሳን በዓላት ተጠቃሾች ናቸው፡፡

በአጠቃላይ በዘመነ ጽጌ ዘወትር እሑድ፣ እሑድ በመላ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አብያተ ክርስቲያናት ማኅሌት በመቆም ታላቅ በዓል ይደረጋል፡፡ የዐርባ ቀኑ ዘመነ ጽጌ (ወርኀ ጽጌ) መታሰቢያነቱ ለቅድስት ድንግል ማርያምና ለጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ እመቤታችን ልጇን ይዛ ከሰሎሜና ከዮሴፍ ጋር ወደ ምድረ ግብጽ በተሰደዱ ጊዜ የደረሰባትን ጭንቅና ውኃ ጥም፤ ግፍና እንግልት ለማስታወስና ከግብጽ ወደ ሀገሯ ናዝሬት መመለስዋን (ሚጠቷን) ለመዘከር ሲባል በዘመነ ጽጌ የደመቀ አገልግሎት ይከናወናል፡፡ በዚህ ወቅት የሚቆመው የሰንበት ማኅሌቱ፣ መዝሙሩና ቅዳሴው እንደዚሁም የሚቀርበው የክብር ይእቲና የዕጣነ ሞገር ቅኔ ሁሉ በዘመነ ጽጌ ላይ የተመሠረተ ነው፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡