ዐቢይ ጾም

በሊቀ ጉባኤ ቀለመወርቅ ውብነህ

የካቲት ፳፰ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

ጾም ማለት መተው መከልከል ማለት ነው፡፡ ጾም በእግዚአብሐር የተቀደሰ ተግባር ስለኾነ ወደ ቅድስና ጎዳና የሚመራ ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያናችንም ሥርዓት ሠርታ ጾመን ከአምላካችን ጋር ኅብረት እንዲኖረን፤ መንፈሳዊ ኃይል እንድናገኝ ታደርጋለች፡፡ በጾም ወራት ከመባልዕት መከልከል ብቻ ሳይኾን ዐይን ክፉ ከማየት፣ አንደበት ክፉ ከመናገር፣ ጆሮ ክፉ ከመስማት መቆጠብ እንደሚገባው በቅዱሳት መጻሕፍት ተጽፎአል፡፡ ‹‹ይጹም ዐይን ይጹም ልሳን እዝንኒ ይጹም እምሰሚዓ ኀሡም በተፋቅሮ›› እንዲል ቅዱስ ያሬድ /ጾመ ድጓ/፡፡ በጾም ወራት ላምሮት፣ ለቅንጦት የሚበሉ ወይም ለመንፈሳዊ ኃይል ተቃራኒ የኾኑ ሥጋዊ ፍትወትን የሚያበረታቱ፣ ሥጋንና የሚያሰክሩ መጠጦችን /ዳን.፲፥፪-፫/፣ ቅቤና ወተትን ከመጠቀም መታቀብ እንደሚገባ ታዟል /መዝ.፻፰፥፳፬፣ ፩ቆሮ.፯፥፭፤ ፪ቆሮ.፮፥፮/፡፡

በብሉይ ኪዳን ጾም ከፍተኛ ቦታ ነበረው፡፡ የብሉይ ኪዳን ነቢያት ከእግዚአብሔር በሚገናኙበት ወራት እህልና ውኃ በአፋቸው አይገባም ነበር /ዘፀ.፴፬፥፳፰/፡፡ አስቴር አስቀድማ ሦስት ቀን ጾማ ጸልያ በእስራኤል ላይ የመጣውን መቅሠፍት እንዲመለስ አድርጋለች /አስቴር ፬፥፲፭-፲፮/፡፡ በዘመኑ በኃጢአት ብዛት የታዘዘው የእግዚአብሔር መዓት የሚመለሰውም ሕዝቡ በጾም ሲለምኑትና ሲማልዱት ነበር  /ዮናስ ፪፥፯-፲/፡፡ በሐዲስ ኪዳንም ጾም ሰው ሠራሽ ሕግ ሳይኾን ራሱ ክርስቶስ የሠራው ሕግ ነው /ማቴ.፬፥፪፤ ሉቃ.፬፥፪/፡፡ ቅዱሳን ሐዋርያትም በየጊዜው ከመንፈስ ቅዱስ ትእዛዝ የሚቀበሉት በጾም በጸሎት ላይ እንዳሉ ነበር /ሐዋ.፲፫፥፪/፡፡ ለስብከተ ወንጌል የሚያገለግሉ ዲያቆናትና ቀሳውስትም የሚሾሙት በጾምና በጸሎት ነው /ሐዋ.፲፫፥፫፤ ፲፬፥፳፫/፡፡ እንደ ቆርነሌዎስ ያሉ ምእመናን ያላሰቡትን ክብር ያዩና ያገኙ የነበረውም በጾምና በጸሎት ፈጣሪያቸውን በመማጸን ነው /ሐዋ.፲፥፴/፡፡

ዐቢይ ጾም ጌታችን ከተጠመቀ በኋላ ዐርባ ቀን የጾመው፤ እኛም እንድንጾማቸው በቤተ ክርስቲያናችን ከታዘዝናቸው ሰባቱ የአዋጅ አጽዋማት አንዱ ነው፡፡ ምእመናን ጌታችን ያደረገውን ምሳሌ ተከትለን ጾሙን በየዓመቱ እንጾመዋለን፡፡ ዐቢይ ጾም ስምንት ሳምንታት (፶፭ ቀኖች) አሉት፡፡ በውስጡ ስምንት ቅዳሜዎች፣ ሰባት እሑዶች ይገኛሉ፡፡ ይኸውም ዐሥራ አምስት ቀን ማለት ነው፡፡ እነዚህ ቀናት ከጥሉላት እንጂ ከእኽል ውኃ ስለማይጦሙ የጦሙ ወራት ዐርባ ቀን ብቻ ይኾናል፡፡

ጾሙ በተለያዩ ስሞች ይጠራል፤ አንደኛ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከተጠመቀ በኋላ የጾመው በመኾኑ፣ እንደዚሁም ‹‹ዐቢይ እግዚአብሔር ወዐቢይ ኀይሉ ዐቢይ እግዚአብሔር ወብዙኅ አኰቴቱ›› /መዝ.፵፯፥፩፤ መዝ.፻፵፮፥፭/ የተባለ ጌታችን የጾመው ጾም ስለኾነ ‹‹ዐቢይ ጾም›› ይባላል፡፡ ሁለተኛ ‹‹ሁዳዴ ጾም›› ይባላል፡፡ ይህም የመንግሥት እርሻ ወይም ማንኛውም የሕዝብ ብዛት ያለበት ሥራ ሁዳድ ስለሚባል ሲኾን፣ ዐቢይ ጾምም ከአጽዋማት ዅሉ ብዙ ቀናት ስለሚጾምና ኃያሉ አምላካችን ስለጾመው ነው /አሞ.፯፥፩/፡፡ ሦስተኛ ‹‹በአተ ጾም›› ይባላል፡፡ የጾም መግቢያ፣ መባቻ ማለት ነው፡፡ አራተኛ ‹‹ጾመ ዐርባ›› ይባላል፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የጾመው ፵ ቀን ስለኾነ /ማቴ.፬፥፩/፡፡ አምስተኛ ‹‹ጾመ ኢየሱስ›› ይባላል፡፡ ጌታችን እርሱ ጾሞ፣ ጹሙ ብሎ ስላዘዘን፡፡ ስድስተኛ ‹‹ጾመ ሙሴ›› ይባላል፡፡ ቅዱስ ያሬድ በዘወረደ ጾመ ድጓው ‹‹ከመዝ ይቤ ሙሴ እስመ ለዓለም ሙሴኒ ይቤ በውስተ ኦሪት›› እያለ ስለዘመረ /የሰኞ ዕዝል/፡፡

ከዐቢይ ጾም ሳምንታት መካከል የመጀመሪያው ሳምንት ‹‹ዘወረደ (ዘመነ አዳም)›› ይባላል፡፡ ዘወረደ ማለት ከላይ የመጣ፣ የወረደ ማለት ነው፡፡ ይህም አምላካችን አዳምንና ልጆቹን ከሞት ለማዳን ሲል ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሰው መኾኑንና የፈጸመውን የማዳን ሥራ ያመለክታል፡፡ ‹‹ከሰማይ ከወረደው በቀር ወደሰማይ የወጣ የለም›› ካለው ከጌታችን ከመድኃኒታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ቃል በመነሣት ሊቁ ቅዱስ ያሬድ ‹‹ዘወረደ እምላዕሉ አይሁድ ሰቀሉ ወሚመ ኢያእመሩ እግዚአ ኵሉ ዘየሐዩ በቃሉ›› በማለት በጾመ ድጓው መጀመሪያ ላይ ይህን ዕለት ገልጾታል፡፡ ትርጕሙም ‹‹አዳምን ለማዳን ከሰማይ የወረደውን አምላክ አይሁድ ሰቀሉት፤ የሰማይ ሥልጣን ያለው የዅሉ ጌታ እንደኾነም ምንም አላወቁም›› ማለት ነው፡፡ ይህም ድርሰት በቤተ ክርስቲያናችን የጾም መጀመሪያ የኾነው ዕለተ ሰንበት ዋዜማ፣ መግቢያ (መሐትው) ኾኖ ከዋዜማ በፊት ምንጊዜም በየዓመቱ ይቆማል፤ ይዘመራል፤ ይመሰገናል፡፡

በዚህ ሳምንት በተለይም እሑድና ሰኞ የሚነገሩት ውዳሴያት ከመጻሕፍተ ኦሪትና ነቢያት የተወሰዱ ናቸው፡፡ ሁለተኛም ሳምንቱ ‹‹ሙሴኒ›› በመባል ይታወቃል፡፡ እግዚአብሔር አምላክ አዳምን ለማዳን ከሰማይ መውረዱንና በመስቀል መሰቀሉን ስለሚያወሳ ነው፡፡ በተጨማሪም ይህ የመጀመሪያው ሳምንት ‹‹ጾመ ሕርቃል›› ይባላል፡፡ ሕርቃል (ኤራቅሊየስ) የቤዛንታይን ንጉሥ ነበር፡፡ ይህ ሳምንት በስሙ የተጠራበት ምክንያት በዘመኑ ፋርሶች ኢየሩሳሌምን ወርረው፣ የጌታችንን መስቀል ማርከው ወስደውት ነበር፡፡ እርሱ ወደ ፋርስ ዘምቶ መስቀሉን ከእነርሱ ነጥቆ ይዞ ወደ ኢየሩሳሌም ተመልሷል፡፡

ሕርቃል ከፋርሶች ጋር ከመዋጋቱ በፊት ሐዋርያት በሲኖዶሳቸው ‹‹ነፍስ የገደለ ሰው እስከ ዕድሜ ልኩ ይጹም›› ብለው ሥርዓት ሠርተዋልና ጾሙን ፈርቶ ስለነበር በኢየሩሳሌም የነበሩ ምእመናን አሳቡን ደግፈው ‹‹አንተ ጠላታችንን አጥፋልን፤ መስቀሉን አስመልስልን እንጂ የአንድ ሰው ዕድሜ ቢበዛ ሰባ፣ ሰማንያ ዓመት ነው፡፡ ጾሙን አምስት አምስት ቀን ተከፋፍለን እኛ እንጾምልሃለን›› ብለው ጾመውለታል፡፡ ይህንን መሠረት በማድረግ ያላወቁት አንድ ጊዜ ጾመው ትተውታል፡፡ ያወቁት ግን ቀድሞም ሐዋርያት ጾመውታል ብለው ሥርዓት አድርገው በዓመት በዐቢይ ጾም መጀመሪያ ላይ ጾመ ሕርቃል እያሉ የሚጾሙት ኾነዋል፡፡ ቤተ ክርስቲያናችን ይህንን ሥርዓት መሠረት በማድረግ ከጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጾም የመጀመሪያውን ሳምንት ጾመ ሕርቃል በሚል ስም ሰይማ እንዲጾም አድርጋለች (የመጋቢት ፲ ቀን ስንክሳርን ይመልከቱ)፡፡

በቅዱስ ያሬድ ጾመ ድጓ ዘወረደ እየተባለ የሚታወቀው፣ በጾመ ዐርባው ወቅት በተለይም በመጀመሪያው ሳምንት የሚገኘው ድርሰት በነግህ በሠለስት፣ በቀትርና በሠርክ እንደዚሁም ቅዳሜና እሑድ በሌሊት የሚዘመር ነው፡፡ በውስጡም የያዘው ፍሬ ሐሳብ የጾምን፣ የጸሎትን፣ የምጽዋትንና የፍቅርን ጠቃሚነት አጕልቶ የሚያስተምር ነው፡፡ ሊቁ ቅዱስ ያሬድ በዘወረደ ጾመ ድጓው ‹‹አዘዞ እግዚአብሔር ለሙሴ ወይቤሎ ሰብእከ ወላህምከ ወኵሉ ቤትከ ያዕርፉ በሰንበት፤ እግዚአብሔር ሙሴን ሕዝብህ የከብትህ መንጋህ ቤተሰብህ ዅሉ በሰንበት ቀን ከድካማቸው ይረፉ በማለት አዘዘው፤›› በማለት ሰንበት ለሰው ልጆች ብቻ ሳይኾን፣ ሕይወት ላለው ነገር ዅሉ ጸጥታና ሰላም የሰፈነባት የዕረፍት ቀን ስለመኾኗ ተናግሯል /ዘፀ.፳፥፲፤ ፳፫፥፲፪/፡፡ በዚህም ወቅቱ ‹‹ዘመነ ጾም›› ወይም ‹‹ጾመ ሙሴ›› ይባላል፡፡

በአጠቃላይ ጾምን መጾም የፈቃድ ብቻ ሳይኾን የትእዛዝም ነው፡፡ ነቢዩ ኢዩኤል ‹‹ቀድሱ ጾመ ወስብኩ ምሕላ …፤ ጾምን ያዙአጽኑ፡፡ ምሕላንም ዐውጁ፡፡ ሸማግሌዎቹን ከፈጣሪያችን ቤት ሰብስባችሁ በአንድነት ኾናችሁ ወደ እግዚአብሔር ጩኹ (ለምኑ)፤›› ብሏል /ኢዩ.፩፥፲፩፤ ፪፥፲፪፤ ፲፪፥፲፭-፲፮/፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስም ‹‹ወኩኑ ላእካነ ለእግዚአብሔር በጾም ወበንጽሕ፤ በጾም፣ በንጽሕና ተወስናችሁ እግዚአብሔርን አገልግሉ፤›› ብሏል /፪ቆሮ.፮፥፬-፮/፡፡ ጾም ባያስፈልግ ኖሮ ጌታችን ‹‹በምትጾሙበት ጊዜ እንደ ግብዞች አትኹኑ … ስለ ጽድቅ የሚራቡ የሚጠሙ ንዑዳን ክብራን ናቸው፤›› ባላለም ነበር /ማቴ.፭፥፮-፲፮/፡፡ ነቢዩ ዳዊትም ‹‹ጕልበቶቼ በጾም ደከሙ፤ ሥጋዬም ቅባት በማጣት ከሳ፤›› /መዝ.፻፰፥፳፬/ ማለቱ የጾምን አስፈላጊነት ያስረዳል /ዳን. ፱፥፫-፬፤ ፲፬፥፭/፡፡ በቁራኝነት አብሮ የሚኖር መንፈስ ርኩስ (ሰይጣን) እንኳን በጾም የሚወገድ መኾኑን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተናግሮአል /ማቴ.፲፯፥፳፩፤ ማር.፱፥፪/፡፡

ቅዱሳን ሐዋርያት ‹‹ሙሽራውን ከእነሱ ለይተው የሚወስዱበት ጊዜ ይመጣል፡፡ ያን ጊዜ ይጾማሉ፤›› ያለውን የጌታን ቃል መሠረት በማድረግ ጌታችን ሞቶ ከተነሣ እና ካረገ በኋላ ጾመዋል፤ የጾምንም ሕግ ሠርተዋል /ሐዋ.፲፫፥፫/፡፡ ሠለስቱ ምዕትም ‹‹ሐዋርያት የጾሙትንና እንዲጾም የወሰኑትን መጾም ይገባል›› ብለው አጽዋማትን እንድንጾም መወሰናቸው ይህን የጌታችንን ቃል መሠረት በማድረግ ነው፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ሠራዔ ሕግ እንደመኾኑ ዐርባ ቀን ዐርባ ሌሊት ጾሞ እንጂ ዝም ብሎ ጾሙ አላለንም፡፡ ስለዚህ ጾም ትእዛዝ (ሕግ) መኾኑን ተገንዝበን ዅላችንም መጾም አለብን፡፡ ጾመን ለማበርከት ያብቃን!

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡