Emebetachin-Eriget

“ወልድኪ ይጼውአኪ ውስተ ሕይወተ ወመንግሥተ ክብር” ልጅሽ ወደ ሕይወትና ክብር መንግሥት ይጠራሻል፡፡

ነሐሴ 15 ቀን 2004 ዓ.ም.

በዲ/ን ዮሴፍ ይኲኖ አምላክ
 

እንኳን ለወላዲተ አምላክ ለቅድስት ድንግል ማርያም የትንሣኤ በዓል በሰላም አደረሳችሁ እያልን ፈጣሪያችን በዓሉን የበረከት፣ የረድኤት ያድርግልን፡፡

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በየዓመቱ ነሐሴ 16 ቀን የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያምን ትንሣኤ በታላቅ መንፈሳዊ ሥነ ሥርዓት ታከብራለች፡፡

ቅዱስ ያሬድ የእመቤታችንን ፍልሰተ ሥጋ አስመልክቶ ዝማሬ በተባለው ድርሰቱ “በስብሐት ውስተ ሰማያት መላእክት ወሊቃነ መላእክት ወረዱ ለተቀብሎታ፣ እብለኪ ወእሙ ለእግዚእየ እብለኪ ዳዊት አቡሃ ምስለ መሰንቆሁ ሙሴኒ እንዘ ይፀውር ኤፉደ መጽኡ ሃቤሃ ጴጥሮስ ወጳውሎስ ሐዋርያት አጠኑ ሥጋሃ በማዕጠንተ ወርቅ፣ ሱራፌል ወኪሩቤል ሰፍሑ ከነፊሆሙ ላዕሌሃ፣ ወረደ ብርሃን እምሰማያት ወመብረቀ ስብሐት እምውስተ ደመናት፣ ተለዓለት እምድር ውስተ አርያም በስብሐት ወበህየ ነበረት ዘምስለ ወልዳ በየማነ አብ ወመንፈስ ቅዱስ” ብሏል፡፡ ይኸውም “መላእክትና ሊቃነ መላእክት ቅዱስ ሥጋዋን ለማሳረግ በታላቅ ምሥጋና ከሰማይ ወረዱ፤ አባቷ ዳዊት ከመሰንቆው ጋር ሙሴም የአገልግሎት ልብሱን ለብሶ፣ ሐዋርያት ጴጥሮስና ጳውሎስም ወደ እርሷ መጡ ሥጋዋንም በወርቅ ማዕጠንት አጠኑ፡፡ ሱራፌልና ኪሩቤልም በላይዋ ክንፎቻቸውን ዘረጉ /ጋረዱ/፡፡ ከሰማያት ብርሃን የምስጋና መብረቅም ከደመናት ውስጥ ወጣ፡፡ ከምድር ወደ ሰማያት በምስጋና ከፍ ከፍ አለች ከልጇ ጋርም በአብና በመንፈስ ቅዱስ ቀኝ ተቀመጠች” ማለት ነው፡፡ ይህም “በወርቅ ልብስ ተጎናጽፋና ተሸፋፍና ንግሥቲቱ በቀኝህ ትቆማለች፡፡” መዝ.44፥9 ተብሎ የተነገረላትን ቃለ ትንቢት የተፈጸመላት መሆኑን ያመለክታል፡፡

 

የዚህም ጥንተ ነገሩ እንደምን ነው ቢሉ ታሪኩ ይህን ይመስላል፡-

እሑድ ጥር 21 ቀን እመቤታችን አርፋለች፡፡ ሐዋርያት ባጎበር አድርገው ወደ ጌቴ ሴማኒ ይዘዋት ሲሄዱ አይሁድ “ቀድሞ ልጇን ሰቅለን ብንገድለው ደቀ መዛሙርቱ ተነሣ፣ ዐረገ” እያሉ ሲያውኩን ኖሩ፤ ዛሬ ደግሞ እርሷን ተነሣች፣ ዐረገች እያሉ ሊያውኩን አይደለምን? በእሳት እናቃጥላታለን” ብለው ተነሡ፡፡ ታውፋንያ የሚባል አይሁዳዊ ተራምዶ አጎበሩን ጨበጠው፡፡ መልአኩ ቅዱስ ሩፋኤል የታውፋንያን ሁለት እጁን በሰይፍ መትቶ ቀጣው፡፡ በዚህም የታውፋንያ ሁለት እጁ ከአጎበሩ ተንጠልጥሎ ቀረ፡፡ ከዚያ በኋላ መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወንጌላዊውን ቅዱስ ዮሐንስ ጨምሮ በደመና ነጥቆ ከገነት በዕፀ ሕይወት ሥር አኖራት፡፡ ሐዋርያት ዮሐንስን “እንደምን ሆነች” አሉት፡፡ እርሱም፡- “በገነት ከዕፀ ሕይወት ሥር አለች” አላቸው፡፡ “ዮሐንስ አይቶ እኛ ሳናይ” ብለው፤ በነሐሴ መባቻ ጾም ጀመሩ፤ ሰኞ ነሐሴ 1 ቀን ጀምረው እሑድ ነሐሴ 14 ቀን ፈጽመዋል፡፡ በዚሁ ቀን ጌታችን ትኩስ በድን አድርጎ የእመቤታችንን ሥጋ ሰጥቷቸው ቀብረዋታል፡፡ እርሷም እንደ ልጇ በተቀበረች በሦስተኛው ቀን /ማክሰኞ/ ተነሥታ አርጋለች፡፡ “ከመ ትንሣኤ ወልዳ” ያሰኘውም ይህ ነው፡፡ በዚሁ ጊዜ ከሐዋርያት ወገን የሆነው ቅዱስ ቶማስ አልነበረም፡፡ ደመና ጠቅሶ ከሀገረ ስብከቱ /ከሕንድ/ ሲመጣ ስታርግ አገኛት፡፡ “ወፈቀደ ይደቅ እምደመናሁ” ይላል፤ ተበሳጨ፡፡ “ቀድሞ የልጅሽን ትንሣኤ ሳላይ ቀረሁ፤ ዛሬ ደግሞ ያንቺን ትንሣኤ ሳላይ ቀረሁኝ” አለ፡፡ በዚህ ጊዜ የልቡናን ሐዘን የምታቀል እመቤታችን፡- አይዞህ አትዘን እኒያ ትንሣኤዬን ዕርገቴን አላዩም፡፡ አንተ አይተሃል፡፡ ተነሣች፣ ዐረገች ብለህ ንገራቸው፡፡” ብላEmebetachin-Eriget የያዘችውን ሰበን ሰጥታ ሰደደችው፡፡ ከዚህ በኋላ ሄዶ፤ “የእመቤታችን ነገር እንደምን ሆነ?” አላቸው “ሥጋዋን አግኝተን ቀበርናት” አሉት፡፡ እርሱም “ሞት በጥር በነሐሴ መቃብር ተዉ ይህ ነገር አይመስለኝም” አላቸው፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ “አንተ እንጂ ልማድህ ነው፡፡ አንተ ብቻ ተጠራጥረህ አትቀርም፤ አንተ እየተጠራጠርህ ሰውን ሁሉ ስታጠራጥር ትኖራለህ” አለው፡፡ እርሱም የያዘውን ያውቃልና ጸጥ ብሎ ይሰማቸዋል፡፡ ከዚህ በኋላ ቅዱስ ጴጥሮስ ተቆጥቶ ሂዶ መቃብሩን ቢከፍተው የእመቤታችን ሥጋዋን አጥቷል፡፡ በዚህም ምክንያት ደንግጦ ቆመ፡፡ ይህን ጊዜ ቅዱስ ቶማስ “አታምኑኝም ብዬ ነው እንጂ እመቤታችንስ ተነሣች ዐረገች” አላቸው፡፡ የያዘውንም ሰበን እያሳያቸው፡- “ቅዱስ ሥጋዋን የገነዛችሁበት ጨርቅ /ሰበን/ ይህ አይደለምን” ብሎ ሰበኑን ሰጣቸው፡፡ ይህንንም ለበረከት ተካፍለውታል፡፡ ከዚህ በኋላ በዓመቱ “ቶማስ ትንሣኤሽን ዕርገትሽን አይቶ እኛ ሳናይ በማለት ጾም ጀመሩ፡፡ በ16ኛው ቀን እመቤታችንን መንበር ቅዱስ ጴጥሮስን ንፍቅ ቄስ፣ እስጢፋኖስን ሠራዒ ዲያቆን አድርጎ ራሱ ቀድሶ አቁርቦአቸዋል፡፡

 

እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በእናት አባቷ ቤት 3 ዓመት፣ በቤተ መቅደስ 12 ዓመት፣ ጌታችንን ከወለደችበት ጊዜ አንሥቶ ለ33 ዓመት ከ3 ወር ከተወዳጅ ልጇ ጋር፣ ለ15 ዓመት ከ9 ወር ከቅዱስ ዮሐንስ ጋር፣ በአጠቃላይ በዚህች ምድር ለ64 ዓመታት ቆይታ በተነገረላት ተስፋ ትንሣኤና ትንቢት መሠረት እርሷም እንደ ልጇ ወደ መቃብር በወረደች በሦስተኛው ቀን በልጇ ፈቃድ ከሙታን ተለይታ ተነሥታለች፡፡

 

“አቤቱ ወደ ዕረፍትህ ተነሥ፥ አንተና የመቅደስ ታቦት” /መዝ.131፥8/ የሚለው የነቢየ እግዚአብሔር የቅዱስ ዳዊት ቃልም ፈጻሜውን አግኝቷል፡፡

እግዚአብሔር አምላካችን ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም በረከት ረድኤት ያሳትፈን፡፡