ኒቆዲሞስና አዲሱ ልደት

መጋቢት 20 ቀን 2007 ዓ.ም.

በዲ/ን ታደለ ፈንታው

በቅዱስ ዮሐንስ ወንጌል በምዕራፍ ሦስት ብዙ አሕዛብ ወደ ክርስትና እምነት የተቀላቀሉበት ምዕራፍ ነው፡፡ድኅነትን በትጋት ለመፈጸም የሚታገሉ ክርስቲያኖች ይሄንን ምዕራፍ ሲያነቡ ከኒቆዲሞስ ጎን መቆማቸው የሚያጠራጥር አይሆንም፤ ከጌታ ጋር ምስጢራዊ የሆነ ውይይትን መቀጠል ይፈልጋሉ፡፡ በሕይወታቸው የተከፈተ የአዲስ ኪዳን መንገድን እንዳለ ሲገነዘቡም ጌታን ይከተላሉ፡፡ ከእርሱ ጋር ከቅዱስ መንፈሱም ጋር አንድ ይሆናሉ፡፡ አዲስ ልደትን ያገኛሉ ፤ይህም በጥምቀት የሚገኝ ልጅነት ነው፡፡

ይህ ምዕራፍ መልካም ሥነ ምግባር በነበረው ፈሪሳዊ ሕያውና መንፈሳዊ በሆነው ምንጭ በጌታችን በመድኀኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ መካከል የነበረውን ውይይት ይዟል፡፡

ኒቆዲሞስ እንደ ፈሪሳዊ በአይሁድ ትውፊትና በብሉይ ኪዳን ትምህርት የታጠቀ ነው፡፡ ጠንካራ ሞራል እንደገነባ ሰው ወደ ጽድቅ የሚወስደውን ትውፊት የሚያውቅ ሰው በፈቃዱ መታዘዝ እንዳለበት የሚያምን ነው፡፡ ይህ የሚሆነው ደግሞ ሰው በሚያደርገው ጠንካራ ትግል እንደሆነ ያምናል፡፡ይህ ትግል በሰው በጎ ፈቃድና ሕጉን በደረቁ በመተርጎም እንደሚገኝ ያምናል፡፡ ኒቆዲሞስ ጌታን ያገኘው ሕጉን የሚቃወም ሆኖ ሳይሆን ሕጉን በጥልቀት የሚተረጉም አይሁዳዊ ሆኖ ነው፡፡

ስለዚህም ነው ወደ መድኀኒታችን ከተሳቡ ወገኖች መካከል ወንጌላዊው የኒቆዲሞስን ጉዳይ በትኩረት የጻፈው፡፡ በዚህ ዐውድ ቅዱስ ዮሐንስ እንዲህ ይላል፡-በፋሲካ በዓልም በኢየሩሳሌም ሳለ ያደረገውን ምልክት ባዩ ጊዜ /ዮሐ.2፡23/፡፡ ኒቆዲሞስ ጌታ ከእግዚአብሔር እንደመጣ አወቀ፤ አመነም /ዮሐ.3፡2/፡፡ ነገር ግን ምናልባት ኒቆዲሞስ ጌታ ትምህርቱን ማኅበራዊ ጉዳይ ላይ ትኩረት ሰጥቶ እንደሚያስተምር ሊያስብ ይችላል፡፡ የሕጉን ጥሬ ትርጉም እንጂ ፍካሬያዊ ትርጉም አልተገነዘበም፡፡ የአይሁድን ኑሮ ሊያሻሽል የመጣ ነው ብሎም ሊያስብ ይችላል፡፡

የኒቆዲሞስ አመለካከቱና ልምዱ በክርስቶስ ኢየሱስ ያለውን አዲስ ሕይወት ለመቀበል አያበቃውም፡፡ በአዲሱ ልደት የሚገኘው የጸጋ ልጅነት አይገነዘበውም፡፡ የመንፈሳዊው ሕግ ጥቅም ግን ይህ ነበር፡፡ ሥጋዊውን ከመንፈሳዊ ምድራዊውን ከሰማያዊ መለየት ያስችላል፡፡ ጌታ የኒቆዲሞስን አሳቡን፣ ልቡን፣ ስሜቱን፣ ዕውቀቱን ሁሉ ወደ ሰማያዊ ነገር እንዲያሸጋግረው ፈቀደ፡፡ ይህን በማድረግ ከሰማይ የወረደው እርሱም የሰው ልጅ በሰማይ የነበረው€ እንደሆነ ይገነዘባል፡፡ ወደ ሰማይ መውጣትም የሚቻለው እርሱ ነው፡፡ በእርሱ የሚያምኑ ወገኖችን ከፍ ከፍ የሚያደርጋቸው ከፍ ያለውንም ነገር እንዲመለከቱ የሚያደርጋቸው እርሱ ነው፡፡

የኒቆዲሞስና የጌታ ግንኙነት ትኩረታችንን ወደ ክርስቶስ እንድናደርግ ያደርገናል፡፡ ለእያንዳንዱ የሰው ልጅ ነፍስ መዳን ምን ያህል ትኩረት እንደሚሰጥ ከእያንዳንዱም ወገን ጋር ሲነጋገር ያለውን ትህትናም እንገነዘባለን፡፡ ከኒቆዲሞስ ጋር ሲወያይ የአዲሱን ልደት ጠባይ ዘርዝሯል፡፡ ኒቆዲሞስ የእግዚአብሔርን መንግሥት ማወቅ ፈልጓል፤ ይሄንን መንግሥት ለማወቅ በውኃና በመንፈስ ይጠመቅ ዘንድ ግድ መሆኑን ያስረዳል፡፡

ይህ ሁኔታ አስፈላጊ ነው፤ ክርስቲያን ዘወትር የእግዚአብሔር ልጅ ሆኖ እንዲኖር ያስችለዋልና ይጠመቅ ዘንድ የግድ ነው፤ በመንፈሱም እንዲኖር ያደርገዋል፡፡ በዚህ ምዕራፍ ጌታ ከምድራዊ ነገሮች ያወጣና አሳባችን ሰማያዊ በሆነው ጉዳይ እንዲያዝ ያደርጋል፡፡ ይህንን ማድረግ የምንችለው ከሰማያዊው ጋር ሕብረት ስንፈጥር መሆኑን ይነግረናል፡፡

ጌታ ጥምቀቱን ከመስቀሉ ጋር አያይዞታል ፡፡ እግዚአብሔር አብ ለሰው ልጆች ሁሉ ያለውን እውነተኛ ፍቅር የገለጠበት፣ የባሕርይ ልጁን ወደ ዓለም በመላክ ዓለሙ ዘላለማዊ ሕይወትን ያገኝ ዘንድ ልጁ ከፍ ከፍ ያለበትም የነገሠበትም ዙፋኑ ነውና፡፡ አዲሱን ልደትን በማንሣት ጌታ ከፍርሃት ባርነት አውጥቶ መለኮታዊ የሆነውን ብርሃን እንድንመለከት ያደርገናል፡፡

ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ ጌታ ሲጠመቅ የነበረውን ሁኔታ ሲነግረን ለሚያምኑ ወገኖች ያለውን አንድምታም ሲገልጽ ደስታው ፍጹም ነበር፡፡ በዚህ ምዕራፍ ውስጥ

1.ስለ አዲሱ ልደት ገለጻ /1፡13/

2.አዲሱ ልደትና የመስቀሉ ሥጦታ /14-17/

3.አብርሆትና እምነት /18-21/

4.በጌታ ጥምቀት ጊዜ የዮሐንስ ሁኔታ /22-36/ ተዘርዝሯል፡፡

ስለ አዲሱ ልደት ገለጻ

ከፈሪሳውያንም ወገን የአይሁድ አለቃ የሆነ ኒቆዲሞስ የሚባል አንደ ሰው ነበረ /ቁ.1/€ ኒቆዲሞስ የአይሁድ ስም ሲሆን ትርጓሜው ሕዝብን ያሸነፈ€ ማለት ነው፡፡ የአይሁድ አካል የሰንሃድሪን አይሁድ ሸንጎም አባል ነው፡፡ መለኮታዊው ጥሪው መላውን የሰው ልጆች ያካተተ ነው፡፡ የመደብ ልዩነት አልተደረገበትም፡፡ ነገር ግን በከፍተኛ ሓላፊነት ከነበሩ የመንግሥትና የሃይማኖት መሪዎች መካከል ለዚህ ጥሪ መልስ የሰጡ ጥቂቶች ነበሩ፡፡ ከፈሪሳውያን መካከል እጅግ ጥቂቶች፤ ከጥቂቶቹ አንዱ ኒቆዲሞስ ነበር፡፡

ጌታን ሊያነጋግር የመጣው ብቻውን ነው፡፡ ምናልባት አንድ ወይም ሁለት አጃቢዎች ሳይኖሩት አይቀሩም፡፡ በአይሁድ ሸንጎ የተከበረ ሰው ነበረ፡፡ ጌታ ግን ይህችን አንዲት ለመዳን የወሰነች ነፍስ ዝቅ አላደረጋትም፤ ሞትን የተቀበለው ስለ እያንዳንዱ ነፍስ ነውና፡፡ ፈሪሳውያን ለመለኮታዊው እውነት የሰጡት መልስ ጥላቻና የዓመጽ መንፈስን የተመላ ነው፡፡ ነገር ግን ከተማሩ አይሁድ መካከል ጌታን ለማግኘት የቸኮሉ በሩም ተከፍቶ የጠበቃቸው ጥቂቶች ነበሩ፡፡ የእግዚአብሔር ጸጋ በተማሩም ባልተማሩም ወገኖች ላይ ይሠራል፡፡ በተራውም ሕዝብ፣ በአለቃውም፣ በየዋኁም፣ በዓመጸኛውም ላይ ይሠራል፡፡

ኒቆዲሞስ ደረጃው ከአመጸኞቹ ቢሆንም ወደ ጌታ መጣ፤ ጊዜው ሲደርስ የቻለውን ያህል ይጠይቅና ያውቅ ዘንድ ሞከረ፡፡ በጥያቄ ላይ እንደነበረ ታሪኩ ያስረዳል፡፡ ጊዜው ሲደርስ ለደቀ መዛሙርቱ ያልተቻለው ለዚህ ሰው ተቻለ፡፡ ከጲላጦስ አስፈቀዶ አዲስ ባሳነጸው መቃብር ላይ እንዲቀበር አደረገ፡፡

ቤን ረጊን በአይሁድ ታሪክ መጽሐፍ ስለ ኒቆዲሞስ ሲናገር ይህ ሰው በጣም ሀብታም ከመሆኑ የተነሣ በኢየሩሳሌም የነበሩ ብዙዎችን ለብዙ ዓመታት ይረዳ ነበር ይላል፡፡

እርሱም በሌሊት ወደ ኢየሱስ መጥቶ መምህር ሆይ እግዚአብሔር ከርሱ ጋር ከሆነ በቀር አንተ የምታደርጋቸውን እነዚህን ምልክቶች ሊያደርግ የሚችል የለምና መምህር ሆነህ ከእግዚአብሔር ዘንድ እንደ መጣህ እናውቃለን /ቁ.2/አለው፡፡

ቅዱስ ዮሐንስ ኒቆዲሞስን በብዙ ቦታዎች ጠርቶታል፡፡ ጌታን ማታ ማታ ይጎበኝ እንደነበረ ተገልጧል፤ ይህ ሁኔታ ሦስት ጊዜ ያህል ተጠቅሷል /ዮሐ.ዮሐ.3፡2፣ 7፡50፣ 19፡39/

ስለምን ወደ ጌታ በምሽት መጣ

1.የመጀመሪያው ምክንያት ጌታችን በአደባባይ የሚያስተምረውን ትምህርት ከሰዎች መስማቱ ብቻውን በቂ አይደለም፡፡ ከምንም በላይ ጌታ በአደባባይ የሚያደርገውን ምልክት በሕዝብ መካከል በግልጽ መጥቶ ማየት አልወደደም፡፡ ድኅነትና ነፍስን የሚመለከቱ ጉዳዮችን በጥሞና ከጌታ ሥር ቁጭ ብሎ መነጋገር ልቡ ፈቅዷል፡፡ቃሌስ በቅንነት ለሚሄድ በጎ አያደርግምን /ሚክ.2፡7/ ተብሎ እንደተጻፈ የቅንነትን መንገድ መርጦ ወደ ጌታ ቀርቧል፡፡

ኒቆዲሞስ ከጌታ ጋር ይነጋገር ዘንድ ወደደ፡፡ ጌታ እንኳን ከሕዝቡና ከደቀመዛሙርቱ ተለይቶ ከአብ ጋር ሲነጋገር የሚያድርበት ጊዜ ነበር፡፡ እኛማ ሌሊቱን በሙሉ ከእግዚአብሔር ጋር እንደምን መነጋገር ይገባን ይሆን፡፡ በተለይ በሌሊት ሁሉንም ነገር ትተን ከጌታ ጋር የግል ጭውውት ማድረግ ይጠበቅብናል፡፡ አዲሱን ሕይወትና የዚህን ሕይወት ባህርይ፣ በዚህ ሕይወትም ውስጥ ካለች ከመንፈስ ሕብረት ተካፋዮች እንሆን ዘንድ ይገባናል፡፡

2.ሁለተኛው ምክንያት ምናልባት ጥበብን ለመማር የማታው ጊዜ የተሻለ እንደሆነ በመረዳቱ ነው፡፡ ጌታ ቀን ቀን ሕዝቡን በማስተማር ተይዞ እንደሚውል ያውቃል፡፡ ስለዚህ ኒቆዲሞስ ምሽት እስከሚመጣ ድረስ ጠበቀ፡፡ ጌታን ለማግኘትና የድኅነት ጨዋታን ይጨዋወቱ ዘንድ ወደደ፡፡

3.ሦስተኛው ምክንያት አንዳንድ ምልክቶችን ከተመለከተ በኋላ ጌታን ለማግኘት የመጀመሪያውን ዕድል በምሽት አግኝቶ ይሆናል፡፡ ሁሉም ሰው ሲተኛ ከጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጋር መንፈሳዊ የሆነች ምሽትን ማሳለፍ ፈልጎ ይሆናል፡፡ ምናልባትም እንዲህ አይነት ዕድል ወደፊት ሊገጥመው እንደማይችል ሥጋት አድሮበት ሊሆን ይችላል፡፡

4.አራተኛው እንደ ነቢዩ ዳዊት ምሳሌውን ሊከተል ፈልጎ ::ዳዊት ሌሊቱን ለምስጋና ይጠቀምበት ነበርና /መዝ.36፡6፤119፡148/

5.አምስተኛው ምናልባትም ኒቆዲሞስ ወደ ጌታ ዘንድ እየሄደ መማሩ ለካህናት አለቆች ወሬው ሊደርስ ይችላል ብሎ ከፍርሃት የተነሣ ሊሆን ይችላል፡፡

6.ስድስተኛው ኒቆዲሞስ ወደ ጌታ ዘንድ መድረሱን አይሁድ ቢያውቁ ጌታችንን ለመዋጋት ቁጣቸውን ይጨምርላቸዋል፡፡ ኒቆዲሞስን ራሱን ለመጉዳት አይሁድ ፈሪሳውያን ሊነሳሡበት ይችላሉ፡፡ ምንም እንኳን በጌታ ትምህርት የተሳበ ቢሆንም በቀን እንዳይሄድ እምነት አንሶት ሊሆን ይችላል፡፡

7.ሰባተኛው ምክንያት ከምንም በላይ ጌታ የዓለም ብርሃን መሆኑን በእርግጠኝነት አለመረዳቱ ነው፡፡ ኒቆዲሞስ የአይሁድ አለቃ ነው፤ የእስራኤል መምህር ነው፡፡ ሰማያዊውን ደስታ ገንዘብ ያደርግ ዘንድ አዲስ ልደት የሚያስፈልገው ሰው ነው፡፡ በምሽት ሲመጣ ደካማ የሆነ እምነትን ይዞ ነበር የመጣው፤ ነገር ግን የጌታ በር ተከፍቶ አገኘው፡፡ ጌታ ስሜቱን ሊጎዳው አልወደደም፡፡

ሁሉ ነገር የሚቆጠረው እምነት እንደሰናፍጭ ቅንጣት ቀስ በቀስ በልቡ ውስጥ እንደሚያድግ ነበር፡፡ ጌታ የፈለገው ያች ቅንጣት አብባ፣ አፍርታ፣ ጌታ በሚሰቀልበት ጊዜ ትልቅ ዛፍ ትሆን ዘንድ ነበረ፡፡ እንደዚያ ሲሆን ነው በዚያ እምነት ደረጃ ላይ ሲደርስ ነው በድፍረት የጌታን ሥጋ የቀበረው፡፡

ኒቆዲሞስ ከጌታ ጋር በተገናኘ ጊዜ የአይሁድ ድካም በእርሱም ላይ ይንጸባረቅ ነበር፡፡ አስቀድመን እንዳልነው በብርሃን ሳይሆን በጨለማ የመምጣቱም ምክንያት ይህ ነበር፡፡ ነገር ግን መኃሪው አምላክ አልጠላውም፤ ትምህርቱንም አልከለከለውም፡፡ ከዚህ በተቃራኒው ጌታ በጉጉት ከእርሱ ጋር ተነጋገረ፤ ከፍ ያለውንም ምስጢር ገለጠለት፡፡ በርግጥ ለኒቆዲሞስ የተሰወረ ነበረ፡፡ ጌታ ግን አብራራለት፤ ክፉ አሳብ ከነበራቸው ወገኖች አንጻር ሲመዘን ይህ ሰው ይቅርታን ያገኝ ዘንድ እንደሚገባው ጌታ ቆጥሯልና፡፡ ክፉ ሰዎች ይቅርታ የላቸውም፡፡

ምንም እንኳን ኒቆዲሞስ ከአይሁድ የተለየ ቢሆንም ጌታን የቆጠረው ሰው አድርጎ ነው፡፡ ይናገረው የነበረው እንደ ነቢይ ነው፡፡ ያደረገውን ምልክት እያደነቀ ነበር የጠየቀው፡፡

መምህር ሆይ ከእግዚአብሔር ዘንድ እንደመጣህ እናውቃለን /ቁ.2/ አለው፡፡

ታዲያ ኒቆዲሞስ ሆይ ስለምን በምስጢር በምሽት መጣህ? ከእግዚአብሔር ዘንድ እንደመጣ የእግዚአብሔር የሆነውንም ነገር እንደሚናገር እያወቅህ፡፡ ስለምን ከእርሱ ጋር ነገሮችን በግልጽ አልተወያየህም? ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ኒቆዲሞስን እንዲህ ዓይነት ጥያቄዎችን አልጠየቀውም፡፡ አልወቀሰውምም፡፡ ነቢዩ እንዲህ ይላል €œአይጮኸም፤ ቃሉንም አያነሣም፣ ድምፁንም በሜዳ አያሰማም፡፡ የተቀጠቀጠ ሸምበቆን አይሰብርም፣ የሚጨስንም ክር አያጠፋም€ /ኢሳ.42፡3/ ጌታ ራሱ እንዲህ ብሏል፡፡ ዓለሙን ላድን እንጂ በዓለሙ ልፈርድ አልመጣሁም፡፡ /ዮሐ.12፡47/

€œእግዚአብሔር ከርሱ ጋር ከሆነ በስተቀር አንተ የምታደርጋቸውን እነዚህን ምልክቶች ሊያደርግ የሚችል የለምና /ቁ.2/

የጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ትሕትና ተመልከቱ! እንዲህ አላለም €œእኔ ሁሉን በራሴ ማድረግ ይቻለኛልና የማንም እርዳታ አያስፈልገኝም፡፡ እኔ ራሴ እግዚአብሔር ነኝ፡፡ የያዝኩት ኀይል የአባቴን ኀይል ነው፤ ይህንን ቢል ለሚያዳምጡት ወገኖች ከባድ በሆነ ነበር፡፡

ነገር ግን ድርጊቱን ሲፈጽም በተመሳሳይ መንገድ አልነበረም፤ ምልክትን ሲያደርግ በኀይል ነው፤ ስለዚህም እንዲህ አለ €œልትነጻ እወዳለሁ /ማቴ.8፡3/ ጣቢታ ተነሽ /ማር.5፡4/ እጅህን ዘርጋ /ማር.3፡5/ ኀጢአትህ ተሠረየችልህ /ማቴ.9፡2/ ፀጥ በል /ማር.4፡39/ አልጋህን ተሸከምና ሂድ /ማቴ.9፡6/፤ አንተ ርኩስ መንፈስ ከዚህ ሰው ውጣ /ማር.5፡8/፤ ማንም ስለምን እንዲህ ታደርጋላችሁ ቢላችሁ ለጌታ ያስፈልገዋል በሉት ማር.11፡3/፤ ዛሬ በገነት ከእኔ ጋር ትሆናለህ /ማር.23፡43/፡፡ ለቀደሙት አትግደል እንደተባለ ሰምታችኋል የገደለም ሁሉ ፍርድ ይገባዋል እኔ ግን እላችኋለሁ በወንድሙ ላይ የሚቆጣ ሁሉ ፍርድ ይገባዋል፡፡ /ማቴ.5፡21-22/ ተከተለኝ ሰውን አጥማጅ አደርግሃለሁ /ማቴ.1፡17/፡፡

በማንኛውም ሁኔታ ታላቅ ሥልጣኑን እንመለከተዋለን፡፡ ስለዚህ ሲሠራ ማንም ወገን በርሱ ላይ ስህተትን ማግኘት አይቻለውም፡፡ ነገር ግን ሊያጠምዱበት የሚቻላቸው በአንድ መንገድ ብቻ ነው እርሱም በንግግሩ ብቻ ነው፤ ማለት ንግግሩን በተሳሳተ መንገድ በመተርጎም፡፡

ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እንዲህ ይላል፡-

ስለዚህ ነው ጌታ ኒቆዲሞስን በግልጥ ያናገረው፤ ነገር ግን የአብ የባሕርይ ልጅነቱን በመግለጽ አልጀመረም፤ ምልክት የሚያደርገው በተመሳሳይ ሥልጣን መሆኑን አልገለጠለትም፡፡

ኒቆዲሞስ በሥሙ ከሚያምኑ ከጌታ ጋር ግን ግንኙነት ከሌላቸው ወገኖች አንዱ ነበረ፡፡ ስለዚህ በምሽት ወደ ጌታ ዘንድ መጣ፡፡ የመጣው ወደ ብርሃን ቢሆንም በጨለማ መጣ፡፡

ምንም እንኳን ኒቆዲሞስ የመጣው ወደ ጌታ ቢሆንም የመጣው በምሽትና የሚናገረው በጨለማ ነፍሱ ነበር፡፡ ስለዚህ በሰው ሁሉ ላይ የሚያበራውን ብርሃን የሚናገረውን መልእክት ሊረዳው አልተቻለውም፡፡

ኒቆዲሞስ መምህር ነበረ ወደ እውነተኛው ብርሃን በጨለማ የመምጣቱ ምስጢርም ምናልባት ለክብሩ ተጠንቅቆ ነው፡፡ የሚናገረውን ማንነት ገና አላወቀምና፤ መማሩ እንዲያፍር አደረገው፤ በግሌ እኔ መምህርን ማዳመጥ እንጂ ሰዎች እንደመምህር ሲያዳምጡኝ አይደለም የምጠቀመው፡፡ የመጀመሪያ በመሆን ፍላጎትና ዝንባሌ ያላቸውን ወገኖች ጌታ እንዲህ ብሎ ሲገሥጻቸው አውቃለሁ፡፡ እናንተ ግን መምህር ተብላችሁ አትጠሩ መምህራችሁ አንድ ነውና /ማቴ.23፡8/

በማንኛውም ሁኔታ ኒቆዲሞስ በምሽት ወደ ጌታ የመጣው ለመጠመቅ አልነበረም ለመማርና የጌታ ደቀመዝሙርም ለመሆን አይደለም፡፡

በአይሁድ ትውፊት መሠረት ማንም ወገን በምሽት ወደ አይሁድ እምነት፣ ለመገረዝ ወይም ለመጠመቅ አይመጣም፡፡ ይህ ሕግን መተላለፍ ነው፡፡ እንደ ተማሪ ከጌታ ሥር ቁጭ ብሎ ለመማር ሳይሆን የጌታን አሳብ ለማወቅና በጎዳናውም ይጓዝ ዘንድ ነው፡፡

ለአንድ ቅዱሳት መጻሕፍትን ጠንቅቄ አውቃለሁ ለሚል የአይሁድ መምህር ረቢ ብሎ ጌታን መጥራት ቀላል ነገር አይደለም፡፡ የሕዝብ አለቃ ነኝ ብሎ የሚያስብ ሰው በትህትና ረቢ ብሎ ሲናገር መመልከት በርግጥም ያስደንቃል፡፡€œመምህር ሆይ ከእግዚአብሔር ዘንድ እንደመጣህ እናውቃለን/ቁ.2/ ምንም እንኳን ኒቆዲሞስ የአይሁድ መምህር ቢሆንም የተናገረው ፖለቲካ ወይም የአገር ጉዳይ አይደለም፡፡ ነፍሱ ስለምትድንበት ሁኔታ ብቻ ነው የጠየቀው፡፡

ኒቆዲሞስ ስለ ጌታ አንድ ነገር ያውቃል፤ ጌታ በአይሁድ ምሁራን ወይም በታወቀ የአይሁድ ትምህርት ቤት ገብቶ የተማረ አይደለም፡፡ ትምህርቱ ከሰማይ ነው፡፡ ጌታ የያዘው የእውነትን ኀይል እንጂ የሰይፍን ኀይል አለመሆኑን ተገነዘበ፡፡ የሰውን ጥበብ ባለፈ ፍጹም መለኮታዊ ጥበብ እንደሚናገር ተገንዝቧል፡፡ የሚያደርገው ምልክት በመለኮታዊ ኀይል መሆኑን ተገንዝቧል፡፡

በጣም አስደናቂው ንግግሩ €œእናውቃለን€ የሚለው ነው፡፡ ምናልባት ከርሱ ጋር ሌሎች ሰዎች እንዳሉ ያመለክታል፤ ወይም ፈሪሳውያንን ወክሎ እየተናገረ ይሆናል፡፡ ምክንያቱም ምግባቸውም መጠጣቸውም ወሬአቸውም ክርስቶስ ሆኗልና፡፡ ከእነርሱ መካከል ኒቆዲሞስ የሚያምነውን እምነት የሚያምኑ ፈሪሳውያን ሊኖሩ ይችላሉ፡፡ ነገር ግን ከእነርሱ መካከል ጌታን በግልጥ ወይም በስውር ሊያገኘው የፈለገ ወገን የለም፡፡

ኢየሱስም መልሶ እውነት እውነት እልሃለሁ ሰው ዳግመኛ ካልተወለደ በቀር የእግዚአብሔርን መንግሥት ሊያይ አይችልም አለው /ቁ.3/€

ኒቆዲሞስ ምልክትን ማድረግ ለክርስቶስ ከእግዚአብሔር ዘንድ እንደሆነ ለማመኑ ማሣያ አድርጎ ቆጥሮ ነበር፡፡ ምክንያቱም የአይሁድ ረበናት እምነትን ምልክት ከመሥራት ጋር አያይዘውታልና፡፡ ስለ ክርስቶስ ማንነት ለመመስከር ከዚህ ወንዝ ባሻገር ያቋረጠው የለም፡፡ ስለዚህ ጌታን ዕሤተ በጎነት ያለው መምህር፣ የእግዚአብሔር ሰው አድርጎታል፡፡ እግዚአብሔር ይስሐቅን €œአትፍራ እኔ ከአንት ጋራ ነኝና /ዘፍ.26፡24/ እንዳለው ሰው ዓይነት አድርጎ ገምቶት ነበር፡፡ ወይም እንደ መበለቲቱ ልጅ ኢያሱ ከሙሴ ጋር እንደ ነበርሁ ከአንተም ጋር እሆናለሁ /ኢያ.1፡5/ ያለው ዓይነት ነቢይ ነበር ጌታ ለኒቆዲሞስ፡፡

ሌሎች ብዙ አለቆችና ነቢያት ተመሳሳይ ልምድ ነበራቸው፤ ነገር ግን ኒቆዲሞስ ምንም እምነትን ይዞ ቢመጣም ከፈሪሳውያን ጠባብ አስተሳሰብ ልጓም እንዳይወጣ የሚያደርግ አዕምሮ ነበረው፡፡ የተማረውም ይኼንን እውነታ ነው፡፡ በጌታና በኒቆዲሞስ መካከል የነበረው ውይይት የሚከተሉት ነጥቦች የትኩረት አቅጣጫዎቹ ነበሩ፡፡

1.የዳግም ልደት አስፈላጊነት እርሱም ውስጣዊው ዓለም የተሻለ እንደሆነ የሚያሳይ ነው፤ እርሱም የእግዚአብሔር መንግሥት ነው፡፡ ይህ አባባል በቅብጥ፣ በሶርያ፣ በላቲን በመጀመሪያይቱ ቤተ ክርስቲያን አባቶች ጽሑፍ የተካተተ ነው፡፡ ዮስጢኖስ፣ ቀሌምንጦስ ዘእስክንድርያ፣ ጠርጡለስ፣ አውግስጢኖስና፣ ዠሮም ለአብነት ይጠቀሳሉ፡፡ጌታችን ኒቆዲሞስን እንደገና እንዲወለድ እንደጋበዘው ተረድቷል፡፡ ይህ አስደነቀው፡፡ አሳቡ በልቡ ውስጥ መዳህ ጀምሯል፡፡ ሰው ከሸመገለ በኋላ እንዴት ሊወለድ ይችላል አለ፡፡

2.አዲሱ ልደት ከላይ ነው ሰማያዊ ነው /3/ ይህ ድርጊት በቅዱሱና በሰማያዊው የእግዚአብሔር መንፈስ ብቻ የሚፈጸም ነው፡፡ የሰውን አሳብ ሁሉ ያለፈ ስጦታ ነው፡፡

3.አዲሱ ልደት የሚፈጸመው በውኃና በመንፈስ ነው /5/

4.ይህ ልደት በኀይል ያለ በነፍስ የተመሰለ ነው፡፡ ስለዚህ ማንም ምስጢሩን ሊገነዘበው አይችለም፡፡

በአይሁድ ጽሑፍ እውነት የሚለው ቃል መደገሙ በእውነት ቅዱስ ከሚለው ጋር ተመሳሳይ ነው፤ ጌታችን የሚናገረው ነገር በጣም ጠቃሚና ትኩረት የሚያሻው መሆኑን ለመናገር ይጠቀምበታል፡፡

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱሱ ክርስቶስ በርጋታ ለኒቆዲሞስ የገለጸለት ኢየሱስ ክርስቶስ በእግዚአብሔር ዘንድ መምህር መሆኑን ማመን ብቻውን በቂ አለመሆኑን፣ ተአምራቱንም ማድነቅና የተለዩ መሆናቸውን ማወቅ በራሱ ግብ አለመሆኑን ነው፡፡ በርግጥም የሚያስፈልገው እንደገና መወለድ ነው፡፡ እርሱም ሰማያዊ የሆነ ልደት ነው፡፡ ሰማያዊ መንፈሳዊ የሆኑ ጉዳዮችን ለማየት ያስችላልና፡፡ በእናቱ ማኅፀን ያለ ፅንስ በዚህ ዓለም እየሆነ ስላለው ነገር የሚያውቀው ነገር የለም፡፡ በተመሳሳይ ሁኔታ አንድ ሰው ከውኃና ከመንፈስ ካልተወለደ በስተቀር የእግዚአብሔርን መንግሥት መመልከት አይቻለውም፡፡ እንደገና ከተወለደ ብቻ ነው የአዲሱን ዓለም ብርሃን መመልከት የሚችለው፡፡

ሊያይ የሚለው ጌታችን አጽንዖት ሰጥቶ የተናገረው ግሥ ለእውነተኛ ክርስቲያን አስፈላጊ ነው፡፡ አዲሱን ልደት ያጣጥም ዘንድ ስለተወለደ እንዲመካ አይደለም የእግዚአብሔርን መንግሥት ሊመለከት ለመንግሥቱም እንደሚገባ ሊመላለስ ይገባዋል እንጂ፡፡

ይህ ማለት አዕምሮውና ልቡ ሰማያዊ በሆነ ነገር ላይ ማተኮር አለበት ማለት ነው፡፡ ከሰማያዊ ሕግ ጋር አብሮ የሚሄድ ሕግን ያለማወላወል ሊከተል ይገባዋል፡፡ አዲስ ግብ፣ አዲስ ተስፋ አዲስ ኀይልን ገንዘብ አድርጎ፡፡

በአዲሱ ልደት ክርስቲያን በአይነቱ የተለየ ኑሮን መኖር ይጀምራል፤ አሮጌውን የሰውነቱን ሕንፃ አፍርሶ መሠረቱ ክርስቶስ የሆነውን አዲስ ሕንፃ በማነጽ አሮጌው ሰዋችን ተወግዶ የክርስቶስን መልክ የያዘው አዲሱ ሰው ሊታይ ይገባዋል፡፡

አስቀድመን ኀጢአት ጥንተ ተፈጥሮአችንን ስላጠፋው፣ የልባችንም ጥልቅ በኀጢአት ተይዞ ስለኖረ፣ ሥጋውያን በሥጋ ሕግና ፈቃድም የምንመራ ሆነናል፡፡ የምንመራውም የመልካም ነገር ጠላት በሆነ በዲያብሎስ ነበረ፤ ስለዚህ አዲሱ ልደት ልንሸሸው የማይገባ ጠቃሚ ጉዳይ ሆኖ ቀርቧል፡፡ እውነት እውነት እልሃለሁ የሚለው የጌታ ቃል ለዚህ እውነት ማሣያ ነው፡፡

የእግዚአብሔር መንግሥት ምንድነው? ከሰማያዊው መሲሕ ሌላ መመልከት እንደሌለብን የምታሳስብ መንግሥት አይደለችምን! በእኛ መካከል መንግሥቱን መሥርቶ ይኖራል፡፡ ከእርሱ ጋር አንድነትን ፈጥረን የምናየው፣ የምንኖረው ሁሉ ለዚህ ሕይወት እንደሚገባ ነው፡፡ እርሱ ቅዱስ ስለሆነ እኛም ቅዱሳን እንሆናለን፡፡ በእኛ የሚኖረው የእግዚአብሔር መንግሥት ትክክለኛ ትርጉምም ይኼው ነው፡፡ ጌታ መንግሥተ ሰማያት ቀርባለችና ንሥሐ ግቡ /ማቴ.4፤17/ አለ፡፡ እንደገናም መንግሥተ ሰማያት በመካከላችሁ ናት /ሉቃ.17፡21/ ብሏል፡፡ በእግዚአብሔር መንግሥት ያለንን ሥፍራ ሲናገር፡፡ ጌታ መንግሥትም ለአምላኩና ለአባቱም ካህናት እንድንሆን ላደረገ /ራዕ.1፡6/ ይላል፡፡

ይህ መንግሥት ከጌታችን ከመድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጋር ኅብረትን የምንፈጥርበት መንግሥት በመሆኑ እንዲህ ተብሏል፡-€œየእግዚአብሔር መንግሥት ጽድቅና ሰላም በመንፈስ ቅዱስም የሆነ ደስታ ናት እንጂ መብልና መጠጥ አይደለችም€ /ሮሜ.14፡17/

ይህ መንግሥት ለዘላለማዊ ሕይወት ዋስትና ነው፡ ወደ ሰማይ እንድንጓዝ ጌታ በጌትነቱ ሲመጣ አስደናቂውን ክብር እንድንካፈል ያደርገናል፡፡ ከምንም በላይ አሳባችንን ከፍ ከፍ አድርጎ ውስጣዊ ነፍሳችንን የመጨረሻውን ቀን እንድትመለከት ጌታ ሲመጣ ሰማያዊ ዘውድን ደፍተን ያለፍርሃት በፊቱ እንቆም ዘንድ የሚያስችለንን ጸጋ እንይዝ ዘንድ ያስችለናል፡፡

የጌታን ቃል እንደገና በሌላ አባባል እንግለጠው ብንል ዳግመኛ ካልተወለድህ ከመንፈስ ጋር ኅብረት ካልፈጠርህ በጥምቀት ልጅነትን ካላገኘህ እኔን በተመለከተ ትክክለኛ የሆነውን አሳብ አታገኝም´የሚል ይሆናል፡፡

€œኒቆዲሞስም ሰው ከሸመገለ በኋላ እንዴት ሊወለድ ይችላል ሁለተኛ ወደ እናቱ ማኅፀን ገብቶ ይወለድ ዘንድ ይችላልን? /ቁ.4/ በማለት ጠየቀ፡፡

የኒቆዲሞስ ጥያቄ የእውቀት ድካሙን ይገልጣል፡፡ ጌታ የሚናገረው በመንፈሳዊ ቋንቋ ነው፡፡ የኒቆዲሞስ ልብ ነገሮችን የሚያገናኘው ቁሳዊ ዓለማዊ ከሆኑ ነገሮች ጋር ነው፡፡ ቁሳዊ ነገሮችን ከልቡናው ከአእምሮው ካላወጣ መንፈሳዊና ሰማያዊ የሆኑ ምስጢራትን እንደምን ሊገነዘብ ይችላል? ያኔ ነው ወደ እውነት መድረስ የሚቻለው፡፡ በእግዚአብሔር መንፈስ አዲስ መንፈሳዊ ጉልበትን ይዞ ምስጢርን መረዳት የሚቻለው፡፡

ኒቆዲሞስ ጌታ በተናገረው አዲስ ልደት ተደንቋል፤ ልክ እንደ ሌሎች አይሁድ ዘመዶቹ የአብርሃም ዘር በመሆኑ የሚመካ ነው፡፡ ጌታ ደግሞ እንደገና ተወለድ እያለው ነው፤ አይሁድ ለእግዚአብሔር የተመረጡና የተወደዱ አድርገው ራሳቸውን ይቆጥሩ ነበር፡፡

በነቢያትና በተስፋው ቃል ኪዳን የተቀደሱ ሕዝቦች ነን ይሉ ነበር፡፡ ከምንም በላይ እግዚአብሔር ከእነርሱ አባቶች ጋር ቃል ኪዳን ገብቶ ነበር፡፡ ልዩ መቅደስና መሥዋዕትም ነበራቸው፡፡ ኒቆዲሞስ እስራኤላዊ ብቻ አልነበረም ፈሪሳዊም ጭምር እንጂ፡፡

ምን ዓይነት ከዚህ የበለጠ ልደት ጌታ ይሰጠኛል ብሎ ሊያስብ ይችላል? አይሁድ መሲሑ ሲመጣ የእስራኤል መንግሥት እንደሚያምንበት እንደገናም እንደሚወለዱ ይገምታሉ፡፡ ነገር ግን አስቀድሞ በነበራቸው ኩራትና ትምክህት አንጻር ሲመዝኑት ይህ የሚሆን አይመስላቸውም ነበር፡፡ እነርሱ አሁን ከያዙት የአብርሃም ልጅነት የከበረ ልደት ያለ መስሎ አይታያቸውም ነበር፡፡ ስለ ትውልድ ሀገራቸው ይመኩ ነበር፤ ስለዚህ ሌላ ልደት መስማት የሚሆንላቸው አይደለም፡፡

ይህ ሁሉ ነገር እያለ ኒቆዲሞስ ጀርባውን ለጌታ አልሰጠም፤ እርሱ የጎደለው አንድ ነገር እንዳለ አምኖ ትምህርቱን ቀጥሏል፡፡ በግብሩ ምንም እንኳን መምህርና አለቃ ቢሆንም በትሕትና እውነተኛ የሆነ ነገርን ለመማር የተዘጋጀ መሆኑን ገልጧል፡፡ ነገር ግን ጌታ የሚለው አዲስ ልደት የማይቻል እንደሆነ ገምቷል፡፡ አስደናቂ ሰው ነው፡፡ ረጅም ዘመን የትምህርትና የአመራር ልምድ ያለው ሰው ከጌታ እግር ሥር ተንበርክኮ አዲስ ነገርን ሲማር መመልከት ያስደንቃል፡፡ ለእውነተኛ አለቃ ጌታ የሰጠው ምሳሌ አስቸጋሪ ሊሆንበት ይችላል፡፡ አሁን ኒቆዲሞስ ስለ ትምህርትና ስለ አመራር ልምዱ ሲመካ አንመለከተውም፡፡ እስከመጨረሻው እስትንፋሱ ድረስ ሲማር እንጂ፡፡ አምብሮስ እንዲህ ይላል፡- የኒቆዲሞስ ሁኔታ የሚያሳየን መማር የማያስፈልገው እግዚአብሔር ብቻ መሆኑን ነው ይላል፡፡

ኒቆዲሞስ ወደ ጌታ መጣ፤ ከፍ ያሉ ነገሮችን አዳመጠ፡፡ እንዲህ ዓይነት ጉዳዮች ተራ ሰው የሚገልጣቸው አይደሉም፡፡ ማንም ሰውም ከዚህ አስቀድሞ ሰምቷቸው አያውቅም፡፡ በቅፅበት ኒቆዲሞስ ወደ ከፍታ ወጣ፤ ነገር ግን መረዳቱ ጨለማ ነበር፡፡ ነገር ግን በራሱ ማስተዋል ገና የቆመ በመሆኑ ሊሸከማቸው ስላልቻለ ወደቀ፤ የጌታን ቃል እንዴት ሊሆን ይችላል? በማለት ጠየቀ፡፡ ጌታ የተናገረውን ነገር እንዲያብራራለት ሰው ከሸመገለ በኋላ ወደ እናቱ ማኅፀን ገብቶ ይወለድ ዘንድ ይችላልን በማለት ማብራሪያ ጠየቀ፡፡

ኒቆዲሞስ ስለ መንፈሳዊ ልደት ሰምቷል፡፡ ነገር ግን በመንፈስ አልተለማመዳቸውም /አያውቀውም/፡፡ኒቆዲሞስ ትውክልቱን ያደረገው ቁሳዊ መረጃ ላይ ነው ፤ይህንን ትልቅ ትርጉም ለመረዳትና ለመተርጎም ምሳሌ አድርጎ ያቀረበው የሰውን የሥጋ ልደት ነው፡፡ ይህንን ሁኔታ ቅዱስ ጳውሎስ እንዲህ በማለት ይገልጠዋል €œለፍጥረታዊ ሰው የእግዚአብሔር መንፈስ ነገር ሞኝነት ነውና አይቀበለውም በመንፈስም የሚመረመር ስለሆነ ሊያውቀው አይችልም€ /1ቆ.2·14/

በዚህ ሁሉ ነገር ኒቆዲሞስ ክብርና ጉጉት ይታይበታል፡፡ ጌታ የነገረው ነገር አላስቆጣውም፡፡ ነገር ግን ይህ ሁኔታ የማይቻል መሆኑን አስቦ ጥያቄ ጠይቆ ዝም አለ፡፡ ሁለት ነገሮችን ተጠራጥሯል፡፡ ምን አይነት እንደገና መወለድ እና የእግዚአብሔር መንግሥት፡፡ አይሁድ በየትኛውም ጊዜ ስለ እግዚአብሔር መንግሥት የተናገሩት ነገር የለም፡፡ ስለ ዳግም ልደትም እንዲሁ፡፡ ስለነዚህ ነገሮች ሰምተውም አያውቁም፡፡ ኒቆዲሞስን ያስደነቀውም ነገር ይህ ነው፡፡

ቅዱስ አውግስጢኖስ እንዲህ ይላል፡- ይህ ሰው ከአዳምና ከሔዋን የሚደረግ ልደትን ሰምቷል፤ ከእግዚአብሔርና ከቅድስት ቤተ ክርስቲያን ስለሚደረገው ልደት ግን አያውቅም፡የሚያውቀው ዘርን የሚተኩ ወላጆች በሞት ፍጻሜያቸውን እንደሚያገኙ ነው፡፡ ነገር ግን ሕይወትን ስለሚሰጠው ስለ አዲሱ ልደት ያለው ግንዛቤ ከመረዳት በታች ነው፡፡ ንብረታቸውን የሚወርሱ ልጆችን የሚወልዱ ቤተሰቦች ያውቃል፡፡ ነገር ግን ዘወትር የሚኖሩ ልጆችን የሚወልዱ የማይሞቱ ወላጆችን በተመለከተ እውቀት የለውም፡፡ ሁለት ዓይነት መወለድ አለ፡፡ አንደኛው በምድር የሚደረግ ሁለተኛው ሰማያዊ፡፡ የመጀመሪያው ከሥጋና ከደም ሁለተኛው ከውኃና ከመንፈስ፤ የመጀመሪያዎቹ ለሞት የተጋለጡ ናቸው የኋለኞቹ ዘላለማውያን ናቸው፡፡ የመጀመሪያዎቹ የተወለዱት ከወንድና ከሴት የኋለኞቹ ከእግዚአብሔርና ከቅድስት ቤተ ክርስቲያን ነው፡፡ ኒቆዲሞስን በተመለከተ የሚያውቀው አንድ ልደትን ብቻ ነው፡፡

ኢየሱስም መለሰ እንዲህ ሲል እውነት እውነት እልሃለሁ ሰው ከውኃና ከመንፈስ ካልተወለደ በስተቀር ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ሊገባ አይችልም፡፡ /5/

ጌታ ይህንን እውነት ዝቅ አድርጎ እንዳይመለከተው በማሰብ አስቀድሞ የተናገረውን ነገር ደገመለት ፡፡ በርግጥ የእግዚአብሔር ቃል አዎ አይደለም ከሚለው አፍአዊ ነገር በዘለለ መልስን የሚጠይቅ ነው፡፡ ምንም እንኳን ኒቆዲሞስ ከመረዳት አቅሙ በላይ ቢሆንም ጌታ እንደገና መወለድ ትምህርቱ ላይ ጠንከር ብሎ ሄዷል፤ ያለዚህ ልደት የእግዚአብሔርን መንግሥት ለማየትም ለመግባትም የሚያስችል መንገድ የለም፡፡

ሰው ከውኃና ከመንፈስ መወለድ አለበት ይላል፤ ስለምን ውኃን ይጠቀማል? ውስጣዊ የመንፈስ መታጠብን ለማመልከት ነው፡፡ /ቲቶ.3፡5፣ 1ቆሮ.6፡11፣ ሕዝ.36፡25/ €œ

ይህ ውስጣዊ የመንፈስ መታጠብ በመንፈስ ቅዱስ የሚፈጸም ነው፡፡ እርሱ ብቻ ያጥባል ያነጻል ውስጣዊ ልባችንን አዲስ ያደርጋል፡፡ ጌታ በሰርግ ቤት ተገኝቶ ውኃውን ወደ ወይን በመቀየር በሰርጉ ቤት ለነበሩ ዕድምተኞች ደስታን እንደሰጠ በመንፈሱ የሰጠው ውጫዊ የሰውነት መታጠብ አይደለም፡፡

ይህ ውኃ ማንም የተጠማ ቢኖር ወደ እኔ ይምጣ ይጠጣ በማለት ለሳምራዊቷ ሴት የነገራት የሕይወት ውኃ ነው፡፡ በያዕቆብ ጉድጓድ ውስጥ እንዳለው ውኃ አይነት አይደለም ያዕቆብ፣ ልጆቹና፣ ከብቶቹ የጠጡት ውኃ የሚያረካው የሥጋን ጥማት ነው፡፡ ጌታችን የሚሰጠን ውኃ ግን የነፍስን ጥማት የሚያረካ ነው፡፡

በአዲሱ ልደት ውኃ አስፈላጊ ሆኗል፤ ጥምቀት የሚፈጸመው በመዘፈቅ ነውና፡፡ ይህም ሞትን የመቀበልና ከኢየሱስ ክርስቶስ ጋር የመቀበር ምልክት ነው፡፡ ከእርሱ ጋር እንነሣ ዘንድ የግድ ያስፈልገናል፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ እንዲህ ይላል፡-

እንግዲህ ክርስቶስ በአብ ክብር ከሙታን እንደተነሣ እንዲሁ እኛም በአዲስ ሕይወት እንድንመላለስ፣ ከሞቱ ጋር አንድ እንሆን ዘንድ በጥምቀት ከእርሱ ጋር ተቀበርን€

ከውኃና ከመንፈስ መወለድ የአሮጌውን ሰው መሞትና የአዲሱን ሰው ትንሣኤ ይጠይቃል፡፡ በመንፈስ ቅዱስ የሆነውን አዲስ ሕይወትም መቀበል ነው፡፡ እርሱም የትንሣኤ መንፈስ ነው፡፡ ለኃጢአት ሞተን ለጽድቅ እንድንኖር የሚያደርገንን አዲሱን ሰው የመፍጠር ሂደት ነው፡፡ በፈጣሪያችን መልክ የተፈጠረውን አዲስ ሰው መመልከት ነው፡፡

በጌታችን በመድኀኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም አምነው መስቀሉን ሊሸከሙ የሚወዱ ወገኖች በአብ በወልድና በመንፈስ ቅዱስ ስም መጠመቅ አለባቸው፡፡ የጌታ ቃል ትርጉም ለኒቆዲሞስ ምንድነው ብላችሁ ብትጠይቁኝ መልሴ የሚሆነው ጌታ ከሥጋ ትውልድ ወጣ ብሎ መንፈሳዊውን ትውልድ እንዲያስብ ሳበው የሚል ይሆናል፡፡

ጌታ እንዲህ በማለት የነገረው ይመስላል፡፡ ኒቆዲሞስ ሆይ እየተናገርሁህ ያለሁት ስለ ሌላ ልደት ነው፡፡ ስለምን ነው ንግግሬን ወደ ምድራዊ ነገር የምታወርደው፡፡ ስለምን የምነግርህ ነገር በተፈጥሮ ሕግ እንዲገዛ ታደርጋለህ? ይህ ትውልድ /ልደት/ በአይነት በሥጋ /በምጥ/ ከሚደረገው ትውልድ የተለየ ነው፡፡ አጠቃላይና የተለመደ ከሆነ ልደት ራስህን አውጣ፤ እኔ ሌላ ልደት ወደሚገኝበት መንፈሳዊ ዓለም ሾሜሃለሁና፡፡ ሰዎች ሁሉ ከዚህ አዲስ ልደት እንዲወለዱ እወዳለሁ፡፡ አዲስ ዓይነት ልደትን ይዤ ወደ ምድር መጥቻለሁ፡፡ ሰውን የፈጠርሁት ከምድር አፈርና ከውኃ ነበር፡፡ ይህ ያገለግለኛል ብዬ የፈጠርሁት ምርጥ ዕቃ የተፈጠረበትን ዓላማ ዘንግቶ አግኝቸዋለሁና እንደገና ከአፈርና ከውኃ ልሠራው አልፈቅድም እንደገና በውኃና በመንፈስ እንዲወለድ እፈቅዳለሁ እንጂ፡፡

ምናልባት ከመካከላችሁ አንዱ እግዚአብሔር ሰውን እንዴት ከውኃ ፈጠረው ብሎ ሊጠይቅ ይችላል፡፡ እኔ መልሼ እጠይቀዋለሁ፡፡ ሰውን እንዴት ከምድር አፈር አበጀው? ጭቃን እንደምን አድርጋችሁ ወደተለያየ ክፍል ትከፋፍሉታላችሁ? አጥንት፣ ነርብ፣ የደም ሥር፣ የደም ቧንቧ ከየት ተሠሩ? ቆዳ፣ ደም፣ ጉበት ከየት ተሠሩ? ይህ ታላቅ ሥራ ለምን የተከናወነ ይመስላችኋል? የተለያየውስ ቀለም? እነዚህ ሁሉ አይነቶች ውሁዶች ከየት ተገኙ? እነዚህ ሁሉ ነገሮች የምድርም የጭቃም አካል አይደሉምና፡፡

ምድር ዘርን ስትቀበል እንዴት አድርገው ሥር ይሰድዳሉ? ነገር ግን በእኛ አካል ውስጥ ሲሆኑ እነዚህ ዘሮች ይፈጫሉ፡፡ ምድር ዘርን ምን መግባ ዘር ፍሬ እንዲያፈራ ታደርጋለች? እንደገናስ ሰውነታችን እንዴት በእነዚህ ዘሮች ይገነባል? ምድር ውኃን ትቀበላለች ወደሚያፈራ ወይንም ትቀይረዋለች፡፡ የእኛ ሰውነት ግን ወይንን ተቀብሎ ወደ ውኃ ይቀይረዋል፡፡ በአሳብ የምትሰጠው ፍሬ ሁሉ የእርሷ ውጤት መሆኑን በምን በምን በምን መንገድ ነው የሚለውን ግን ማስረዳት ቀላል ነገር አይደለም፡፡ ምድር በፍሬዋ ሰውነታችንን ታጠግባለች፤ በእግዚአብሔር ላይ ያለኝ እምነት ብቻ ነው እነዚህ ሁሉ ነገሮች የምድር ውጤቶች ናቸው ብዬ እንድቀበል የሚያደርገኝ፡፡

አሁን እነዚህ ሁሉ ዓይነት ተጨባጭ ነገሮች በየቀኑ የሚከሰቱ ስለሆነ እምነት የሚይጠይቁ ስለሆነ መንፈሳዊ የሆነው ጉዳይ በቂ የሆነ ትኩረትና ቅድምና ማግኘት እንደሚኖርበት ትገነዘባላችሁ፡፡ የማይንቀሳቀሰው ምድር ለእግዚአብሔር ፈቃድ መልስ ይሰጣል ምድር የምትሸከመው ይህ ሁሉ ነገር የተገኘው ለዚህ ፈቃድ ነውና፤ በተመሳሳይ ሁኔታ ከመረዳታችን በላይ የሆነ ጽንፍ የያዘ ብዙ ምልክት ይፈጠራል፤ መንፈስ ቅዱስ በውኃ ላይ በኖረ ጊዜ ምን ተከሰተ?

ምናልባት ከመካከላችሁ አንዱ ውኃ ለዚህ ልደት ለምን ያስፈልጋል? ብሎ ቢጠይቀኝ መልሴ የሚሆነው ይህ ልደት አምላካዊ ጠቀሜታ አለው የሚል ነው፡፡ መቃብር፣ መቀበር እምነት፣ ሕይወትና፣ ትንሣኤ እነዚህ ሁሉ ምሥጢራት በጥምቀት ጊዜ የሚከናወኑ ናቸው፡፡ጭንቅላታችንን ውኃ ውስጥ እንነክራለን፤ ወደመቃብር እንደምንወርድ ሁሉ አሮጌውን ሰዋችን እንቀብር ዘንድ ጭንቅላታችንን ስናነሣ አዲሱ ሰው በተመሳሳይ ሁኔታ ይገኛል፡፡

ከመንፈስ የሚወለድ እርሱ ማነው €œእንደሚያታልል ምኞት የሚጠፋውን አሮጌውን ሰው አስወግዶ በአእምሮው መንፈስ ከሚታደስ ሰው በስተቀር€ /ኤፌ.4፡23/ በእርግጥ ይህ ከውኃና ከመንፈስ ቅዱስ እንደገና የተወለደ ሰው ነው፡፡

ይህ በዘላለማዊ ሕይወት የመተማመን ውጤት ነው፡፡ ይህም በጥምቀት አማካኝነት የሚፈጸም ነው፡፡ በእርግጥም እንዲህ ዓይነት ሰው እንደምሕረቱ መጠን በአዲስ ልደት በሚሆነው መታጠብም በመንፈስ ቅዱስ በመታደስ /ቲቶ.3፡5/ መንፈሳዊ ልጅነትን የተቀበለ ነው፡፡ በሌላ ንባብ ቅዱስ ጴጥሮስ እንዲህ ይላል €œበመንፈስ ቅዱስ ስም ትጠመቃላችሁ€ /ሥራ.11፡16/፡፡ ከውኃና ከመንፈስ ከተወለደ ወገን ውጭ በመንፈስ ቅዱስ የተጠመቀ ማነው? እውነት እውነት እላችኋለሁ ከውኃና ከመንፈስ ከተወለደ ወገን ውጭ በመንፈስ ቅድስ የተጠመቀ ማነው? እውነት እውነት እላችኋለሁ ከውኃና ከመንፈስ ካልተወለዳችሁ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት መግባት አይቻላችሁም፡፡

የሐዋርያት ሥራ መጽሐፍ በተጠመቀ ሰው ላይ ያደረ መንፈስ ቅዱስ የሚናገረውን ምስጢር ይናገራል፡፡ ጥምቀት €œለአዲስ ልደት የሚሆን መታጠብ /ቲቶ.3፡5/ ተብሏል በመንፈስ ቅዱስ የሚሆን መታደስ ነው፡፡

በምስጢረ ጥምቀት የኀጢአት እሥራት ይፈታል ስለዚህ ምክንያት ሕፃናት ሳይቀሩ ይጠመቃሉ፡፡€

€œሰው ከውኃና ከመንፈስ ካልተወለደ በስተቀር ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ይገባ ዘንድ አይቻለውምና፡፡

ጥምቀት ኀጢአታችን ሁሉ ያጥባል፡፡ ለእግዚአብሔር የተቀደሰ መቅደስ እንድንሆን ያደርገናል፡፡ ሰማያዊ ተፈጥሮአችንን ያድሳል ይህም በመንፈስ ቅዱስ ግብር የሚፈጸም ነው፡፡

በቅዱስ ጥምቀት ሰው ከሰይጣን ኀይል ነጻ ይሆናል፤ እንደ አርባ ቀን ሕፃንም ይሆናል፡፡ ይህም በመንፈስ ቅዱስ የሚከናወን ነው፡፡ የተጠመቀውን ሰው የሚቀድስና የሚያነጻ መንፈስ ነው፡፡ በእንደዚህ ዓይነት ሰው ላይ ሰይጣን የወደደውን ያደርግበት ዘንድ አቅሙ አይኖረውም፡፡

ሰው በጥምቀት ከክርስቶስ ጋር አንድነትን ሲፈጥር እንደገና ከመወለዱ ባሻገር ክርስቶስን በሁለንተናው ይለብሰዋል /ገላ.3፡27/ ይህን በንባብ ብቻ የምንረዳው አይደለም፡፡የፍቅር መግለጫ ነውና፡፡ይህንን የምንረዳው ጌታ ሥጋችንን ተዋሕዶ በእኛ መጠን መወለዱና ስለእኛም ሲል ለአብነት በመወለዱ ነው፡፡