ታቦት

እህተ ፍሬስብሐት

 ልጆች ታቦት ምን እንደሆነ ታውቃላችሁ?

ልጆች ታቦት ማለት የእግዚአብሔር ትዕዛዝ የተፃፈበት ቅዱስ ሰሌዳ ማለት ነው፡፡ በመጀመሪያ ታቦትን ከእግዚአብሔር እጅ የተቀበለው ሙሴ ነበር።

እስራኤላውያን በግብፅ በስደት ከኖሩ በኋላ በሙሴ መሪነት ወደ ሀገራቸው ወደ እስራኤል ጉዞ ጀመሩ፡፡ ብዙ ቀናቶችን ከተጓዙ በኋላ እረፍት አድርገው እግዚአብሔር ሙሴን ሲና  ወደተባለው ተራራ እንዲወጣ አዘው፡፡ ሙሴም ወንድሙ አሮን ህዝቡን እንዲጠብቅ አድርጎ ወደ ተራራው ወጣ፡፡ በተራራውም ላይ 40 ቀንና 40 ሌሊት ከፆመ በኋላ ከእግዚአብሔር እጅ ሁለቱን ታቦቶች ተቀበለ፡፡ በታቦቱ ላይም አስር የእግዚአብሔር ትዕዛዞች ተፅፈውበታል፡፡ እግዚአብሔር ታቦትን የሰጠበት ምክንያት ሌሎች ህዝቦች ጣኦትን ያመልኩ ስለነበር እስራኤላውያን ግን እግዚአብሔርን ስለሚያምኑ ሌሎች ህዝቦችን አይተው ጣኦት እንዳያመልኩ የእግዚአብሔር መንፈስ ያለበትን ታቦት እንዲያመልኩ ታቦትን ለሙሴ ሰጠው፡፡

ሙሴ ከሲና ተራራ ታቦታቱን ይዞ እስከሚመለስ እስራኤላውያኑ 40 ቀን መታገስ አቅቷቸው አሮንን አስገድደው ጣዖት ሠርተው ሲሰግዱ አገኛቸው። በዚህ ጊዜ ሙሴ ህዝቡ እግዚአብሔርን ትተው ጣኦትን በማምለካቸው በጣም ስለተናደደ ታቦቶቹን በጣኦቱ ላይ ጣላቸው እና ታቦቱም ጣኦቱም ተሰባበሩ፡፡ ሙሴ ታቦቶች በመሰባበራቸው በጣም አዘነ፡፡ እግዚአብሔርም የሙሴን ማዘን ተመልክቶ “የሰበርካቸውን አስመስለህ አንተ ራስህ ስራ እኔም እባርክልሃሁ” አለው፡፡ ሙሴም እንደታዘዘው ቅርፁን ከሰራ በኋላ እግዚአብሔርም እንደገና አስሩ ትዕዛዞችን በጣቶቹ ፃፈበት እና ባረከለት፡፡

ልጆች በሌላ ቀን ደግሞ የእግዚአብሔር አስሩ ትዕዛዞች ምን እንደሆነ እንነግራቹሀለን፡፡