ተረት…………ተረት (ለህጻናት)

      ልጆች ዛሬ አንድ ተረት ይዤላችሁ ቀርቤአለሁ፡፡ አንድ ጊዜ ምን ሆነ መሰላችሁ ፀሐይና ነፋስ ረጅም መንገድ አብረው ጉዞ ጀመሩ፡፡ እነዚህ ጓደኛሞች አብረው እየሔዱ ጨዋታ አንስተው ሲያወሩ ነፋስ ፀሐይን አንድ ጥያቄ ጠየቃት «ሰዎች የምትፈልጊውን ነገር እንዲያደርጉልሽ የምታደርጊያቸው በምንድን ነው?» ሲል ነፋስ ጠየቃት ፀሐይም የነፋስን ጥያቄ ሰማችና «እኔማ ከሰዎች የምፈልገውን መጠየቅ ብፈልግ በጣም ቢቆጡ፣ ቢሳደቡ እንኳን ቀስ አድርጌ በትህትና በፍቅር ረጋ ብዬ እጠብቃቸውና የምፈልገውን እንዲሰጡኝ /እንዲያደርጉልኝ/ አደርጋለሁ» አለችው፡፡ ነፋስ ወዲያውኑ ቀበል አደረገና «በጣም ተሳሳትሽ የምን መለማመጥ? የምትፈልጊውን ለማግኘት በጉልበት መጠቀም ነው እንጂ» አለ፡፡ «ፀሐይ እንደሱማ አይቻልም» አለች፡፡

                    

      ነፋስም እኔ እችላለሁ ተመልከች «ያ» መንገድ ላይ የሚጓዘውን ሰውዬ በደቂቃ ውስጥ ልብሱን በየተራ ብትንትን አድርጌ አስወልቀዋለሁ» ሲል ፎከረ፡፡ ነፋስም በአንዴ ኃይሉን አነሣና የሰውየውን ልብስ ለማስወለቅ መታገል ጀመረ፡፡ ይኼኔ ሰውየው ልብሱን እንዳይወስድበት በኃይል ልብሱን ጭብጥ አድርጎ አስጣለ /አዳነ/፡፡ ነፋስም ሰውየው ስላሸነፈው ተናደደና አዋራ አስነሥቶ ሰውየው ዐይን ላይ በትኖበት ጥሎት ሔደ፡፡ ፀሐይም በመገረም እየተመለተችው እሺ አያ ንፋስ አሸንፈህ የፈለከውን አገኘህ)» ብላ ጠየቀችው ነፋስም «ይገርምሻል ልብሱን አልለቅም ሲለኝ አዋራ አንሥቼ ዐይኑ ላይ ጨመርኩበት» አላት፡፡

      ፀሐይ ሳቅ እያለች «አይ አያ ነፋስ፡፡ በትግል አልሆን ሲልህ በጉልበት ለመጠቀም ሞከርክ? ግን እንደዚህ አይደለም እኔን አስተውለህ ተመልከተኝ» አለችውና ልታሳየው ወደ ሰውየው ሔደች፡፡

      ሰፊ ከሆነው ከሰማይ መቀመጫዋ ብድግ አለችና ሰውየውን ገና ጠዋት ከሚመጣው ሙቀቷ ሰላምታ አቀረበችለት ሰውየውም የፀሐይን ሙሉ ፈገግታና ትህትና በጣም ደስ አሰኝቶት ከሙቀቷ ስር ቁጭ አለ፡፡ እንደገና ከሰዓት በኋላ መንገድ ሲሔድ ሰላም አለችውና ከሙቀቱ ጭምር አደረገች፡፡ «በጣም ስለሞቀህ ለምን ኮትህን አታወልቅም?» ስትል ጠየቀችው ደስ ብሎት ምንም ሳይከፋው ፈጠን ብሎ «እሺ» አለና ውልቅ አድርጎ ያዘው፣ አሁንም ሙቀቷን ጨመረችና «ሸሚዙን ብታወልቀው» አለችው አወለቀው ሙቀቷ በጣም እየጨመረ መጣ፡፡ «ለምን በቀዝቃዛ ውኃ አትታጠብም ስትል ቀስ አድርጋ ጠየቀችው በጣም ደስ ይለኛል አለና ሰውነቱን በቀዝቃዛ ውኃ አስነከረችው፡፡»

      ይሔኔ ነፋስ በጣም ደነቀው፡፡ በራሱ ኃይለኝነት በጣም አፈረ፡፡ ሰዎች ነፋስን ብርድ በመጣ ቁጥር የበለጠ እየፈሩት ወደ ሙቀት እንደሚሸሹት አወቀ፡፡ ፀሐይ ግን በትህትና በፍቅር ሰዎችን ስለምትቀርብ ወደ ቅዝቃዜ ብትወስዳቸው እንኳን ቅር አይላቸውም፡፡ በደስታ እንደሚከተሏት ተመለከተ፡፡ የፀሐይን ጥሩ ፀባይ በጣም አደነቀ፡፡

       አዎን ልጆች ከሰፈር አብሮ አደጎቻችሁ ከትምህርት ቤት ጓደኞቻችሁ እንዲሁም ከወላጆቻችሁ ጋር አብራችሁ ስትኖሩ የምትፈልጉትን ለማግኘት በመሳደብ፣ በኃይል፣ በመማታት አይደለም፡፡ ነፋስን አይታችኋል አይደል? ክፉና ኃይለኛ መሆን ሰዎች እንዲርቁን እንዲጠሉን አዋቂዎችም እንዲረግሙን ያደርገናል፡፡ እና ልጆች ልክ እንደ ፀሐይ ጥሩና ደግ ትሁትና ታዛዥ ሆናችሁ ሰዎትን ብትቀርቡ ሁሉም ይወዳችኋል፣ ይመርቃችኋል፡፡ እሺ ልጆች? ደኅና ሁኑ ልጆች ደኅና ሁኑ፡፡