ብስራት

እመቤት ፈለገ

በመጋቢት 29 ቀን እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በቤተመቅደስ ውስጥ ሆና ስትጸልይ በጣም የሚንፀባርቅ ታላቅ ብርሃን ሆነ፤ ወዲያው እጅግ የሚያምር ስሙም ገብርኤል የተባለ መልአክ አየች፤ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤልም በማመስገን ሰላምታ አቀረበላትና ‹‹ከሴቶች የተለየሽ ጸጋን የተመላሽ ደስተኛይቱ ሆይ እግዚአብሔር ካንቺ ጋር ነውና ደስ ይበልሽ›› አላት፡፡

 

እመቤታችን ድንግል ማርያምም ከንግግሩ የተነሳ ደነገጠችና ‹‹እንዴት እንዲህ ባለ ቃል ታመሰግነኛለህ›› አለችው፡፡ ቅዱስ ገብርኤልም ደስ በሚያሰኝ ቃል እመቤታችንን አረጋጋትና ‹‹እነሆ ታላቅ ልጅ ትወልጃለሽ ስሙንም ኢየሱስ ትይዋለሽ እርሱም የእግዚአብሔር ልጅ ይባላል›› አላት፡፡ እመቤታችንም ‹‹ይህ ነገር እንዴት ሊሆን ይችላል›› አለችው፡፡ መልአኩም ‹‹እግዚአብሔር ማድረግ የማይችለው ምንም ነገር የለም፤ ዘመድሽ ኤልሳቤጥ እንኳን ካረጀች የመውለጃዋ ጊዜ ካለፈ በኋላ ጸነሰች፤ እንዲያውም ከጸነሰች ስድስት ወር ሆኖቷል፤ ስለዚህ አንቺም በድንግልና ትጸንሻለሽ፡፡›› አላት፡፡ እመቤታችንም ‹‹እኔ የእግዚአብሔር አገልጋይ ነኝ ፤ እግዚአብሔር ያዘዘኝን ሁሉ አደርጋለሁ፡፡ እንደ ቃልህ ይደረግልኝ›› አለችው ስለዚህም እመቤታችን የአምላክ እናት ሆነች፡፡