በበልበሊት ኢየሱስ ገዳም ዙርያ የተነሣው የእሳት ቃጠሎ ጠፋ

የምዕራፈ ቅዱሳን በልበሊት ኢየሱስ ገዳም ሕንጻ ቤተ ክርስቲያን

በዝግጅት ክፍሉ

መጋቢት ፲፱ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

በሰሜን ሸዋ ሀገረ ስብከት በእንሳሮ ወረዳ ቤተ ክህነት በምዕራፈ ቅዱሳን በልበሊት ኢየሱስ አንድነት ገዳም ዙርያ የተነሣው የእሳት ቃጠሎ መጥፋቱን የገዳሙ አበምኔት ገለጹ፡፡

መጋቢት ፲፰ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ከምሽቱ ፲፩ ሰዓት ገደማ በግልጽ ባልታወቀ ምክንያት የተነሣው ይህ የእሳት ቃጠሎ በገዳሙ መነኮሳት፣ በአካባቢው ሕዝበ ክርስቲያን እና በወረዳው የመንግሥት አካላት ጥረት ከሌሊቱ ፭ ሰዓት ገደማ ጠፍቷል፡፡

01

የአካባቢው መልክዐ ምድር

ቃጠሎው በቤተ ክርስቲያኑ ላይ ምንም ዓይነት ጉዳት ባያደርስም በግምት አምስት ሄክታር የደን ሽፋንና ሦስት ሄክታር የአትክልት ቦታ በድምሩ ስምንት ሄክታር የሚኾነውን የገዳሙ መነኮሳት ያለሙትን የገዳሙን ይዞታ ማውደሙን የገዳሙ አበምኔት በኵረ ትጉሃን ቆሞስ አባ ሐረገ ወይን አድማሱ አስታውቀዋል፡፡

ከሥፍራው ያገኘነው መረጃ እንደሚያመለክተው የሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ፣ በማኅበረ ቅዱሳን የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል አገልጋዮች መጋቢት ፲፱ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም በገዳሙ ተገኝተው ማኅበረ መነኮሳቱን ያጽናኑ ሲኾን፣ ማኅበረ መነኮሳቱም ተረጋግተው ወደ ቀደመ የጸሎት ተግባራቸው ተመልሰዋል፡፡

?

ገዳሙ ከሁለት መቶ አምሳ በላይ መነኮሳት እና መነኮሳይያት፤ እንደዚሁም ወደ ሁለት መቶ የሚደርሱ የቅኔ፣ የድጓ እና የቅዳሴ ደቀ መዛሙርት የሚገኙበት ሲኾን፣ ገዳሙ የሚተዳደርበት በቂ ገቢ የሌለው ከመኾኑ ባሻገር የአብነት ተማሪዎቹም በመጠለያ እና በምግብ እጥረት ምክንያት ትምህርታቸውን በአግባቡ ለመከታተል ተቸግረዋል፡፡ ‹‹ስለዚህም የገዳሙን ህልውና ለመጠበቅ እና የአብነት ተማሪዎችን ከስደት ለመታደግ መላው ሕዝበ ክርስቲያን ድጋፋችሁ አይለየን›› ሲሉ የገዳሙ አበምኔት በገዳሙና በማኅበረ መነኮሳቱ ስም ጥሪያቸውን አቅርበዋል፡፡

02

ቃጠሎው ያደረሰው ጉዳት በከፊል

ምዕራፈ ቅዱሳን በልበሊት ኢየሱስ አንድነት ገዳም መልክዐ ምድራዊ አቀማመጡ ለጎርፍ አደጋ ተጋላጭ በመኾኑ በየጊዜው በግምት ስድሳ ሄክታር የሚደርስ የገዳሙ ይዞታ በጎርፍ መወሰዱን፤ በአሁኑ ሰዓትም በክልሉ መንግሥት በጀት በገዳሙ ዙርያ የአፈር ጥበቃ ሥራ እየተከናወነ መኾኑን ከገዳሙ ጽ/ቤት ለመረዳት ተችሏል፡፡

መረጃውን ያደረሰን በማኅበረ ቅዱሳን የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል ነው፡፡

የተወደዳችሁ ምእመናን! በየጊዜው በገዳሞቻችን ላይ የሚደርሰውን የእሳት ቃጠሎ እና መሰል አደጋ ከፍተኛ ጉዳት ከማድረሱ በፊት ዅላችንም ተግተን፣ ነቅተን ቤተ ክርስቲያናችንን እንጠብቅ ስንል መልእክታችንን እናስተላልፋለን፡፡

እርማት

በዚህ ዜና ሦስተኛው አንቀጽ ላይ ‹… ስምንት ሺሕ ሄክታር …› በሚል የተገለጸው በስሕተት ስለ ኾነ ስምንት ሄክታር› ተብሎ መስተካከሉን ከይቅርታ ጋር ለማስገንዘብ እንወዳለን፡፡