በሕይወት ያለ ማስታወሻ ለገና ሥጦታ

የዘመነ ማቴዎስ 4ኛ ወር የመጨረሻውን ቀን በሚመስጥ የሕይወት ትምህርት በመማር አሳለፍኩት፡፡ ጠዋት ከጓደኛዬ ጋር ቁርስ አድርገን እርሱ ሊወስደኝ ካሰበው ሥጦታ መስጫ ቦታ ሄድን፡፡ይህ የስጦታ መለዋወጫ ቦታ ለእነርሱ ልማድ ነው፡፡ በዓል በመጣ ቁጥር የሚሄድበት የውዴታ ግዴታ የሆነበት ልማድ በእርግጥ ሲጀምረው ጥልቅ ደስታና እርካታ የተሞላ ነበር።

እኔ ከጉዟችን መልስ በድርጊቱ ተደምሜያለሁ፣ እርሱ በዓመት ሦስቴ ለበዓላት በመሄድ ገንዘብ ያደረገው ልማድ!! ይህ የልደት በዓል በጠዋቱ መልካም የሕይወት ተሞክሮ እያስተማረኝ እንደሆነ መረዳቴ የዘመኑን መልካም ጅማሮ እንድወደው አስገደደኝ ገና ሦስት ሩብ ዓመታት ይቀራሉና!!

‹ታምሜ ጠይቃችሁኛል?…… ተርቤ አብልታችሁኛል?› የሚሉት የክርስቶስ የወንጌል ቃላት ለእርሱ የሕይወት ልምምድ መሠረቶች ነበሩ፡፡ እንዴት ልፈጽመው ከሚል በጎ መሻት የመነጨ ልምድ፣ እናም ወሮታ የማይከፈልበት ብድር ከማይመለስበት፣ ይሉኝታ ከሌለበት፣ ከሥጋዊ የራስ ጥቅም አድልዎ የነጻ ዕረፍት፣ ጥልቅ ደስታና የሕይወት እርካታ ያገኝ ዘንድ በበዓላት በሆስፒታል የተኙ ህመምተኞችን ቤት ያፈራውን በመያዝ ‹እንኳን አደረሳችሁ…..እግዚአብሔር ከእናንተ ጋር ይሁን፤ እግዚአብሔር ይማራችሁ! በማለት ይጠይቃቸዋል፡፡ ከቤተሐኪም ገብቶ የሚጠይቃቸው፣ የሚያጫውታቸውና የሚያጐርሳቸው በአጠገባቸው አስታማሚ(ጠያቂ) የሌላቸውን ብቸኛ ህመምተኞች ናቸው፡፡ ይደርስላቸዋል፣ ከጐናቸው!!

አዎ! ማንም ህመምተኛ ድኖ ሲነሣ ውለታ ለመክፈል አይጨነቅም በውለታ አልታሰረምና፡፡ አያውቃቸውም አያውቁትም ቀድሞ እንዲሁ ነበር ዛሬም እንደዛው ወደፊትም እንዲያው ሊሆን ይችላል፡፡ እናም የማያውቁትን በመጠየቃቸው ብድር የማይመልሱትን እርሱም ለነገ ብድራት የማያስቀምጠውን ግን ህመምተኛ ጠያቂን ፈላጊ የሆነን ሰው እንደው ደርሶ ‹እንኳን አደረሰህ› ብሎ የፈጣሪን ምሕረት ለምኖ መጽናናትን መፍጠር እርግጥ ምን ያህል ዋጋ ያለው ደስታ ይኖረው ይሆን… ወዘተርፈ፡፡

የዓውደ ዓመት በዓል ይሄን ያህል ደስታ ይፈጥር ይሆንን? እርግጥ በቤተሰብ መሀል ለሚኖር ሰው ደስታው፣ ጨዋታው፣ ሁካታው፣ መጠያየቁ፣ መልካም ምኞቱ ደስታ ሊፈጥሩ ይተጋገዙለት ይሆናል ይሄን ቢጨምርበት ግን ደስታው ሊያገኘው ከሚታገለው እጥፍ ሲበዛለት ሲበረክትለት ወደ እርካታ ሲመራው በሕይወቱ ሊማር እንደሚችል አምናለሁ፡፡ ምናልባትም የምንጠይቀው አንዱ ህመምተኛ የሕይወትን ቃል ሊያሰማን ምክንያት ቢሆንስ? ኑ እንውረድ በዓርአያችን እንደምሳሌያችን ሰውን እንፍጠር ያለው ለዚህ ይሆን እንዴ?!
ይህ ነው የገና ሥጦታ የተሰጠኝ፣ የሕይወት ትምህርታዊ ገጸ በረከት! ማስተዋሉን ላደለው መልካም ትምህርት ነበር ግሩም!!

/ በዕለት ውሎ መመዝገቢዬ ለጽሑፍ በሚሆን መልክ የተቀዳ
በኤርምያስ ትዕዛዝ  ዘሐብታም
መስከረም 1 2001 ዓ.ም /