ቅዱስ ጳውሎስ(ለሕፃናት)

ግንቦት 23 2003 ዓ.

በእመቤት ፈለገ

እንደምን ሰነበታችሁ ልጆች? ደህና ናችሁ? ዛሬ ስለ አንድ ትልቅ የቤተ ክርስቲያን ሐዋርያ ታሪክ እንነግራችኋለን በደንብ ተከታተሉን፡፡
 
በድሮ ጊዜ በኢየሩሳሌም ከተማ የሚኖር ክርስቲያኖችን የሚጠላና በእነርሱ ላይ ክፉ ሥራ የሚሠራ ሳውል የሚባል ሰው ነበረ፡፡ ደማስቆ ወደምትባል ከተማም ክርስቲያኖችን ሊገድል ጉዞ ጀመረ፡፡
 
ደማስቆ ለመድረስ ጥቂት ሲቀረው ብርሃን በዙሪያው አንጸባረቀበት እርሱም በምድር ላይ ወደቀ በዚያን ጊዜ “ሳውል ሳውል ለምን ታሳድደኛለህ?” የሚል ድምጽ ሰማ፡፡ ሳውልም “አቤቱ አንተ ማን ነህ?” አለው፡፡ እርሱም “አንተ የምታሳድደኛ የናዝሬቱ ኢየሱስ ነኝ፡፡” አለው ፡፡ልጆች ሳውል የሚያሳድደው ክርስቲያኖችን ሆኖ ሳለ ጌታችን ለምን እኔን ታሳድደኛለህ ብሎ ጠየቀው? ምክንያቱ ምን እንደሆነ ታውቃላችሁ? ቤተ ክርስቲያንን እና ክርስቲያኖችን መጥላት ወይም በእነርሱ ላይ ክፉ ነገር ማድረግ ማለት በአምላካችን ላይ ክፉ ነገር ማድረግ ማለት ስለሆነ ነው፡፡
 

ሳውል ከወደቀበት ተነሥቶ ዐይኑን ሲገልጥ ምንም ነገር ማየት አልቻለም ስለዚህ ሰዎች እጁን ይዘው እየመሩ ወደ ደማስቆ አስገቡት “ሦስት ቀንም ዐይኑ ማየት አልቻለም፤ አልተመገበም፡፡ በደማስቆ ሐናንያ የሚባል አንድ ደቀመዝሙር ነበር፤ ጌታችንም ለሐናንያ ተገልጦ ሳውል የሚባል ሰው ይሁዳ በሚባል ሰው ቤት እየጸለየ ነው አግኘው አለው፡፡ ሐናንያም እጅግ በጣም ፈራ፡፡ ለጌታችንም “ይህ ሰው በክርስቲያኖች ላይ ምን ያህል ክፉ ነገር እንዳደረገ ሰምቻለሁ፡፡ ወደዚህም የመጣው ይህን ሊያደርግ ነው” አለው፡፡ ጌታችንም እንዲህ አለው “ሂድ ይህ ሰው ከዛሬ ጀምሮ ማንንም ክርስቲያን አይጎዳም ይልቁንም ሰዎችን የሚያስተምር ትልቅ አባት ይሆናል” አለው፡፡ ሐናንያም ወደተባለው ቤት ገባ፤ በሳውል ላይም እጁን ጭኖ “ወንድሜ ሳውል ሆይ በመንገድ ላይ የተገለጠልህ ኢየሱስ ክርስቶስ ዐይንህ እንዲበራና በመንፈስ ቅዱስ እንድትሞላ እኔን ልኮኛል” አለው፡፡ ሳውልም ማየት ቻለ፤ ተነሥቶም ተጠመቀ፤ ምግብም በላ፡፡
 
ጌታችን ሳውል እንዲድን ብዙ ነገር አዘጋጀለት ሐናንያን ላከለት ደግሞም ማየት እንዲችል አደረገው፡፡ የሠራውን ሁሉ ይቅር ብሎት ክርስቲያን አደረገው፡፡ በኋላም ሳውል ትልቅ ሐዋርያ ሆኖ ቅዱስ ጳውሎስ ተባለ፡፡ 


ወስብሐት ለእግዚአብሔር