ስለ እመቤታችን ቤተመቅደስ መግባት

እህተ ፍሬስብሃት

 

ኢያቄምና ሐና የሚባሉ በተቀደሰ ትዳር የሚኖሩ የእግዚአብሔር ሰዎች ነበሩ፡፡ ሁለቱም እግዚአብሔርን የሚወዱ ደግ ሰዎች ነበሩ፡፡ ነገር ግን ሐና ልጅ መውለድ አትችልም ነበር፡፡ ልጅም ስለሌላቸው በጣም አዝነው ይኖሩ ነበር፡፡ ሁልጊዜ ወደ ቤተ እግዚአብሔር እየሄዱ ልጅ እንዲሰጣቸው ልመና ያቀርቡ ነበር፡፡ ለእግዚአብሔርም ልጅ ከሰጠኸን ለአንተ ብጽአት (ስጦታ) አድርገን እንሰጣለን ብለው ተሳሉ፡፡

 

እግዚአብሔርም ልጅ ሰጣቸው፡፡ ሐናም በግንቦት አንድ ቀን ከፀሐይ የምታበራ ሴት ልጅ ወለደች፡፡ ሕፃኗንም ማርያም ብለው ስም አወጡላት፡፡ ልጃቸው እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን በንጽህና ሲያሳድጉ 3 ዓመት ከሆናት በኋላ በተሳሉት ስእለት መሠረት ወደ ቤተ እግዚአብሔር መውሰድ እንዳለባቸው ተነጋገሩ፡፡ ለመንገድ የሚሆን ስንቅና ለቤተ እግዚአብሔር የሚሆን ስጦታ ሁሉ አዘጋጁ፡፡ 
 

ከዚያም ልጃቸውን ድንግል ማርያምን ይዘው ወደ ቤተመቅደስ ሄዱ፡፡በቤተ መቅደስ የካህናት አለቃ የነበረው ካህኑ ዘካርያስ ተቀበላቸው፡፡ሐና እና ኢያቄም ለእግዚአብሔር የገቡትን ቃል የተደረገላቸውንም ድንቅ ተአምር ነገሩት፡፡
 
ካህኑ ዘካርያስም ለእግዚአብሔር የገቡትን ቃል ባለመርሳታቸው እጅግ ተደሰተ፡፡ ነገር ግን ወዲያው አንድ ነገር አሳሰበው፡፡ምን መሰላችሁ ልጆች እመቤታችንን በዚያ በቤተመቅደስ ስትኖር ማን ይመግባታል ብሎ ነበር የተጨነቀው፡፡ 
 
ወዲያው ከሰማይ ቅዱስ ፋኑኤለ የተባለው መልአክ መጣ መልአኩ እመቤታችን አቅፎ በአንድ ክንፉ ከልሎአት ከሰማይ ያመጣውን ኅብስት እና መጠጥ መግቦአት እንደመጣው ሁሉ ወደ ሰማይ አረገ፡፡ካህኑ ዘካርያስና ህዝቡም እግዚአብሔር ምግቧን እና መጠጧን እንዳዘጋጀላት ተመለከቱ፡፡ካህኑ ዘካርያስ በፍፁም ደስታ እመቤታችንን ተቀብሎ ወደ ቤተ መቅደስ አሥገባት ይህ ዕለት ታኅሳስ 3 ቀን ሲሆን በዓታ ለማርያም ተብሎ በታላቅ ድምቀት ይከበራል፡፡

 

ልጆች እኛም በዓሉን በማክበር ከእመቤታችን በረከትን ማግኘት አለብን፡፡