Silestu Dekik.jpg

ሠለስቱ ደቂቅ

በአዜብ ገብሩ
እንደምን ሰነበታችሁ ልጆች?ደህና ናችሁ ልጆች? ዛሬ ስለ ሦስቱ ህጻናት ታሪክ እንነግራችኋለሁን በደንብ ተከታተሉን እሺ፡፡
 

በአንድ ወቅት በባቢሎን ከተማ የሚኖር ናቡከደነፆር የሚባል ንጉሥ ነበር፡፡ይህም ንጉሥ ከወርቅ የተሰራ ትልቅ ጣኦት አሠርቶ አቆመ፡፡ ሕዝቡንም ሁሉ ሰበሰበና ለጣኦቱ እንዲሰግዱ አዘዘ፡፡ ለጣኦት ያልሰገደ ግን በእሳት ውስጥ ይጣላል ብሎ አዋጅ አስነገረ፡፡

Silestu Dekik.jpg
 
ከሕዝቡም መካከል ሚሳቅ፤ሲድራቅ እና አብደናጎም የተባሉት ህፃናት ግን ለጣኦቱ አንሰግድም አሉ፡፡ምክንያቱም እግዚአብሔርን ስለሚወዱ ለእርሱ ስለሚገዙ ነው፡፡ንጉሡ እነዚህን ህጻናት ለጣኦቱ አንሰግድም በማለታቸው በጣም ተቆጣ፡፡ካልሰገዱም ወደ እሳት እንደሚጣሉ ነገራቸው፡፡ህጻናቱም የሚያመልኩት አምላክ በሰማይ እንዳለና እርሱም ከእሳቱ እንደሚያድናቸው ነገሩት፡፡እንዲህም ሲሉ ወደ እግዚአብሔር ጸለዩ ‹‹አንተ ከእኛ ጋር ነህና ክፉውን አንፈራም››። ንጉሡም በመለሱለት መልስ ይበልጥ ተቆጣ፡፡ እሳቱንም ይነድ ከነበርው ሰባት እጥፍ እንዲያነዱትና ወደ እሳቱ ውስጥ እንዲጥሏቸው አዘዘ፡፡
ሲድራቅ ሚሳቅና አብደናጎም ግን እሳቱ አላቃጠላቸውም ነበር፡፡ በእሳት ውስጥ ሆነው እግዚአሔርን በመዝሙር እያመሰግኑ ነበር፡፡ከእነርሱም ጋር ሌላ አራተኛ ሰው ይታይ ነበር፡፡ እርሱም ከእሳቱ ሊያድናቸው  ከእግዚአብሔር ዘንድ የተላከው መልአክ  ቅዱስ ገብርኤል ነበር፡፡ በእሳቱ ውስጥ ሆነው መዝሙር ሲዘምሩ ንጉሡ በጣም ተገረመ ከእሳቱ እንዲያወጧቸው አዘዘ። ከፀጉራቸው አንዲቷ እንኳን ሳትቃጠል በሰላም ከእሳቱ ወጡ፡፡ንጉሡም ባየው ተዓምር ተደንቆ የእነርሱን አምላክ አመለከ በፊታቸውም ለእግዚአብሔር ሰገደ።
አያችሁ ልጆች እነዚህ ሦስቱ ህጻናት  ጎበዞች ናቸው፤ አምላካቸው እንደሚያድናቸው በሁሉም ቦታ ቢሄዱ ከእነርሱ ጋር እንደሆነ ስለሚያምኑ እሳቱን አልፈሩም፡፡እግዚአባሔርም ስለእምነታቸው እሳቱን አቀዘቀዘው፡፡በሰላም ከእሳቱም አወጣቸው፡፡