ማኅበረ ቅዱሳን መደበኛ የቴሌቭዥን መርሐ ግብሩን ሊቀጥል ነው

ነሐሴ ፲፪ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ማኅበረ ቅዱሳን መደበኛ የቴሌቭዥን መርሐ ግብሩን ከመስከረም ፩ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም ጀምሮ በልዩ ልዩ ቋንቋዎች ሊቀጥል ነው፡፡

በአሌፍ የቴሌቭዥን ጣቢያ በአዲስ ዓመት ልዩ ዝግጅት የሚጀምረው የማኅበሩ መንፈሳዊ የቴሌቭዥን መርሐ ግብር በአማርኛ፣ በአፋን ኦሮሞ እና በትግርኛ ቋንቋዎች የሚቀርብ ሲኾን፣ ሥርጭቱም ለጊዜው በየቀኑ ለሁለት ሰዓታት እንደሚተላለፍ የማኅበረ ቅዱሳን ጽ/ቤት አስታውቋል፡፡

ማኅበሩ ካሁን በፊት በኢቢኤስ የቴሌቭዥን ጣቢያ በሳምንት ለአንድ ሰዓት በአማርኛ ቋንቋ ሲያስተላልፍ የነበረው መንፈሳዊ መርሐ ግብር በልዩ ልዩ ምክንያት ከተቋረጠ በኋላ በየሳምንቱ ለሁለት ሰዓታት በኢንተርኔት ቴሌቭዥን በሚያሠራጫቸው መንፈሳዊ ዝግጅቶቹ ለሕዝበ ክርስቲያኑ ትምህርተ ወንጌል ሲያቀርብ ቆይቷል፡፡

ከዚሁ ዅሉ ጋርም የኦቢኤስ ቴሌቭዥን ጣቢያ ሥራ እስካቆመበት ጊዜ ድረስ በሳምንት ለሠላሳ ደቂቃ በአፋን ኦሮሞ ቃለ እግዚአብሔር ሲያስተምር መቆየቱ የሚታወስ ነው፡፡

በእግዚአብሔር መልካም ፈቃድ አገልግሎቱን ይበልጥ በማስፋት በመጪው አዲስ ዓመት በሚያስተላልፈው መንፈሳዊ የቴሌቭዥን ሥርጭቱም ኦርቶዶክሳዊውን አስተምህሮ ለሕዝበ ክርስቲያኑ ለማዳረስ ዝግጅቱን አጠናቋል፡፡

የቴሌቭዥን መርሐ ግብሩንም ከመስከረም ፩ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም ጀምሮ በሚከተለው የሥርጭት አድራሻ መከታተል የምትችሉ መኾኑን ማኅበሩ ያሳስባል፤

Aleph Television Nilesat (E8WB)

Frequency: 11595

Polarization: Vertical

Symbol Rate: 27500

FEC: 3/4