‹‹… መስቀል የገደለውን ጥል እንደ ገና እንዳናመጣው በእጅጉ መጠንቀቅ ያስፈልጋል፡፡›› ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ

መስከረም ፲፰ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

abun
የመስቀል ደመራ በዓል ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ፣ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ በጠቅላይ ቤተ ክህነት የየመምሪያ ሓላፊዎች፣ የአድባራትና ገዳማት አስተዳዳሪዎች፣ ካህናትና ሰባክያነ ወንጌል፣ የሰንበት ት/ቤትና የማኅበራት አባላት፣ በብዙ ሺሕ የሚቈጠሩ ምእመናን፣ ከፍተኛ የመንግሥት ባለ ሥልጣናትና ከልዩ ልዩ የዓለም ክፍሎች የመጡ ጐብኝዎች በተገኙበት መስከረም ፲፮ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም በአዲስ አበባ ከተማ በመስቀል ዐደባባይ ተከብሯል፡፡

img_5471-2

mezmur

በሥርዓቱ ላይ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት ‹‹ወለጽልዕ ቀተሎ በመስቀሉ፤ ጥልንም በመስቀሉ ገደለው›› /ኤፌ.፪፥፲፮/ በሚል ኃይለ ቃል መነሻነት ቃለ ምዕዳን ሲያስተላልፉ ‹‹መስቀልን ማሰብና ማክበር ሁለት ነገሮችን እንድናስታውስ ያስገድደናል፤ ይኸውም አንደኛ በመስቀል ላይ ተሰቅሎ ያዳነንን ክርስቶስንና ፍቅሩን፤ ሁለተኛ በመስቀል ላይ የተፈጸመው የድኅነታችን መሥዋዕትነትን እንድናስብ ያደርገናል›› ካሉ በኋላ አያይዘውም መስቀል ሰላምን፣ አንድነትን፣ ነጻነትን፣ ዕርቅን የሚሰብክና የሚያስተምር፤ ስለ ድኅነተ ሰብእ የሚመሰክር፤ የእግዚአብሔር የማዳን ዓርማ፣ የድልና የአሸናፊነት ምልክት መኾኑን አስታውሰዋል፡፡

mk-2

 

‹‹የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የመስቀል በዓልን በከፍተኛ ድምቀት የምታከብርበት ዋና ምክንያት የመስቀሉ አስተምህሮ የጥል ግድግዳን የሚያፈርስና መለያየትን የሚንድ፤ በምትኩ ሰላምን፣ አንድነትን፣ ወንድማማችነትን፣ መተሳሰብን፣ መከባበርን፣ መተማመንን፣ መቻቻልን፣ መተጋገዝንና ፍጹም ዘላቂ ፍቅርን በዋናነት የሚያስገኝ በመኾኑ ነው›› ያሉት ቅዱስነታቸው መስቀለ ክርስቶስ ዓለምን በአጠቃላይ ለመስበክ የሚያስችል ምቹ መድረክ ማግኘቱንና በዓለ መስቀል በኢትዮጵያ ስም በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት መመዝገቡን አድንቀው ‹‹ለዚህ ዕድል ያበቃንን እግዚአብሔርን እጅግ አድርገን እናመሰግነዋለን›› ብለዋል፡፡

 

ቅዱስነታቸው በመቀጠልም ‹‹መስቀል ‹የሚያደርጉትን አያውቁምና ይቅር በላቸው› ብሎ ለገዳዮቹ ምሕረትንና ይቅርታን እየለመነ ፍጹም ፍቅርን ይሰብካል፤ መስቀል በንስሐ ለቀረበ በደለኛ ‹ዛሬዉኑ ከእኔ ጋር በገነት ትኖራለህ› እያለ በእግዚአብሔር መንግሥት ውስጥ እንዲኖር ይፈቅዳል፤ መስቀል ለሰው ድኅነት ሲባል ራስን አሳልፎ በመስጠት ፍጹም ድኅነትን ይሰብካል፡፡ ሌሎችንም ለሰው ልጅ ጠቃሚ የኾኑ ነገሮችን ያስተምራል፤ ትምህርቱም በነፍስና በሥጋ ያድናል›› በማለት አስተምረዋል፡፡

tirit

ቅዱስ ፓትርያርኩ በመተጨማሪም ‹‹ዛሬ በአገራችን አልፎ አልፎ የሚከሠተው የጥል መንፈስ ያለበት የሚመስል ክሥተት የመስቀሉን ስብከትና ትምህርት በቅጡ
ካለማዳመጥና ካለማስተዋል የተነሣ እንደ ኾነ መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡ የመስቀልን ምልክት በአካሉ፣ በአንገቱ፣ በግንባሩና በልብሱ የተሸከመ ሰው ወንድሙን አይጠላም፤ መናናቅን አያስተናግድም፡፡ መከፋፈልን፣ መለያየትን፣ መነታረክን፣ መጨቃጨቅንና ራስ ወዳድነትን የመሳሰሉ የዲያብሎስ የጥፋት ሠራዊት መስቀልን ባነገበ ክርስቲያን ዘንድ ቦታ የላቸውም›› ሲሉ አስረድተዋል፡፡

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ በመጨረሻም ‹‹የመስቀሉን ትምህርት ከእኛ አልፎ በዓለሙ ኹሉ ለማዳረስ በምንሮጥበት በአሁኑ ጊዜ የአገራችን ሕዝቦች የመስቀል ትርጕም ሰላምና ፍቅር መኾኑን መረዳት አቅቷቸው በጥላቻ ዓይን የሚተያዩ ከኾነ የማስተማሩን ብቃት ጥያቄ ውስጥ ይከተዋል፤ መስቀል የገደለውንም ጥል እንደ ገና ስበንና ጎትተን እንዳናመጣው በእጅጉ መጠንቀቅ ያስፈልጋል›› በማለት አባታዊ መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡demera-3