Melakit_Yemegebuat_Blatena.jpg

መላእክት የመገቧት ብላቴና

መ/ር መንግሥተአብ አበጋዝ

  Melakit_Yemegebuat_Blatena.jpg

እንደምን ሰነበታችሁ ልጆች? መላእክት በሰማይ የሚኖሩ የእግዚአብሔር አገልጋዮች መሆናቸውን ታውቃላችሁ አይደል? በመጽሐፍ ቅዱስ የሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ መልእክት ወደ ዕብራውያን ሰዎች ምዕራፍ 1 ቁጥር 7 ላይ ይገኛል፡፡

 

በጣም ጥሩ ልጆች ከዚህ በተጨማሪ መላእክት በማቴዎስ ወንጌል ምዕራፍ 18 ቁጥር 10 ላይ እንደተገለጸው፤ እኛን የሰው ልጆችን ሁሉ ከክፉ የሚጠብቁ እና በእግዚአብሔር ፊት የሚጸልዩልን ናቸው፡፡

ዛሬ የምንነግራችሁ ከቅዱሳን መላእክት አንዱ የሆነው ቅዱስ ፋኑኤል የተባለው መልአክ የፈጸመውን ተግባር ነው፡፡

ኢያቄምና ሐና የተባሉ የእግዚአብሔር ሰዎች በስዕለት ያገኟትን ልጃቸውን ለእግዚአብሔር ቤት ሊሰጧት በሦስት ዓመቷ ወደ ቤተ መቅደስ ይዘዋት መጡ፡፡
የቤተ መቅደሱም አገልጋዮች /ካህናት/ በኢያቄምና ሐና አሳብ ተገርመው ሕጿኗን ምን እንመግባታለን እያሉም ተጨነቁ፡፡

በዚህ ወቅት ነበር አንድ አስደናቂ ነገር በቤተ መቅደሱ ዙሪያ የታየው፡፡ ስሙ ፋኑኤል የተባለው መልአክ በእጁ ሕብስትና ወይን ይዞ መጥቶ ነበርና የቤተ መቅደሱ አካባቢ በብርሃን ተሞላ፡፡

የቤተ መቅደሱ ሓላፊ ካህኑ ዘካርያስ ለእርሱ መልእክት ሊያደርስ የመጣ መስሎት ወደ መልአኩ ተጠጋ፡፡ መልአኩ ግን ከእርሱ ራቀ፡፡ ደግሞም በየተራ ሕዝቡም ካህናቱም ወደ መልአኩ ቀረቡ መልአኩ ግን ከሁሉም እየራቀ ከፍ አለ፡፡

ከዚህ በኋላ ካህናቱ የእግዚአብሔር ጥበብ አይታወቅምና መልአኩ የመጣው ለብላቴናዋ /ለሕጻኗ/ ይሆናልና፤ ሐና ሆይ እስኪ ትተሻት እልፍ በይ አሏት፡፡ ሐናም ሕጻን ልጇን ትታት ራቅ አለች፡፡ በዚህ ጊዜ መልአኩ ብላቴናይቱን አንድ ክንፉን አንጥፎ አንድ ክንፉን ጋርዶ የሰው ቁመት ያህል ከመሬት ከፍ አደረጋትና መግቧት ወደ ሰማይ ተመለሰ፡፡

በእግዚአብሔር ሥራ ሕዝቡ ሁሉ ተደነቁ፡፡ ምን እንመግባታለን? እያሉ ይጨነቁ የነበሩት ካህናትም የምግቧን ነገር መልአኩ ከያዘልንማ ብለው ቤተ መቅደስ እንድትገባ አደረጓት፡፡ ብላቴናይቱም መላእክት እየመገቧት እስከ አሥራ አምስት ዓመቷ በቤተ መቅደስ ኖረች፡፡

ልጆች ይህች ብላቴና ማን ናት?

እናትና አባቷ ማን ይባላሉ? 

ይመግባት የነበረው መልአክ ስሙ ማን ነው? በሉ ደህና ሁኑ!
ወላጆች:- ለሕጻናት ተጨማሪ ጥያቄ በማቅረብ ታሪኩን በቃል እንዲያጠኑና እንዲነግሯችሁ አድርጉ፡፡