ቅዱስ ተክለ ሃይማኖት

ለአባ የትናንቱ

ዲያቆን ሄኖክ ኃይሌ

ግንቦት 23፣2003ዓ.ም

ያለ ማወቅ ጽልመት ሀገሩን ሲወርሰው ቅዱስ ተክለ ሃይማኖት

ማን ነበር ትውልዱን በወንጌል ያረሰው?

አባ ተክለ ሃይማኖት አባ የትናንቱ

ትዝ አለኝ ተጋድሎው ውል አለኝ ሕይወቱ

በቆላ በደጋ የተንከራተትኸው

የሃይማኖትን ተክል ዞረህ የተከልኸው

የኢትዮጵያ ፀሐይ አባ ተክለ አብ

እስቲ መለስ ብዬ ሥራህን ላስብ

በቀንና በሌሊት ከላይ ታች ዞረህ

ሕዝቡን አዳረስከው አስተምረህ መክረህ

ስንት ነበር አባ ‹የጉዞ አበልህ›?

ያረፍህበት ስፍራ የተዘጋጀልህ

የት ነበር መኝታው ጎን ማሳረፊያህ?

ንገረኝ እባክህ ማን ነበር የሸኘህ?

እሳት አባቴ ሆይ እኔ አመድ ልጅህ

በዘመኔ ቋንቋ እስኪ ልጠይቅህ?

/ምንጭ፦ ሐመር መጽሔት ግንቦት 2003 ዓ.ም እትም/